የኮንሶ ብሔረሰብ የዞን ምሥረታ ጥያቄ ከሕግ አንጻር ሲፈተሸ
ውብሸት ሙላት
ኮንሶ፣ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል በሰገን ሕዝቦች ዞን ውስጥ የምትገኝ ወረዳ ናት፡፡ ቀደም ሲል ግን ልዩ ወረዳ ነበረች፡፡ ኮንሶ አስተዳደር እርከን ብቻ ብቻ አይደለችም፤ብሔረሰብም ጭምር እንጂ! የሰገን ሕዝቦች ዞን ደግሞ በፊት የኮንሶ፣ የደራሼ፣ የአማሮ እና የቡርጂ ልዮ ወረዳዎች የነበሩትን በማጠቃለል የተመሠረተ ነው፡፡
በደቡብ ክልል ሕገ-መንግሥት መሠረት ልዩ ወረዳ ከዞን ጋር አቻ ሥልጣን አለው፡፡ ተጠሪነቱም ቀጥታ ለክልሉ ነው፡፡ ልዩ ወረዳ፣ ብዙ ጊዜ በአንድ ብሔር ብቻ ስለሚመሠረት የአንድ ብሔር ብቻ አባላት ያሉበት የወረዳ ምክር ቤት ይኖረዋል፡፡ የራሱ የልዩ ወረዳው የሥራ ቋንቋ እንዲኖረው መወሰን ይችላል፡፡ በዞን ደረጃ የሚኖሩትን መንግሥታዊ መዋቅሮችን በወረዳው በማቋቋም በርካታ የብሔረሰቡ ተወላጆች የሥራ ዕድል እንዲኖራቸው ያስችላል፡፡
መደበኛ ዞኖች ሕግ አውጪ የላቸውም፡፡ የዞን ሥራ አስፈጻሚዎችም የሚሾሙት በቀጥታ በክልሉ ሥራ አስፈጻሚ በመሆኑ የክልል ውክልና እንጂ በምርጫ የተገኘ ሥልጣን አይደለም፡፡ ወረዳዎችም ቢሆኑ ለአስተዳደር ቅልጥፍና፣ ድጋፍና ክትትል ሲባል በተጨማሪነት ለዞን ተጠሪነት ያለባቸው ቢሆንም ይህ ሁኔታ የመነጨው የክልሉ አስፈጻሚ አካላት በሚሰጠው ውክልና ላይ ተመሥርቶ እንጂ ሕገ-መንግሥታዊ መነሻ የለውም፡፡ ለዚያም ነው የወረዳ አስተዳዳሪዎችና ከንቲባዎች በዞን አስተዳዳሪዎች የማይሾሙትም ሆነ የማይወርዱት፡፡
በልዩ ዞኖች ግን የብሔረሰብ ምክር ቤት ስላላቸው፣ የዳኝነት መዋቅርና ሹመት በክልል ደረጃ ቢከናወንም እንኳን ከዞኑ የሚጠቆሙትና የሚሾሙት ዳኞች ላይ አስተያየት የመስጠት መብት አላቸው፡፡
የኮንሶ ብሔረሰብ፣ የዞንነት ጥያቄ በማንሳት ተቃውሞ ከጀመረ አንድ ዓመት አለፈው፡፡ ከተቃውሞው ጋር በተያያዘ ቀላል የማይባል የሰው ሕይወት ጠፍቷል፡፡ የክልሉ የኮሚኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ሓላፊ ለአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ በቅርቡ በተናገሩት መረጃ እንኳን ከ1500 ቤቶች በላይ ተቃጥለዋል፡፡ ከአንዳንድ መገናኛ ብዙኃን እንደሚሰማው የዞንነት ጥያቄው ካልተሳካ ወደ ኦሮሚያ ክልል የመካለል ጥያቄንም በአማራጭነት ሕዝቡ እያነሳ ነው፡፡
ይህ ጽሑፍ ዞን የሚመሠረትበትን ሕጋዊ አሠራር ይፈትሻል፡፡ የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን መብት ጋር የሚኖረውን ግንኙት በማየት የኮንሶ ብሔረሰብ ጥያቄ ከክልሉ እና ከፌደራሉ ሕገ-መንግሥት እንዲሁም ከሌሎች አግባብነት ካላቸው ሕጎች አንጻር ዳሰሳ ያደርጋል፡፡ እግረ-መንገዱንም አንድ ወረዳ ወይንም ሌላ አስተዳደረዊ መዋቅር ከአንድ ክልል ወደ ሌላ ክልል መጠቃለል የሚችልበትን ሕገ መንግሥታዊ ሁኔታም ካለ ምጥን ፍተሻ ያደርጋል፡፡
ኮንሶ ከሌሎች ዞኖች ጋር በሕዝብ ብዛት ስትነጻጸር፤
የኮንሶን የዞን ምሥረታ ጥያቄን በአግባቡ ለመረዳት በኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት ዞኖች ጋር፣ በ1999 ዓ.ም. የተደረገውን የሕዝብና ቤት ቆጠራን መሠረት በማድረግ እናነጻጽራለን፡፡ በዚህ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት መሠረት የኮንሶ ልዩ ወረዳ ወደ 235 ሺህ የሚጠጋ ሕዝብ ነበረው፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የነበረው የወረዳው ሕዝብ ብዛት ማለት ነው፡፡ ከወረዳው ውጭም የሚኖሩትን ጨምሮ፣ የኮንሶ ብሔረሰብ ብዛት ከ250 ሺህ በላይ ነው፡፡ ዞን ለመመሥረት በአንድ አካባቢ መኖርን ስለሚጠይቅ፣ ለዞን ምሥረታ ጥያቄው ተገቢው ቁጥር መኖር ቅድመ-ሁኔታ ነው ማለት ይቻላል፡፡
የኮንሶ ወረዳ ሕዝብ፣ ከሀረሪ ክልል ሕዝብ ይበልጣል፡፡ የዛሬ አስር ዓመት የክልሉ ሕዝብ ብዛት፣ ገና 200 ሺህ እንኳን አልሞላም ነበር፡፡ የኮንሶ ወረዳ በሕዝብ ብዛት፣ ከትግራይ ክልል የመቀሌ ልዩ ዞንን፣ ከአፋር ክልል የዞን ሦስት እና አምስትን፣ ከአማራ እና ከኦሮሚያ ክልሎች ከዞኖች ጋር አቻ ከሆኑት የባሕር ዳር፣ የደሴ፣ የጎንደር፣ የአዳማ እና የጅማ ከተሞችን፣ ከቤኒሻንጉል-ጉሙዝ፣ የካማሼ ዞንን፣ የጋምቤላ የሁሉንም ዞኖችን፣ እንዲሁም ከራሱ ከደቡብ ክልል ደግሞ የሸካ ዞንን በሕዝብ ብዛት ይበልጣል፡፡ የጋምቤላ ክልል ከኮንሶ ሕዝብ ወደ 80 ሺህ በሚጠጋ ቁጥር ብቻ ነው የሚበልጠው፡፡
ራስን በራስ የማስተዳደር መብት፤
የኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 89(1)፣ መንግሥት በዴሞክራሲያዊ መርሆች ላይ በመመሥረት ሕዝቡ በሁሉም ደረጃዎች ራሱን በራሱ የሚያስተዳደርበትን ሁኔታ ማመቻቸት ያለበትን ስለመሆኑ የፖለቲካዊ ፖሊሲው በጥቅሉ አስቀምጦታል ፡፡ ማንኛውም የብሔርነት፣ የብሔረሰብነት ወይንም ደግሞ የሕዝብነት ዕውቅና ያገኘ ማኅበረሰብ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱን ተግባራዊ የሚያደርግበትን አስተዳደራዊ መዋቅር የመመሥረት ገደብ የሌለው ሕገ-መንግሥታዊ መብት እንዳለው የፌደራሉም የክልሎችም ሕገ መንግሥት አንቀጽ 39 (3) ላይ ተደንግጓል፡፡
ራስን የማስተዳደር ሙሉ መብት በክልል ላይ ብቻ የተንጠለጠለ አይደለም፡፡ ይህ መብት ውጤታማ እንዲሆን ያልተማከለ አስተዳደር ተግባራዊ መሆን አለበት፡፡ ያልተማከለ አስተዳደርን እንደ አንድ ፕሮግራም ብናየው ብዙ የሚያካትታቸው ነጥቦች አሉት፡፡ ከሚያካትታቸው ነጥቦች ውስጥ በባሕርያቸው የአካባቢው መንግሥት ሥልጣንና ሥራ የሆኑትን ለአካባቢው መተው፣ እንዲሁም ባሕርያቸው አካባቢያዊ ባይሆኑም እንኳን እነሱ ቢፈጽሟቸው የሚሻል ከሆነም ለአካባቢው መንግሥት መተው አለባቸው፡፡
እንዲህ መሆኑ ከታመነበት ግጭትን ለመቀነስም ሆነ በልበ-ሙሉነት ለመሥራት ሲባል ሥልጣንና ተግባራቸው በግልጽ ተለይቶ መቀመጥን ይፈልጋል፡፡
የአካባቢ መንግሥታት (Local Government) የራሳቸውን ጉዳይ በራሳቸው የመጨረስ፣ ፖሊሲ የመንደፍ፣ ለፖሊሲያቸው የሕግ ማዕቀፍ የመስጠት የመጨረሻ የሥልጣን ባልተቤት መሆን ያሻቸዋል፡፡
አካባቢያዊ መንግሥታት፣ አስተዳደራዊ ተቋሞችን የማቋቋምና ለሥራ ምቹ በሚሆን መንገድ በነጻነት የማዋቀርና የሰው ሃይል የመቅጠርም የማባረርም ሥልጣንን ይይዛል፡፡ ስለሆነም አካባቢያዊ መንግሥታት ፖለቲካዊ፣ የገቢና ወጭ፣ እንዲሁም አስተዳደራዊ ሥልጣንን ያካትታል ማለት ነው፡፡ ይህ አሠራር የማእከላዊ መንግሥት ድጋፍና ቁጥጥር እንዲሁም በይነመንግሥታዊ ትብብርንም አያስቀርም፡፡
ፖለቲካዊ ራስ ገዝነት ባልተማከለ አስተዳደርም ይሁን ራስን በራስ በሚያስተዳድሩ ብሔሮች ዘንድ ቁልፍ የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ ማእከላዊም ይሁን የክልል መንግሥታት ባሰኛቸው ጊዜ የሚያፈርሷቸው ሲመቻቸው ደግሞ የሚያቋቁሟቸው ልዩ ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ቀበሌዎች ሊኖሩ አይገባም፡፡ ቀጣይ መሆን አለባቸው፡፡ በመኖርና በመፍረስ በስጋት እየወላወሉ የሚኖሩ ተቋማት ሊሆኑ አይገባቸውም፡፡ ወይንም ደግሞ እንዴት እንደሚቋቋሙም ይሁን እንደሚፈርሱ ግልጽ ሕግ፣ሁሉም የተስማሙበት ኖሮ በዚያው መሠረት መፈጸም አለበት፡፡ የኮንሶ ነገርም፣ በአንድ ወቅት ልዩ ዞን የነበረች ሲሆን አሁን ግን መደበኛ ወረዳ ብቻ በመሆን በሰገን ሕዝቦች ሥር ትገኛለች፡፡
በሕገ-መንግሥቱ በአንቀጽ 50(4) ከተገለጸው አንጻር ቋሚነት አላቸው ማለት ቢቻልም በተግባር እንደታየው ግን፣ ከ1994 ዓ.ም. በፊት ይህ ዓይነት ሥልጣን የሌላቸው ሲሆን፣ በኋላ ደግሞ መለወጡ ብሎም በአንዳንድ ክልሎች ሥልጣናቸው በሕገ-መንግሥት ሳይሆን በአዋጅ መገለጹ ወይንም በግልጽ አለመቀመጡ አጠራጣሪ አስመስሎታል፡፡
በተጨማሪም እንዴት ወረዳዎች እንደሚመሠረቱና እንደሚታጠፉ፣ ድንበራቸው እንደሚካለልና እንደሚደካ አለመገለጹ፤ መሥፈርቶቹን አንዳንድ ክልሎች በአዋጅ (ለምሳሌ ደቡብና ኦሮሚያ) ሌሎቹ ደግሞ ለአስፈጻሚው አካል መተው (ለምሳሌ ቤኒሻንጉል ጉሙዝና አማራ) ጉራማይሌ አድርገውታል፡፡ በመሆኑም ለልዩ ዞኖችም ይሁን ወረዳዎች የተሻለ ዋስትና መስጠት ያስፈልጋል፡፡ የዚህ ዋስትና አለመኖር ነው ኮንሶን በአንድ ወቅት ልዩ ወረዳ፣ በሌላ ጊዜ መደበኛ ወረዳ በመሆን ምንአልባትም ለተለያዩ ተቃውሞዎች መነሻ የሆነው፡፡
የልዩ ዞንና ወረዳ ምሥረታ ሂደት፤
በሽግግሩ ዘመን ሥራ ላይ በነበረው አዋጅ ቁጥር 7/1984 መሠረት ወረዳን ጨምሮ ወደ ላይ ያሉ መስተዳድሮችን ማቋቋም የማይችሉት በግልጽ ተዘርዝረው ነበር፡፡ በሕገ-መንግሥቱ ይህ ገደብ ተነስቷል፡፡ በተጨማሪም ክልል መመሥረት እንደመገንጠል ሁሉ ገደብ የለውም፡፡ ለነገሩ ክልል መመሥረትም ጉዳዩ ከክልል መሆኑ ነው እንጂ ያው መገንጠል ነው፡፡ ገደብ አለመኖሩን ለማመልከት “በማናቸውም ጊዜ” የሚል ቃል ተጠቅሟል፡፡
በሕገ-መንግሥቱ እንዲህ ዓይነቱ “መድልኦ” ተወግዷል ብንልም እንኳን በጋምቤላ አኙዋ፣ ኑዌርና መዠንግር ልዩ ዞን ሊያቋቁሙ እንደሚችሉ ሲገለጽ ኡፖና ኮሞ አይችሉም በማለት የክልሉ ሕገ-መንግሥት ገልጿል፡፡ በዚህም ከብሔረሰቦች መርጦ ለዞንና ለወረዳ አለ ማለት ነው፡፡ ቁጥራቸው አናሳ (በ1999ኙ ዓ.ም. በተደረገው ቆጠራ በክልሉ ውስጥ የሚኖሩት ማኦ 64፣ ኡፖ ደግሞ 990) መሆናቸው አንድ ነገር ሆኖ በሕገ-መንግሥት መከልከል ደግሞ ሌላ ነገር ነው፡፡
የአሁኑ ደቡብ ክልል ከመመሥረቱ በፊት አራት ክልሎች ነበሩ፡፡ አንድ ክልል ከሆኑ በኋላ ዞኖችና ወረዳዎች በተለያዩ ጊዜያት እንደገና ተዋቅረዋል፡፡ ለምሳሌ ሰሜን ኦሞ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ፣ዳውሮ) ወደ ሦስት ብሔረሰብ ዞኖች ተከፋፈለ (ወላይታ፣ ጋሞ-ጎፋ እና ዳውሮ ) ተብለው፡፡ እንዲሁም ሁለት ልዩ ወረዳዎች ተጨመሩ ባስኬቶና ኮንታ፡፡ ሌላ ካፋ-ሸካ የሚል እንደ አንድ ልዩ ዞን ቢቋቋሙም ውሎ አድሮ ካፋ እና ሸካ ልዮ ዞኖች ተብለው ራሳቸውን ቻሉ፡፡ ቤንችና ማጂ ይባሉ የነበሩት ሁለት ዞኖች፣ ኋላ ላይ ቤንች-ማጂ ተብለው አንድ ዞን ሆኑ፡፡ ስልጤ ዞንም ከጉራጌ ተነጥሎ ራሱን ቻለ፡፡ ቀደም ሲል ስምንት ልዩ ወረዳዎች የነበሩ ሲሆን አሁን አራቱ (ኮንሶ፣ደራሼ፣ ቡርጂ እና አማሮ) በአንድነት ሰገን ዞንን መሥርተዋል፡፡
ቋንቋ፣ማንነት፣ የአሰፋፈር ሁኔታና ፍቃደኝነት ላይ መሠረት በማድረግ የሚቋቋሙ አካባቢያዊ መስተዳድሮች (local territorial autonomy) ጉዳትም እንዳላቸው የሚገልጹ አሉ፡፡ ከእነዚህም ጉዳቶች መካከል ክፍፍልን ያባብሳል፣ ክልሎች በአብዝኃኛው ወጥ የሆነ አንድ ብሔር ስለማይኖርባቸው አሁንም ቢሆን በኢትዮጵያ የአናሳና የብዙኃንን ግንኙነት ማስቆም አያስችልም፤ በተጨማሪም አሁን ባለው ሁኔታ ዞኖችና ወረዳዎች ሲዋቀሩም ይሁን ሲዋሃዱ ወጥ የሆነ የታወቀ ሕገ-መንግሥታዊ መርሕ የለውም፤ እንደገዥው ፓርቲ የፖለቲካ ግምገማና ድምዳሜ የሚወሰን ነው፤ ዘፈቀዳዊም ነው የሚሉ ክሶች ይቀርባሉ፡፡
የዞንና ምሥረታ በደቡብ፤
ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ማንነታቸው ከታወቀ እንደቡድን ማንኛውንም አስተዳደራዊ እርከን የመመሥረት መብት አላቸው ብለናል፡፡ ከደቡብ ውጭ ያሉት ክልሎች፣ በውስጣቸው የሚገኙት ነባር ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ዝቅተኛ ስለሆነ፣ ወይ መሥርተዋል፤ አሊያም ትተዋቸዋል፡፡ መመሥረት ቢፈልጉ ደግሞ እንዴት ጥያቄያቸውን እንደሚያቀርቡ፣ ለማን እንደሚያቀርቡ፣ ምን ምን ሁኔታዎችን ማሟልት እንዳለባቸው ወዘተ የሚያሳይ ሕግ የላቸውም፡፡ ደቡብ ግን አለው፡፡
የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ስላለው፣ የዞንም ይሁን የወረዳ አመሠራረት ጥያቄ እንዴት መስተናገድ እንዳለበት፣ ይህንን ምክር ቤት ለማጠናከርና ሥልጣንና ተግባሩን ለመወሰን በወጣው አዋጅ ላይ ተገልጿል፡፡ ሥነ-ሥርዓቱ ከክልል ምስረታ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ልዩነቱ ጥያቄውን ያቀረበው በአስተዳደራዊ መዋቅር ተደግፎ ከሆነ (ለምሳሌ ልዩ ወረዳ የነበረው ልዩ ዞን መሆን ቢፈልግና ጥያቄው የቀረበው የወረዳው መስተዳደር ቢሆን) የመስተዳድሩ ምክር ቤት በሁለት ሦስተኛ ድምፅ ከደገፈው ወይንም ጥያቄውን ያቀረበው፤ ሕዝቡ ከሆነ (5% የሚሆነው ስምና ፊርማ አስፍሮ) ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ሲደግፈው እና የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ሲወስን ተፈጻሚ ይሆናል፡፡
በዚህ ሕግ መሠረት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ ወስኖ እንኳን ምክር ቤቱ ተጨማሪ ማስረጃ የማሰባሰብ ሥልጣን ስላለው አሰባስቦ ከመረመረ በኋላ ነው ውሳኔውን የሚያሳውቀው፡፡ ውሳኔውን ያሳውቃል ማለት ሕዝቡ በአብላጫ ድምፅ የወሰነውንም ሊሽረው ይችላል ማለት ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ አሠራር ወለፈንድ ይመስላል፡፡ ድምፅ ሳይሰጡ ቢሆን እንኳን ይሻላል፤ ድምፅ ሰጥተው ከጨረሱ በኋላ የሌሎች ብሔረሰቦች ተወካዮች የሕዝብን ውሳኔ ካላከበሩ የት ላይ ነው ታዲያ የራስን ዕድል በራስ መወሰኑ? ይሔው ሕግ ይሔንኑ ጉዳይ በሚደነግግበት ክፍሉ ስለየራስን ዕድል በራስ መወሰን ነው የሚያወራው፡፡ በራሳቸው የወሰኑት ከተሻረ የትኛው ዕድላቸው ላይ ወሰኑ?
ሌላው ይህ ሕግ በዝርዝር ባያብራራውም በውሳኔው መሠረት ለብቻቸው ተለይተው ራሳቸውን ማስተዳደር የሚጀምሩት ብሔረሰቦች ቀድሞ ከነበሩበት ዞን ወይንም ወረዳ ፍትሐዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል ሊያደርጉ እንደሚችሉ አስቀምጧል፡፡ ክልል ሲመሠርቱ ያልተቀመጠውን፣ በደቡብ ክልል ውስጥ ዞንና ወረዳ (ልዩም ይሁን አይሁን) ሲመሠርቱ የንብረት ክፍፍል እንዲደረግ ያስቀምጥና ስለተግባራዊነቱም የብሔረሰቦች ምክር ቤት እንደሚከታተል ገልጿል፡፡ ፌደሬሽን ምክር ቤት አዋጅ ወይንም የፌደራሉ ሕገ-መንግሥት ስለ ክልል ምሥረታ ያላስቀመጠውን በሥሩ ለሚገኙ መስተዳድሮች ማስቀመጡ ለፌደራሉም መንግሥት ትምህርት ነው፡፡
የክልሉ ብሔረሰቦች እና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች ሚና ሲገመገም፤
ከላይ በጥቅሉ ባስቀመጥነው መሠረት የኮንሶን ጉዳይ እንመልከተው፡፡ የኮንሶ ሕዝብ ከጠቅላላው አምስት ፐርሰንት ድጋፍ ካገኘ በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አማካይነት ሕዝበ-ውሳኔ ይካሄዳል፡፡ የልዩ ዞንነቱን ጥያቄ አብዝኃኛው ድምጽ ሰጪ ከደገፈው ውጤቱ ለክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ቀርቦ ከጸደቀ በኋላ የዞን ምሥረታው ተግባራዊ ይሆናል፡፡ ምክር ቤቱ፣ ስለ ድምጽ አሰጣጡ እና በአጠቃላይ ስለ ነበረው ሁኔታ እና ሂደት ካጣራ በኋላ ሊያጸድቅም ሊሽረውም ይችላል፡፡
ጥያቄው አዲስ ክልል የመመሥረት ቢሆን ኖሮ ግን፣ ጥያቄውን ያቀረበው ብሔረሰብ ምክር ቤት፣ለምሳሌ ሲዳማ ቢሆን የሲዳማ ምክር ቤት፣ በሁለት ሦስተኛ ድምጽ ድጋፍ ካገኘ ይሄንኑ ውሳኔ በጽሑፍ ለክልል ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ጥያቄው የቀረበለት የክልል ምክር ቤት ሕዝበ-ውሳኔ ከማዘጋጀት የዘለለ በሕግ የተቀመጠ የመከልከል ወይንም ሌላ ሥልጣን የለውም፡፡ ጥያቄውን ለማብረድ ፖለቲካዊ ሥራ ሊሰራ ይችል ይሆናል፡፡ ጥያቄው በደረሰው በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ድምፀ-ውሳኔ ማዘጋጀት አለበት፡፡
የኮንሶን በተመለከተ፣ የደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድም ሙሉ በሙሉ ጥያቄውን ካልተቀበለ አሊያም ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ካላዘጋጀ ወይንም ደግሞ የሕዝበ-ውሳኔውን ውጤት ከሻረው ጉዳዩን በይግባኝ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ማምጣት ይቻላል፡፡ምክር ቤቱ ጥያቄውን በአወንታ ተቀብሎ ሕዝበ-ውሳኔ ሊያዘጋጅ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች መኖራቸውን ስለማይታወቅ ወደ ፌደሬሽን ምክር ቤት ሊመጣ ይችላል ማለት ነው፡፡
የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት አወቃቀሩ ልክ እንደ ፌደሬሽን ምክር ቤት በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ከእያንዳንዱ ብሔር አንድ አባል ያለበት፣ ነገር ግን ከአንድ ሚሊዮን በላይ ቁጥር ካለው ለእያንዳንዱ አንድ ሚሊዮን ሌላ ተጨማሪ አንድ አባል ለምክር ቤቱ ይጨመርለታል፡፡
አባላቱ የሚመረጡት የብሔረሰቡ ዞኖች ወይንም ወረዳዎች ምክር ቤት መካከል ሆኖ መሥተዳድር ከሌላቸው ግን በቀጥታ ከብሔረሰቡ ተመርጠው ይወከሉበታል፡፡ የፌደሬሽን ምክር ቤት ደግሞ ለክልል ምክር ቤት ከተመረጡ ተወካዮች ውስጥ በክልሉ አሸናፊ የሆነው የፖለቲካ ፓርቲ የፈለገውን ሰው ከምክር ቤቱ አባላት መርጦ ይልካል፡፡ ስለሆነም፣ የደቡብ ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት የሚኖረው የአባላት ብዛት እና ክልሉ በፌደሬሽን ምክር ቤት የሚኖረው ውክልና እኩል ነው፡፡
የኮንሶ ብሔረሰብ፣ ቢያንስ 65 አባላት በሚኖሩት የብሔረሰቦች ምክር ቤት አንድ ወኪል ይኖረዋል፡፡ በፌደሬሽን ምክር ቤትም እንዲሁ፡፡ ከሕገ መንግሥታዊነት እና ሕጋዊነት ይልቅ፣ ከሕገ መንግሥቱ ጋር አብሮ በማይሄደው ፓርቲያዊ የሆነው ዴሞክራሴያዊ ማእከላዊነት ላይ በመመርኮዝ ውሳኔዎች እንደሚሰጡ ስለሚታወቅ፣የብሔረሰቦቹ ምክር ቤት አባላትም ለተመረጡበት ፓርቲ መታመን ስለሚጠበቅባቸው በክልል እና በፌደሬሽን ምክር ቤቶች መካከል የተለያዩ ውሳኔዎችን መጠበቅ አይቻልም፡፡
የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች በክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ላይ የሚኖራቸው ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የበለጠ የሚከፋው ደግሞ እነዚህ የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልሎቹን ርዕሰ መስተዳደር ጨምሮ፣የፌደሬሽን ምክር ቤት አባል መሆናቸው ነው፡፡ ክልል ላይ ላደረሱት በደል አቤቱታ ሲቀርብባቸው፣ በፌደሬሽን ምክር ቤት በዳኝነት ይሰየማሉ፡፡
የፌደሬሽን ምክር ቤት ካሉት 153 አባላት ውስጥ፣ ከ65 የማያንሱ ከደቡብ ክልል የተወከሉ ናቸው፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች የክልሉ አቋም ለኮንሶ የዞን ጥያቄን አለመቀበል ከሆነ፣ የፓርቲውን ጫና እና የተማከለ ውሳኔውን እንኳን ብንተወው፣ የፌደሬሽን ምክር ቤት ላይ አብላጫ ድምጽ ለማግኘት በጣት የሚቆጠሩ ደጋፊዎችን ማፍራት ብቻ ነው የሚጠበቅበት፡፡
የኮንሶ ብሔረሰብ ወደ ኦሮሚያ ክልል ለመጠቃለል …..
የፌደራሉ ሕገ መንግሥት እንዴት መገንጠል እንደሚቻል እንጂ ሌሎች አገራት ከኢትዮጵያ ጋር መዋሃድ ቢፈልጉ እንዴት ሊቀላቀሉ እንደሚችሉ የሚገልጽ ሥነ-ሥርዓት አላስቀመጠም፡፡ አንድ ክልል ከሌላ ክልል ጋር መዋሐድ ቢፈልግ ወይንም አንድ ብሔር ከአንድ ክልል ወጥቶ ወደ ሌላ ክልል መካለል ቢፈልግ፣ ይሄንን ማስተናገድ የሚችል ግልጽ የሆነ ሕግ የለንም፡፡ እንደ አዲስ ክልል መመሥረት ለሚፈልግ ሥርዓት አለው፡፡ ግንኙነቱም በተገንጣዩ እና በቀሪው ክልል መካከል ይሆናል፡፡ ወደሌላ ክልል መጠቃለል ከሆነ ግን የሌላ ክልል ተሳትፎን ይጠይቃል፡፡
የኮንሶ ሕዝብ በኦሮሚያ ክልል ከቦረና፣ሊበን ከሚባለው አካባቢ መጣን ብለው ስለሚያምኑ፣ የቋንቋው ቤተሰብም ኩሽቲክ በመሆኑ፣ ከኦሮሞ ሕዝብ ባህል ጋር የሚመሳሰሉ ልምዶች ስላላቸው ይመስላል ይህ ዓይነት አማራጭ ሊነሳ የቻለው፡፡ የሁለቱ ክልሎች ቅንነት እስካለ ድረስ የድንበር ግጭት ሊፈታ በሚችልበት መንገድ በስምምነት መጨረስ ይቻላል፡፡ በተጨማሪም፣ የድንበር ማካለል ጥያቄ በማንሳት በሕዝበ ውሳኔ መፍታት ይቻላል፡፡
ይህን ለማድረግ ግን፣በኮንሶ ጉዳይ፣የኦሮሚያ ክልል የድንበር ጥያቄ ማንሳት ወይንም የሕዝቡን ጥያቄ መቀበል አለበት፡፡ ከወልቃይት ጉዳይ የሚለየው የኮንሶ ሕዝብ የኦሮሞነት ጥያቄ አለማንሳቱ ነው፡፡ ሁለቱም ቢሆኑ የድንበር ማካለል ብቻ አይደሉም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄዎችም ሕጋዊ አሠራር የሚያስፈልጋቸው ይመስላል፡፡
ሲጠቃለል፣ ሁሉም ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በማናቸውም ጊዜ ክልል የመመሥረት ሕገ-መንግሥታዊ የሆነ መብት አላቸው፡፡ ነገር ግን ከሰማኒያ በላይ ክልል የማቋቋም አቅም አለን ወይ? እንኳን ክልልና ወረዳና ዞን መቋቋምም ከወጭ አንጻር ከባድ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ ከ50 በላይ የሚሆኑት ብሔረሰቦች ቁጥራቸው ከ100,000 በታች ሲሆኑ ሃያ አንዱ ደግሞ ከ10,000 በታች ናቸው፡፡ ለቀበሌና ለወረዳ የመሳሰሉት አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትንስ መቋቋም ይቻላልን? የበጀት፣ የሰው ኃይል እና የመሳሰሉትን ፍላጎቶች መሸፈን መቻሉ አጠራጣሪ ነው፡፡ይሁን እንጂ፣ መተግበር የማይቻል መብት ውሎ አድሮ ቅያሜ ማምጣቱ አይቀርም፡፡ የኮንሶም ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ እናም የአሰፋ አባተን ግጥም ልዋስና ልደምደም፡፡
“የማትበላ ወፍ ተይዛ በጭራ፣
ልቤን አደማችው ሞጭራ ሞጫጭራ፤”
እንዳለው የማይተገበር መብት አስቀምጦ የሰው ሕይወት እና ንብረት እንዲጠፋ ምክንያት ከመሆን እንደ አዋጅ ቁጥር 7/1984 በግልጽ የትኞቹ ብሔረሰቦች ምን ዓይነት መስተዳደር ማቋቋም እንደሚችሉ አስቀድሞ ሕገ መንግሥቱን በማሻሻል ማስቀመጥ፣ ወይንም ደግሞ መብቶቹን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ አንድ ጊዜ ልዩ ወረዳ፣ ሌላ ጊዜ እንደ ኮንሶ፣ ከሌሎች ጋር በመቀላቀል ዞን ማድረግ ግጭትን መጥራት ነው፡፡ ተመጣጣኝ የሕዝብ ቁጥር እያላቸው፣ አንዱን መርጦ ዞን እንዲኖረው ማድረግ ፍትሐዊ አይደለም፡፡
በኮንሶ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ሁለት ሰዎቸ ተገደሉ
በደቡብ ክልል ከዚህ ቀደም በልዩ ወረዳ አስተዳደር የነበረና በአሁን ወቅት የሰገን አካባቢ ዞን ስር ወደ ወረዳ አስተዳደርነት እንዲወረድ የተደረገው የኮንሶ ማኀበረሰብ አባላት የዞን አስተዳደር መዋቅር እንዲፈቀድላቸው መጠየካቸውን ተክትሎ በመንግሥት ተጣቂዎች በተወሰደ እርምጃ በግብርና የሚተዳደሩ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል፡፡
እሁድ መጋቢት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀትር ላይ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት አቶ ሞሌ አዛዥ እና አቶ ፋንታዬ ጊዮርጊስ በግብርና ሙያ የሚተዳደሩ ጎልማሶች እንደሆኑ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከተገደሉት በተጨማሪ 3 ሰዎች በፀኑ የቆሰሉ ሲሆን፤ ማኀበረሰቡም የተገደሉ 2 አስከሬኖች ይዞ ወደ ካራት አደባባይ በመውጣት ከፍተኛ ተቃውሞ ማሰማቱ ታውቋል፡፡
የአዲስ ሚዲያ መረጃዎች እንዳረጋገጡት፤ ይህ እስከተዘገበበት ድረስ አሁንም በኮንሶ በርካታ የደቡብ ልዩ ፖሊስ ኃይል የደንብ ልብስ የለበሱ ፖሊሶች በኮንሶ ዋና ከተማ ካራት እና በተለያዩ የገጠር ቀበሌዎች ጭምር እንደሰፈሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የህዝባዊ ተቃውሞ ዋነኛ ምክንያት 55ሺህ የኮንሶ ማኀበረሰብ ስምና ፊርማ ያለበት ስምምነት ወደ ዞን አስተዳደር እንደግ የሚል ጥያቄ ከደቡብ ክልል እስከ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ማስገባታቸውና መንግሥትም በሐረገ-መንግሥቱ መሰረት ተገቢውን መልስ ሳይሰጥ ከልዩ ወረዳነት ወደወረዳነት በማውረድ ጥያቄያቸው ምላሽ ባለማግኘቱ በተፈጠረ አለመግባባት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ተቃውሞንም ተከትሎ የኮንሶ ባህላዊ ንጉስ ካላ ገዛኸኝ ወልደ ዳዊትን ጨምሮ ከ200 ያላነሱ የአካባቢው ዜጎች መታሰራቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥት የሰጠው ይፋዊ ምላሽ ባይኖርም በአካባው ከፍተና ውጥረት መኖሩን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
በኮንሶ የመብት ጥያቄን ተከትሎ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ ህዝቡን አስቆጣ
በደቡብ ክልላዊ መንግሥት ከዚህ ቀደም ኮንሶ ራሱን ችሎ ልዩ ወረዳ በነበረበት ወቅት የዞን አስተዳደር ደረጃ እውቅና እንዲሰጠው ህዝቡ ቢጠይቅም፤ ከነበረበት ልዩ ወረዳ አንሶ በአዲሱ የሰገን ህዝቦች ዞን በሚል አስተዳደር ወደ ወረዳነት መውረዱን በመቃወም ተደጋጋሚ ጥያቄ ቢያቀርቡም ከክልሉም ሆነ ከፌደራል መንግሥት ምላሽ ሳያገኙ ቅተዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ህዝቡ የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. በኮንሶ ዋና ከተማ ካራት የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል፡፡
በተቃውሞ ሰልፉ የደቡብ ክልል ልዩ የፖሊስ ኃይልና መከላከያ ሰራዊት በወሰዱት የኃይል እርምጃ 23 ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ ህዝቡም የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የወሰዱትን የኃይል እርምጃ በመቃወም ዋና ከተማቸውን አቋርጦ የሚያልፈውን ከአርባ ምንጭ ጂንካ የሚወስደውን ዋና መንገድ ሙሉ ለሙሉ ዘግተው እንደነበርም ታውቋል፡፡
መንግሥት ተቃውሞን ለማስቆምና የተዘጋውን መንገድ ለማስከፈት በሚል በድጋሚ በወሰደው የኃይል እርምጃ ከዋና ከተማ ካራት በተጨማሪ በአጎራባች የገጠር ቀበሌዎች ጭምር በመዝለቅ ነዋሪዎች ላይ ጉዳት ማድረሱ የተገለፀ ሲሆን፤ በዚህም የደቤና ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ሷይታ ጋራ የተባሉ ግለሰብ ወዲያው ህይወታቸው እንዳለፈና የ65 ዓመት አዛውነትንና ወጣት ተስፋዬ ማሙሽን ጨምሮ 23 ሰዎች ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ እስካሁን ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ሰዎችም በከተማው ፖሊስ ጣቢያ እና በካራት ቴክኒክና ሙ ማሰልጠኛ ተቋም መታሰራቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በመጨረሻም የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተዘጋውን መንገድ በኃይል ማስከፈታቸውን የተገለፀ ሲሆን፤ ይህ ዘገባ እስከ ተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ በርካታ የክልሉ ልዩ የፖሊስ ኃይል እና የመከላከያ ሰራዊት አባላት በአካባቢው ሰገን ወንዝ ሰፍረው እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ በተለይ በዋና ከተማዋ ካራት የ1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተዘግተው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ የነበሩ ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ በከተማዋና አካባቢ የሰፈረው የመንግሥት የፀጥታ ኃይል በበቀል የህዝብ ንብረት ላይም ጉዳት እያደረሰ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ይህ እስከተዘገበበት ድረስም በአካባቢው የተለመደው የትራንሶፕርተና ማኀበራዊ አገልግሎት ከመስተጓገሉ በተጨማሪ አለመረጋጋቶች እንደሚስተዋሉ ተጠቁሟል፡፡ ይሁን እንጂ በአካባቢው የነበረውን አለመረጋጋትና ተቃሞ በተመለከተ ከመንግሥት አካል የተገለፀ ነገር የለም፡፡