Tag Archives: TPLF/EPRDF Ethiopia

በሽብር የተከሰሱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ላይ የአቃቤ-ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ

᎐መገናኛ ብዙኃን የምስክሮችን ቃል መዘገብ አይችልም ተብሏ

prisoners

በሽብርተኝነት ተከሰው ጉዳያቸው እየታየ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የቀድሞው አንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ፡፡ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተካተቱት አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሽና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች ላይ አቃቤ ህግ አሉኝ ያላቸውን የሰው ማስረጃዎች ምስክርነት ዛሬ ሰኔ 01 ቀን 2007 ዓ.ም በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ማሰማት ጀምሯል፡፡
ምስክሮች መሰማት ከመጀመራቸው በፊት አከራካሪው ጉዳይ ምስክሮቹ በግልጽ ችሎት ይሰሙ ወይስ በዝግ ችሎት የሚለው ነበር፡፡ በዚህም አቃቤ ህግ የጸረ ሽብር አዋጁ አንቀጽ 32 ላይ የተመለከተውን የምስክሮች ጥበቃ ድንጋጌ በመጥቀስና ምስክሮቹ ዛቻና ማስፈራሪያ እንደደረሰባቸው በማውሳት ችሎቱ ምስክሮችን በዝግ እንዲሰማ ጠይቋል፡፡ ተከሳሾች በበኩላቸው ህገ መንግስቱን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት በማስረጃ ያልተደገፈ ስለሆነ ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ተከራክረዋል፡፡
ሶስተኛ ተከሳሺ አቶ ዳንኤል ሽበሺ “አቃቤ ህግ እስከ ሞት በሚያደርስ ወንጀል ከሶናል፤ ይህን ጉዳይ በግልጽ መከታተል አለብን፡፡ እናንተ ብቻ ሳትሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብም መፍረድ አለበት” በማለት ችሎቱ ምስክሮችን በግልጽ እንዲሰማ አሳስቧል፡፡ አቶ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ “እኛ ዋስትና ተከልክለን በእስር ቤት ነን፤ የምስክሮች ስም ዝርዝር እንኳ አልተገለጸልንም፡፡ ታዲያ ማን ነው ምስክሮች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ የሚያደርስባቸው?” ሲል አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ጠይቋል፡፡
አቶ ሀብታሙ ሁሉንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዳው ደግሞ ፍርድ ቤቱ ምስክሮችን በዝግ የሚሰማ ከሆነ ሁሉም የግፍ ፍርደኛ ሆነው ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ “ሁሉንም ወክየ ነው የምናገረው…በዝግ ችሎት ምስክሮችን የምትሰሙ ከሆነ ዛሬውኑ የግፍ ፍርደኞች ሆነን ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁዎች ነን፤ ከዚህ በኋላም አንዳችንም ክርክር አናደርግም፡፡”
ፍርድ ቤቱ በአቃቤ ህግና በተከሳሾች መካከል የተነሳውን ክርክር መርምሮ ብይን የሰጠ ሲሆን በብይኑ መሰረትም የአቃቤ ህግ ምስክሮች በግልጽ ችሎት እንዲሰሙ ወስኗል፡፡ ሆኖም ግን ፍርድ ቤቱ የህትመትም ሆነ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የምስክሮችን ቃል ዝርዝር በተመለከተ መዘገብ እንደማይችሉ በብይኑ ላይ አመልክቷል፡፡
ሰኔ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. መሰማት የጀመረው የአቃቤ ህግ ምስክሮች እስከ ሰኔ 3 ቀን 2007 ዓ.ም.እንደሚቀጥል ቀጠሮ ተይዞ እንደነበርም ታውቋል፡፡
በዚሁ መዝገብ ተከሳሾች መካከል አምስተኛ ተከሳሽ የሆነው የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ ዳኞቹ ሲሰየሙና ስሙ ሲጠራ ከመቀመጫው ባለመነሳት በችሎቱ ላይ ተቃውሞውን ገልጹዋል፡፡ አቶ የሺዋስ ዳኞቹ ለምን እንደማይነሳ ሲጠይቁት በዝምታ ያለፋቸው ሲሆን፣ ተነስ ሲባልም ያለምንም ንግግር በተቀመጠበት ተረጋግቶ እንደነበር ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

ከፍተኛው ፍርድ ቤት በብሎገሮቹ እና ጋዜጠኞች ላይ የቀረቡ የሲዲ መረጃዎችን ውድቅ አደረገ

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት የዞን ዘጠኝ ብሎገሮች እና ሶስቱ ጋዜጠኞች ግንቦት 19 ቀን 2007 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡ መዝገቡ የተቀጠረው አቃቤ ህግ አሉኝ ባላቸው ሲዲዎች እና ቀሪ ምስክሮቹን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ብይን ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጥቷል፡፡ ቀሪ ምስክሮቹን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ አቃቤ ህግ ምስክሮቹን ለማቅረብ ፍርድ ቤቱ በተደጋጋሚ የሰጠውን እድል ባለመጠቀሙ እና ምስክሮቹን ላለማቅረቡ የሰጠው ምክንያትም በቂ ባለመሆኑ አቃቤ ህግ ያቀረበውን የተጨማሪ ጊዜ ባለመፍቀድ ከዚህ በኋላ ምስክሮቹን እንደማይሰማ አመልክቷል፡፡

z9

አቃቤ ህግ በኤግዚቢትነት ይዟቸው የቆያቸውን የ12ቱን ሲ.ዲዎች ጉዳይ በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ሲ.ዲዎቹ በማስረጃ ዝርዝሩ ውስጥ ፕሪንት ተደርገው የተያያዙ ሰነዶችን እንደያዙ ስለተገለጸ ሲ.ዲዎቹ ከማስረጃነትም ሆነ ከኤግዚቢትነት ውድቅ መደረጋቸውን ገልጹዋል፡፡

አቃቤ ህግ በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የሲ.ዲ ዶክሜንተሪ ማስረጃ ማቅረቡን በመግለጽ ፍርድ ቤቱ እንዲመለከትለት የጠየቀ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ከሰዓት በኋላ አቃቤ ህግ ሲ.ዲውን በጽህፈት ቤት በኩል እንዲያስገባ በማዘዝ በአንደኛ ተከሳሽ ላይ የቀረበውን ዶክሜንተሪ በቢሮ ዳኞቹና ጠበቆቹ እንዲመለከቱት ከተደረገ በኋላ ሲ.ዲው ሌሎችን ተከሳሾች ይመለከታል ወይስ አይመለከትም የሚለውን አይቶ ብይን ለመስጠት ለሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ተከሳሾች ጥያቄያቸውን ለፍርድ ቤቱ ለማስረዳት በሞከሩበት ጊዜ ፍርድ ቤቱ የመናገር እድል ሲነፈጉ የተስተዋለ ሲሆን፣ ተከሳሾቹ ፍርድ ቤቱ እንዲፈቅድላቸው ሲጠይቁ ‹‹ስነ-ስርዓት አድርጉ!›› ባለ ጊዜ ጦማሪ አቤል ዋበላ ‹‹እናንተ ራሳችሁ ስነ-ስርዓት አድርጉ….እንናገርበት! ይህ የመብት ጉዳይ ነው…በግልጽ ችሎት ላይ ህገ መንግስታዊ መብታችንን አክብሩ እንጂ…ጥያቄ አለን ተቀበሉን›› ሲል በመናገሩ ችሎት ደፍረሃል ተብሏል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ በአቤል ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለግንቦት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ለቀድሞው የአንድነት አመራር “ እናርድሃለን፣…ራስህን በጥይት እንበትነዋለን….” የሚል ማስጠንቀቂያ ተሰጣቸው

የመንግሥት ደህንነቶች ለቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት ተክሌ በቀለ የመጨረሻያሉትን እናርድሃለን፣…ራስህን በጥይት እንበትነዋለን..የሚል ማሰጠንቀቂ መስጠታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ማስጠንቀቂያውና ማስፈራሪው በሌሎቹም የቀድሞው የፓርቲ አመራሮች ላይም የቀጠለ ሲሆን፣በዛው ዕለት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ አባልና የማኀበራዊ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አለነ ማፀንቱ መታሰሩ ታውቋል፡፡በተለይ የአቶ ተክሌ በቀለ ሁኔታን በተመለከተ ራሳቸው በአጭሩ እንደሚከተለው አስቀምጠውታል፡፡

ተክሌ በቀለ

ተክሌ በቀለ

ለሆነ ጎዳይ ከእንድ ጓደኛየ ጋር ዛሬ ግንቦት 7 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ 7፡30 ላይ ከቦሌ ተነስተን ኮተቤ(02) አካባቤ ሄድን፡፡ የቤት ታርጋ የለጠፈች ነጭ መኪና 4 ጎሮምሶችን ይዛ ትከተን ነበር፡፡ ቦታ ስተን ኑሮ የሆነ መታጠፊያ ላይ ወደ ኋላ ስንዞር ተገጣጠምን፡፡ ባንድ መስመር ስዞር ቦታ የዘጋሁባቸዉ መስሎኝ ይቅርታ ስጠይቃቸዉ የሚነዳው ወንድም መኪናዉን አቁሞ ሳይወርድ የስድብ መዓት አወረደብኝ፡፡ ያ ያገሬ ልጅ! ከዚያም ሄዱ፡፡እነማን እንደ ሆኑም ገባኝ፡፡ ጓደኛየ ወደ ቢሮዉ ገብቶ ጉዳዩን ጨርሶ እስኪወጣ ወርጄ ስጠብቀዉ በመኪኗ ተመልሰዉ መጡ፡፡ በማዶ ላይ የቀን ሰራተኞች ምሳ በልተዉ ሰዓቱ እስኪደርስ ጥላ ላይ ያረፉ ነበሩ፡፡ሁኔታዉን ይከታተሉ ኖሮ ትተዉኝ ሲሄዱ መጥተዉ ጠየቁኝ፡፡የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባል እንደነበርኩና አሁን እንደሌለሁበት፤የስርኣቱ ደህንነት ነን ባዮች ሲሆኑ እያስፈራሩኝ መሆኑንም ስነግራቸዉ በጣም ተናደዱ፡፡ለምን ግርግር አትፈጥርም ነበር አንለቃቸዉም ነበር…..ክብር ለዜጎች! ውድ ህይወት ተከፍሎበት በነበረ ስርዓት ውስጥ፤ህግ አክባሪና ሃይማኖተኛ በሆነ ማህበረሰብ ዉስጥ ተወልዶ ያደገ፤ከድሃ ግብር ደሞዝ የሚበላ የደህንነት ሰራተኛ ነኝ ባይ “እናርዳሃለን….መንግስት ነን፣ ራስህን በጥይት እንበትነዋለን…የምትሰራዉን ሁሉ እናዉቃለን…እድሉን ተጠቀምበት የመጨረሻህ ነዉ….” የሚሉ ቃላት እንዲናገሩ ሰልጥነዉ ሲላኩ በእዉነት ያሳፍራል፡፡ ዱላ ቀረሽ ስድብ አዝንበዉብኝ መኪናቸዉን አስነስተዉ እብስ አሉ፡፡ የመጀመሪያየ ባይሆንም የከዚህ ቀደሞቹ ግን ጨዋዎች ነበሩ! ግን፤ አርፈንም እንድናርፍ አይፈቀድልንም እንዴ? እኛ እንሰራው የነበረው ፖለቲካ ፍጽም ሰላማዊና ህገ መንግስታዊ ነበር፡፡ አሁንም መብታችን ነዉ፡፡ የነአሞራዉ ደም የፈሰሰዉ ለዚህም እንደነበር እንረዳለን፡፡ተሸብራችሁ ከሆነ በስራችሁ እንጂ በኛ አይደልም፡፡ እኛ ግን ለግዜው ከጨዋታው ውጪ ስላደረጋችሁን በጨዋታው ሜዳ የለንበትም፡፡ ለማስጠንቀቂያውም ለመረጃውም ስርዓት አለው፡፡ የመንግስት አካል የሆነ ተቋም በፈለገዉ መንገድ ህጋዊ ሆኖ ማናገር ይችላል፡፡ መንግስትነት ትልቅ ሃላፊነትና ተቋም መሆኑን ልንነግራችሁ አቅም የለንም፡፡ የተበተነን የቀድሞ የፓርቲ አመራር ማስፈራራትና ማሰር ተራ ብቀላ ይመስላል፡፡ ተራ ህይወት እየመራንም፤አርፈን ተቀምጠንም ልትተዉን ካልቻላችሁ በግፉ መንገድ ግፉበት፡፡ እኛ ከማን እንበልጣለንና ነው!!!

የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ላይ የኢህአዴግ እስር እና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ ቀጥሏል

 በላይ ፈቃዱ

በላይ ፈቃዱ

በኢትዮጵያ የሰላማዊ ፖለቲካ ትግል ትልቅ ተስፋ ተጥሎበት የነበረውና በመላ ሀገሪቱ ፅህፈት ቤቶች ከፍቶ ሲንቀሳቀስ የነበረው የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ላይ የኢህአዴግ እስር እና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለፀ፡፡ በተለይ ምርጫ ቦርድ ባለፈው የካቲት 2007 ዓ.ም. ፓርቲው የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ዋነኛ የኢህአዴግ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቅረብ መወሰኑን እና ለዚህም ይፋ የምርጫ እንቅስቃሴ መጀመሩን ተከትሎ ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን በማፍረሱ የቀድሞው የአንድነት አመራሮች እና አባላት ከፖለቲካው እንቅስቃሴ እንዲታቀቡ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡

ተክሌ በቀለ

ተክሌ በቀለ

ይሁን እንጂ የተወሰኑ የአንድነት ፓርቲ አመራሮች እና አባላት ፓርቲያቸው በኢህአዴግ እና በምርጫ ቦርድ በይፋ ተነጥቆ እንዲፈርስ በመደረጉ የተወሰኑ አመራሮች እና አባላት ሰማያዊ ፓርቲን በይፋ ተቀላቅለው የፖለቲካ ትግሉን ቢጀምሩም አሁንም ከኢህአዴግ እስርና ማስፈራሪያ መዳን አልቻሉመ፡፡ በዚህም በርካታ የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ወጣት አመራሮች እና አባላት ሰማያዊ ፓርቲን ከተቀላቀሉ በኋላ እነ ስንታየሁ ቸኮል በእስር ላይ ይገኛሉ፡:

አለነ ማፀንቱ

አለነ ማፀንቱ

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፓርቲያቸው በምርጫ ቦርድ ፈርሶ፤ ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን ለእኔ ለሚታዘዙልኝ በሚል ራሱ ቦርዱ ለመረጣቸው አካላት ቢያስተላልፍም በርካታ የቀድሞ የአንድነት አመራሮች ከፖለቲካ ድርጅት ትግል እንዲታቀቡ ቢደረግም፤ ማስፈራሪያና እስሩ ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡ በዚህም ትናንት ግንቦት 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ አባልና የማኀበራዊ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አለነ ማፀንቱ ያለምንም የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ከመኖሪያ ቤቱ በደህንነት እና በፖሊስ ኃይል ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ ከፍተኛ ድብደባ በመፈፀም የኢሜይል አካውንቱን የይለፍ ቃል በግድ በደህንነቶች ከተወሰደ በኋላ በአዲስ አበባ ጉለሌ ፖሊስ ጣቢያ መታሰሩ ታውቋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ፓርቲው ፕሬዘዳንት የነበረው አቶ በላይ ፈቃዱ እና ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት የነበረው አቶ ተክሌ በቀለም በተመሳሳይ ዕለት በደህንነት ኃይሎች ከፍተኛ ማስፈራሪ እና ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዳዊት አስራደ

ዳዊት አስራደ

ፓርቲው በምርጫ ቦርድ ከፈረሰ በኋላ የስራ አስፈፃሚ አባል የነበረው አቶ ዳዊትአስራደን ጨምሮ በርካታ ወጣቶች እስማኤል ዳውድ፣ ስንታየሁ ቸኮል፣ መሳይ ትኩዕ፣ ፋንቱ ዳኜ በደህንነት እና ፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸውና መደብደባቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲው ወጣት ከፍተኛ አመራሮች የነበሩት አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ ዳንኤል ሺበሺ እና ሀብታሙ አያሌው በእስር ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ አንድነት የፊታችን እሁድ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሚደረገው ሀገራዊ ምርጫ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከ450 በላይ ዕጩ ተወዳዳሪዎችን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ በቀጠለው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል እንቅስቃሴ ምክንያት የካቲት 2007 ዓ.ም. ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን አፍርሶ “ለእኔ ለሚታዘዙልኝ…” በሚል ጋዜጣዊ መግለጫ ራሱ ቦርዱ ለመረጠው አመራር የፓርቲውን ስም መስጠቱን ይፋ ማድረጉ አያዘነጋም፡፡

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል 6 ወር ሲፈረድበት፤ ፋንቱ ዳኜ ከመኖሪያ ቤቱ ተወስዶ መታሰሩ ተሰማ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ የአዲስ አበባ ወጣቶች አመራር የነበረውና በአሁን ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ አባል ወጣት ስንታየሁ ቸኮል 6 ወር እስራት ተፈረደበት፡፡ ወጣት ስንታየሁ ቄራ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ ደህንነቶች ተወስዶ ከታሰረ በኋላ የፌደራሉ ፍርድ ቤት ቄራ ምድብ ችሎት ቀርቦ የአካባቢው የኢህአዴግ ካድሬዎች ከመሰከሩበት በኋላ እንደተፈረደበት ታውቋል፡፡

ስንታየሁ ቸኮል

ስንታየሁ ቸኮል

ፍርድ ቤቱ ለቀረበበት ክስ መከላከያ ምስክር አሊያም የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ቢጠይቀውም፤ ወጣት ስንታየሁ “ከሳሼም፣መስካሪየም፣ፈራጁም ኢህአዴግ ስለሆነ የመከላከያ ምስክር ብዬ ሰዎችን አላንገላታም፣የቅጣት ማቅለያም አላቀርም፤የፈለጋችሁትን ፍረዱ” ሲል ችሎት ላይ መናገሩ ትውቋል፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ በችሎት የተናገርውና የቀረበበት ክስ ከዓመት በላይ የሚያስቀጣ ቢሆንም፤ ፍርድ ቤቱ በ6 ወር እስራት እንዲቀጣ መፍረዱ ታውቋል፡፡

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከአንባቢ ውጭ የተደረጉ ጋዜጦችን መፈክር ይዞ

ወጣት ስንታየሁ ቸኮል በተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከአንባቢ ውጭ የተደረጉ ጋዜጦችን መፈክር ይዞ

ስንታየሁ ቸኮል ባለትዳርና የሁለት ልጆች አባት ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም ከቀድሞው አንድነት ፓርቲ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ የፀጥና ደህንነት ኃይሎች ተደጋጋሚ ሲታሰርና ሲደበደብ እንደነበር ይታወቃል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ በተደረጉ በተለያዩ የስርዓቱ ተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የስርዓቱን ድርጊት የሚያመለክቱ ልዩ መፈክሮችን ይዞ በመውጣትም ይታወቃል፡፡

ወጣት ፋንቱ ዳኜ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ ቅስቀሳ ላይ እያለ የተነሳው

ወጣት ፋንቱ ዳኜ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ ቅስቀሳ ላይ እያለ የተነሳው

በተያያዘ ዜና ሰኞ ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ኦዲትና ኢንስፔክሽን ፀሐፊ የነበረው ፋንቱ ዳኜ ሳሪስ አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች ተይዞ መታሰሩ ታውቋል፡፡ አቶ ፋንቱ በወቅቱ ሳሪስ ፖሊስ ጣቢያ ቢወሰድም እስካሁን ለምን እንደተያዘ እና እንደታሰረ የተገለፀ ነገር እንደሌለ ለማወቅ ተችሏል፡፡ወጣት ፋንቱ ከቀድሞ የአንድነት ፓርቲ ጠንካራ ወጣት አመራሮች መካከል አንዱ እንደነበር ምንጮች አስታውቀዋል፡፡