ሰማያዊ ፓርቲ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች አባላቱ እየታሰሩና እየተደበደቡ መሆናቸው ገለፀ
በጋሞጎፋ ዞን በርካታ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች እየታደኑ እየታሰሩ መሆኑን የዞኑ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች ገልጸዋል፡፡ ከትናንት ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ጋሞ ጎፋ ዞን ጎፋ ወረዳ ሳውላ ከተማው ውስጥ በርካታ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች መታሰራቸውን የጋሞ ጎፋ ዞን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በተመሳሳይ በትናንትናው ዕለት በጋሞጎፋ ዞን ዳራማሎ ወረዳ ቅስቀሳ ላይ የነበሩ 17 የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ታስረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በጋሞጎፋ ዞን ቦንኬ ወረዳ ለፖሊስ “ለሰማያዊ ፓርቲ የሚቀሰቅስ ማንኛውም አካል ላይ እርምጃ ውሰዱ” የሚል ትዕዛዝ መተላለፉን የዞኑ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች ገልፀዋል፡፡
በሰሜን ወሎ ዞን ሀብሮ ወረዳ ጎራና ቀበሌ የሰማያዊ ፓርቲ የተወካዮች ምክር ቤት ዕጩ የሆነው አቶ ዮናታን ሰይድ በካድሬዎች ድብደባ እንደተፈፀመበት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ አቶ ዮናታን ዛሬ ከዋቱ 3፡20 አካባቢ ጊራና ከተማ ላይ የምርጫ ቅስቀሳ እያደረገ በነበረበት ወቅት የብአዴን/ኢህአዴግ ካድሬዎች ‹‹ለምን ትቀሰቅሷላችሁ? ደፍራችሁናል!›› በማለት ድብደባ እንደፈፀሙበት ገልጾአል፡፡ ሆስፒታል ሆኖ በስልክ ያነጋገረን አቶ ዮናታን በተለይ እግሩ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ገልጾአል፡፡
መንግስት ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም አይ ኤስ አይ ኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ሰበብ እየታደኑ እየታሰሩ መሆኑን የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ ሀሙስ ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም ብሌን መስፍንና ተዋቸው ዳምጤ ከመስሪያ ቤት ተይዘው የታሰሩ ሲሆን ሚያዝያ 24 ቀን 2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርበው ‹‹ሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተደረገውን አመጽ መርታችኋል፡፡›› በሚል ፖሊስ ክስ እንዳቀረበባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሳሳይ ዛሬ ሚያዝያ 26 ቀን 2007 ዓ.ም ማቲያስ መኩሪያ ቤቱ ውስጥ እያለ በፖሊስ ተይዞ ታስሯል፡፡ ማቲያስ፣ ብሌንና ተዋቸው ወረዳ 10 (ላዛሪስት ፖሊስ ጣቢያ) ታስረው ይገኛሉ፡፡ ይህንን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ የሚደረገው እስርም “መንግስት በሰማያዊ ፓርቲ ላይ የጀመረውን የሀሰት ክስ እውነት ለማስመሰል የታቀደ ነው፡፡ ፖሊስ ምርመራ ሳይጨርስ በሀሰት 20 አባላትንና 6 አመራሮችን አስረናል ብለው ነበር፡፡ እነሱ የፈለጉት ይህን ሚዲያ ላይ ወጥተው በሀሰት የፈፀሙትን ውንጀላ ማሰመሰል ነው፡፡” ሲል አቶ ዮናታን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡
በሌላ ዜና በየ ክፍለ ሀገሩ የሚገኙ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ ደህንነትና ፖሊስ የሚፈፅመው ድብደባ አሁንም መቀጠሉ ተገልጾአል፡፡ የደብረማርቆስ ከተማ ነዋሪና የሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆነችው የሀሳብ ጌታቸው “ለሰማያዊ ፓርቲ ወረቀት በትነሻል” በሚል ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀሙባት ተገልጾአል፡፡
ፖሊስ በ”በሁከትና ብጥብጥ” ተጠርጣሪዎች ላይ ሦስት መዝገብ አደራጅቻለሁ አለ
•እነ ወይንሸት ለሁለተኛ ጊዜ 6 ቀን ተቀጥሮባቸዋል
•”ወይንሸት ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ስታሸብር ነበር” ፖሊስ
ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ላይ “ሁከትና ብጥብጥ አስነስታችኋል፤ ተካፍላችኋልም” በሚል ፖሊስ ባሰራቸው ሰዎች ላይ ሦስት የተለያዩ መዝገቦች ማደራጀቱን አስታውቋል፡፡
ሚያዝያ 22 ቀን 2007ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የቀረቡ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ሌሎች በዕለቱ የተያዙ ሰዎችን በተመለከተ ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ እንደገለጸው፣ ፖሊስ የራሱን ቡድን በማዋቀር ተጠርጣሪዎችን በሦስት መዝገቦች ስር እንደየተሳትፏቸው አደራጅቻለሁ ብሏል፡፡ በዚህ መሰረት በሶስተኛው መዝገብ ላይ ያካተታቸውን በርካታ ታሳሪዎች አጣርቶ መልቀቁን የገለጸው ፖሊስ፣ በሁለተኛውና በአንደኛው መዝገብ ላይ ባሉት ተጠርጣሪዎች ግን ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጹዋል፡፡
አንደኛው መዝገብ ላይ በእነ ወይንሸት ሞላ መዝገብ 5 ሰዎች የተካተቱ ሲሆን አራቱ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ናቸው፤ አንደኛዋ ተጠርጣሪ ደግሞ ፖሊስ የፓርቲው አባል እንደሆነች የሚገልጸው፣ እሷ ግን አባል አለመሆኗን የገለጸች መሆኗን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ስለሆነም በዚህ መዝገብ የተካተቱት ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ማስተዋል እና የፓርቲው አባል ያልሆነችው ቤተልሄም ይገኙበታል፡፡ ማስተዋል በዛሬው ዕለት ቀደም ብሎ የተሰጠው የቀጠሮ ቀን ስላልደረሰ ፍርድ ቤት አልቀረበም፡፡ ቤተልሄም ‹‹የሰማያዊ ፓርቲ አባል ሳልሆን አባል ነሽ እየተባልኩ ምርመራ ይደረግብኛል፤ ሌሊት እየተጠራሁ እመኝ እየተባልኩ ነው›› ስትል ለፍርድ ቤቱ ገልጻለች፡፡
በሁለተኛው መዝገብ ላይ ደግሞ 15 ተጠርጣሪዎች ተካትተዋል፡፡ ፖሊስ በዚህ መዝገብ በተካተቱ ተጠርጣሪዎች ላይ ክሱን ሲያሰማ እንዲህ ብሏል፤ “ተጠርጣሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ሲያደርጉ ‹ጠንካራ መሪ እንጂ ጠንጋራ መሪ አንፈልግም›፣ ‹ወያኔ አሳረደን›፣ ‹ፍትህ የለም! በማለት ሁከት እንዲነሳ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡”
የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በምርመራ ወቅት የገጠማቸውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ ያሰሙ ሲሆን፣ በተለይ የሚደረግባቸው ምርመራ ከፓርቲው ጋር የተያያዘ እንጂ ከተጠረጠርንበት ጉዳይ ጋር የተያያዘ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ምርመራው ከጉዳዩ ጋር የሚገናኝ አይደለም፤ ሌሊት ሌሊት እየተጠራሁ ምርመራ ይደረግብኛል፡፡ የፓርቲ አባል መሆን ወንጀል እስኪመስለኝ በፓርቲ አባልነቴ ጫና ይደረግብኛል፡፡ በዚያ ላይ የጤና እከል ገጥሞኛል፤ ህክምና ያስፈልገኛል” ስትል ለፍርድ ቤቱ ያስረዳችው ወይንሸት ሞላ፣ ፍርድ ቤቱ የዋስትና መብት እንዲሰጣት ጠይቃለች፡፡
በሁለቱም መዝገብ የተካተቱት ሁሉም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፖሊስ በበኩሉ በመጀመሪያው መዝገብ ላይ ያሉት እነ ወይንሸት ላይ የምርመራ ስራውን እንዳልጨረሰ በመግለጽ 14 ቀን ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ በተለይ ወይንሸት ሞላ ላይ ፖሊስ፣ “ከአሁን በፊትም ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር ተመሳስላ በመልበስ ስታሸብር ነበር” በማለት ዋስትና እንዳይሰጥና የጠየቀው የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ በሁለተኛው መዝገብ ላሉት ደግሞ 7 ቀን ፖሊስ ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ በሁለቱም መዝገብ ላይ በተመሳሳይ የ6 ቀን ጊዜ በመስጠት ለሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶ እንደነበር አይዘነጋም፡፡
መንግስት በጠራው ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ወጣቶች እስር አሁንም እንደቀጠለ የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ በትናንትናው ዕለትም ሦስት የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አባላት (አንደኛው አሁን ላይ የሰማያዊ አባል) መታሰራቸው ይታወሳል፡፡
በተያያዘ ዜና ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስ ሊቢያ በሚገኙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የፈጸመውን አሰቃቂ የሽብር ድርጊት ለማውገዝ ጠርቶት በነበረው ሰልፍ ሳይጀመርና ከሰልፉ በኋላ ተይዘው የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ቤት ተበረበረ፡፡ ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው የሚገኙት የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ትናንት ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ለሁለተኛ ጊዜ ቀርበው የ6 ቀን ቀጠሮ ከተሰጠባቸው በኋላ ምሽት ላይ ቤታቸው መበርበሩንና ንብረቶቻቸው መወሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡
በብርበራው ወቅት የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት በሰላማዊ ሰልፍና በሌሎች አጋጣሚዎች የሚለብሱት የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ የምርጫና ሌሎች ቅስቀሳ ወረቀቶችም ለ‹ምርመራ› ተወስደዋል፡፡
ቤታቸው ለሰዓታት የተበረበረባቸው ወይንሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ጸጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ማስተዋል ፍቃዱ ሲሆኑ ወይንሸት ሞላ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ወረቀቶች፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ ሲዲዎች፣ አርማ የሌለው የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ (በተናጠል አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ የሆነ)፣መጽሐፎች እና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች እንደተወሰዱባት ገልጻለች፡፡ ዳንኤል ተስፋዬ የሰማያዊ ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አርማ ያለበት ቲሸርት፣ በአንድ ላይ ያስጠረዛቸው የፋክትና የአዲስ ጉዳይ እትሞች፣ ሲዲዎችና ካሴቶች ተወስደውበታል፡፡ በተመሳሳይ ኤርሚያስ ጸጋዬ ዴስክ ቶፕ ኮምፒውተር፣ የሰማያዊ ፓርቲ ሰነዶች፣ ሲዲዎች፣ ማስታወሻ ደብተሮችና ሌሎችም ህጋዊ ሰነዶች ተወስደውብኛል ብሏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር ዋስትና የከለከላቸውን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እየወሰደ እየመረመረ ነው፡፡ ሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ላይ የታሰሩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም ጠዋት በቄራ የፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ቀርበው የ6000 ብር የሰው ዋስትና እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመሻር በእስር አቆይቷቸዋል፡፡
ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ጥሶ በአሁኑ ወቅት ካሳንቺስ 6ኛ ፖሊስ ጣቢያ አስሯቸው የሚገኙትን የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ማዕከላዊ እየወሰደ እየመረመረ ይገኛል፡፡ በዛሬው ዕለት ዳንኤል ተስፋዬ ወደ ማዕከላዊ እስር ቤት ተወስዶ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ውስጥ በምርመራ ላይ እንደሚገኝ ምንጮች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡
በሀዲያ ዞን በምርጫ 2007 ዓ.ም. ቅስቀሳ ምክንያት የሁለት ሰዎች ህይወት አለፈ
በደቡብ ክልል በሀድያ ዞን ሶሮ ወረዳ ጊምቢቹ ከተማ በህዝብና በራሱ ላይ በሚፈፀመው አስተዳደራዊ በደል የተማረረውና በተደጋጋሚ በሚፈፀሙት አስተዳደራዊ በደሎች ላይ ቅሬታ አቅርቦ መፍትሄ ያላገኘው የአካባቢው የ2007 ዓ.ም. ምርጫ የመድረክ ዕጩ የነበረው መምህር ጌታቸው አብርሃም ሚያዝያ 17 ቀን 2007ዓ.ም በጊምቢቹ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ግቢ ውስጥ ራሱን ያቃጠለ ሲሆን በሆሳዕና ሆስፒታል ህክምና ሲደረግለት ቢቆይም ህይወቱ እንዳለፈች ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ቡሬ ለንጌ ትምህርትር ቤት የሲቪክስ መምህር የነበረው መምህር ጌታቸው በአካባቢው ባለው የከፋፍለህ ግዛና የጎሳ ፖለቲካ ተጠቂ ከመሆኑም ባሻገር በህዝብና በእሱ ላይ የሚደርሰውን በደል በመቃወም መፍትሄ እንዲሰጥ ለባለስልጣናት ሲያሳውቅ መቆየቱን፣ ሆኖም ህዝቡ እና በራሱ ላይ የሚፈፀምበት በደል በመባባሱና መፍትሄ ማግኘት ባለመቻሉ አስተዳደሩ ግቢ ውስጥ ራሱን ማቃጠሉ ታውቋል፡፡
መምህር ጌታቸው ራሱና ህዝብ ላይ የሚደርሰውን በደል በመቃወም በከተማው አስተዳደር ምክር ቤት ግቢ ውስጥ ራሱ ላይ ጋዝ በማርከፍከፍ ራሱን ባቃጠለበት ወቅት ግቢው ውስጥ የነበሩት ሰዎች ደርሰው እሳቱን በማጥፋታቸው ህይወቱን ለማዳን ጥረት አድርገው የነበር ቢሆንም የደረሰበት ጉዳት ከፍተኛ ስለነበር ህይወቱ አልፏል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛው በሀድያ ዞን አምቡላንሶች ለምርጫ ቅስቀሳ እየዋሉ በመሆኑ ህመምተኞች በተለይም ነፍሰ ጡር እናቶች ህክምና ሳያገኙ ለሞት እንደሚዳረጉ ነዋሪዎቹ ገለፁ፡፡ ሚያዝያ 20 ቀን 2007 ዓ.ም አንዲት ምጥ የተያዙ እናት በአቅራቢያቸው በሚገኝ የጎምበራ የጤና ጣቢያ በሄዱበት ወቅት ‹‹ከአቅማችን በላይ ነው!›› ተብለው ወደ ሆሳዕና ሪፈራል ሆስፒታል ሄደው እንዲታከሙ ሪፈር ቢፃፍላቸውም በትራንስፖርት ችግር ነፍሳቸው አልፋለች፡፡
ለጤና ጣቢያው የተመደበችው አምቡላንስ በጎምበራ ወረዳ ኦሌ ቀበሌ ለገዥው ደኢህዴን/ኢህአዴግ ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ በመውጣቷ ቤተሰብ ነፍሰጡሯን ከጎምበራ ክሊኒክ ወደ ሆሳዕና ሪፈራል ሆስፒታል በቃሬዛ ለመውሰድ መገደዳቸውን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአካባቢው ነዋሪዎች ወደ ሆሳዕና ሆስፒታል በቶሎ መድረስ ባለመቻላቸው የነፍሰ ጡሯ ህይወት መንገድ ላይ ሊያልፍ ችሏል፡፡
ነዋሪዎቹ እንደገለጹት ከሆነ አምቡላንሶች ለምርጫ ቅስቀሳ በመዋላቸው ምክንያት በርካታ ህመምተኞች በተለይም እናቶችና ህፃናት በቶሎ ወደ ሆስፒታል መድረስ ባለመቻላቸው ተመሳሳይ ችግር እየገጠማቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ በምርጫ 2002 ዓ.ም ወቅትም በተመሳሳይ መልኩ በዚሁ በሀዲያ ዞን አምቡላንሶች ለኢህአዴግ ምርጫ ቅስቀሳ ወጥተው ነፍሰ ጡር እናቶች ህይወታቸው ማለፉ አይዘነጋም፡፡
በሜዴትራኒያን ባህር ላይ በደረሰ የጀልባ አደጋ ከ16 በላይ ኢትዮጵያውያን ህይወታቸው አለፈ
ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሜዴትራኒያን ባህር ከሊቢያ ወደ አውሮፓ በስደት ሲጓዙ ከነበሩ 700 ሰዎች መካከል በርካቶች መሞታቸውንና የ28 ሰው ህይወት ብቻ በጣሊያን ባህር ኃይሎች ማትረፍ ቢቻልም፤ የአብዛኛው ተጓዥ ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡ ህይወታቸው ካለፉት ውስጥ በርካታ ኤርትራውያን እንዳሉበት ቀደም ሲል የተገለፀ ቢሆንም፤ አሁን እየወጡ ባሉ መረጃዎች በተለይም ከሞት በተረፉ ኢትዮጵያውያን እንደተገለፀ ከሆነ ከ16 በላይ ኢትዮጵያውውን መሞተታቸው ታውቋል፡፡ በጉዞ ጀልባዋ ላይ በደረሰ የመስጠም አደጋ ህይወታቸው ካለፉት መካከል 8 ወጣቶች ከአዲስ አበባ መርካቶ ልዩ ስሙ አባኮራን በሚባል አካባቢ፣ 8 ወጣቶች ከባሌ እንዲሁም የድሬዳዋ ልጆች ህይወታቸው ማለፉን ቢቢኤን እና ፍትህ ሬዲዮን ጨምሮ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ከሀገር ቤት ቤሰቦቻቸውን ዋቢ በማድረግ ያሰራጩት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በተለይ ከአዲስ አበባ መርካቶ አባኮራን አካባቢ በጋራ ከተጓዙ 10 ወጣቶች መካከል 9ኙ በአደጋው ህይወታቸው ማለፉን እና አንዱ ከአደጋው የተረፈው ኢትዮጵያዊ ወጣት ጣሊያን እንደገባ ሀገር ቤት ደውሎ ማርዳቱ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም መሰረት የ8ቱ ቤተሰቦች ሀዘን ሲቀመጡ የአንዱ ወጣት ወላጆች ግን እስካሁን የልጃቸው ህይወት አልፏል መባሉን እንዳላመኑ እና እንዳልተቀበሉም የአካባቢው ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ሜዲትራኒያን ባህር በደረሰው አደጋ ህይወታቸው ካለፈ የአዲስ አበባ አባኮራን ሰፈር ወጣቶች መካከል አብዱ ጅላል ወጉ (ሙራድ)፣የሐዋሳ ዩኒቨርስቲ ተማሪ የነበረው ኑሩ መሐመድ፣አብዱልከሪም ዘይኒ፣ ሰይድ ይመር፣ አሊ መሐመድ፣ ነጃ ሳቢር አወል እና የኢንፎኔት ኮሌጅ ተመራቂ የነበረው ኢድሪስ አደም እና ወጣት ሸበቴ ህይወታቸው በማለፉ ቤተሰቦቻቸው ተረድተው ሀዘን መቀመጣቸው ተጠቁሟል፡፡ በሰጠመችው ጀልባ ከባሌ አካባቢ ህይወታቸው ካለፉት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል አብዱረዛቅ አቡበክር፣ በሪሲና አብዱልወሃብ፣ ሰይፈዲን አሊዪ፣ ሬድዋን ሙሃመድ፣ አሊይ ረሻድ፣ ኢሳ አማን፣ ኑእማን ሁሴን እና ሲራጅ ሙሃመድ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡ በዚህ አደጋ ከድሬዳዋ አካባቢም ህይወታቸው ያለፈ ወጣቶች እንደሚገኙበትና ቤተሰብም ተረድቶ ሀዘን መቀመጣቸውን የቢቢኤን ዘገባ አመልክቷል፡፡
በዚህ አደጋ ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ከ350 ያላነሱ ኤርትራውያንን ጨምሮ በርካታ የሶማሊያ እና የተለያዩ የአፍሪካ ሀገር ዜጎች ህይወታቸው ማለፉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ ባለፈውበደደቡብ አፍሪካ፣ በየመን እንዲሁም በሊቢያ በረሃ በዓለም አቀፉ አሸባሪው አይ ኤስ አይ ኤል 28 ኢትዮጵያውያን መገደላቸው ተከትሎ በመላ ሀገሪቱ ያለው የሀዘን ድባብ ሳያባራ አሁን ደግሞ በሊቢያ ሜዴትራኒያን ባህር ሰጥመው መሞታቸው ህዝቡን የበለጠ ሀዘን ውስጥ መክተቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ መጨረሻ 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ታስረው የነበሩ 27 ኢትዮጵያውያን በግብፅ መንግሥት ጥረት እንዲለቀቁ ተደርገው ወደ ካይሮ ሲገቡ የግብፁ ፕሬዘዳንት አብዱል ፈታህ ኤል ሲሲ በአውሮፕላን ማረፊያው ድረስ በመሄድ አቀባበል ማድረጋቸው አይዘነጋም፡፡
መንግሥት ራሱ በጠራው ሰልፍ በርካታ ሰዎችን ሲደበድብ፤ ከመቶ በላይ ሰዎች ታስረዋል
ሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መንግሥት በሊቢያ፣በደቡብ አፍሪካና በየመን ኢትዮጵያውያን በግፍ መገደላቸውን በተመለከተ በአዲስ አበባ ድርጊቱን ለማውገዝና ለመቃም ሰልፍ ጠርቶ የነበረ ቢሆንም፤ በሰልፍ የተገኙ በርካታ ሰዎች በፖሊስ ተደብድበው ወደ አካባቢው ሆስፒታሎች የተወሰዱ ሲሆን፤ ከ100 በላይ ሰዎች መታሰራቸውንም አልጀዚራን ጨምሮ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ከስፍራው በቀጥታ ዘግበዋል፡፡ በተለይ በአሸባሪው በ አይ ኤስ አይ ኤል (ISIL) ቢያንስ 28 ኢትዮጵያውያን በጭካኔ መገደላቸውና መንግሥትም ለዚህ ያሳየው ቸልተንነት ህዝቡን የበለጠ በማስቆጣቱ ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ያለማንም ቀስቃሽ የአዲስ አበባ ነዋሪ ለተቃውሞ ሰልፍ ቢወጣም መንግሥት ፈቃድ አልሰጠሁም በሚል በርካቶች ከደበደበ በኋላ ለሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. ራሱ ድርጊቱን በመቃወም ሰልፍ ቢጠራም መጨረሻው በፖሊስ ከፍተኛ ድብደባና እስር ተጠናቋል፡፡ ሰልፉ ከመጀመሩ በፊት የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶችን ጨምሮ በርካታ ወጣቶች ወደሰልፉ ሲሄዱ የታሰሩ ሲሆን፤ ከሰልፉ በኋላ የመንግሥት ባለሰልጣናት መስቀል አደባባይ ንግግር ሲያደርጊ ህዝቡ በልቅሶ ተቃውሞ ካሰማ በኋላ የአዲስ አበባ እና የፌደራል ፖሊስ እዛው ሰልፉ ቦታ ሲደበድብ ታይቷል፡፡ ይሄንንም የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን በቀጥታ አሰራጭተዋል፡፡
ዓለም አቀፍ አሸባሪው ቡድን ISIL በሊቢያ የገደልኩት ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን ቢልም፤ በአዲስ አበባው ተቃውሞ የእስልምና እና የክርስትና ኃይማኖት ተከታዮች በጋራ ድርጊቱን ሲያወግዙ ተስተውሏል፡፡ በዕለቱም በርካታ መፈክሮች የተሰሙ ሲሆን፤
ታርዷል ወገኔ፣ ታርዷል ወገኔ…(በኡኡታና ልቅሶ)
ሽብርን እንቃወማለን፣እናወግዛለን
መንግሥት ኃላፊነቱን አልተወጣም
ሞት ለወያኔ፤ ያረደንም ያሳረደንም ወያኔ ነው
ይለያል ዘንድሮ የዌኔ ኑሮ
ውሸት ሰለቸን፤ የወንድሞቻችን ደም ይመለስ
የሀገር ውስጥ ISIL ወያኔ ነው፤…በቃን
ISIL እስልምናን አይወክልም፤ እኛ የኢትዮጵያውያ ሙስሊሞች ወንድሞቻችን ክርስቲያኖች በአሸባሪ ቡድኑ መገደላቸውን አጥብቀን እናወግዛለን፤ ድርግቱም ሽብር እንጂ እስልምናን አይወክልም (በተለይ በሰልፉ የተገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች)
መንግሠት የሌለው እዚህ ብቻ ነው
የኢትዮጵ አምላክ ይፍረድ (በተለይ የሟቾቹ ቤተሰቦች)
ና ና መንጌ ና ና (የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት መንግሥቱ ኃይለማርያምን)
የቤት አንበሳ የውጭ እሬሳ (መንግሥትን) የሚሉ መፈክሮች ይገኙበታል፡፡
በመጨረሻም በመንግሥት ላይ የህዝቡ ተቃውሞ ተጠናክሮ ሲቀጥል የመንግሥት ባለስልጣናት ንግግር በቅጡ ሳይሰማ የተቋረጠ ሲሆን፤ ፖሊስም ወዲያውኑ ያገኘውን ሁሉ እያሳደደ ሲደበድብ ለማየት ተችሏል፡፡ በቂርቆስ ሰፈር ልቅሶ ቤት አካባቢ በነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻ በስፍራው እጅግ በርካታ ፖሊሶች በስፍራው የነመበሩ ሲሆን፤ በኋላም ከፍተኛ የመሳሪያ ተኩስ ተሰምቷል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በተተኮሰው ጥይት በሰው ህይወትና አካል ላይ ጉዳት ስለማደረሱ የተረጋገጠ መረጃ ባይኖርም መስቀል አደባባይ በነበረው የፖሊስ ድብደባ ራሳቸውን ስተው የወደቁ ሴቶች፣እናቶችና ወጣቶች የታዩ ሲሆን፤ ብዙ ወጣቶች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በአምቡላንስ እና በሰው እግዛ ወደ ህክምና ጣቢያ ሲሄዱና የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ታይቷል፡፡
መንግሥትም በተመሳሳይ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የሽብር ድርጊቱን በመቃወም በመዋቅሩ ሰልፍ ማዘጋጀቱና ለዚህም የኢህአዴግ ሊግና ፎረነም አባላት ከየቀበሌው በነበረው መዋቅር ወደሰልፍ እንዲወጡ፣ ሌላ ወደተቃውሞው ሰልፍ የሚመጣ ካለ በደንብ ከበው እንዲከታተሉት፣ መፈክሮችም በኢህአዴግ ብቻ እንዲዘጋጅ ከዛ ውጭ ያለ መፈክር ይዞ የሚመጣ ማንኛውም አካል ካለ ወደሰልፉ መሐል ከመቀላቀሉ በፊት ጥብቅ ምርመራ መደረግ እንዳለበት ትዕዛዝ መሰጠቱንም ምንጮች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡
በተለይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ቀደም ሲል የሽብር ድርጊቱን በማውገዝ መንግሥት እርምጃ እንደሚወስድ በፌስ ቡክ ግድግዳቸው ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቢናገሩም፤ በመጨረሻም አሸባሪው ድርጅት ላይ በመንግሥት እርምጃ ይወሰዳል ተብሎ ሲጠበቅ፤ በአዲስ አበባ ሰልፈኛ ላይ እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡ መንግሥት በበኩሉ እርምጃ የተወሰደው ፖሊሶች ላይ ድንጋይ ስለተወረወረ ነው የሚል ምክንያት ሰጥቷል፡፡
በተለይ በሊቢያ የሟቾች ማንነት እየተለየ ሲሆን፤ ስማቸውም ኢያሱ ይኮኖአምላክ፣ ባልቻ በለጠ፣ ብሩክ ካሳ፣ በቀለ ታጠቅ እና ኤልያስ ተጫኔ ከአዲስ አበባ ቂርቆስ ሰፈር፤ መንግሥቱ ጋሼ እና አወቀ ገመቹ ከወለጋ ነቀምት፣ በቀለ አርሰማ ከጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ ካራቻ አካባቢ፣ የጅማ ዩኒቨርስቲ ምሩቅ የነበረው ዳንኤል ሓዱሽ፣ አለም ተስፋይ እና ዳዊት ሀድጉ ከትግራይ መቀሌ አካባቢ፣ ክርስቲያን ወንድሞቼን ለይታችሁ አትገድሉም፤ በእስልምና የሰውን ህይወት ማጥፋት ኃጥትም ወንጀልም ነው፣ እኔ ከእነሱ አልለይም በማለት ሲከራከር የነበረው ኢትዮጵዊው ሙስሊም ጀማል ረህማንም አብሮ መገደሉ ታውቋል፡፡ በአሸባሪው ቡድን ከተገደሉ ኢትዮጵያውያን ጋር ተስፋይ ኪዳኔን ጨምሮ ሶስት ኤርትራውያንም እንደሚገኙበት የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ ተስፋይ ከዚህ በፊት በእስራኤል ጥገኝነት ጠይቆ በመከልከሉ በሊቢያ ወደ አውሮፓ ለመሄድ ሲሞክር በአሸባሪ ቡድኑ እጅ መግባቱ ተጠቁሟል፡፡








