ፍትህ ሚኒስቴር የጠበቃ ተማም አባቡልጉን የጥብቅና ፈቃድ ማገዱ ታወቀ
የታዋቂው ጠበቃ ተማም አባቡልጉ የጥብቅና ሙያቸው የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት የጥፋተኝነት ብይን በተላለፈበት ቀን መሰረዙ ታወቀ፡፡ ፍትህ ሚኒስቴር የአቶ ተማም አባቡልጉን ጥብቅና ለአንድ ዓመት ከሰባት ወር የጥብቅና ፈቃዳቸው መታገዱ ታውቋል፡፡
የህዝበ ሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ፣ የፖለቲካ አመራሮች፣ ጋዜጠኞች እና በተለያዩ የህግ ጉዳዮች ጠበቃ የሆነው ጠበቃ ተማም አባቡልጉ በፍርድ ቤት ላይ በሚያደርጋቸው ክርክሮች በተለይም መንግስት ከጅሃዳዊ ሀረካት ጀምሮ የሰራቸውንና ኢትዮጵያ ውስጥ የፍትህ ስርዓቱን ዝቅጠት በመረጃና በህግ በማጣቀስ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ በማጋለጣቸው ምክንያት ከዚህ ክስ ተመስርቶባቸው እንደነበር ይታወቃ፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ማስፈራሪያና ዛቻዎች ከመፈጸማቸው ሌላ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ይታወቃል፡፡ ይህ እስከ ተዘገበበት ድረስ የፈቃዱ መሰረዝ ምክንያት አልታወቀም፡፡
ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው
በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቃገኘው የክስ መዝገብ የተከሰሱት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በመያዝ የሕግ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ድብደባ ተፈፀመባቸው፡፡ ድብደባው የተፈፀመባቸው ዛሬ መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ..ም. እነ አብርሃ ደስታ በነበራቸው የፍርደ ቤት ቀጠሮ ተገኝተው የሚጠበቅባቸውን የሕግ አገልግሎት ሰጥተው ከፍርደ ቤት ከወጡ በኋላ ብሔራዊ አረቄ ፋብሪካ አካባቢ ወደ አዋሳ ለሌላ የህግ አገልግሎት ለመስጠት እያመሩ በነበረበት ወቅት በማያውቁት ግለሰብ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ከስፍራው የደረሰን መረጃ አመልክታል፡፡
ደብዳቢው ግለሰቡ ድብደባ ከፈፀመ በኋላ እሮጦ ለማምለጥ ሲሞክር በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ትብብር የተያዘ ሲሆን፤ በወቅቱም ደብዳቢው የአእምሮ ችግር እንዳለበት ለመምሰል ከሞከረ በኋላ የብአዴን-ኢህአዴግ አባል እንደሆነና 400 ብርም እንደተከፈለው መናገሩን እንዲሁም አዲስ አበባ ለቡ አካባቢ 105 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቶት ቤት እየሰራ እንደሆነ መግለፁን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ጠበቃ ተማም ነገ አዋሳ ላይ ሌላ የነ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ የፍርድ ቤት ጉዳይ ስላለ ዛሬ የግድ ሄደው ማደር ስለነበረባቸው ደብዳቢውን እንዲለቀቅ አድርገው ወደ አዋሳ ማምራታቸው ታውቋል፡፡
ጠበቃ ተማም ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጉዳይ በተጨማሪ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎችን፣ የተለያዩ ጋዜጠኞችን፣በሀገር ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን እና ሌሎች በርካታ የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ለማኀበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ከጥብቅና አገልግሎት በተጨማሪ በተለያዩ ጋዜጦች የህግ ነክ ጉዳዮችን በተመለከተ ይፅፉ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ በዚህም ከመንግሥትና ከስርዓቱ ደጋፊዎች ከፍተኛ ጫና እየተደረገባቸው እንደሆነ ይታወቃል፡፡

