በደብረማርቆስ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ እና በትግራይ ሑመራ የዓረና/መድረክ አባል ተገደሉ
በምስራቅ ጎጃም የሰማያዊ ፓርቲ ፀሐፊ እና ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በተደረገው ምርጫ በደብረማርቆስ ከተማ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ የነበረው ወጣት ሳሙኤል አወቀ ዓለም ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ማታ ላይ በሁለት ግለሰቦች በተፈፀመበት ከፍተኛ ድብደባ ሆስፒታል ቢገባም ህይወቱ ሊትርፍ አልቻለም፡፡ ወጣቱ ቀደም ሲል ሚያዝያ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. በመንግሥት ደህንነቶችና ፖሊስ አባላት ድብደባ እንደደረሰበት ከነጉዳቱ ለህዝብ ይፋ አድርጎ ነበር፡፡
ከሚያዝያው ድብበደባ በኋላም በተደጋጋሚ የደብረማርቆስ ደህንነት አባላት፣ የከተማው የፖሊስ አዛዥን ጨምሮ የብአዴን/ኢህአዴግ ካድሬዎች ዛቻና ማስፈራሪያ ይፈፅሙበት እንደነበርና ከፖለቲካው እንቅስቃሴ እንዲወጣ አሊያም ሀገር ለቆ እንዲሄድ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ እንደሰጡት በራሱ የማኀበራዊ ሚዲያ ገፆቹ ላይ ይገልፅ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ወጣቱ ይሰጠው የነበረውን ማስፈራሪያና ዛቻም እንደማይቀበልና ሰላማዊ የፖለቲካ ትግሉንም እንደሚቀጥል በተደጋጋሚ መግለፁን ከራሱ የማኀበራዊ ገፅ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተለይ በግንቦት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚደርስበት ዛቻና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ መቀጠሉን እና ከሐሰት ክስ እስከ ግድያ የሚደርስ እርምጃ ሊወስዱበት እንደታሰበ ራሱ በፌስ ቡክ ገፁ የሚከተለውን ገልፆ ነበር፡-
ውድ የደብረማርቆስ ከተማ ኗሪዎች ፤ ሰማያዊ ፓርቲን የመረጣችሁ ከ25,0000 በላይ መራጮች(ኮረጆውን) እርሱት እና በተጨማሪም በ31 ዩኒቨርስቲ የምትገኙ ከ14,000 በላይ ሰማያዊ ፓርቲን የመረጣችሁ ሌሎች ደጋፊዎች እና የኢሕአዴግ አባላትም የማያፍረው ብአዴን / ኢሕአዴግ ድምፅ መቀማቱ ሳያንስ በ21/08/2007 ዓም አፍነው ደብድበው ከሞት መትረፌ ቆጭቷቸው እሰር ቤት ለመወርወር ያለመከሰስ መብቴን እንኳን ተዳፍረው የሀሰት ክሰ እየፈጠሩ ነው!!!” በስልኬ እደተደወለም ያለፍላጎቴ ደሕንነት እያስገደደኝ ይገኛል!!!!! ተገደልሁም ታሠርሁም ፤ ታፈንኩም ነፃነት አይቀርም እና ለማሰረጃነት የደሕንነቶችን ስም፤ ፎቶግራፍ ፤ እና አድራሻ እንዲሁም በሐሠት ምሰክርነት እና ከሳሽነት የተደራጁ አካላት እና ዋና ተወካዮች የደብረማርቆስ ከተማ 04 ቀበሌ አመራሮች እና ፖሊስ ለታሪክ አሰመዘግባለሁ፡፡ ማንኛውም የምከፍለው ዋጋ ለሀገሬ እና ለነፃነት ነው ከታሠርሁም ሕሊናዬ አይታሰርም ከገደሉኝም ትግሌን አደራ በተለይ የኔ ትውልድ አደራ !!!!” አገራችን የወያኔ ዘረኞች ብቻ መፈንጫ መሆን የለባትም፡፡ ትግላችን የነፃነት ጉዟችን ጎርባጣ መድረሻችን ነፃነት ታሪካችን ዘላለማዊ ነው!!!! (ከሳሙኤል አወቀ ዓለም – የሰማያዊ ፓርቲ የደብረ ማርቆስ የሕዝብ ተወካዮች እጩ ተወዳዳሪ)
የ27 ዓመቱ የህግ ባለሙያና የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረው ወጣት ሳሙኤል የቀብር ስነ ስርዓት ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም የትግል አጋሮቹ፣ ጓደኞቹና ዘመዶቹ በተገኙበት በምስራቅ ጎጃም ዞን በጎንቻ ሲሶነሴ ወረዳ ሰቀላ ቀበሌ ግንደወይን አርባይቱ እንሰሳ ቤተ ክርስቲያን ከቀኑ 11፡30 ላይ ተፈፅሟል፡፡ በዕለቱ ማታ ከቀብር መልስ ወደ ደብረማርቆስ ይመለሱ የነበሩ ወዳጆቹና ዘመዶቹ ታግተው እንደነበር የነገር ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡ የወጣት ሳሜኤል አወቀ አሟሟትን በተመለከተ እስካሁን ከመንግሥት በኩል የተሰጠ ምንም ዓይነት ምላሽ የለም፡፡
በተያያዘ ዜና የዓረና መድረክ አባል አቶ ታደሰ አብርሃ በትግራይ ክልል በቃፍታ ሑመራ ማይካድራ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆኑ ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት አካባቢ ሶስት ሰዎች አንቀዋቸው ሞተዋል ብለው ቢሄዱም ህይወታቸው እስከ ሌሊቱ 9፡15 ድረስ እንደነበርና ከዛ በኋላ ህይወታቸው እንዳለፈ የዓረና ፓርቲ መረጃ አመልክቷል፡፡ከዚህ በፊት አቶ ታደሰ ከዓረና/መድረክ ፓርቲ አባልነትና ተሳትፎ እንዲያቆሙ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያና ማስፈራሪያ ከደህነነቶችና ከህወሓት/ኢህአዴግ አመራሮች ይደርሳቸው እንደነበርና ለዚህም አማላጅ ይላክባቸው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
የ48 ዓመቱ አቶ ታደሰ አብርሃ በፖለቲካው ንቁ ተሳትፎ ያላቸው መሆኑን እና እስካሁን ይህ እስከተዘገበበት ድረስ ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ታንቀው በተገደሉበት ወቅት በኪሳቸው የነበረው 300 ብር እንዳልተወሰደና ግድያው ፖለቲካዊ ይዘት እንዳለው ተጠቁሟል፡፡ የአቶ ታደሰ አብርሃን ገዳዮችና አሟሟታቸውን በተመለከተ አስከሬናቸው በሑመራ ሆስፒታል ምርመራ እንዲደረግ ቢሞከርም የአካባቢው ፖሊሶችና የኢህአዴግ አመራሮች መከልከላቸውም ታውቋል፡፡ በሶስት ቀናት ልዩነት የሰማያዊ እና የዐረና/መድረክ አመራሮች ተገድለዋል፡፡
ክምርጫ 2007 ዓ.ም. ጋር በተያያዘ በታህሳስ 2007 ዓ.ም. የዓረና/መድረክ አመራር የነበሩት ልጅዓለም ኻልዓዩ ማንነታቸው እስካሁን ባልታወቁ ሰዎች አዲስ አበባ ላይ ሲገደሉ በምርጫው ወቅት የኦፌኮ/መድረክ አባል በአርሲ ኮፈሌ ና በደቡብ እንዲሁ አንድ መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከምርጫ 2007 ዓ.ም. ጋር በተያያዘ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እና አባላት ግድያ እስካሁን ባይቆምም፤እስካሁን በጉዳዩ ዙሪያ ከመንግሥት የተሰጠ ምንም ምላሽ የለም፡፡
አቶ ዳዊት አስራዳ ለሶስተኛ ጊዜ የዋስትና ገንዘብ ከፍሎ ታሰረ
የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር አቶ ዳዊት አስራደ ትናንት ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም አራዳ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ በ5,000 ብር ዋስ እንዲፈታ ዋስትና የተፈቀደለት ቢሆንም ገንዘቡን ካስያዘ በኋላ ዋስትናው እንደተነሳ ተነግሮት በእስር ላይ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡ በትናንትናው ችሎት ፖሊስ ተከሳሾቹ ምስክሮችን ያባብሉብኛል በሚል ምስክሮችና መረጃዎችን አሰባስቦ እስኪያቀርብ ጊዜ ድረስ 14 ቀን እንዲሰጠው ጠይቆ የነበር ቢሆንም አቶ ዳዊት አስራደ፣ ሌላው የቀድሞው አንድነት ስራ አስፈፃሚ አባል እና የማኀበራዊ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አለነ ማፀንቱና ወይዘሪት ሜሮን አለማየሁ የ5,000 ብር ደሞዝ ያለው የሰው ዋስ ወይንም ገንዘብ አስይዘው ከእስር እንዲወጡ ፈቅዶ ነበር፡፡
ይሁንና የአቶ ዳዊት አስራደ ቤተሰቦች መፍቻ ይዘው ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ጣቢያ (ሶስተኛ) ሲሄዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ጣቢያ (ሶስተኛ) ፖሊስ አቶ ዳዊትን ለቄራ ፖሊስ ጣቢያ ማስረከቡን እንደገለጸላቸው ጠበቃው አቶ ገበየሁ ይርዳው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ የቄራ ፖሊስ ጣቢያም ከአሁን ቀደም አቶ ዳዊት አስራደ በተመሳሳይ ክስ ተፈቅዶለት የነበረውን ዋስትና ማንሳቱን በመግለጽ እንዳሰረው ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሳሳይ በተፈቀደለት ዋስትና መሰረት 5000 ብር ያስያዘውን አቶ አለነ ማህፀንቱን ፖሊስ መጀመሪያ ወደ ማታ እፈታዋለሁ፣ እንዲሁም ከቆይታ በኋላ ይግባኝ እጠይቃለሁ ብሎ እስር ላይ ቢያቆየውም አሁንም ድረስ ይግባኝ ሳይጠይቅ በእስር ላይ እንደሚገኝ ጠበቃው ገልፀዋል፡፡
መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ የታሰረው አቶ ዳዊት አስራዳ በተመሳሳይ ክስ ለሶስተኛ ጊዜ የዋስትና ገንዘብ እያስያዘ እንደገና በእስር ላይ የቆየ ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ 25 ሺህ፣ በቀጣይነትም 6 ሺህ፣ እንዲሁም ሰኔ 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ሌላ 5 ሺህ ብር በአጠቃላይ 36 ሺህ ብር ዋስትና አስይዞ እንደገና ታስሯል፡፡ አቶ ዳዊት አስራደና ወይዘሪት ሜሮን አለማየሁ ሚያዝያ 14 መንግስት ላይ በተነሳው ተቃውሞ ሰበብ በአንድ ጉዳይ ሁለት ክስ ተመስርቶባቸው በሁለት ፍርድ ቤቶች ጉዳያቸውን ሲከታተሉ ቆይተዋል፡፡ በቄራና ሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያም በፈረቃ ሲታሰሩ መቆየታቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
በሽብር የተከሰሱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ላይ የአቃቤ-ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ
᎐መገናኛ ብዙኃን የምስክሮችን ቃል መዘገብ አይችልም ተብሏ
በሽብርተኝነት ተከሰው ጉዳያቸው እየታየ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የቀድሞው አንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ፡፡ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተካተቱት አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሽና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች ላይ አቃቤ ህግ አሉኝ ያላቸውን የሰው ማስረጃዎች ምስክርነት ዛሬ ሰኔ 01 ቀን 2007 ዓ.ም በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ማሰማት ጀምሯል፡፡
ምስክሮች መሰማት ከመጀመራቸው በፊት አከራካሪው ጉዳይ ምስክሮቹ በግልጽ ችሎት ይሰሙ ወይስ በዝግ ችሎት የሚለው ነበር፡፡ በዚህም አቃቤ ህግ የጸረ ሽብር አዋጁ አንቀጽ 32 ላይ የተመለከተውን የምስክሮች ጥበቃ ድንጋጌ በመጥቀስና ምስክሮቹ ዛቻና ማስፈራሪያ እንደደረሰባቸው በማውሳት ችሎቱ ምስክሮችን በዝግ እንዲሰማ ጠይቋል፡፡ ተከሳሾች በበኩላቸው ህገ መንግስቱን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት በማስረጃ ያልተደገፈ ስለሆነ ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ተከራክረዋል፡፡
ሶስተኛ ተከሳሺ አቶ ዳንኤል ሽበሺ “አቃቤ ህግ እስከ ሞት በሚያደርስ ወንጀል ከሶናል፤ ይህን ጉዳይ በግልጽ መከታተል አለብን፡፡ እናንተ ብቻ ሳትሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብም መፍረድ አለበት” በማለት ችሎቱ ምስክሮችን በግልጽ እንዲሰማ አሳስቧል፡፡ አቶ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ “እኛ ዋስትና ተከልክለን በእስር ቤት ነን፤ የምስክሮች ስም ዝርዝር እንኳ አልተገለጸልንም፡፡ ታዲያ ማን ነው ምስክሮች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ የሚያደርስባቸው?” ሲል አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ጠይቋል፡፡
አቶ ሀብታሙ ሁሉንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዳው ደግሞ ፍርድ ቤቱ ምስክሮችን በዝግ የሚሰማ ከሆነ ሁሉም የግፍ ፍርደኛ ሆነው ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ “ሁሉንም ወክየ ነው የምናገረው…በዝግ ችሎት ምስክሮችን የምትሰሙ ከሆነ ዛሬውኑ የግፍ ፍርደኞች ሆነን ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁዎች ነን፤ ከዚህ በኋላም አንዳችንም ክርክር አናደርግም፡፡”
ፍርድ ቤቱ በአቃቤ ህግና በተከሳሾች መካከል የተነሳውን ክርክር መርምሮ ብይን የሰጠ ሲሆን በብይኑ መሰረትም የአቃቤ ህግ ምስክሮች በግልጽ ችሎት እንዲሰሙ ወስኗል፡፡ ሆኖም ግን ፍርድ ቤቱ የህትመትም ሆነ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የምስክሮችን ቃል ዝርዝር በተመለከተ መዘገብ እንደማይችሉ በብይኑ ላይ አመልክቷል፡፡
ሰኔ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. መሰማት የጀመረው የአቃቤ ህግ ምስክሮች እስከ ሰኔ 3 ቀን 2007 ዓ.ም.እንደሚቀጥል ቀጠሮ ተይዞ እንደነበርም ታውቋል፡፡
በዚሁ መዝገብ ተከሳሾች መካከል አምስተኛ ተከሳሽ የሆነው የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ ዳኞቹ ሲሰየሙና ስሙ ሲጠራ ከመቀመጫው ባለመነሳት በችሎቱ ላይ ተቃውሞውን ገልጹዋል፡፡ አቶ የሺዋስ ዳኞቹ ለምን እንደማይነሳ ሲጠይቁት በዝምታ ያለፋቸው ሲሆን፣ ተነስ ሲባልም ያለምንም ንግግር በተቀመጠበት ተረጋግቶ እንደነበር ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡
ከፍተኛው ፍርድ ቤት በብሎገሮቹ እና ጋዜጠኞች ላይ የቀረቡ የሲዲ መረጃዎችን ውድቅ አደረገ
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች እና ሶስቱ ጋዜጠኞች ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡ መዝገቡ የተቀጠረው አቃቤ ህግ አሉኝ ባላቸው ሲዲዎች እና ቀሪ ምስክሮቹን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ብይን ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጥቷል፡፡ ቀሪ ምስክሮቹን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ምስክሮቹን ለማቅረብ ፍርድ ቤቱ በተደጋጋሚ የሰጠውን እድል ባለመጠቀሙ እና ምስክሮቹን ላለማቅረቡ የሰጠው ምክንያትም በቂ ባለመሆኑ አቃቤ ህግ ያቀረበውን የተጨማሪ ጊዜ ባለመፍቀድ ከዚህ በኋላ ምስክሮቹን እንደማይሰማ አመልክቷል፡፡
አቃቤ ህግ በኤግዚቢትነት ይዟቸው የቆያቸውን የ12ቱን ሲ.ዲዎች ጉዳይ በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ሲ.ዲዎቹ በማስረጃ ዝርዝሩ ውስጥ ፕሪንት ተደርገው የተያያዙ ሰነዶችን እንደያዙ ስለተገለጸ ሲ.ዲዎቹ ከማስረጃነትም ሆነ ከኤግዚቢትነት ውድቅ መደረጋቸውን ገልጹዋል፡፡
አቃቤ ህግ በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የሲ.ዲ ዶክሜንተሪ ማስረጃ ማቅረቡን በመግለጽ ፍርድ ቤቱ እንዲመለከትለት የጠየቀ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ከሰዓት በኋላ አቃቤ ህግ ሲ.ዲውን በጽህፈት ቤት በኩል እንዲያስገባ በማዘዝ በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የቀረበውን ዶክሜንተሪ በቢሮ ዳኞቹና ጠበቆቹ እንዲመለከቱት ከተደረገ በኋላ ሲ.ዲው ሌሎችን ተከሳሾች ይመለከታል ወይስ አይመለከትም የሚለውን አይቶ ብይን ለመስጠት ለሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ተከሳሾች ጥያቄያቸውን ለፍርድ ቤቱ ለማስረዳት በሞከሩበት ጊዜ ፍርድ ቤቱ የመናገር እድል ሲነፈጉ የተስተዋለ ሲሆን፣ ተከሳሾቹ ፍርድ ቤቱ እንዲፈቅድላቸው ሲጠይቁ ‹‹ስነ-ስርዓት አድርጉ!›› ባለ ጊዜ ጦማሪ አቤል ዋበላ ‹‹እናንተ ራሳችሁ ስነ-ስርዓት አድርጉ….እንናገርበት! ይህ የመብት ጉዳይ ነው…በግልጽ ችሎት ላይ ህገ መንግስታዊ መብታችንን አክብሩ እንጂ…ጥያቄ አለን ተቀበሉን›› ሲል በመናገሩ ችሎት ደፍረሃል ተብሏል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ በአቤል ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለግንቦት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
የኢትዮጵያ 2007 ዓ.ም. ምርጫ ውጤት ተዓማኒነት ከወዲሁ ውግዘትና ትችቶች እየቀረቡበት ነው
ባለፈው ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የተደረገው ሀገር አቀፍ ምርጫ ውጤት በገዥው ኢህአዴግ አሸናፊነት መጠናቀቁን ምርጫ ቦርድ ይፋ ያደረገ ሲሆን፤ እስካሁን ቦርዱ ደረሱኝ ባላቸው ከ547 ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ፤ 440 መቀመጫ ውጤቶች በሙሉ ኢህአዴግ ማሸነፉን ይፋ አድርጓል፡፡ ቀሪዎቹ 107 መቀመጫ ውጤቶች አሸናፊ በቦርዱ ባይገለፅም፤ የኢህአዴግ ደጋፊ መሆኑን በድረ-ገፁ የገለፀው “አይጋፎረም” ገና ምርጫው ሳይጠናቀቅና በይደር የታለፉ ጣቢያዎች እያሉ በምርጫው ዕለት ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት ኢህአዴግ 100 ማሸነፉን ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ ድረ-ገፁ የመድረክ አንጋፋ ተወካዮች ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ እና ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ ሁሉም የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች በመላ ሀገሪቱ ሙሉ ለሙሉ በኢህአዴግ መሸናፋቸውን ይፋ ያደረገውን መረጃ፤ ከሁለት ቀናት በኋላ ሊያነሳ ችሏል፡፡ ምርጫ ቦርድም ለጊዜው በቁጥር ካስቀመጠው መቀመጫ በስተቀር ምርጫው ሳይጠናቀቅ ቀድሞ የኢህአዴግን ማሸነፍ ይፋ ካደረገው አይጋ ፎረም የተለየ መረጃ እስካሁን ሊሰጥ አልቻለም፡፡
በምርጫው ዋዜማ እና ዕለት በተለይም ከገዥው ኢህአዴግ ጋር ጠንካራ ተፎካካሪ የነበሩት የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር (መድረክ) እና የሰማያዊ ፓርቲ ታዛቢዎች በተለያዩ የሀገሪቱ ምርጫ ጣቢያዎች በደህንነት እና ፖሊሶችታስረውና ታግተው እንዳይታዘቡ መደረጋቸውን ፓርቲዎቹ ቀድመው ማሳወቃቸው ይታወሳል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ የምርጫውን ውጤትም ሆነ ሂደቱን እንደማይቀበሉት አስታውቀዋል፡፡ ኢህአዴግ በምርጫ 1997 ዓ.ም. በተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ሽንፈት ገጥሞት ስልጣኑን ባይለቅም፤ በምርጫ 2002 ዓ.ም. 99.6 በመቶ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ማግኘቱን ይፋ ካደረገ በኋላ የነበረው የምርጫ ሂደትና ውጤት ላይ በሀገር ውስጥና ከውጭ የተለያዩ ቅሬታዎችን እና ትችቶችን ማስተናገዱ ባይዘነጋም፡፡
ምርጫውን የታዘበው የአፍሪካ ህብረት በሰጠው ጊዜያዊ መግለጫ ታዛቢ ቡድኑ ከታዘባቸው ከ21 በመቶ የማያንሱ የምርጫ ጣቢያዎች ኮሮጆዎች ድምፅ መስጠት ከመጀመሩ በፊት በዶ መሆናቸው ተከፍቶ እንዲታይታዛቢ ቡድኑ ቢጠይቅም፤ በየጣቢያው ያሉ የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚዎች ፈቃደኛ አለመሆናቸውን እና የድምፅ መስጫ ኮሮጆዎቹ ተከታታይነት ያለው ቁልፎች እንዳልነበሩት በመግለፅ ምርጫው ነፃ ነበር ለማለት እንደሚቸገር አስታውቋል፡፡ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያያን ሀገር አቀፍ ምርጫ ሲታዘቡ የነበሩት የአውሮፓ ህብረት እና የአሜሪካው ካርተር ማዕከል ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን እንዳልታዘቡ ታውቋል፡፡
የእሁዱ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በተደረገው ምርጫ ውጤት ግን ከቀድሞው በባሰ 100 % የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ ያለምንም አማራጭ ሐሳብ በገዥው ኢህአዴግና አጋሮቹ ሊሞላ እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ውጤቱም የህዝብ ድምፅ ዘረፋና ማጭበርበር እንዲሁም የተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ በደረሰው ተፅዕኖ የመጣ እንጂ በነፃ ምርጫ የተገኘ የህዝብ ድጋፍ አይደለም በሚል ከወዲሁ ውግዘትና ትችት ገጥሞታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ውጤቱ የምርጫ ቦርድን ገለልተኛነትንም የበለጠ ጥያቄ ውስጥ ቢከትም፤ ውጤቱን አስመልክቶ ከዥው ፓርቲ በኩል እስካሁን የተሰጠ ይፋ መግለጫ የለም፡፡








