በአዲስ አበባ የ24 ሰዓቱ ሰልፍ ቅስቀሳ ተጠናክሮ ቀጥሏል
- 5 የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ታስረዋል
ህዳር 27 እና 28 2007 ዓ.ም የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የሚያደርጉት የአዳር (24 ሰዓት) ሰልፍ ቅስቀሳ ተጠናክሮ መቀጠሉን የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ መግለፃቸው ተጠቁሟል፡፡ እስካሁን ሰው በሰውና ቲሸርት በመልበስ ቅስቀሳ ሲደረግ እንደቆየና በተለይ ዛሬ ህዳር 24 ቀን 2007 ዓ.ም ከሰዓት ጀምሮ በአዲስ ከተማ፣ ጉለሌ፣ አራዳ፣ የካ፣ ንፋስ ስልክ፣ ኮልፌና ሌሎች የአዲስ አበባ ክፍለ ከተማዎች ወረቀት በመበተን የተሳካ ቅስቀሳ መደረጉን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል አራዳ ክፍለ ከተማ ፒያሳ አካባቢ ለአዳር ሰልፉ ሲቀሰቅሱ ከነበሩት መካከል የሰማያዊ ፓርቲ አባላት የሆኑት ሜሮን አለማየሁ፣ ወይንሸት ንጉሴ፣ ባህረን እሸቱ፣ ማቲያስ መኩሪያ እንዲሁም ጉለሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ ሲቀሰቅስ የነበረው ሲሳይ በፖሊስ ተይዘው መታሰራቸው ተግልጾአል፡፡
ከአሁን ቀደም ለሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ቅስቀሳ ላይ ሲያደርጉ በርካታ የፓርቲው አመራሮችና አባላት መታሰራቸውን ያስታወሱት አቶ ዮናታን “ይህ የገዥው ፓርቲ የተለመደ እርምጃ ነው፡፡ በቀጣይነትም ሌሎች አባላትንና አመራሮች መታሰራቸው አይቀረም፡፡ ትግሉ መስዋዕትነት የሚያስከፍል እንደመሆኑ በእስሩ ሳንገታ ትግሉን እንቀጥላለን፡፡” ሲሉ እንቅስቃሴያቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል፡፡ የዛሬው ቅስቀሳ 12 ሰዓት ላይ የተጠናቀቀ ሲሆን ነገ ጠዋት ጀምሮ በተለያዩ የአዲስ አበባ ክፍሎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ዘግይቶ በደረሰን ዜና ከታሰሩት 5 ወጣቶች መካከል ሁለቱ ሴቶች መፈታታቸውንና ወንዶቹ ግን ይህ እስከተዘገበ ድረስ አለመለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡
የማያዳምጥና የማያነብ መንግስት እድሜው ስንት ነው?
ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ
“መንገዱ በዚህ ወር ይጠናቀቃል፤ ባቡሩ በዚህ ወር ስራ ይጀምራል” ይሉናል፡፡ መንገዱ ወዴት ያደርሳል? ባቡሩ ወዴት ይወስዳል? ልጆቻችን ወጥተው የማይገቡበት መንገድ፣ የማይሳፈሩበት ባቡር ምን ያደርጋል? መንገዱ ሲሰፋ፣ መጓጓዣው ሲበረክት የልጆቻችን ፍርሀት፣ የእኛ የወላጆች ጭንቀት ከመበርከቱ በቀር ትርፉ ምንድነው?
ቁሳዊ ልማት ብቻውን ማህበረሰባዊ እድገት አያመጣም፤ ቀውስ ካልሆነ በቀር፡፡ የማህበረሰብህን . . . የነገ ወራሽህን. . የወጣቱን አስተሳሰብና አሰራር ሳታለማ (ሳትለውጥ) ታክሲ ብታመጣ፣ ወንዝ ውሀ ስትቀዳ፣ ጫካ እንጨት ስትለቅም ትደፈር የነበረችውን ልጃገረድ፣ ታክሲ ውስጥ ታስደፍራታለህ፤ ነገም ባቡር ውስጥ (ዛሬ በህንድ ሀገር ባቡር ማለት ብዙ የማያስከፍል ፔንሲዮን ነው)፡፡ እኛ ሀገር ብዙ መንገድ ብዙ ወንጀል፣ ሰፊ ኢንቨስትመንት ሰፊ ዝርፊያ፣ ትልቅ ባለስልጣን ትልቅ ዘራፊ ከማለት የተለየ ፍቺ የሚኖረው መቼ ነው?
“ልማታዊ መንግስት ነን፣ ኒዎ ሊብራሊዝምን እንቃወማለን” ይሉናል፡፡ በልማት ስም ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ መብታችንን አንጠፍጥፈው ወሰዱት፡፡ ይበጃል ያልነውን ስንጽፍና ስንናገር ጸረ ልማት ይሉናል፡፡ ደፈር ብለን መብታችንን ከጠየቅን አሸባሪ ይሉናል፡፡ በየእስር ቤቱ ያጉሩናል፤ ድንበር አሻግረው ያሰድዱናል፡፡ መብታችንንና የመናገር ነጻነታችን ልማታዊ ላሉት መንግስት ጭዳ አደረጉት፡፡
“ልማታዊ አይደላችሁም! ኒዎ ሊብራል ናችሁ አንላቸዋለን፡፡ የምትኖሩበት ቤት፣ የምትነዱት መኪና፣ ልጆቻችሁ የሚማሩበት ትምህርት ቤት (ሀገር)፣ የምትገበያዩበት ሱፐር ማርኬት፣ የምትዝናኑበት ሪዞሪት. . . የልማታዊነት ሳይሆን የኒዎ ሊብራሎች መገለጫ ነው፡፡” እንላቸዋለን፡፡
“ዝም በሉ! የምንላችሁን አሜን ብላችሁ ተቀበሉ” ይሉናል፡፡ ማተሚያ ቤቱ የእነሱ ነው፤ ራዲዮና ኢቲቪው የእነሱ ነው፤ አዋጅና መመሪያ የሚጥልብን ፓርላማ የእነሱ ነው፡፡ አዋጅ ጣሳችሁ፣ አሸበራችሁ፣ እራለ የሚይዘን ፖሊስ የእነሱ ነው፤ ከፖሊሶቹ ተቀብሎ የሚፈርድብን ፍርድ ቤት የነሱ ነው፡፡ ያለ ወንጀሉ ተከስሶ የሚፈረድበት ዜጋ እሱ ራሱ የራሱ አይደለም፡፡ ራሳችንም የእነሱ ነን፡፡ የእኛ የሆነው ተስፋችን ብቻ ነው! ለሀገራችንና ለወገናችን ያለንን ብሩህ ተስፋ ምንም ሊያስረው አይችልም፡፡ የኔ ተስፋ ልጆቼ ውስጥ፣ ያልተወለደው የልጆቼ ልጆች . . . . . ውስጥ አለ፡፡ ተስፋ የሚታሰረው፣ የሚሞተው እርኩስ፣ ለሀገርና ለወገን የማይበጅ ሲሆን ብቻ ነው፡፡
ዛሬ አትጻፉ ተብለናል፡፡ አትናገሩ ተብለናል፡፡ አንጽፍም፡፡ አንናገርም፡፡ ከተማው ጭር ብሏል፡፡ ሀገሩ ጭር ብሏል፡፡ መንግስትም ጭርታው ተስማምቶታል፡፡ እኛ ግን አንጽፍም እንጂ እንነበባለን፤ አንናገርም እንጂ እንደመጣለን፡፡ የማያነበንና የማያዳምጠን የኢህአዴግ መንግስት ብቻ ነው፡፡ አንድ መንግስት ህዝቡን ሳያዳምጥና ሳያነብ ምን ያህል እድሜ ይኖራል? እንጃ! . . . . . አንድ ቀን መንግስት ህዝብን ማንበብ፣ ህዝብን ማዳመጥ ግዴታው ይሆናል፡፡ አቤት ታዲያ ያኔ የሚያነበው መአት! የሚያዳምጠው ቁጣ! ያኔ ማንም መንግስትን መሆን አይመኝም፡፡ እውነቴን እኮ ነው፣ አሁን 1983 ዛሬ ቢሆን ደርግን መሆን የሚመኝ አለ?
በርካታ የአንድነት ፓርቲ አባላትና አመራሮች በቃሊቲ እስር ቤት ታግተው መለቀቃቸው ተገለፀ
የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃምን ጨምሮ ከ40 ያላነሱ የፓርቲው አባላት ቃሊቲ እስር ቤት መታገታቸው ተገለፀ፡፡
አንድነት ፓርቲ ለአንድ ሳምንት የሚቆይ “የሚሊዮኖች ድምፅ ለህሊና እስረኞች” በሚል መሪ ቃል ከህዳር 14 ጀምሮ እያካሄደ ያለው የማህበራዊ ሚዲያ ንቅናቄ አካል የሆነውን የህሊና እስረኞችን የመጎብኘት መርሀ-ግብር ለመሳተፍ አመራሮቹና አባላቱ ወደ ቃሊቲ እስር አቅንተው ነበር፡፡ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም እና የፓርቲው የአዲስ አበባ ሰብሳቢ አቶ ነገሰ ተፈረደኝን ጨምሮ ከ40 ያላነሱ የአንድነት ፓርቲ አባላት ለግዜው ባልታወቀ ምክንያት በእስር ቤቱ ግዜያዊ ማቆያ እንዲገቡ መደረጋቸውን የፍኖተ ነፃነት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በተለይ እገታውን በተመለከተ የአንድነት ለዴሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ አስራት አብርሃም ተናገሩት እንደታለው ከሆነው ‹‹እነእስክንድርንና አንዷለምን መጠየቅ አትችሉም ተባልን፡፡ ከዚያም ‹‹ለምን?›› ብለን ስንጠይቅ በዋናው በር በኩል ኃላፊውን አነጋግሩ የሚል መልስ ተሠጠን፡፡ እኛም ይህንን አምነን ሄድን፡፡ ነገር ግን በተባለው በር ስንደርስ በቁጥጥር ሥር ውላችኋል ብለውን መታወቂያችንን ከመዘገቡ በኋላ በአንድ ክፍል ውስጥ ለጊዜው ታገተው እንደነበር ሚኒሊክ ሳልሳዊ ዘግቧል፡፡ በመጨረሻም በኮንቴይነር ውስጥ ታግተው የነበሩት እስረኛ ጠያቂዎች ከበድ ያለ ፍተሻ ተደርጎላቸው ከቃሊቲ ግቢ እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን፤ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ወጣት ትዕግስት ካሳዬ የተባለች የአዲስ አበባ የፓርቲው አመራር ግን ከእገታው እንዳልተለቀቀች ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
እስረኞችን ሊጠይቁ የሄዱ የአንድነት አባላት በዛሬው እለት በአከባቢው የጠበቃቸው የደህንነት ቡድን በእያንዳንዱ ላይ ፍተሻ በማድረግ በኪሳቸው የነበረውን የአንድነት ፓርቲ ወረቀት እንዲሁም አንዲት ሴት የአንድነት አባል ፎት ልትነሳ መሞከር በሚል በተፈጠረ ሰበብ እንዲሁም በአባላቶቹ እጅ የተገኙት የፍኖተ ነፃነት እትሞች መቀማታቸው ተጠቁሟል፡፡ ይህ የተፈፀመው በቶዮታ ነጭ ዲኤክስ መኪና ተጭነው የመጡት የደህንነት አባላት እስረኛ ሊጠይቁ የሄዱትን በቁጥጥር ስር ካዋሉ በኋላ ስም ዝርዝራቸውን መዝግበው በመውሰድ እንዲፈቱ ትእዛዝ ሰጥተው ደህንነቶቹ መመለሳቸውን እና ከአንዲት አባል በስተቀር ሌሎች መለቀቃቸው ተጠቁሟል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ
-ህዝብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ ቀርቧል
9ኙ ፓርቲዎች በትብብር ለሚያዘጋጁትና ሰማያዊ ፓርቲ ለሚያስተባብረው የህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደረገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ ሲቀሰቅሱ እና ታሳሪዎቹን ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ በሄዱበት ወቅት የታሰሩት 6 የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ምግብ እንዳይገባላቸው ተከለከሉ፡፡
በሌላ በኩል ለነገው የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ በአብዛኛው የአዲስ አበባ ክፍሎች ስኬታማ ቅስቀሳ መደረጉን የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ገልጸዋል፡፡ይህ በእንዲህ እንዳለ አገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ ለውጥ ፈላጊ ኢትዮጵያውያን፤ ህዝቡ በአደባባይ ስብሰባው እንዲሳተፍ በስልክ (በመደወልም ሆነ መልዕክት በመላክ)፣ በማህበራዊ ድህረገጽና ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የበኩላቸውን እንዲያደርጉ፣ ለአንድ ወሩ መርሃ ግብርም ሆነ በሌላ የትግሉ አካል ሁለገብ ድጋፍና ተሳትፎ እንዲያደርጉ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ጥሪ አድርጓል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ከቅስቀሳው ጋር በተያያዘ የታሰሩትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ለመጠየቅ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ባቀኑበት ወቅት የታሰሩት አቶ ወሮታው ዋሴና አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድም በምሽት መለቀቃቸውን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ እሁድ ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በአዲስ አበባ ቀበና ቤለር የጠሩት ህዝባዊ ስብሰባ በፖሊስ መበተኑ ተገለፀ፡፡
ቤተ ክርስቲያን እንዳይፈርስ የተቃወሙት ዜጎች የት እንደደረሱ አልታወቀም ተባለ
‹‹ይህ ሁሉ የሆነው የእምነቱን ተከታዮች በመናቅ ነው››
ትናንት ህዳር 3 ቀን 2007 ዓ.ም ከቀኑ 5 ሰዓት ጀምሮ በቦሌ ክፍለ ከተማ የቅድስት የማሪያም ቤተ ክርስቲያን እንዳይፈርስ በመቃወማቸው የታፈኑት ዜጎች የት እንደደረሱ አልታወቀም ሲሉ በወቅቱ ጉዳዩን ሲከታተሉ የነበሩ የአካባቢው ነዋሪዎችና የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ፡፡
በወቅቱ 600 ያህል ዜጎች ተገኝተው ቤተ ክርስቲያኗ እንዳትፈርስ ሲቃወሙ እንደተመለከቱ የገለጹት የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች የቤተ ክርስቲያኗን መፍረስ የተቃወሙትን ጨምሮ ሌሎች በአካባቢው የተገኙ ዜጎችም በፖሊስ መታፈሳቸውን ገልጸዋል፡፡ ነዋሪዎቹ ‹‹ህዝቡ በሰንደቅ አላማ አምላክ አታፍርሱብን እያለ ቢለምንም እነሱ ግን ጥይት ወደላይ በመተኩስ ህዝቡን ከማሸበራቸውም በላይ ያገኙትን እየደበደቡ በ9 የድንጋይ መጫኛ መኪና አስገድደው በመጫን ወዳልታወቀ ቦታ ውስደዋቸዋል፡፡ አድማ በታኝ ፖሊስ ቄስ፣ አዛውንት፣ ህጻንና ሴት ሳይል ያገኘውም አፍሶ ወስዷል፡፡ የኮብል ስቶን ጠራቢዎች ሳይቀሩ በአካባቢው በመገኘታቸው ታፍሰው ታስረዋል፡፡ አሁን የት እንዳሉ አይታወቅም፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ ከተሰራች ከሁለት አመት በላይ እንደሆነ የገለጹት አንድ የአካባቢው ነዋሪ ‹‹ቤተ ክርስቲያኗ ከተሰራችበት ጊዜ ጀምሮ እንድትፈርስ ጥያቄ እንደቀረበ ተገልጾልን አያውውም፡፡ አሁን ነው ደርሰው ያፈረሱት፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን አገልጋዮች ጨምሮ በጣም ብዙ ሰው በዱላ ተደብድቧል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የእምነቱን ተከታዮች በመናቅ ነው፡፡›› ሲሉ ቅሬታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
የአካባቢው ነዋሪዎችና አማኞች ከቀኑ 5 ሰዓት ጀምሮ እስከ 9 ሰዓት ቤተ ክርስትያኗ እንዳትፈርስ እንደተቃወሙ፣ አድማ በታኝ ፖሊስ በአካባቢው ያገኘውን ሰው ካፈሰ በኋላ ቤተ ክርስቲያኗን በማፍረስ ቆርቆሮውን በመኪና ጭኖ እንደሄደ የአይን እማኞች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ