Daily Archives: May 2nd, 2013

የነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና አንዱዓለም አራጌ ይግባኝ ላይ ውሳኔ ተሰጠ

 

 

esekinderበፌደራሉ አቃቤ ህግ በሽብርተኝነት ክስ ተመሰርቶባቸው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት በነ አንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ የተላለፈውን ውሳኔ በመቃወም 6 ኪሎ በሚገኘው የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ የጠየቁ ሲሆን ፍርድ ቤቱም ውሳኔ ለመስጠት ለ5 ጊዜ ተደጋጋሚ ቀነ ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ሚያዚያ 24 ቀን 2005ዓ.ም. ከረፋዱ 4፡00 ሰዓት ላይ በዋለው ችሎት ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት ቀደም ሲል በአንዱዓለም አራጌ የክስ መዝገብ ከተከሰሱት 24 ተከሳሾች መካከል ይግባኝ የጠየቁት የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊና ምክትል ሊቀመንበር አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ ሌላው የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አቶ ናትናኤል መኮንን፣ ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለም፣  አቶ ዮሐንስ ተረፈ እና የቀድሞ ፓርላማ አባል የተከበሩ አቶ አንዱዓለም አያሌው  በተጨማሪ እውቁ የፖለቲካ ተንታኝ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ ናቸው፡፡

ቀደም ሲል የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአቶ አንዱዓለም አራጌ ላይ ዕድሜ ልክ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ላይ 18 ዓመት፣ አቶ ናትናኤል መኮንን ላይ 18ዓመት፣ ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለም 15ዓመት፣ አቶ ዮሐንስ ተረፈ 13ዓመት፣  አቶ አንዱዓለም አያሌው 14ዓመት፣ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ 25ዓመት ፅኑ እስራት እንደተፈረደባቸው ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ሐሙስ ሚያዚያ 24 ቀን 2005ዓ.ም. የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በዋለው ችሎት ተከሳሾች በተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ክስ የአቶ ክንፈሚካቼል ደበበን የቅጣት ውሳኔ ከ25ዓመት ወደ 16 ዓመት ዝቅ ከማድረግ በስተቀር ከላይ የተጠቀሱትን የሌሎቹን ይግባኝ ክስ ተቀባይነት ሳያገኝ የስር ፍርድ ቤቱ የቅጣት ውሳኔን(ፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት 3ኛ ወንጀል ችሎት የቅጣት ውሳኔ) እንዲፀና በመወሰን የፌደራሉ ማረሚያ ቤት ቅጣቱን እንዲያስፈፅም ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በዕለቱ በችሎት ተሰይመው የነበሩትና ይግባኙን ሲመረምሩ የቆዩት ዳኛ ሽመክት አሰፋ፣ ዳኛ በላቸው አንሺሶ እና ዳኛ ዳኜ መላኩ ሲሆኑ የፍርድ ውሳኔውን በንባብ ያሰሙት የመሐል ዳኛው ዳኜ መላኩ ናቸው፡፡ ውሳኔው በንባብ ከመሰማቱ በፊት የመሐል ዳኛው ዳኜ መላኩ ተከሳሾችና የችሎት ታዳሚዎች ውሳኔው በሚሰማ ሰዓት ስነስርዓት እንዲይዙ ማስጠንቀቂያ በመስጠት  የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን ውሳኔ በንባብ አሰምተዋል፡፡ በችሎቱ ላይ ውሳኔውን ያነበቡት የመሐል ዳኛው ዳኜ መላኩ በተደጋጋሚ የመጨናነቅ ስሜት የታየባቸው ከመሆኑ በተጨማሪ ፊታቸውን በመሃረም እየጠራረጉና ያነበቡትን አረፍተ ነገር በመደገሃገም ይቅርታ ያዘወተሩ ሲሆን የግራና ቀኝ ዳኞች የነበሩት ሽመክት አሰፋና በላቸው አንሺሶም በከፍተኛ ትካዜ ላይ ሆነው ተከሳሾችን በመመልከት የተለመደው የፊታቸው ገፅታ በወቅቱ አልነበረም ነበር፡፡ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የስር ፍርድ ቤቱ የቅጣት ውሳኔ ከፍተኛ የሚለውን ወደመካከለኛ ያወረደው መሆኑን፣ በተከሰሱበት 2ኛው ክስ ላይ ደግሞ ተከሳሾቹ በነፃ ያሰናበተ መሆኑን በመግለፅ ነገር ግን የቅጣት ውሳኔ ዓመቱ ላይ ምንም ለውጥ እንደማይኖረው አስታውቋል፡፡

በችሎቱ ላይ የተገኙት ተከሳሾች አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን እና አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ ብቻ ሲሆኑ ቀሪዎቹ አቶ አንዱዓለም አያሌው ፣ አቶ ዮሐንስ ተረፈ እና ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለም ረቡዕ ሚያዚያ 23 ቀን 2005ዓ.ም. ይግባኝ ቀጠሮ እንዳላቸው እየታወቀ ወደ ዝዋይ ወህኒ ቤት በመወሰዳቸው ሊገኙ ባይችሉም በሌሉበት የይግባኝ ውሳኔው ተሰጥቷል፡፡ በሰዓቱ ከአቃቤ ህግ አቶ ብርሃኑ ወንድማገኝ ብቻ የተገኙ ሲሆን ከተከላካይ ጠበቆች አቶ አበበ ጉታ፣ አቶ ደርበው ተመስገን እና አቶ ሳሙኤል አባተ ተገኝተዋል፡፡

በመጨረሻም በውሳኔው ዙሪያ ከተከሳሾቹ መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ”እውነት ተደብቆ አይቀርም፣ይህን ህዝብ እንዲያውቅልኝ እፈልጋለሁ…”፤ አቶ ናትናኤል መኮንን “መጀመሪያም ቢሆን የተከራከርናው ፍትህ እናገኛለን ብለን አይደለም” ሲል ባለቤቱ ወይዘሮ ፍቅርተ በበኩላቸው “እኔ ቀድሞውንም ለውጥ ይኖራል ብዬ አልጠበኩም” ብለዋል፡፡ አቶ አንዱዓለም አራጌ በበኩላቸው “…ፍትህ በኢትዮጵያሞተ ይህንንም ዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ሊያውቀው ይገባል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ችሎቱን ለመከታተል በርካታ የታሳሪዎቹ ቤተሰቦችና ወዳጆች፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች፣ የተለያዩ ፖለቲከኞችና አድናቂዎቻቸው እንዲሁም የዓለም አቀፉ ዲፕሎማቶች የተገኙ ሲሆን ወደ ችሎት የገቡት ግን ጥቂቶች ብቻ ናቸው፡፡ በነበረው ሁኔታና በውሳኔውም በተለይ እጅግ ማዘናቸውንም ያነጋገርናቸው  የታሳሪ ቤተሰቦቻቸውና አድናቂዎቻቸው ገልፀዋል፡፡

ስለአቡነ ጴጥሮስ ፍቅር ስል…

በእውቀቱ ስዩም

ማለዳ መነሣት አልወድም፡፡ዛሬ ግን አቡነ ጴጥሮስ ከመታሰቢያቸው ዙፋን ሲወርዱ ለመታዘብ በማለዳው ካልጋየ ጨክኘ ወረድሁ፡፡ለአቡነ ጴጥሮስ ፍቅር ስል የማለዳ እንቅልፌን ብሰዋ አይቆጨኝም፡፡በቅርቡ በሚከፈተው ጦማሬ ላይ ስለ ጀግናው ጴጥሮስ በሰፊው የመጻፍ ሐሳብ አለኝ፡፡

 

936244_4165292428989_159364385_n
በቦታው ስደርስ፣የጴጥሮስ ሀውልት በጣውላ ተገንዞ ቆሟል፡፡ድብርት ተጫጫነኝ፡፡ምናልባት አያቶቼ አቡኑ ሲረሸኑ በተመለከቱበት ሰአት የተሰማቸው ስሜት እንዲህ ሳይሆን አይቀርም፡፡ የራስ ቁር የደፉ የቀን ሠራተኞች በአቡኑ ትክሻ ላይ እንደ ወፍ ሰፍረዋል፡፡ ወደ መርካቶ በሚሄዱ ተሳፋሪዎች የተሞሉ ሚኒባሶች አደባባዩን ታክከው ሽው ይላሉ፡፡ ተሳፋሪዎቹ፣ በመስታውት አሻ…ግረው የሚመለከቱት ትእይንት ብዙ የመሰጣቸው አይመሰልም፡፡በፋሲካ አስፈሪ የዶሮ ዋጋ ለተጠመደ አእምሮ ታሪክ ምኑ ነው??
ከተመልካቹ በላይ የፖሊሱ ቁጥር የሚበልጥ መሰለኝ፡፡አንድ ፒካፕ መኪና ስትበር መጣችና ቁና ሙሉ ፌደራል ፖሊስ አራገፈች፡፡ሰብሰብ ብለን በቆምንበት አንዱ ፖሊስ ጠጋ አለና‹‹ እናንተን አይመለከታችሁም ከዚህ ሂዱ›› አለ፡፡ካጠገቤ የቆመ ጎበዝ ‹‹ማየት መብታችን ነው›› ብሎ መልሶ ጮከበት፡፡አሀ! የጴጥሮስ መንፈስ አልከሰመም ማለት ነው፡፡ፖሊሱ ምንም ሳይመልስ ከሬድዮ መገናኛው ጋር እየተመካከረ ካካባቢው ራቀ፡፡
ከጥቂት ጊዜ በኋላ ጋዜጠኛ ጓደኞቼ ካሜራቸውን ታጥቀው ደረሱና ተቀላቀሉኝ፡፡ ሀውልቱን ማስቀረት ስላልቻሉ ምስሉን ቀርጸው ለማስቀረት ተሯሯጡ፡፡
ድንገት ቀና ብየ ሳይ ከሀውልቱ ፊትለፊት ጅማ በር የሚባል ፣ጣልያን የሠራው አሮጌ ሕንጻ ይታየኛል፡፡ባቡሩ የአቡነ ጴጥሮስን መታሰቢያ ደቅድቆ ሲያልፍ፣ጣልያን ሠራሹን ግንብ ንክች አያደርገውም፡፡ጉደኛ ባቡር!!!
በጣውላ የተገነዘውን የአቡኑን ሀውልት ለመሸከም አንድ አዳፋ ረጅም ተጎታች መኪና ብቅ አለ፡፡ዳይኖሰር የመሰለ ክሬን ሀውልቱን ነቅሎ ሲያንጠለጥለው፣ሀውልቱ የነበረበት ቦታ ጥርስ የወለቀበት አፍ መሠለ፡፡ቀሪውን የማየት ፍላጎት ስላልነበረኝ ከጓደኛየ ጋር ወደ ፒያሳ አቀናሁ፡፡ብዙ ነገር እዬተለወጠ መሆኑን አየሁ፡፡የጥንቱ መሀሙድ መዚቃ ቤት ወደ ቡቲክ መቀየሩን አስተዋልሁ፡፡የጥንቱ አያሌው ሙዚቃ ቤት ፍራፍሬ መሸጫ ሱቅ ሆኗል፡፡ከጥቂት ወራት በፊት ብርቱካኔ የሚለው ሙዚቃ ይንቆረቆርበት የነበረው ቦታ ፣አሁን ብርቱካን በኪሎ ይሸጥበታል፡፡
አዲስአበባ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ያለጥርጥር፣ባቡር ይኖራታል፡፡ቀለበት መንገዶች ይኖሯታል፡፡አሪፍ ህንጻዎች ይኖሯታል፡፡ነገር ግን፣ ትናንት የሚባለው ነገር አይኖራትም፡፡ A city without past ላዲስ አበባ የተገባ ቅጽል ነው፡፡
ወደ ሰፈሬ የሚሄድ ታክሲ ስፈናጠጥ፣ የሚከተሉት የጸጋየ ገብረመድህን ግጥሞች ሽው አሉብኝ፡፡
….መጭው ደመና ጥቁረቱ፣
ጮቁ ፣ማጡ፣የክረምቱ፣አቤት ዝቅጠቱ ማስፈራቱ
የኛስ ትውልድ አከተመ፣አገራችንን አምክነን
የነገስ ዘር ምን ይበለን፣ስንተወው ሲኦል አውርሰን

%d bloggers like this: