Tag Archives: Ethiopia

ነባር የኢሕአዴግ አመራሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለመከላከያ ምስክርነት ተቆጠሩ

ምሁራንና ፖለቲከኞችም ተካተዋል

በታምሩ ጽጌ

TPLF_EPRDF Juntas

ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ማይካድራ በተባለ ቦታ ላይ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው የተለገጸውና በሽብር ድርጊት ወንጀል የተከሰሱ አራት ተጠርጣሪዎች፣ አቶ በረከት ስምኦን፣ አቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ አቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሃት)፣ አቶ አዲሱ ለገሰ፣ አቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ጄነራል ሳሞራ የኑስንና ሌሎችንም ነባር ታጋዮችንና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ጨምሮ 141 ሰዎች በመከላከያ ምስክርነት ቆጠሩ፡፡

መከላከያ ምስክሮቹን የቆጠሩት ተጠርጣሪዎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ወ/ሪት እየሩሳሌም ተስፋውና አቶ ፍቅረማርያም አስማማው ናቸው፡፡ በክሱ ከላይ የተጠቀሱትን ተጠርጣሪዎች ወደ ኤርትራ ድንበር እንዲሻገሩ በመምራት የተጠረጠረው አቶ ደሴ ካህሳይም ተካቷል፡፡
ተከሳሾቹ ከዓመት በፊት የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለው ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክስ የተመሠረተባቸው፣ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ወንጀል ሆኖ የተደነገገውን ለሽብርተኛ ድርጅት ውስጥ መሳተፍን ተላልፈዋል በሚል ነው፡፡

ተከሳሾቹ ከላይ የተጠቀሱትን የሕግ ድንጋጌዎች በመተላለፍ፣ የሰው ሕይወት በማጥፋትና ንብረት በማውደም፣ በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ፖለቲካዊ ሥልጣን ለመያዝ እየተንቀሳቀሰ ካለው የግንቦት ሰባት ድርጅት ጋር አብሮ ለመሥራት መዘጋጀታቸውም ተጠቅሷል፡፡ ከአዲስ አበባ ተነስተው በባህር ዳር፣ በጎንደርና በሁመራ አድርገው ወደ ኤርትራ ለመሻገር ሲንቀሳቀሱ በፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውንም፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ ያቀረበውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤቱ፣ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ታኅሳስ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ብይን ሰጥቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን (141) በዝርዝር ጽፈው አቅርበዋል፡፡ ከምስክሮቻቸው መካከል ለአቶ በረከት ስምዖን፣ ለአቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ ለአቶ አዲሱ ለገሰ፣ ለወ/ሮ ሮማን ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ለአቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሀት)፣ ለወ/ሮ ፍሬ ሕይወት አያሌው፣ ለዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል፣ ለጄኔራል ሳሞራ የኑስና ለአቶ ቴዎድሮስ ሐጐስ እነሱ መጥሪያ ለማድረስ እንደማይችሉ (ከፍተኛ ባለሥልጣናት በመሆናቸው) በፍርድ ቤቱ በኩል እንዲደርሳቸው እንዲደረግ አመልክተዋል፡፡

ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፣ ለዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ለአቶ አስገደ ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ገብሩ አሥራት፣ ለወ/ሮ አረጋሽ አዳነ፣ ለአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ (ዝዋይ)፣ ለአምስት ጦማሪያን፣ ለጠበቃ ተማም አባቡልጉ፣ ለኢንጂነር ይልቃል ጌትነት (ሰማያዊ ፓርቲ) ጨምሮ በድምሩ 141 የመከላከያ ምስክሮችን በመቁጠር ለፍርድ ቤቱ አሳውቀዋል፡፡ ረቡዕ ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ተከሳሾቹ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

እነ ኦኬሎ አኳይ እስከ 9 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ተቀጡ

የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እነ ኦኬሎ አኳይ እስከ ዘጠኝ ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ቀጣ፡፡ ተከሳሾችም ሆኑ የፌደራል አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ሚያዚያ 17 ቀን 2008ዓ.ም ለፍርድቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ፍረድቤቱ የግራ ቀኙን አይቶ ዛሬ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 የእስራት ፍርድ ስጥቷል፡፡

Okello Akuay

አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቆ የነበረ ቢሆንም ፍርድቤቱ የወንጀል ድርጊቱ የተፈፀመው በአመዛኙ የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ከመውጣቱ በፊት በመሆኑ እና በድርጊቱም የተጎዳ ሰውም ሆነ ንብረት ስለሌለ የአቃቤውን ጥያቄ አልተቀበለም፡፡

ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት ፍርድቤቱ መድቦ እንዲቀጡ አቃቤህግ የጠየቀውን ውድቅ ያደረገው ፍርድቤቱ ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አቃቤህግ ያመለከተውን ተቀብሎታል፡፡

ተከሳሾች በበኩላቸው ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው ታሳቢ ተደርጎ ቅጣት እንዲቀልላቸው ያመለከቱተን ፍርድቤቱ የተቀበለ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ መሆኑን ጠቅሰው እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው ያመለከቱትን ግን ፍርድቤቱ አልተቀበለውም፡፡

በዚህም አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል በቡድን ሆኖ የአመራር ሚናን በኃላፊነት በመምራታቸው በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሽ ዴቪድ ኡጁሉ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል እና የውጪ ጉዳይ ኃላፊ በመሆን የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ቡድኑን በአመራር በማገልገላቸው በተመሳሳይ በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት ቀጥቷል፡፡

ከሶስተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች (ኡቻን ኦፔይ፣ ኡማን ኝክየው፣ ኡጁሉ ቻም፣ አታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡመድ ) በጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን የተለያዩ ተሳትፎዎችን በማድረጋቸው ሁሉም ተከሳሾች በሰባት አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡
በሰኔ ወር 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ ክስ የተመሰረተባቸው እነ ኦኬሎ አኳይ ለሁለት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብቶቻቸው እንዲታገዱ ፍርድቤቱ አዟል፡፡
ምንጭ፡-http://ehrp.org

በአዲስ አበባ ሰሚት አካባቢ ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ

በአዲስ አበባ ከተማ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ባለ 5 ፎቅ ህንፃ ተደርምሶ በንብረት ላይ ጉዳት አደረሰ።

Addis Ababa Poor construction

የአዲስ አበባ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ እንደገለጹት፥ የህንፃ መደርመስ አደጋው ዛሬ ማለዳ 12 ሰአት ላይ ነው በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሰሚት አካባቢ የተከሰተው።

ባለ 5 ፎቅ ህንፃው ሙሉ በሙሉ ያልተጠናቀቀ ቢሆንም ከታችኛው ወለል ላይ ሁለት ባንኮች አገልግሎት መስጠት ጀምረው እንደነበርም አቶ ንጋቱ ጠቁመዋል።
የመደርመስ አደጋው በስራ ሰዓት ቢደርስ በሰው ላይ ከባድ አደጋ ሊያደርስ ይችል እንደነበርም ነው ባለሙያው ያነሱት።
የባንኮቹ የጥበቃ ሰራተኞች ህንፃው ከመድርመሱ በፊት ከባድ ድምፅ በመስማታቸው ከአደጋው ሊያመልጡ ችለዋል።

ምንጭ፡-ፋናቢሲ

አቃቤህግ እነ ኦኬሎ አኳይ በከባድ ወንጀል ክስ እንዲቀጡ ጠየቀ

በሰኔ 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ የሽብር ክሰ ተመስርቶባቸው ክሳቸው በከፍተኛው ፍርድቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እየታየላቸው የሚገኙት እነ ኦኬሎ አኳይ(ሰባት ሰዎች) መጋቢት 28 ቀን 2008 ዓ.ም በዋለው ችሎት ጥፋተኛ ስለመሆናቸው ፍርድቤቱ ውሳኔ ካስተላለፍ በኃላ ከሁለቱም ተከራካሪዎች የቅጣት አስተያየት ለመስማት ለዛሬ ሚያዚያ 17 ቀጠሮ ስጥቶ ነበር፡፡

Okello Akuay

ተከሳሾችም ሆኑ አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ለፍርድቤቱ ያቀረቡ ሲሆን አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
ከአንደኛ አስከ ሶስተኛ ያሉ ተከሳሾች የወ/ህ/ቁ 27/1/፣ 32/1/ሀ፣ 38 እና 241 በመተላለፍ ወንጀል ለመፈፀም በተቋቋመ ቡድን አመራር፣ አባል፣የደህንነት ዘርፍ እንዲሁም የውጭ ግንኙነት ሃላፊ በመሆን፣ ገንዘብ በማሰባሰብ እና አባላትን በመመልመል ፣ የቡድኑ አባላት ወታደራዊ ስልጠና የሚያገኙበትን ሁኔታ በማመቻቸት፣ መሳሪያ በመግዛት፣የጦር መሳሪያ ድጋፍ ለማግኘት ከኤርትራ መንግስት ጋር እና ከኦነግ እና ግንቦት ሰባት ከተባሉ ቡድኖች ጋር በመደራደር በከፍተኛ አመራርነት ሲንቀሳቀስሱ የነበረ መሆኑን አቃቤህግ ጠቅሶ ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን ፍርድቤቱ የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት እንዲመድብ ጠይቋል፡፡

የቡድኑን አላማ አውቀው፣ በቡድኑ ወታደራዊ ስልጠና በመውሰድ ጥቃት ለመፈፀም በዝግጅት ላይ ነበሩ ያላቸውን ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች የወንጀል አፈፃፀማቸው በመካከለኛ ይመደብልኝ ሲል የጠየቀው አቃቤህግ ሁሉም ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አመልክቷል፡፡

ተከሳሾች በበኩላቸው በጠበቃቸው አማካኝነት ጥፍተኛ የተባሉት ከ2006 ዓ.ም በፊት ፈፅማቹኃል በተባለው ድርጊት መሆኑ ከቀረበባቸው ክስም ሆነ ፍርድቤቱ በሰጠው ውሳኔ እንድሚታወቅ አስረድተው፣ ለጥፋተኝንት ውሳኔው መሰረት የሆኑት ድርጊቶች ተፈፀሙ በተባለበት ጊዜ በስራ ላይ በነበረው እና በ2002 ዓ.ም በወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ፍርድቤቱ እንዲወስንላቸው ጠይቀዋል፡፡

የወንጀል ህጉ አንቀፅ241 ስር በተደነገገው እና ተከሳሾች ጥፋተኛ በተባሉበት የወንጀል ድርጊት በየትኛውም አካል ላይ ስለመድረሱ የተረጋገጠ የገንዘብም ሆነ የአካል ወይም የህይወት አደጋ የለም ያሉት ተከሳሾቹ ፈፀሙ በተባሉት ወንጀል የደረሰ ጉዳት ባለመኖሩ የወንጀሉ አፈፃፀም ቀላል በሚል ሊያዝ ይገባል ሲሉ አመልክተዋል፡፡ ተከሳሾች የቅጣት ማቅለያዎንም ፍርድቤቱ እንዲቀበላቸው ጠይቀዋል፡፡

ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው እንዲሆም አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ በመሆኑ እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው አመልክተዋል፡፡

ፍርድቤቱ የቅጣት አስተያየቶቹን ተመልክቶ የቅጣት ፍርድ ለመስጠት ለረቡዕ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 ቀጠሮ ስጥቷል፡፡
ምንጭ፡-ኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (EHRP)

የአዋሽ ወንዝ ሊሞላ ስለሚችል የአካባቢው ወረዳዎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማሳሰቢያ ተሰጠ

በዚህ ሳምንት ውስጥ እንደሚጥል በተተነበየ ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ አማካይነት የአዋሽ ወንዝ ሞልቶ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል፣ ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ፡፡

Awash river

ኮሚሽኑ ለሪፖርተር የላከው የቅድመ ማስጠንቀቂያ መልዕክት እንደሚገልጸው፣ ከሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ በስተቀር በአብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እስከ ሚያዝያ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጥል እንደሚችል፣ ከብሔራዊ የሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲ መረጃ ማግኘቱን ይጠቁማል፡፡

ከአዋሽ ተፋሰስ ባለሥልጣን በተገኘው ሌላ መረጃ መሠረትም የአዋሽ ወንዝ በቀጣዩ ሳምንት ሊሞላ ስለሚችል፣ ከዚህ ጋር ተያይዞ ጐርፍ በተፋሰሱ ባሉ አካባቢዎች ሊከሰት እንደሚችል መረጃዎች የሚያመለክቱ መሆኑን፣ በኮሚሽኑ የቅድሚያ ማስጠንቀቂያና ምላሽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሉነህ ወልደ ማርያም ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም በበቾ ወረዳ፣ በዓለም ጤና ወረዳ (ሁምቡሌና ጐሮ አካባቢዎች)፣ በስሬ ወረዳ፣ በወንጂ በተለይም በቆቃ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በመርቲ ወረዳ፣ በመተሃራ (ፈንታሌ)፣ በአሚባራ፣ በዱለቻ፣ በገላአሎ፣ በገዋኔ፣ በተንዳሆ ግድብ አካባቢ የሚኖሩ፣ በአሳይታና በአፋምቦ ወረዳዎች የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጐርፍ ሊከሰትባቸው ስለሚችል ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኮሚሽኑ አሳስቧል፡፡

የተጠቀሱት አካባቢዎች የመስተዳደር አካላትም በአካባቢዎቹ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ከወንዙ በማራቅ ከጉዳት መጠበቅ እንዲችሉ የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉም አሳስቧል፡፡

ባለፈው መጋቢት ወር መጨረሻ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በተከሰተው የጐርፍ አደጋ ከ20 ሰዎች በላይ መሞታቸው ይታወሳል፡፡

ብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በ2008 ዓ.ም. የመጀመሪያ ወራት እንደ አዲስ የተቋቋመና በሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን የመከላከልና የቅድመ ማስጠንቀቅ ሥራ የማከናወን ኃላፊነት የተጣለበት ተቋም ሲሆን፣ ተጠሪነቱም በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ