ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በገዛ ፍቃዳቸው ሥልጣናቸውን ሲለቁ፤ አቶ በላይ ፍቃዱ ቀጣዩ ፕሬዘዳንት በመሆን ተመርጠዋል
የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ብሔራዊ ምክር ቤት ዛሬ ጥቅምት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በነበረው ስብሰባ ፕሬዚዳንቱ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ሪፖርት ካቀረቡ በኋላ፤ ከውስጥና ከውጭ በተፈጠሩ አንዳንድ የማያሰሩ ችግሮች፣ ካለባቸው የሥራ ጫና እና ፓርቲው ወደፊት አንድነቱን ጠብቆ ለ2007 ምርጫ አሸናፊ ሆኖ እንዲወጣ በማሰብ ስልጣናቸውን በቃዳቸው መልቀቃቸውን ይፋ ማድረጋቸው ተጠቁሟል፡፡
ምክር ቤቱም በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የፕሬዘዳንቱን ጥያቄ በአድናቆት ተቀብሎ፤ ፓርቲውን በፕሬዘዳንትነት በመምራት መጪውን ምርጫ ውጤታማ ለማድረግ እንዲያስችል 1ኛ. አቶ በላይ ፈቃዱ፣2ኛ. አቶ ደረጀ ኃይሉ እና 3ኛ. አቶ ትዕግስቱ አወሉን በዕጩነት በማቅረብ፤አቶ በላይ ፈቃዱን በፕሬዘዳንት መርጧል፡፡ ምርጫውም በምስጢር ድምፅ አሰጣጥ እዛው በፓርቲው ምክር ቤት የተከናወነ ሲሆን፤በመጨረሻም አቶ በላይ ፈቃዱ በከፍተኛ ድምፅ ማሸነፋቸው መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ከምርጫው ውጤት በኋላ አቶ በላይ በቀጣይ የስልጣን ጊዜያቸው ፓርቲውን ለመምራት ቃለ መሐላ የፈፀሙ መሆናቸውን የፍኖተ ነፃነት ዘገባ ያስረዳል፡፡ አቶ በላይ ጠንካራ የፖለቲካ ልምድና ተሳትፎ ካላቸው የፓርቲው ወጣት አመራሮች መካከል በውጤታማነት ከሚጠቀሱት አንዱ እንደሆኑ የተጠቆመ ሲሆን፤የትምህርት ደረጃቸውም በስታስቲክስ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ድግሪ (BSc) እና በኢኮኖሚ ፖሊሲ አናሊስስ የማስተርስ ድግሪ (MSc) ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያላቸው ሲሆን፤ በስራ ልምዳቸውም በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አገልግለዋል፡፡ አቶ በላይ ወደ ፓርቲው ፕሬዘዳንትነት ከመምጣታቸው በፊት፤ በራሳቸው የጥናትና ምርምር ድርጅት በማኔጂንግ ዳይሬክተርነት ያገለግሉ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፓርቲው መጪውን 2007 ዓ.ም. ምርጫ እንዲያሸንፍ ትልቅ ሚና ይኖራቸዋል በሚል ከአባላትና ከደጋፊዎች ትልቅ ተስፋ እንደተጣለባቸውና ኃላፊነታቸውንም በስኬት ሊወጡ እንደሚችሉ ተገምቷል፡፡