የተራራቁት የለውጥ ዕይታዎች
ነአምን አሸናፊ
ሐሙስ ነሐሴ 16 እና ዓርብ ነሐሴ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የስብሰባ ማዕከል በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያላቸው የፖለቲካና የአካዳሚክ ልሂቃን በአገሪቱ ጅመር የለውጥ ሒደት፣ ዕድሎች፣ ፈተናዎችና ሥጋቶች ላይ የሁለት ቀናት ውይይት አድርገው ነበር፡፡ በዚህ ለሁለት ቀናት በቆየው ውይይት መድረክ ላይ በለውጡ ዙሪያ የተለያየ ሐሳቦች የተሰነዘሩ ሲሆን፣ በተለይ በሁለተኛ ቀን ውሎ ሦስት ፖለቲከኞችን በአንድ መድረክ ያገናኘው ውይይት የብዙዎችን ቀልብ የሳበ ነበር፡፡ በሁለተኛው ቀን ውይይት ሐሳባቸውን ያጋሩት ተወያዮች በለውጡ ላይ ያላቸውን አተያይ ያስረዱ ሲሆን፣ የግለሰቦቹ ምልከታ በራሱ በለውጡ ላይ አንድ ወጥና ተመሳሳይ አቋም፣ እንዲሁም አረዳድ ላይ አለመደረሱን አመላካች ነበሩ፡፡ በምሥሉ ላይ ከግራ ወደቀኝ አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ጌታቸው ረዳና አቶ ልደቱ አያሌው ከአወያያቸው ወ/ሮ ፀዳለ ለማ ጋር ይታያሉ፡፡
ለውጡን አስመልክቶ ያሉ አተያዮች
ሐሙስ ነሐሴ 16 እና ዓርብ ነሐሴ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. በአገሪቱ የፖለቲካ ምኅዳር ተሳታፊ የሆኑ ፖለቲከኞችና በፖለቲካ ሒደቱ ላይ የተለያዩ ምርምሮችን ያካሄዱና ጽሑፎችን ማቅረብ የቻሉ ምሁራን፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ቅጥር ግቢ ውስጥ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት የተከሰተውን ለውጥ አስመልክቶ ለመወያየትና አሁን ያለበትን ደረጃና ፈተናዎች ለመተንተን ለስብሰባ ተቀምጠዋል፡፡
ይህን የውይይት ኮንፈረንስ ያዘጋጁት ኢንተር አፍሪካ ግሩፕ፣ የምክክር የጥናትና ትብብር ማዕከል፣ አማኒ አፍሪካ፣ ቤርጎፍ ፋውንዴሸን፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ስትራቴጂክ ጥናት ማዕከል ሲሆኑ፣ የሁለት ቀናቱን የውይይት መድረክ በንግግር የከፈቱት ፕሬዚዳንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴ ነበሩ፡፡
ከ1960ዎቹ የፖለቲካ ተዋንያን አንስቶ እስከ ቅርብ ጊዜ እስከ ተመሠረቱት ፓርቲ አባላትና አመራሮች በውይይት መድረኩ ላይ የተገኙ ሲሆን፣ አንጋፋ ምሁራን እንዲሁ ‹‹የኢትዮጵያ የለውጥ ሒደት ወቅታዊ ቁመናው፣ መፃኢ ዕድሎቹ፣ ፈተናዎቹና ሥጋቶቹ›› በሚል ርዕስ ለተዘጋጀው መድረክ የልምዳቸውን ለማካፈል ተሰይመዋል፡፡
ከእነዚህ የአገር ውስጥ ምሁራንና ፖለቲከኞች በተጨማሪም፣ የዓለም አቀፍ የለውጥ ተሞክሮዎችን ለማውሳትና ልምዳቸውን ለማካፈል የውይይቱ አካል ነበሩ፡፡ በዚህም መሠረት በቱኒዚያ ሕዝባዊ አመፅ ማግሥት በተቋቋመው ሕዝባዊ የውይይት ምክር ቤት አባል የነበሩ፣ የየመን ሕዝባዊ የውይይት ምክር ቤት አባል የነበሩ ሁለት ተወካዮች በለውጥ ሒደት ውስጥ የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን እንዴት መፍታት እንደሚቻልና እንደሚገባ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከሽግግር አስተዳደር ጋር በተያያዘ በርካታ ምርምሮችን ያደረጉት ማይክል ሉንድ ገለጻ አድርገዋል፡፡
ምንም እንኳን በመጀመርያው ቀን የውይይቱ ውሎ ለውይይቱ ከተሰጠው ርዕስ አንፃር የለውጡን ፈተናዎች፣ ተግዳሮቶችና መልካም ዕድሎችን አስመልክቶ በዝርዝር የቀረበ የውይይት ሐሳብ ባይኖርም፣ በታዋቂው የታሪክ ምሁር ገብሩ ታረቀ (ፕሮፌሰር) አወያይነት፣ እንዲሁም በሌላው ታዋቂው የታሪክ ምሁር ባህሩ ዘውዴ (ፕሮፌሰር) እና የቀድሞው የመኢሶን መሥራችና መሪ በነበሩት በአቶ አንዳርጋቸው አሰግድ መነሻ ሐሳብ አቅራቢነት ኢትዮጵያ ያመከነቻቸውን የለውጥ ዕድሎች አስመልክቶ ገለጻና ውይይት ተደርጓል፡፡
የመጀመርያ ዕለት ውሎ በእነዚህ አጠቃላይ ሐሳቦችና ጉዳዮች ሲወያዩና ውይይቱን ሲያዳምጡ የነበሩ ተሳታፊዎች፣ በሁለተኛው ቀን ግን አሁን አገሪቱ ካለችበት የፖለቲካ ሁኔታ አንፃር አንገብጋቢ የሆኑ ጉዳዮች የተዳሰሱበት የሦስት ፖለቲከኞችን ውይይት በተመስጦ አዳምጠዋል፡፡ ከማዳመጥ ባለፈም የምሣ ሰዓትን እስከ መግፋት የደረሰ ጥያቄና መልስ፣ ውይይትና ሙግት አካሂደዋል፡፡
በሁለተኛው ቀን የከፍተኛ ፖለቲከኞችና ምሁራን ውይይት በለውጡ ወቅታዊ ቁመና፣ ፈተናዎቹና ዕድሎቹ ዙሪያ ያላቸውን አተያይ እንዲያቀርቡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) እና የዝሕባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ሥራ አስፈጻሚ አባል አቶ ጌታቸው ረዳ፣ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ታዋቂውን ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌውን በመድረኩ ሰይሟል፡፡
እነዚህ ሦስት ፖለቲከኞች ከሚወክሉት የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም አንፃር፣ ለውጡን አስመልክቶ ሊለዋወጡ የሚችሉት ሐሳብ ከመጀመርያው ቀልብን የሳበ ነበር፡፡
ባለፈው አንድ ዓመት ተኩል በአገሪቱ እየተካሄደ ባለው ለውጥ ምንነት ዙሪያ ሦስቱም ሐሳብ ሰንዛሪዎች የተለያየ አረዳድ እንዳላቸው የገለጹ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ግን ሒደቱ በጀመረበት ፍጥነት ካለመጓዙም በላይ ሊቀለበስ እንደሚችል ሥጋታቸውን አጋርተዋል፡፡ ሆኖም ሦስቱም ተናጋሪዎች አሠራሮችን ዳግም ለማየት ከተሞከረ ሒደቱን ከመቀልበስ አደጋ መታደግም እንደሚቻል አውስተዋል፡፡
ለውጡን ለመተርጎም በመሞከር ንግግራቸውን የጀመሩት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ለውጥ የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ላይ በሒደቱ ተዋናይ የሆኑት ቡድኖች ወጥ ትርጓሜ እንደሌላቸው አውስተዋል፡፡ ለዚህም በምዕራባውያን ስለለውጡ የሚሰጠው ትርጓሜና በኢትዮጵያውያን ፖለቲከኞች ዘንድ የሚሰጠው ትርጓሜ ለየቅል መሆኑን በማውሳት ነው፡፡
‹‹የፖለቲካ ምኅዳሩን ማስፋት በሚሉ በጣም አጓጊ ቃላት የሚታጀብ ቢሆንም፣ በዋነኛነት የምዕራባውያን የለውጥ ጽንሰ ሐሳብ ተቋማትን ወደ ግል ይዞታ ብቻ ሳይሆን ወደ ምዕራባውያን የግል ይዞታ ከማዞር አንፃር ብቻ ነው የሚያዩት፤›› በማለት፣ የምዕራባውያንን አረዳድ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ ደግሞ፣ ‹‹በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ኃይሎች የራሳቸው ውስንነት ቢኖራቸውም ለውጥ ሲሉ የፖለቲካ ምኅዳር መስፋትን፣ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት መጠናከርን፣ በግለሰብና በቡድን ነፃነትና መብቶች መካከል ያለውን ሚዛን መጠበቅ፣ አገራዊ ማንነትና ብሔራዊ ማንነትን ማመጣጠን የሚሉ በርካታ ነገሮችን ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፤›› በማለት፣ በአገራዊውና በውጭው ኃይሎች መካከል ያለውን የጉዳዩን አረዳድ አስረድተዋል፡፡
ከዚህ አንፃር እነዚህ ውስንነት ያሉበትን ጽንሰ ሐሳብ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደተፈታና ስምምነት እንደተደረሰበት አድርጎ ማቅረቡ በራሱ ችግር አለበት በማለት፣ በጉዳዩ ላይ የጠራ አቋም መያዝ አስፈላጊነት ላይ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ አቶ ጌታቸው የለውጡ ባለቤትነት ጥያቄ ያስከተላቸው ውዥንብሮች በራሱ የለውጡ ተግዳሮት እንደሆነ በመግለጽ፣ በዋነኛነት ግን ለውጡ የኢሕአዴግ ነው በማለት በተለያዩ መድረኮች በተደጋጋሚ የሚገልጹትን አቋማቸውን በዚህ መድረክም አራምደውታል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘም፣ ‹‹አመራሩ በጋራ አንድ ላይ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ ሲያበቃ በተወሰኑ የአመራር አካላት ግን ለውጡ የእኔ ነው ወደሚል ሁኔታ ተሂዷል፡፡ ስለዚህ ለውጡ የማን ነው የሚለው ጥያቄ ችግር ያለበት ነው፡፡ እዚህ መግለጽ ካለብን ለውጡ የሕዝብ ጥያቄ ያመጣው፣ ግን ደግሞ ኢሕአዴግ በሕዝብ ግፊትም ቢሆን ተገዶ ይህን ካላደረግኩ በስተቀር አገር ይፈርሳል ብሎ አምኖ የተቀበለው ነው፤›› ተብሎ መወሰድ እንዳለበት ሞግተዋል፡፡
ለውጡ የሕዝቡ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጌታቸው የለውጡ ችግሮች ያሏቸውን ሐሳቦችም አያይዘው አቅርበዋል፡፡ ከነዚህ ችግሮች መካከል ለውጡ ኢሕአዴግን እንደ ፓርቲ ማግለሉ፣ የአመራሩ እውነታን መሸሽ፣ በየሥፍራው የታጠቁ ኃይሎች መበራከት፣ እንዲሁም ድሮም ጠንካራ ያልነበሩት ተቋማት ከለውጡ ወዲህ ይበልጥ መልፈስፈሳቸውን እንደ ችግር በመጥቀስ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሳም፣ ‹‹አሁን ባለንበት ሁኔታ ለውጡ ፈተና ውስጥ የገባ ነው የሚል እምነት አለኝ፤›› ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
‹‹ኢሕአዴግ ለውጥ መደረግ አለበት ብሎ ያምናል፡፡ ከአሁን በፊት የሠራቸው ጥፋቶች መቀጠል አለባቸው የሚል ጤነኛ አዕምሮ ያለው ሰው የለም፡፡ ነገር ግን መልካም ነገሮችን አስቀጥሎ ለአገር ህልውና ቀጣይነት በሚያግዝ መንገድ ለውጥ መደረግ አለበት ብሎ መሥራት አንድ ነገር ነው፡፡ ኢሕአዴግን ወደ ጎን አድርገህ በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ስምና ዝና ላይ የተመሠረተ ለውጥ ለማድረግ መንቀሳቀስ፣ አማራጭ የፖለቲካ አስተሳሰብ ባስቀመጥክበትና በቅጡ የተተረጎመ ጽንሰ ሐሳብ እየመራህ ባለህበት ሁኔታ አሁን በምናየው ደረጃ ለውጡን ማስቀጠል ሳይሆን፣ አገር ትርምስ ውስጥ የሚከት ነገር ውስጥ ነው የሚከተን፤›› ብለዋል፡፡
እነዚህን ሥጋቶች ለማስወገድና ቅቡልነት ያለው መንግሥት እንዲመሠረት ደግሞ የመጪው ዓመት ምርጫ መካሄድ አለበት በማለት አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይ የአገሪቱ ዕጣ ፈንታ ላይ ለመወሰን፣ ‹‹የኢትዮጵያን ሕዝብ አምነን ቢቻል በወቅቱ ካልሆነ እንዲያውም አስቸኳይ (Snap) ምርጫ ማድረግ አለብን፤›› ሲሉ ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡
ብዙ የማያግባቡ የታሪክ ሰበዞች እንዳሉ በመጥቀስ ንግግራቸውን የጀመሩት አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው ደግሞ፣ ‹‹ምንም እንኳን የማያግባቡን በርካታ የታሪክ ክስተቶች ቢኖሩም ቢያንስ ግን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ያለማወቃችን፣ ራሳችን በመረጥነው መንግሥት ተዳድረን አለማወቃችንና የመሳሰሉት ነገሮች የሚያግባቡን የታሪክ ሰበዞቻችን ይመስሉኛል፤›› በማለት፣ አሁንም አገሪቱ ውስጥ የተፈጠረውን ሁኔታ ከታሪካዊ ዳራው ጋር እያያያዙ አብራርተዋል፡፡
ባለፉት 27 ዓመታት ግፍ ያልተፈጸመበት የአገሪቱ ክልል የለም ያሉት አቶ በቀለ፣ የግፉ ደረጃ ግን ከሥፍራ ሥፍራ እንደሚለያይ በመጥቀስ በተለይ ባለፉት ሦስትና አራት ዓመታት ከመሬት ጋር በተያያዘ ጥያቄና አመፅ በመላው ኦሮሚያ በመቀስቀሱ፣ እንዲሁም ይህንና መሰል ጥያቄዎች በአማራ ወጣቶች ዘንድ መፈጠራቸውና በገዥው ፓርቲ ውስጥም ለውጥ ያስፈልጋል የሚሉ አመራሮች መፈጠራቸው፣ አሁን ላለው አጠቃላይ አገራዊ ለውጥ አስተዋጽኦ ማድረጉን አትተዋል፡፡
በገዥው ፓርቲ ውስጥ የተፈጠረው የአሠላለፍ ለውጥ በርካታ ትሩፋቶች ማስከተሉን በዝርዝር ገልጸው፣ የእስረኞች መፈታትን፣ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት ቃል መገባቱን፣ የሰብዓዊ መብት ረገጣ መቆሙን ማወጅ፣ የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች ወደ አገር ቤት እንዲገቡ መደረጉን እንደ ምሳሌ ጠቃቅሰዋል፡፡
ይህን ጊዜ የጫጉላ ሽርሽር ጊዜ በማለት በመጥቀስ በተለይ ከውጭ አገር የገቡ ፓርቲዎች ያራመዷቸው አንዳንድ አቋሞች መፈጠር ሲጀምሩ፣ የለውጥ እንቅስቃሴው እየተቀዛቀዘ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት አገሪቱ አሁን ቅርቃር ውስጥ መግባቷን እንደሚያሳይ ገልጸዋል፡፡
‹‹አገሪቱ አሁን በሁለት ጽንፎች መካከል ተወጥራ የምትገኝ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በፊት ያልተሞከረውን ሁሉን ነገር አጥፍተንና አውድመን እንደ አዲስ ከመጀመር አባዜ ወጥተናል ብለን ተስፋ ባደረግንበት ወቅት፣ አሁን ደግሞ ወደዚያ ሊመልሱን የሚችሉ አዝማሚያዎች እየታዩ ነው፡፡ አንደኛው የሌላውን ሐሳብ ለመቀበል ፈጽሞ ያለ መፈለግና የእኔ ብቻ ነው ትክክል የማለት፣ ቁጭ ብሎ ለመደራደርና ለመነጋገር ያለ መፈለግ አዝማሚያዎች እጅግ በጣም እየገነገኑ መጥተዋል፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
እነዚህ ሁኔታዎችም ለውጡን እየመሩ ላሉ ኃይሎች ከባድ ችግር መፍጠራቸውን በመጥቀስ፣ ‹‹ለውጡ ማዝገም ብቻ ሳይሆን ወደ ኋላ እየተንሸራተተ ያለበት ሁኔታ ነው የሚታየኝ፤›› ብለዋል፡፡
ለውጡ ወደ ኋላ ስለመጓዙ ያቀረቡት መከራከሪያና ምክንያት ደግሞ ከዚህ ቀደም የተቃውሞ ምንጭ የነበረው የመሬት ዘረፋ ተስፋፍቶ እየተከናወነ መሆኑ፣ የሕዝብ መፈናቀል፣ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰዎችን ማሰር መቀጠሉን፣ ዴሞክራሲያዊ መብቶች መታፈን መጀመራቸው፣ የመሰብሰብና የመደራጀት መብቶች መገደብ የሚሉትን ነው፡፡ ‹‹ስለዚህ ወደ ቀደመው ሥርዓት እየተመለስን መሆናችን በግልጽ እየታየ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
‹‹ስለሆነም ያሉንን ተቋማት ወደ ማደራጀት እንጂ አዲስ ተቋም ለመገንባት መሯሯጥ የለብንም፤›› ብለው፣ እነዚህን የመሳሰሉ ሥራዎች ምርጫውን በጊዜው በማካሄድ የሚመረጠው መንግሥት በሒደት ሊሠራው ይችላል የሚል እምነት እንዳላቸው አብራርተዋል፡፡
በአገሪቱ ባለፈው አንድ ዓመት ተኩል የተከሰተውን ለውጥ በተመለከተ ያለፉት 27 ዓመታት የአገሪቱ የፖለቲካ ትግል መዘንጋት እንደሌለበት በመግለጽ ሐሳባቸውን መስጠት የጀመሩ አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፣ ‹‹የማስታወስ ችግር ስላለብን ነው እንጂ ለውጡ ላለፉት ሰባት ዓመታት የተደረገ ትግል ውጤት ነው፤›› ካሉ በኋላ፣ ‹‹አንዱና ትልቁ የለውጡ ጉድለት ውለታ ቢስ መሆኑ ነው፤›› በማለት ገልጸውታል፡፡
ከዚህ ባለፈ ግን በዋነኛነት በአገሪቱ የተከሰተው ለውጥ የአገሪቱን መሠረታዊ የፖለቲካ ቅራኔ መፍታት አለበት የሚል አቋም እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ የአገሪቱ መሠረታዊ የፖለቲካ ቅራኔ የሚመነጨው ከሕገ መንግሥቱ እንደሆነ ገልጸው፣ ሕገ መንግሥቱ አገሪቱን ያፈራርሳታል በሚል፣ የለም ሕገ መንግሥቱ በፓርቲ ማዕከላዊነት ተጠለፈ እንጂ የብሔር ብሔረሰቦችን ጥያቄ የሚመልስ ነው በሚል እንደሆነም አስረድተዋል፡፡
‹‹እነዚህ ጥያቄዎች እስካለፈው አንድ ዓመት ተኩል ድረስ መሠረታዊ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ስለዚህ አንድ ለውጥ መመዘን ያለበት እነዚህን መሠረታዊ ቅራኔዎች ለማስታረቅ በሚሄደው ርቀት ነው፤›› በማለት፣ ለውጡን በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ መመልከት ተገቢ መሆኑንና መመዘን ያለበትም በዚህ መሥፈርት እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ከዚህ ባለፈ ግን በአገሪቱ ካለፉት አንድ ዓመት ተኩል ጀምሮ እየተተገበረ ያለውን ለውጥ ጠንካራ ጎኖች አውስተዋል፡፡ ከነዚህም መካከል በአንፃራዊነትም ቢሆን ትግሉ የሰላማዊ ትግል ውጤት መሆኑ፣ በመጣበት ወቅት ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኝቱ፣ ገዥው ፓርቲ እስከ መጨረሻው ድረስ ከመጋፈጥ ይልቅ ሽንፈቱን መቀበሉና ይቅርታ መጠየቁ፣ እንዲሁም የለውጡ መሪዎች ሆነው ብቅ ያሉት ወጣቶች መሆናቸው የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል፡፡
ነገር ግን እነዚህን ጠንካራ ጎኖች ወይም ትሩፋቶች የያዘው ይህ ለውጥ፣ አሁን ግን የመቀልበስ አደጋ ተጋርጦበታል በማለት እሳቸውም እንደ ቀዳሚ ተናጋሪዎች ሥጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
‹‹ምንም እንኳን ይህ ለውጥ የረፈደበት ቢሆንም የመሸበት አይመስለኝም፡፡ ስለሆነም አዲስ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ መግባት አለብን፤›› ሲሉ፣ አዲሱ የለውጥ እንቅስቃሴ ደግሞ ሁሉንም አሳታፊ ያደረገ ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀት ሊጀመር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡
የለውጥ ሒደቱን የሚመራ ፍኖተ ካርታ ማዘጋጀት ድርሻ ደግሞ የሁሉም የኢትዮጵያ ኃይሎች እንደሆነ በመጥቀስ፣ ‹‹ይህን ለማድረግ ግን ቀጣዩ ምርጫ መራዘም አለበት፤›› በማለት ሞግተዋል፡፡
‹‹ይህን ሳናደርግ ወደ ምርጫ ብንገባ ምናልባት በኢትዮጵያ ታሪክ ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ ያደረገችው ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ ያደረገችው ምርጫ እንዳይሆን እሠጋለሁ፤›› በማለት ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡
ባለፉት አንድ ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ የተካሄደውን ለውጥ አስመልክቶ በአገሪቱ የፖለቲካ ልሂቃን ዘንድ ጽንሰ ሐሳቡን ከመረዳት ጀምሮ እስከ ውጤቱ ድረስ፣ የተለያዩና ጽንፍ የያዙ አተያዮች የተስተናገዱበት ይህ መድረክ የተለያዩ ጥያቄዎችን በማስተናገድ ተጠናቋል::
Ethiopian Reporter
በከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ላይ ሰኔ 15 የተፈጸመው ግድያ ዓቃቤ ሕግንና ተጠርጣሪዎችን እያወዛገበ ነው
ታምሩ ጽጌ
‹‹ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተቋሙን የማይመጥን ውሳኔ ሰጥቷል››
ተጠርጣሪዎች
‹‹የተወሰኑ ተጠርጣሪዎች በህቡዕ ተደራጅተው ጦርነት ይመሩ ነበር››
ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ
በአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ በመከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹምና በጓደኛቸው ላይ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በተቀራራቢ ሰዓታት ውስጥ የተፈጸመው ግድያ፣ ዓቃቤ ሕግንና ከግድያው ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው የታሰሩ ተጠርጣሪዎችን ማወዛገቡ ቀጥሏል፡፡
ግድያው በተፈጸመ ማግሥት ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በቁጥጥር ሥር ውለው በተለያዩ ጊዜያት ፍርድ ቤት ሲቀርቡ፣ የተጠረጠሩት ከግድያው ጋር በተያያዘና የሽብርተኝነት ሕግን አዋጅ ቁጥር 652/2001 በመተላለፍ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው መሆኑን የሚናገሩት ቁጥራቸው ከ30 በላይ የሚሆኑት ተጠርጣሪዎች፣ ግድያውን በሚመለከት የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግሥት አመራሮች የተናገሩትና ያሰራቸው የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ የሚናገረው የተለያየ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ የሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ከፍተኛ አመራሮች ግድያን በማቀነባበርና በመሳተፍ ተጠርጥረው፣ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው በፀረ ሽብርተኝነት ሕጉ 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ተጠይቆባቸው ቢፈቀድም፣ ፖሊስ በተሰጠው ጊዜ ምንም ዓይነት ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ባለመቻሉ፣ ፍርድ ቤቱ ሰፊ ትንታኔ በመስጠት በዋስ እንዲለቀቁ ውሳኔ ሰጥቶ እንደነበር ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት አስረድተዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በጠበቆቻቸው አማካይነት ነሐሴ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ባቀረቡት ክርክር እንዳስረዱት፣ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ያቀረቡት የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዝርዝር ትንታኔ በመስጠት ለደንበኞቻቸው የጠበቀላቸውን ሕገ መንግሥታዊ የዋስትና መብት፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ያላግባብ ስለነፈጋቸው ነው፡፡ የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ሕገ መንግሥታዊ የሆነውን የዋስትና መብት የነፈጋቸው፣ ተቋሙን በማይመጥንና የዳኝነትን ብቃት ግምት ውስጥ ሊያስገባ በሚችል ሁኔታ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼውም አንድ የፀረ ሽብር ተግባር ወንጀል ፈጽሟል ተብሎ የተጠረጠረ ዜጋ በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 20 (3) ድንጋጌ መሠረት ምርመራ ሊፈቀድበት የሚችለው 28 ቀናት ሆኖ ተደንግጎ እያለ፣ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በደንበኞቻቸው ላይ የተሰጠው የምርመራ ጊዜ 42 ቀናት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ይኼ ደግሞ የሕጉን ድንጋጌ ከመጣሱም በላይ፣ ምንም ዓይነት ማስረጃ ያልቀረበባቸው ተጠርጣሪዎችን ከሕግ አግባብ ውጪ እንዲታሰሩ ማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ዓቃቤ ሕግ፣ የፖሊስ አባል፣ የአብን አመራሮችና አባላት፣ የተቋማት ሠራተኞችና ሌሎችም ሲሆኑ፣ በመዝገብ ቁጥሮች 181966፣ 181965፣ 182124፣ 182129 እና በመዝገብ ቁጥር 182150 ተካተው በአምስት መዝገቦች ከ30 በላይ ተጠርጣሪዎች የከፍተኛው ፍርድ ቤት ውሳኔን በመቃወም በሰባት ጠበቆች ተወክለው ሰፊ ክርክር አድርገዋል፡፡
የፌዴራል መንግሥትና የአማራ ክልል የመንግሥት አመራሮች በአማራ ክልል አመራሮች ላይ የተፈጸመው ግድያ ‹‹የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ነው›› እያሉ በይፋ ከዕለቱ ጀምሮ በመገናኛ ብዙኃን ጭምር ገልጸው እያለ፣ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል መጠርጠር እርስ በርሱ የሚጣረስና ሕዝብንም እምነት የሚያሳጣ መሆኑን ጠበቆቹ ገልጸዋል፡፡
ፖሊስ ደንበኞቻቸውን በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሯቸዋል ቢባል እንኳን፣ በተፈቀደለት የ28 ቀናት ጊዜ ውስጥ ማን በማን ላይና ምን ዓይነት ወንጀል እንደፈጸመ በመለየት በዝርዝርና በተናጠል ለፍርድ ቤት ማቅረብ እንዳለበት በሕጉ ተደንግጎ ቢገኝም፣ 28 ቀናት ቆይቶ ፍርድ ቤት ሲቀርብ ምንም ዓይነት የምርመራ ውጤት አለማቅረቡን አስረድተዋል፡፡
የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤትም የፖሊስ ምርመራ መዝገቦችን አስቀርቦ ከመረመረ በኋላ፣ ምንም ዓይነት ለሽብር ተግባር ወንጀል የጥርጣሬ መነሻ ነገር ባለማግኘቱ፣ ተጠርጣሪዎቹ ከ2,000 ብር እስከ 5,000 ብር በሚደርስ ዋስትና ከእስር እንዲፈቱ ውሳኔ መስጠቱንም ገልጸዋል፡፡ ፖሊስ ‹‹በሽብር ተግባር ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ›› በማለት ላሰራቸው የአብን አባላት ያቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹ማንን ነው የምትረዱት? ማነው ያሰማራችሁ?›› የሚሉና ‹‹ጠርጥሬያችኋለሁ›› ካለበት መነሻ ሐሳብ ጋር የማይገናኝ መሆኑንም ጠበቆቹ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የአዲኃን ሥልጠና ወስዳችኋል፣ ከእነ ዘመነ ካሴ ጋር ግንኙነት አላችሁ›› የሚሉ የግለሰቦች ወይም የተወሰነ ቡድን ፍላጎትን የሚያንፀባርቁ ጥያቄዎች እንጂ፣ ከሰኔ 15 ቀን የከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር የሚያያዝ ምንም ዓይነት ምርመራ እንዳልተካሄደባቸውም አስረድተዋል፡፡
አንዳንዶቹ በተለይ ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለና የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ባልደረባና የልደታ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያ መርማሪ ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆናቸውን ደርሰንበታልና መረጃ ያቀብላሉ›› ከሚል ምርመራ በስተቀር፣ የሽብር ወንጀል ተሳትፏቸው ምን እንደሆነ ያቀረበው የጥርጣሬ መነሻ ማስረጃ እንደሌለም ገልጸዋል፡፡
‹‹የከፍተኛው ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዋስትና የከለከላቸው አቋም ይዞ ነው፤›› የሚሉት የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች፣ ይኼንንም ሊያስብላቸው የቻለው በዋስ እንዲወጡ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት እያንዳንዳቸው የ5,000 ብር ዋስትና ማቅረብ እንዳለባቸው ውሳኔ የተሰጠላቸው፣ አቶ የወግሰው በቀለና ዋና ሳጅን ሞገስ በቀለ፣ ዋስትናቸው ወደ 200,000 ብር ማሳደጉ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ዋስትና ከተፈቀደላቸው ሳምንት ቢሞላቸውም፣ አቅማቸውን ያላገናዘበ ዋስትና በመሆኑ ከእስር ሊለቀቁ እንዳልቻሉም አክለዋል፡፡ ሌላው ጠበቆቹ ያቀረቡት ክርክር ሕጉ ግልጽ ሆኖ ሳለ፣ ለምን ተለጥጦና ለተጠርጣሪ በማይጠቅም ሁኔታ እንደሚተረጎም እንዳልገባቸው ጠቁመው፣ ከሰኔ 15 ቀን የእነ ጄኔራል ሰዓረ መኮንን ግድያ ጋር በተያያዘ፣ ‹‹የገዳዩ ሚስት ናት›› የተባለችና ከግድው ጋር ምንም ግንኙነት የሌላት ሴትም ታስራ እንደምትገኝ ገልጸዋል፡፡ ዳኞቹ የሚሠሩት ለህሊናቸውና ለሕግ ተገዥ ሆነው ቢሆንም፣ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአግባቡ የሰጠውን ውሳኔ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ያገደበትና ከሕጉ ውጪ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር በአጠቃላይ 42 ቀናት የፈቀደበት ሒደት፣ ከሕግ አግባብ ውጪ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ ራሱ ጠይቆ የነበረው 28 ቀናት እንደሚበቃው ገልጾ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ 42 ቀናት መፍቀዱ ለምንና በየትኛው የሕግ አግባብ እንደሆነ ግልጽ አለመሆኑንም አክለዋል፡፡ አዴፓ ‹‹እርስ በርሳችን ተጠፋፋን›› እያለ ከ30 በላይ ንፁኃን ዜጎችን ማሰር፣ ተገቢ አለመሆኑንም ገልጸዋል፡፡ መፈንቅለ መንግሥት መሆኑ የተገለጸበትን ድርጊት የሽብር ተግባር ወንጀል በማለት ዜጎችን ያላግባብ ማሰር ሆን ተብሎ ሰብዓዊ መብታቸውን ላለማክበር የተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ጠበቆችን ጭምር በነፃነት እንዳይከራከሩና እንዳይናገሩ ጫና በማድረግ፣ በክርክሩ ወቅት ያነሷቸውን መከራከሪያ ሐሳቦች እንኳን እንዳልመዘገበላቸውም አስረድተዋል፡፡ በአጠቃላይ ደንበኞቻቸው ታስረው የሚገኙበት ጉዳይ እንኳን በሽብር ተግባር ወንጀል፣ በተራ ወንጀል እንኳን ሊያስጠረጥር እንደማይችል የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በክርክራቸው አስረድተዋል፡፡
ከሰኔ 15 ቀን ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረዋል ስለተባሉትና ይግባኝ ስለጠየቁት ተጠርጣሪዎች፣ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ቀርቦ ምላሽ የሰጠው (የተከራከረው) የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል መርማሪ ሳይሆን ዓቃቤ ሕግ ነው፡፡ በዕለቱ የቀረቡት ሁለት ዓቃቢያነ ሕግ እንዳስረዱት፣ እያንዳንዳቸው ተጠርጣሪዎች ከሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በፊት ሲደራጁ ቆይተው፣ በተለያዩ አቅጣጫዎች በመንቀሳቀስ ግድያው እንዲፈጸም አድርገዋል፡፡ ይኼ ሁኔታ በተፈጸመበትና ፖሊስ ስለሁኔታው በማጣራት ላይ እያለ፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተጠርጣሪዎቹ በዋስ እንዲወጡ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ድርጊቱን ‹‹ተራ የፖለቲካ ሽኩቻ ነው›› በማለት የዳኛውን ገለልተኛነት የሚያጠራጥር መሆኑንም አክለዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ እንዳብራሩት የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የምርመራ መዝገቡን ወስዶ ለሳምንት ማቆየቱና አልመልስም በማለቱ፣ እጃቸው ላይ በነበረ ሰነድ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብለው፣ የተጠርጣሪዎቹ የዋስትና መብት እንዲታገድ ማድረጋቸውን አስረድተዋል፡፡ በተለይ አራት ተጠርጣሪዎች በኅቡዕ ጦር እየመሩ እንደነበርና መረጃ ሲለዋወጡበት የነበረን ማስረጃ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጠይቀው በመጠባበቅ ላይ እያሉ፣ ዋስትና መፍቀድ ተገቢ አለመሆኑንም ዓቃቢያነ ሕጉ ተናግረዋል፡፡
በግለሰብ እጅ ሊገባ የማይችል የጦር ሜዳ መነጽር መገኘቱንም ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ በወታደራዊ አመራሮች ላይ ግድያ ሲፈጸም የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲቋረጥ ግዳጅ የተሰጣቸው፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሠራተኞች መያዛቸውንም ገልጸዋል፡፡ የጦር መሣሪያ መግዛቱንና 6,000 ጥይቶች ቢኖሩትም ከጎንደር እንዴት እንደሚያሳልፈው ምክክር ሲያደረግ የነበረ ተጠርጣሪና ሌሎችም፣ በኅቡዕ ተደራጅተው በእነማን ላይ ዕርምጃ እንደሚወስዱ ሥልጠና ጭምር የወሰዱ ተጠርጣሪዎች መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ ይኼ ሁሉ ባለበት ገና በምርመራ ላይ እንደሆኑ እየገለጹ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዋስትና መፍቀዱ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰኔ 15 ከፍተኛ አመራሮች ግድያ ጋር በተያያዘ የሽብር ተግባር ስለመፈጸሙ ከተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ጋር እየሠሩ እያለ፣ የወንጀል ተግባሩን በመቀየር ዋስትና መስጠቱም ተገቢ አለመሆኑን ዓቃቢያነ ሕጉ ደጋግመው አስረድተዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በመሀል፣ ‹‹በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት በእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ላይ ለወንጀል ጥርጣሬ መነሻ የሚሆን የምርመራ ውጤት አቅርባችሁ ነበር?›› የሚል ጥያቄ ለዓቃቢያነ ሕጉ አቅርቦላቸው፣ ማን ከማን ጋር ግንኙነት እንደነበረው በቂ መጠርጠሪያ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ቀሪ መረጃና ማስረጃ በመሰብሰብ ላይ እንደሆኑም ማስረዳታቸውን ከኢትዮ ቴሌኮም፣ ከባንክ፣ የባልደራስ ምክር ቤትን እንደ ሽፋን በመጠቀም ወንጀል መፈጸማቸውን ለማሳየት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት መረጃ መጠየቃቸውን ቢገልጹም፣ ፍርድ ቤቱ እንዳልተቀበላቸው አስረድተዋል፡፡
ከፍተኛው ፍርድ ቤት ግን ያቀረቡትን የይግባኝ አቤቱታ በሚገባ ከተመለከተ በኋላ፣ ዋስትናውን እንደሻረውም አክለዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹እናንተ (ዓቃቢያነ ሕጉ ወይም ፖሊስ) 28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ጠይቃችሁ ከፍተኛው ፍርድ ቤት እንዴት ከዚያ በላይ ሊፈቅድ ቻለ?›› በማለት ሲጠይቃቸው፣ ችሎቱ የበዓል ቀናትን ትቶ የሥራ ቀናትን ብቻ በመቁጠር መስጠቱን ጠቁመው ስህተት ከሆነ ሊታረም እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በመቀጠል፣ ‹‹ከሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በምርመራ ላይ ከሆናችሁ እንዴት እስካሁን አልጨረሳችሁም? አሁንስ በምን ላይ ናችሁ?›› የሚል ጥያቄ አቅርቦላቸው፣ ተጠርጣሪዎቹ ሲዘጋጁ የከረሙት ከጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም. ጀምሮ መሆኑን፣ በቤንሻንጉል ጉምዝ ዋና ከተማ በአሶሳና በአዲስ አበባ የተፈጸመውን ሁሉ ማጣራት ስላለባቸው፣ እየሠሩና የጠየቁት ለመረጃ እስከሚመጣላቸው እየጠበቁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች በተሰጣቸው ድጋሚ የመከራከሪያ ዕድል እንዳስረዱት፣ ዓቃቤያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ በመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንት ቀናት በዳኛ ዕግድ መቆየቱን ለችሎቱ መግለጻቸው፣ ከአንድ ከፍተኛ የሕግ ተቋም የማይጠበቅ ምላሽ ከመሆኑም ባለፈ ግምት ውስጥ የሚከት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ፖሊስ የራሱን ዋና የምርመራ መዝገብ ይዞ ለፍርድ ቤት የሚያቀርበው ደግሞ ግልባጩን (ኮፒ) መሆኑን ጠቁመው፣ መዝገቡ ዳኛው ዘንድ ስምንት ቀናት መቆየቱንና ‹‹አልሰጥም አሉኝ›› የሚል ሰበብ ማቅረብ ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሌላው ዓቃቢያነ ሕጉ የምርመራ መዝገቡ አካል ያልሆነን ጉዳይ ‹‹አሶሳ ከተማ የተፈጸመን ድርጊትም እየመረመርኩ ነው›› ማለቱ የማይገናኝ ነገር ለማገናኝት መሞከር መሆኑንም አክለዋል፡፡ የጦር ሜዳ መነጽር ይዘው ተገኝተዋል በማለት ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹን ለመወንጀል ያደረገው ጥረት፣ ‹‹መነጽር አይደለም ታንክ ይዘው ቢገኙ ሽብር ነው ማለት ነው?›› በማለት ጠይቀው፣ ፍርድ ቤቱ መዝገቡን አስቀርቦ እንዲያይላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተገኘ የተባለው የጦር ሜዳ መነጽር የዩኒቨርሲቲ ማስተማሪያና ከመምህር ቤት የተገኘ መሆኑንም አክለዋል፡፡ በኅቡዕ ተደራጅተው ጦር ሲመሩ ነበር የተባሉት ደንበኞቻቸው ጫማ የሚጠርጉ ሊስትሮዎች፣ የቤት ሠራተኞችና የፖለቲካ ድርጅት አባላት መሆናቸውንም አክለዋል፡፡
ግድያው ሰኔ 15 ቀን ተፈጽሞ ደንበኞቻቸው ሰኔ 16 ቀን መያዛቸው የሚገርም እንደሆነ የገለጹት ጠበቆቹ፣ ይኼ የሚያሳየው እነሱን ለመያዝ ዝርዝር ተይዞና ቀደም ብሎ ዝግጅት መኖሩ የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሽብር ተግባር ወንጀል አያስቀጣም ሳይሆን፣ በአዋጅ ቁጥር 652/2011 አንቀጽ (19) መሠረት ሊያስጠረጥራቸው የሚችል ማስረጃ እንዳልተገኘባቸው ወይም ፖሊስ በተሰጠው የ28 ቀናት የምርመራ ጊዜ ሊያቀርብ እንዳልቻለ መግለጹ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ ዓቃቢያነ ሕጉ ተጠርጣሪዎቹ የጦር ሥልጠና ሲያደርጉ እንደነበር መግለጻቸው ስህተት መሆኑን ጠበቆቹ ጠቁመው፣ መንግሥት ራሱ በጀት መድቦ ሲያሠለጥናቸው የነበሩ መሆናቸውን አክለዋል፡፡ በአጠቃላይ ፖሊስ እንኳን ማስረጃ ሊያቀርብባቸው ቀርቶ ቃላቸውን እንኳን እንዳልተቀበላቸውም ጠቁመዋል፡፡
ተጠርጣሪው ዓቃቤ ሕግ አቶ የወግሰው በቀለ ለሥር ፍርድ ቤቶች ከታሰረ 50 ቀናት እንደሞላው ሲያስረዳ፣ ፍርድ ቤቱ ለምን ምርመራ እንዳልጨረሰ ፖሊስን ሲጠይቀው፣ የባልደራስ ምክር ቤት አባል መሆኑን ስለደረሰበት እያጣራ መሆኑን እንደገለጸም አስታውሰዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር የሰማው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት ለነሐሴ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
Ethiopian Reporter