ኦብነግ የኢትዮጵያን መንግሥት በጭፍጨፋ ከሰሰ
በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ውስጥ የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይል ጥቃት አድርሰው ሃምሣ አንድ ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ስሞታ አሰምቷል፡፡

ሶማሌ ክልል ውስጥ ጃማ ዱባድ በሚባል መንደር ሰሞኑን የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይሎች በመንደርተኞች ላይ ጥቃት አድርሰው 51 ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር – ኦብነግ ከስሷል፡፡
“የመንግሥቱ የፀጥታ ኃይሎች በሌሎች አካባቢዎችም በተለያዩ የቅርብ ጊዜያት ከሦስት መቶ በላይ ሰላማዊ ሰዎችን ገድለዋል” ያሉት የኦብነግ ቃል አቀባይ አቶ ሃሰን አብዱላሂ ድርጅታቸው ጉዳዩን ለዓለምአቀፍ ተቋማት ለማድረስ ማስረጃዎችን እያጠናቀረ መሆኑን ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የቪኦኤ የሶማሊኛ ዝግጅት ክፍል ወደ አካባቢው ደውሎ ያነጋገራቸው የጎሣ መሪ ወታደሮቹ ስድስት ሕፃናትና ሴቶችንም ጨምሮ ሃያ አራት ሰዎችን መግደላቸውን አመልክተዋል፡፡ ሌሎች ምንጮች ደግሞ ወታደሮቹ መንደሪቱን ማቃጠላቸውንና አሥር ሰዎች የገበቡበት እንደማይታወቅ ጠቁመዋል፡፡ ስለጉዳዩ ከክልሉም ሆነ ከፌደራል መንግሥቱ የተሰጠ መግለጫ የለም፡፡
ምንጭ፡- VOA Amharic service
የኢትዮጵያ መንግሥት በአሜሪካን ሀገር የፈፀመውን ህግወጥ የቦንድ ሽያጭ ገንዘብ ከነወለዱ እንዲመልስ ተወሰነበት
(አዲስ ሚዲያ) የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካን ህገወጥ የቦንድ ሽያጭ በማድረግ የሰበሰበውን ገንዘብ እንዲመልስ ተወሰነበት። የአሜሪካን የቦንድ ሽያጭና ግዥን የሚቆጣጠረው ኮሚሽን ባቀረበው ክስ መሰረት፤ የኢትዮጵያ መንግስት መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን በአሜሪካን ባልተመዘገበ የቦንድ ሽያጭ የሰበሰበውን 5.8ሚሊዮን ዶላር እና 6 መቶ ሺህ ዶላር ወለድን ጨምሮ በድምሩ 6.45 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንዲከፍል ተስማምቷል።

የኢትዮጵያ መንግሥት ከ2004 ዓ.ም. እስከ 2006 ዓ.ም. በህገወጥ መንገድ ገንዘቡን ሰብስቦት የነበረው ነዋሪነታቸው በአሜሪካን ሀገር ከሆኑ 3,100 ኢትዮጵያውያን ነበር፡፡ ስለሆነም በቦንድ ግዥ የተሰበሰበው ገንዘብ በሙሉ ከነ ወለዱ እንዲመለስ የተደረገው፤ የአሜሪካን ሴኩዩሪቲ ኤንድ ኤክስቼንጅ ኮሚሽን (SEC) ህግን ተላልፎ በመገኘቱ መሆኑን የኮሚሽኑ መግለጫ አስታውቋል። የኢትዮጵያ መንግሥትም የአሜሪካን ህግ በመጣስ የቦንድ ሽያጭ ማካሄዱን በማመን፤ የቦንድ ሙሉ ሽያጩን ከነ ወለዱ ለአሜሪካ መንግሥት ለሚመለከተው አካል ለመክፈል መስማማቱን ኮሚሽኑ በዋሸንግተን ዲሲ ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል፡፡
እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ መከላከል አትችሉም ተባሉ
ማህሌት ፋንታሁን
የካቲት 4 ቀን 2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል በዋለው ችሎት እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ( ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ኢየሩሳሌም ተስፋው፣ ፍቅረማርያም አስማማው እና ደሴ ካህሳይ) አቃቢ ህግ ያቀረበባቸውን ክስ በሰነድና በአንድ የሰው ምስክር ማስረጃዎች አስረድቷል በሚል ተከሳሾች መከላከል ይገባቸዋል ሲል ፍርድ ቤቱ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

ውሳኔውን ተከትሎም መከላከያ ማስረጃዎች ያቀርቡ እንደሆነ በሚል ፍርድ ቤቱ ጠይቆ፣ ተከሳሾች 200 የሰው ምስክሮችና የሰነድ ማስረጃዎች በጋራ እንደሚያቀርቡ አሳውቀው ነበር፡፡ ከዛ በኋላ በነበሩ ቀጠሮዎችም ምስክሮቻቸውን በዝርዝር አስገብተው ነበር፡፡ እንዲሁም ከዛሬ ግንቦት 30 እስከ ሰኔ 8 ቀን 2008ዓ.ም. ድረስ ምስክሮቻቸውን እንዲያሰሙ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም፤ የቀጠሯቸው ቀን ሳይደርስ፤ ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት ቀርበው ጭብጥ እንዲያሲዙ ተጠይቀዋል። እነሱም የምስክርነት ጭብጥ ምስክሮች መሃላ ሳይፈፅሙ መያዝ እንደሌለበት ለፍቤቱ አስረድተው ውሳኔውን ለመስማት ለዛሬ ተቀጥረው ነበር።

ይሁን እንጂ አራት ወር ሙሉ ፍርድ ቤቱ ሲሰጥ ከነበረው ትዕዛዝ በተለየ “መከላከያ ምስክር ማሰማት የለባችሁም ስለዚህ ለፍርድ ብይን ሃምሌ 13, 2008 ቅረቡ” የሚል ውሳኔ አስተላልፏል።
ምንጭ፡-ከማህሌት ፋንታሁን ፌስቡክ ገፅ የተወሰደ
በጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው የሽብር ክስ በንባብ ተሰምቷል
*ተከሳሹ ጥቁር ልብስ ለብሰሃል በሚል በቀጠሮው ሰዓት አለመቅረቡ ታውቋል

የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በሆነው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. የመሰረተው የሽብር ክስ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡
ተከሳሹ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርቦ ክሱ ሊነበብለት የነበር ቢሆንም ከጠበቃው ጋር ሳይመካከር ክሱ እንዲነበብለት እንደማይፈልግ በመግለጹ በቀጠሮ ሰንብቶ ዛሬ ተነቦለታል፡፡ ከክስ ዝርዝሩ መረዳት እንደተቻለው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው ክስ የጸረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ሆኗል፡፡
አቃቤ ህግ በክሱ ላይ እንዳመለከተው ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል ጠቅሷል፡፡
ተከሳሹ ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡
ችሎቱ ክሱን በንባብ አሰምቶ ሲያጠናቅቅ በተከሳሹ ላይ የተጠቀሱ የአቃቤ ህግ የማስረጃ ዝርዝሮችን በተመለከተ እንደገለጸው፣ ተከሳሹ የተጠቀሰበት ማስረጃ የሰነድ ማስረጃ ብቻ መሆኑ ተገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኝ ሲሆን፣ በዛሬው የችሎት ቀጠሮ በጠዋት እንዲቀርብ የሚል ቢሆንም የእስር ቤቱ አስተዳደር ‹‹ጥቁር ልብስ ለብሰህ ፍርድ ቤት መሄድ አትችልም›› በሚል ጠዋት ሳያቀርቡት ከቆዩ በኋላ ከሰዓት ሊያቀርቡት ችለዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሽ የክስ መቃወሚያን ለመቀበል ለሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- EHRP
ታዋቂ የኢትዮጵያ አትሌቶች በፌዴሬሽኑ ላይ ቅሬታ አሰሙ
(አዲስ ሚዲያ)ታዋቂ የኢትዮጵያ አትሌቶች ዛሬ ግንቦት 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት በአዲስ አበባ ስታዲየም በይፋ ባደረጉት ውይይት በአትሌቲክስ ፌዴሬሽኑ ላይ ያላቸውን ቅሬታ ተወያይተው፤ በጉዳዩ ዙሪያ ከፌዴሬሽኑ እና ከሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ጋር ለመወያየት 10 ኮሚቴዎችን ሰይመዋል፡፡ በውይይቱ ላይም አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ፣ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ አትሌት አሰፋ መዝገቡ፣ አትሌት ገብረእግዚአብሔር ገብረማርያም፣ አትሌት አሰለፈች መርጊያ፣ አትሌት ገዛኸኝ አበራ፣ አትሌት ፋንቱ ሜጊሶ፣ አትሌት የማነ ፀጋዬ፣ ኮማንደር አበበ መኮንን እና ሻምበል ቶሎሳን ጨምሮ በርካታ ስመ-ጥር አትሌቶች ተገኝተዋል፡፡

አትሌቶቹ ከሐምሌ 29 እስከ ነሐሴ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. (እ.አ.አ ከነሐሴ 5-21 ቀን 2016 ዓ.ም.) በብራዚል ለሚካሄደው የሪዮ ዲ ጄኔሪዮ ኦሎምፒክ ብቃት ያላቸው አትሌቶች ሊመረጡ እንዳልቻሉ እና አሁንም የ5 ሺህ እና የ10 ሺህ ሜትር ሩጫ ውድድሮች ላይ ተመሳሳይ ችግር እንዳይፈጠር መስራት እንደሚፈልጉ እና ለማራቶን ውድድር የተመረጡትንም ቢሆን በስነ ልቦና ደረጃ ሊያግዝ የሚችል ብቃት ያለው አሰልጣኝም ሆነ አመራር ስለሌለ በመጪው ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ ልታገኝ የምትችላቸው ድሎች አስጊ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ አሁን ያለው ፌዴሬሽን በብቃትም በገንዘብ አቅምም እየተዳከመ ምጣቱን እና አስጊ ደረጃ ላይ መገኘቱን በመጠቆም ብዙ የለፉበትና የለፉለት ተቋም እስኪፈርስ ድረስ መጠበቅ እንደሌለባቸው አስታውሷል፡፡ ያለውን ችግር ለመቅረፍና ለመነጋገር ከዚህ ቀደም የአትሌቶች ማኀበር ፕሬዘዳንት የሆነውን አትሌት ስለሺ ስህንን የአትሌቶች ፒቲሽን የተፈረመበት ደብዳቤ ይዞ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠራ ቢጠይቅም፤ አትሌት ስለሺ አልጠራም በማለቱ ለዛሬው መሰባሰብና ውይይት ምክንያት እንደሆነም ተናግሯል፡፡ አሁን ያለውን ችግርም ለመቅረፍ ከአትሌቶቹ የተውጣጣ ኮሚቴ እንደሚያስፈልግ እና ለዚህም ራሱን ከኮሚቴው አንዱ አድርጎ ዕጩ ማድረጉን በመጠቆም የመጪው ኦሎምፒክ ውጤት አሁን ባለው የፌዴሬሽኑ አሰራር በ5 ሺህ እና በ10 ሺህ የሴቶች ውድድር ካልሆነ በስተቀር ሀገሪቱ የወርቅ ሜዳሊያ ስለማግኘቷ ጥርጣሬ እንዳለውም ሲናገር ተደምጧል፡፡
በተመሳሳይም አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ ገብረእግዚአብሔር፣ አትሌት ፋንቱ ሜጊሶ፣ አትሌት ዳዊት፣ አትሌት አሰፋ መዝገቡ፣ አትሌት የማነ ፀጋዬ እና መቶ አለቃ መኮንንን ጨምሮ የተለያዩ አትሌቶች በፌዴሬሽኑ እና ተጠሪነቱ ከአትሌቶቹ ይልቅ ለፌዴሬሽኑ በሆነ የኢትዮጵያ አትሌቶች ማኀበር ላይ የነበሩ ብልሹ አሰራሮች እና ቅሬታዎችን ሲያነሱ ተደምጧል፡፡
በተለይ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ጥሩ አቋም ላይ እያለ እና ብቃት እያለው በማራቶን እጩዎች ውስጥ አለመካተቱ ስፖርቱን በሚከታተሉ ኢትዮጵያውያን ተቃውሞ ማስነሳቱ ቢታወቅም፤ በታዋቂ አትሌቶችም ዘንድ የቀነኒሳ በቀለ በማራቶኑ ውድድር ላይ ኢትዮጵያን ወክሎ እንዳይገኝ መደረጉ ተመሳሳይ ቅሬታ እንዳደረባቸው በውይይቱ ላይ ተነስቷል፡፡ ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በበኩሉ የአትሌት ቀነኒሳ በኦሎምፒኩ ላይ መሳተፍ ውጤት ብቻ ሳይሆን ቀነኒሳ በውድድሩ ላይ መካተቱ በራሱ ለሀገሪቱ ትልቅ ጥቅም እንዳለው በሲድኒ የነበረውን የራሱን እና የደራርቱ ቱሉን ተሞክሮ አስታውሷል፡፡ በጥሩ ብቃት እንዳለና ለኦሎምፒኩም ዝግጁ ሆኖ ሳለ ባለመካተቱ ቀነኒሳም ቅሬታ እንዳደረበት ያልሸሸገው ቀነኒሳ፤ አሁን የተመረጡ ልጆችንም ቢሆን በስነ ልቦናም ሆነ በቴክኒክ ሊያግዝ የሚችል ብቃት ያለው አስልጣኝም ሆነ አመራር ባለመኖሩ ልናግዛቸው ይገባል፤ በበኩሌ አሁን ቢጋብዙኝም በውድድሩ አልገባም ሲል ተደምጧል፡፡
በነበረው ውይይትም በአትሌት ስለሺ ስህን እና በአትሌት መሰረት ደፋር የሚመራው የአትሌቲክ ማኀበር ቢሮም ሆነ የገንዘብ ድጋፍ እየተደረገለት ያለው በአትሌቲክ ፌዴሬሽን በመሆኑ ነፃ ሆኖ ለአትሌቶቹ ተገቢውን አገልግሎት ሊሰጥ ስላልቻለ አዲስ የአትሌቶች ማኀበርም መቋቋም እንዳለበትም ሐሳብ ተነስቷል፡፡ በተለይ አትሌቶቹን ወክሎ ከሚመለከተው አካል ጋር ለመነጋገ፣ ከ2 ወራት በታች ለቀሩት የኦሎምፒኩ ውድድርም ብቃት ያላቸውና ተገቢ አትሌቶች ተሳትፈው የሚፈለገውን ውጤት ይዘው እንዲመጡ ለማገዝ እና ለአትሌቶቹ መብትና ጥቅም የቆመ ማኀበርንም በተመለከተም ለመነጋገር 10 ኮሚቴዎችን በመምረጥ ውይይቱ ተጠናቋል፡፡
በውድድሩ በ42 የተለያዩ ስፖርት ዘርፎች 206 ያህል የዓለም ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ በ5 የስፖርት በተለይም በሩጫ፣ በብስክሌት፣ በቦክስ በዋና እና በቴክ-ዎንዶ ውድድር ዘርፎች ለመሳተፍ ማቀዷን ይፋ ማድረጓ ይታወቃል፡፡ በዚህ ብራዚሉ ሪዮ ዲ ጄኔሪዮ ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ 4 የወርቅ፣ 4 የብር እና 4 የነሐስ ሜዳልያ ለማግኘት ግብ ማስቀመጧን ከኦሎምፒክ ኮሚቴ የተገኘው መረጃ አመልክቷል፡፡