Category Archives: News

“ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ መብትና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡት ድርጊት ልከሰስ አይገባም” አቶ ዮናታን ተስፋዬ

ታምሩ ጽጌ

በፌስቡክ አድራሻቸው አመፁና ብጥብጥ ቀስቃሽ ጽሑፎችን በማሠራጨት፣ የኦነግን ዓላማ ለማስፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ተብለው በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው የተከሰሱት የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ የቀረበባቸውን ክስ ተቃወሙ፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ ‹‹ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትና በክሱ የተጠቀሰው ብጥብጥና አመፅ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡበት ሁኔታ ልከሰስ አይገባም፤›› ሲሉም ተቃውሞአቸውን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

Yonatan Tesfaye

በኦሮሚያ ክልል ተከስቶ የነበረው ብጥብጥና አመፅ ‹‹የመልካም አስተዳደር ዕጦት ችግር ነው፡፡ የሌላ ሦስተኛ አካል ተሳትፎ የለበትም፤›› በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ማረጋገጣቸውን ያስረዱት ተከሳሹ አቶ ዮናታን፣ የተለያዩ የፌደራልና የክልል ሥራ ኃላፊዎችና ባለሥልጣናትም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር በማጠናከር፣ ዕርምጃ የወሰዱበትና በርካታ ሹማምንትም ከኃላፊነት መነሳታቸውን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ የሚያውቀውና ከማንም ያልተደበቀ በመሆኑ፣ ግልጽ የሆነ የሕግ ግምት (Judicial Notice) የሚወስድበት ጉዳይ መሆኑን አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ዞኖች፣ ወረዳዎችና ቀበሌዎች የተደረገው አመፅና ብጥብጥ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑ ተረጋግጦ ሳለ፣ በቀረበባቸው ክስ ላይ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) እንደተጀመረና እሳቸው በፌስቡክ ገጻቸው ባሠራጩት መጣጥፍ ለማስቀጠል የተደረገ እንደሆነ መገለጹ፣ ከአዋጁ መንፈስ ውጪ መሆኑን በመጠቆም ክሱ ውድቅ ተደርጐ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

አቶ ዮናታን በክስ መቃሚያቸው ላይ እንዳብራሩት፣ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (4)ን መተላለፋቸው ተገልጿል፡፡ በአንቀጹ እንደተገለጸው ተላልፈዋል የተባለው ድርጊት ማቀድ፣ መዘጋጀት፣ ማሴር፣ ማነሳሳትና መሞከር የሚል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ በክሱ ያሰፈረው አቶ ዮናታን ኦነግ ያስጀመረውን አመፅና ብጥብጥ ለማስቀጠል በፌስቡክ ገጻቸው ላይ የተለያዩ ቀስቃሽ ጽሑፎችን ማሠራጨታቸውን የሚገልጽ በመሆኑ፣ በአዋጁ አንቀጽ ሥር ከተመለከቱት ውስጥ በአንዱም የማይሸፈን መሆኑን በመግለጽ አብራርተዋል፡፡ በመሆኑም የዓቃቤ ሕግ ክስ በወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 112 የተደነገገውን ማለትም ‹‹… ወንጀለኛው የፈጸመው ተግባር፣ ወንጀል ከሚያደርገው የሕግ አነጋገር ጋር በጣም የተቀራረበ መሆን አለበት፤›› ከሚለው ድንጋጌ ጋር የሚጋጭ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

አቶ ዮናታን ፈጽመውታል ለተባለው ክስ በማስረጃነት የቀረበው የሰነድ ማስረጃ በፌስቡክ ገጻቸው ተሠራጨ የተባለው መጣጥፍ መሆኑን ገልጸው፣ ፌስቡክ ደግሞ ዘመናዊ የመልዕክት መለዋወጫ ዘዴ መሆኑን፣ ይኼም በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ድንጋጌ ከመሆኑ አንፃር፣ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በየትኛውም ሕግ ገደብና ክልከላ ያልተደረገባቸውና በቀረበባቸው ክስ በተጠቀሰው አንቀጽ ሥር የማይሸፈንና የሽብርተኝነት ተግባር አለመሆኑንም አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ ሕገ መንግሥታዊና ሰብዓዊ መብታቸውን ለማስከበር የተቀመጡ መርሆዎችንና ድንጋጌዎችን የማያሟላ ክስ መሆኑን ገልጸው፣ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸው ክስ ሐሳቡና ይዘቱ አርትኦትና የቃላት ማስተካከል የጎደለው ከመሆኑም በተጨማሪ ለመረዳት የሚያስቸግር፣ በረጃጅም ዓረፍተ ነገሮችና አባባሎች አሳሳች ሆኖ የቀረበ በመሆኑ በወንጀል መዝገብ ሥነ ሥርዓት ቁጥር 111 ድንጋጌን ማለትም፣ ‹‹… የክስ ማመልከቻ ቀን፣ ዓመተ ምሕረት የተጻፈበትና የተፈረመበት…›› የሚለውን የማያሟላ መሆኑን አቶ ዮናታን ጠቁመው፣ ክሱ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ክሱን የሚያሻሽል ከሆነም በሕጉ አግባብ ሥነ ሥርዓቱን ተከትሎ በሚያቀርበው ክስ ላይ የሚጠቅሰው የሕግ አንቀጽ፣ ከክሱ ጋር የሚቀራረብና የተከሳሹን የመከራከር መብት የማያጣብብ አድርጐ እንዲያዘጋጅ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው፣ ጉዳዩን ለሚከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. አመልክተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም የዓቃቤ ሕግን ምላሽ ለመጠባበቅ ለግንቦት 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የሽብርተኝነት ክስ ተመሰረተበት

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

Getachew Shiferaw

የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው ክስ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡

በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የዕንቁ መፅሔት አምደኛ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ፣ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መስራች አባልና የጊዜያዊ አስተባባሪው አመራር እንዲሁም አዲስ ሚዲያ ተባባሪ እና በራሱ የማኀበራዊ ገፅ ብሎገር እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

የብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ሃላፊ አቶ ኢሳይያስ ወልደ ጊዮርጊስ ከስልጣናቸው ተባረሩ

ባሌቤታቸውም ከስራቸው የተነሱ ሲሆን፡ ሁለቱም በጸጥታ ሃይሎች ክትትል ውስጥ ይገኛሉ። በአቶ ኢሳይያስ ምትክ በደርግ ዘመን የደርግ ደህንነት የነበሩት ሃደራ አበራ ተክተዋቸዋል።

Esayas Woldegiorgis ,Inteliggence
ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ቅርብ የነበሩት አቶ ኢሳይያስ ወልደጊዮርጊስ መባረራቸውን ተከትሎ በሌሎች ሃላፊዎችም ሆነ ሰራተኞች ላይ ስለተወሰደ ርምጃ የታወቀ ነገር የለም።

ወ/ሮ አዜብ መስፍን ግን የአቶ ኢሳይያስን ስንብት ተከትሎ ባለፈው ቅዳሜ አሜሪካ ገብተዋል፡ ዋሺንግተን ዳላስ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ካሜራ ዕይታ ውስጥ የገቡት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ከአንድ ልጃቸው ጋር ሰለመጡብት ምክንያት በውል የታወቀ ነገር የለም።
ምንጭ፡- ኢሳት

በቦሌ ወረገኑ በሕገወጥ ግንባታ ምክንያት ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ጉዳት ደረሰ

ታምሩ ጽጌ

‹‹መንግሥት ያለምንም ርህራሔ በክረምት ጐዳና ላይ በተነን›› ቤት የፈረሰባቸው ነዋሪዎች

‹‹መንግሥት ዜጎቹን በማክበር ሕገወጥ ተግባራትን ይከላከላል›› የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

Addis ababa city

በአዲስ አበባ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ቦሌ ቡልቡላ ወረገኑ በመባል በሚታወቀውና በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች እንደሚገኙበት በተገለጸው ሥፍራ፣ ከሕገወጥ ግንባታ ጋር በተገናኘ ረቡዕ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ተጠቆመ፡፡

በአካባቢው ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ ያለምሪት ቤት የሠሩ ቁጥራቸው በርካታ (ከ20 ሺሕ በላይ መሆናቸውን ይገልጻሉ) የሚሆኑ ነዋሪዎች የሚገኙ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 12 አስተዳደር የገነባቸው ቤቶች ሕገወጥ መሆናቸውን በመግለጽ በተደጋጋሚ እንዲያፈርሱ ቢነግራቸውም፣ ‹‹ወዴት እንሂድ? በድህነት አቅማችን የሠራነውን ቤት ግምት ወጥቶለትና ካርታ ተሠርቶለት ሕጋዊ እንሁን፤›› በማለት ሲከራከሩ መክረማቸውን ነዋሪዎቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በአስተዳደሩና በነዋሪዎቹ መካከል መግባባት ሳይፈጠር ቆይቶ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች የታጀበው የወረዳው አፍራሽ ግብረ ኃይል ወደ ነዋሪዎቹ መንደር በመሄዱ፣ ከነዋሪዎቹ ተቃውሞ እንደገጠመው ተገልጿል፡፡
ነዋሪዎች አንድ ላይ በመሆን በድህነት ያቋቋሙት ጎጆ መፍረስ እንደሌለበት በመግለጽ ለመከላከል ባደረጉት እንቅስቃሴ፣ ከፀጥታ አስከባሪዎች ጋር ወደ ከረረ ግጭት በመግባታቸው ሁለቱም ወገኖች መጐዳዳታቸውን የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በወቅቱ በርካታ ጥይት የተተኮሰ በመሆኑ ቁጥራቸው ያልተገለጹ ሰዎች እንደሞቱ የተነገረ ቢሆንም፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ግን አንድም የሞተ ሰው እንደሌለ አስታውቋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አሰግድ ጌታቸው እንደተናገሩት፣ በሕገወጥ መንገድ የተገነቡ 1,040 ቤቶች አሉ፡፡ ሕገወጥ በመሆናቸው እንዲፈርሱ ተደርጓል፡፡ ቤቶቹ ሲፈርሱ በአካባቢው ግርግር ለመፍጠር የሞከሩ የነበሩ ቢሆንም፣ ነገር ግን አንድም ሰው የሞተ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡

የአካባቢው ነዋሪዎችም በወቅቱ አስለቃሽ ጭስ በመርጨት የነበረውን ግርግር ለመበተን ጥረት ሲደረግ ማየታቸውን፣ የጥይት ድምፅ እንደነበርና በርከት ያሉ አምቡላንሶች ሲመላለሱ በማየታቸው፣ የሞተ ሰው ሊኖር እንደሚችል ከመገመት ባለፈ የሞተ ሰው አለማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

ነዋሪዎቹ ጨምረው እንዳስረዱት፣ ወረዳው ሰብስቧቸው በአካባቢው ረጅም ዓመታት ለቆዩ አርሶ አደሮች ምትክ ቦታና ካሳ እንደሚሰጥ ገልጾ፣ ሌሎች ነዋሪዎች ግን በቅርቡ የመጡና በሕገወጥ መንገድ የገነቡ በመሆናቸው እንዲያፈርሱ አስጠንቅቆ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ክረምት እየገባ በመሆኑና በድህነት የቀለሷትን ጎጆ አፍርሰው የት እንደሚሄዱ ግራ በመጋባታቸው፣ መንግሥትን ለመለመን በመዘጋጀት ላይ እያሉ ባላሰቡት ቀን መጥቶ ከነንብረታቸው በግሬደር እንዳረሰባቸው ተናግረዋል፡፡
‹‹እኛ ኃይል የለንም፣ ኃይል የእግዚአብሔር ነው፣ ዜጎቹን የመንከባከብና የማስተዳደር ኃላፊነትና ግዴታ ያለበት መንግሥት በጎዳና ላይ ከበተነን እኛ ኢትዮጵያውያን ነን?›› በማለት ጠይቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የተፈጸመባቸውን በደል አይቶ ብይን እንዲሰጣቸውም ጠይቀዋል፡፡

በአካባቢው የሚገኙ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውንና ልጆቻቸውም ትምህርት ማቆማቸውን ጠቁመው፣ ‹‹የትምህርት ዘመኑ እስኪጠናቀቅና መጪው ክረምት እስከሚወጣ ቢታገሱን ምን ችግር ነበረው?›› በማለትም የተፈጠረባቸውን ሐዘን ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ1988 ዓ.ም. እስከ 1997 ዓ.ም. ግንቦት ወር ድረስ፣ በሕገወጥ መንገድ ቤት ለሠሩ ሰነድ አልባ ቦታዎች ካርታ ሠርቶ በመስጠት ሕጋዊ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ከግንቦት ወር 1997 ዓ.ም. ወዲህ የተያዙ ሕገወጥ ግንባታዎች ግን ሕገወጥ ይዞታዎች መሆናቸውን በማስታወቅ፣ ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑንም አስተዳደሩ ይናገራል፡፡

በቦሌ ወረዳ 12 ወረገኑ በሚባለው አካባቢ ስለተሠሩት ቤቶች የአስተዳደሩ መሬት ልማት ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ኃይሌ እንደገለጹት፣ ግንባታዎቹ ከ2004 ዓ.ም. ወዲህ የተገነቡና ሕገወጥ ይዞታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም አስተዳደሩ በሕገወጥ ይዞታዎች ላይ የማያወላውል ዕርምጃ እንደሚወስድ ተናግረው፣ በወረገኑ የተወሰደው ዕርምጃም ከዚህ የተለየ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

የሚዲያና የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች በኢሕአዴግ ላይ የሰላ ትችት አቀረቡ

የማነ ናግሽ

‹‹ሙስና የሥርዓቱ ባህል እየሆነ መጥቷል›› በማለት ኢሕአዴግ ላይ የሰላ ትችት ያቀረቡት የሚዲያና የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ባለፉት 25 ዓመታት ሙሉ የሚወራው ስለሙስና መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ባለፈው ዓርብ ግንቦት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. 25ኛውን ዓመት የግንቦት 20 የብር ኢዮቤልዮ በዓል አስመልክቶ ከጋዜጠኞችና ከኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ጋር በብሔራዊ ቴአትር በተደረገው ውይይት፣ ተሳታፊዎቹ ኢሕአዴግንና እሱን የሚመራው መንግሥትን ገምግመዋል፡፡ ድርጅቱ ሥልጣን ከያዘ ጊዜ ጀምሮ ስለሙስና፣ ስለኪራይ ሰብሳቢነትና በሥልጣን ስለመባለግ ቢወራም ተመጣጣኝ ዕርምጃ ሲወሰድ አልታየም በማለት ክፉኛ ተችተዋል፡፡

ለውይይቱ መነሻ የሚሆን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ፍሬሕይወት አያሌው የግምገማ ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን፣ ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት ይደበቃል፡፡ ሕዝቡ ግልጽ ሆኖለት ከተታገለው ግን እታች ተወርዶ ማቃጠል ይቻላል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ይህች አገር ፈርሳ ነው እየተሠራች ያለችው፡፡ እስካሁን ያስመዘገብናቸው ድሎችም ሊፈርሱ ይችላሉ፤›› በማለት ነበር የኪራይ ሰብሳቢነት አደጋን አስመልክተው በሰጡት ሐሳብ ጽሑፋቸውን የደመደሙት፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ፈተናው ትልቅ ነው ይላል፡፡ አይደለም ድልን ልናስመዘግብ ያረጋገጥነውም ሊበላብን ይችላል፣ ወደኋላ ሊወረውረንም ይችላል፤›› በማለት፡፡

ውይይቱን የመሩት የብሮድካስቲንግ ባለሥልጣን ኃላፊ አቶ ዘርአይ አስገዶም መድረኩን ለተሳታፊዎች ክፍት ሲያደርጉ አንዳንድ አድናቆቶች የቀረቡ ቢሆንም፣ በአብዛኛው የትችት ሐሳቦች ተንፀባርቀዋል፡፡

አቶ እንድርያስ ተረፈ አስተያየት ከሰጡት መካከል የመጀመርያው ናቸው፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ወደ አዲስ አበባ ሲገባ ‘ሌባ አይወድም’ ይባል ነበር፡፡ ዛሬ ግን ራሱ ኢሕአዴግ ሌብነት መገለጫው እየሆነ መጥቷል፡፡ 25 ዓመት ሙሉ የምናወራው ስለሙስና ነው፡፡ ሌብነት የሥርዓቱ ባህል እስከመሆን ደርሷል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹መኖር ከአቅም በላይ በሆነበት ዘመን ዛሬም የምናወራው ስለሙስና ነው፡፡ ከ25 ዓመት በኋላ ዛሬ ምን ተለወጠ? ምን አገኘንና በምን እንለካው?›› በማለት አክለዋል፡፡

‹‹ቤት አገኛለሁ ብዬ ኮንዶሚኒየም የተመዘገብኩት 97 ላይ ነበር፡፡ ዛሬ ግን ቤቶቹ ጠፉ እየተባሉ ነው፡፡ አንድ ሕንፃ ሲጠፋ ማን ተጠየቀ? ሕንፃዎቹ እስኪጠፉ መንግሥት የት ነበር?›› ብለዋል፡፡

የኪነጥበብ ባለሙያው አቶ ኃይላይ ታደሰ በበኩላቸው የቀረበው ሪፖርት ወደ ጥንካሬው ያመዘነ መሆኑን ገልጸው ነበር ትችታቸውን ያቀረቡት፡፡ ‹‹እንደ ባለሙያዎች እምብዛም ተጠቃሚ አይደለንም፡፡ አንቀጽ 29 ላይ የተቀመጡ መብቶችን እንዳንጠቀም የሚያግዱ አፋኝ ደንቦች እየተረቀቁ ይገኛሉ፡፡ ይኼ ከሴንሰርሺፕ (ሳንሱር) ተለይቶ የሚታይ አይደለም፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ኃይላይ ትችታቸውን በመቀጠል፣ ‹‹ኢሕአዴግ ከአፄ ኃይለ ሥላሴና ከደርግ ጋር ራሱን እያወዳደረ ዕድገት አስመዘገብኩ ሲለኝ ያንስብኛል፣ ይወርድብኛል፤›› በማለት ድርጅቱ እንደ መንግሥት በራሱ ከያዘው ዕቅድ አንፃር፣ ከሰፊው ሕዝብ ተጠቃሚነት አንፃር መመዘን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡

‹‹ስብሰባና በዓል ታበዛላችሁ፡፡ ይኼ ሁሉ የተከፈለው መስዋዕትነት በተግባር ቢለካ አንድ ሰው ሌባ ከሆነ ሌብነቱን በሕዝብ ፊት አጋልጡት፡፡ አለበለዚያ ቁርጠኝነቱ ያላችሁ አይመስለንም፡፡ ከአንድ ቦታ አንስታችሁ ሌላ ቦታ ትሾሙታላችሁ፡፡ ለእኔ ቀልድ ነው የሚመስለኝ፡፡ ተግባብቶ ለውጥ የሚያመጣ ተግባር እያካሄዳችሁ አይመስለኝም፤›› በማለት ቀጥለዋል፡፡

‹‹አንድ ለልማት ተነሽ የሆነ አካባቢ ስታፈርሱትና ስታነሱት በጣም ነው የምትጣደፉት፡፡ አጥራችሁ ስታስቀምጡ ግን ረዥም ጊዜ ነው፡፡ አራት ከንቲባዎች ሲቀያየሩ ታጥሮ የተቀመጠ ቦታ የለም ወይ?›› በማለት የፍትሕ ማጣትና ሌሎች ማሳያዎችንም አቅርበዋል፡፡
ሕዝቡ የዕድገቱ ተጠቃሚ አለመሆኑንና ከአቅሙ በላይ በኑሮ እየተሰቃየ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ ‹‹ዕድገቱ ጤነኛ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ጥቂት ከጉምሩክና ከሌሎች ባለሥልጣናት ጋር የሚመሳጠሩ ዜጎች ያገኙትና የተሠሩ ነገሮች እንደ ዕድገት ከተለኩ እኔ ትክክል አይመስለኝም፡፡ የሕዝቡ ቁጥር መጨመርና ዘመኑ የደረሰበት ቴክኖሎጂ መለኪያው ያ ከሆነ አይገባኝም፤›› በማለት መንግሥት ባልተሠሩ ነገሮች ላይ ትኩረት አድርጎ እንዲንቀሳቀስ አሳስበዋል፡፡ ‹‹ችግሮቹ ያመዝናሉ፤›› በማለት፡፡

‹‹ሥርዓቱ ውስጥ በተደራጀ በቡድን አንዱ ሌላውን የሚጠልፍበት ሁኔታ የለም? ከሕዝብ የተደበቀ ነው? አይመስለኝም፡፡ ራሳችሁን ፈትሹ፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን የፈጠራችሁት እናንተ ናችሁ፡፡ ከሕዝብ የተደበቀ ነገር የለም፡፡ የክፍለ ከተማ ሹማምንቶች ቪ-8 አይደለም የሚያሽከረክሩት? ቪ-8 የሚነዳባት አገር ናት እንዴ ይህች አገር? ታክስ አልከፈልክም ተብሎ ግን ዘብጥያ ይወርዳል፤›› በማለት አስተያየታቸውን የቀጠሉት አቶ ኃይላይ፣ ‹‹ትግሉን ረስታችሁታል፡፡ ከተከፈለው መስዋዕትነት አንፃር ያማል፡፡ ስለዚህ የዚች 25 ዓመታት ስኬት እንደ ትምክህት እንድትወስዷት አልፈቅድም፡፡ መውደቂያችሁ እሱ ነው የሚመስለኝ፡፡ በ1993 ዓ.ም. ታደስን ትላላችሁ፡፡ እሱ ህዳሴ አልነበረም፡፡ መታደስ ያለባችሁ ዛሬ ነው፤›› በማለት ሐሳባቸውን ቀጠሉ፡፡

የመድረክ መሪዎችም ተሳታፊዎችም በፅሞና እያዳመጡ ነው፡፡ አቶ ኃይላይ ግን ትችታቸውን ቀጥለዋል፡፡ ‹‹ለምሳሌ ያ ሁሉ መስዋዕትነት የተከፈለበት አካባቢ ምን ይመስላል? ዛሬ ከማንም የተደበቀ አይደለም፤›› በማለት አንዳንድ የትግራይ ክልል አካባቢዎችን በመጥቀስ በትግል ጊዜ የተጠቀሙበት መንገድ ባለበትና አህያም ተጭና የማትሄድበት ጊዜ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሌላው አስተያየት ሰጪ የዓባይ ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ጋዜጠኛ ሲሆን፣ ውይይቱ እንደተለመደው የፕሮግራም ማሟያ እንዳይሆን ሥጋቱን ገልጾ አስተያየቱን ጀመረ፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት የተሠሩ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ገልጾ፣ ‹‹የተሠሩ ትልልቅ ነገሮችን የሚሸፍኑ የማይረቡ ትንንሽ ስህተቶች ትሠራላችሁ፤›› ሲል በሕዝቡና በመንግሥት በኩል አሉ ያላቸውን ችግሮች ተናግረዋል፡፡ ‹‹በአሁኑ ጊዜ ወረዳዎችና ቀበሌዎች እኮ ትልልቅ መንግሥታት ናቸው፤›› በማለት የተዘረጋው ሥርዓት ለሌብነትና ለስርቆት የተመቸ መሆኑን ተናግሯል፡፡
በጋዜጠኛው ሌባ ለማስያዝ የሚደረግ ጥረት እንደማይሳካና ፍርድ ቤት ተሂዶም ፍትሕ እንደማይገኝ ገልጾ፣ ‹‹እንዲያው ሳስበው ዛሬ ፍትሕ ያለው በኢቢሲ የሚተላለፈው ‹‹ችሎት›› ፕሮግራም ላይ ብቻ ነው፤›› በማለት ተሰብሳቢዎችን ፈገግ አሰኝቷል፡፡ ‹‹ትልቅ ስህተት የምለው፣ የኢሕአዴግ ትልቅ ስህተት የምለው የቀበሌና የወረዳ አስተዳደሮች የፓርቲው አባል በመሆናቸው ነው፡፡ ከአንድ ቦታ በሌብነት የተባረረ ሌላ ቦታ ተቀይሮ ተሹሞ እናገኘዋለን፡፡ ደንበኛ የአሠራረቅ ልምድ ይዞ ሄዷል፡፡ እዚህ ቀበሌ ሌባ የነበረ ሰው እዚያ ሲሄድ ወንበዴ ይሆናል፡፡ ማንም የማይመልሰው ወንበዴ፡፡ ከዚህ በኋላ ያፈጠጡ ሌቦች እንዲሆኑ እያደረጋችኋቸው ነው፡፡ የፓርቲ አባል ስለሆኑ፡፡ በእኔ እምነት ይኼ ሁሉ የፓርቲ አባል አያስፈልጋችሁም፡፡ የፓርቲ ቁጥር አይደለም ሥራ የሚሠራው፡፡ አስተሳሰቡ ያልተለወጠ ሰው ለውጥ አያመጣም፤›› በማለት አንድ ምሳሌ አነሳ፡፡

‹‹በሌላ እንዳይያዝብኝ ስለፓርቲ አይደለም እያወራሁ ያለሁት፤›› በማለት ቀጥሎ ያቀረበው ምሳሌ በ1997 ዓ.ም. ምርጫ ቀንደኛ የቅንጅት ደጋፊ የነበረ ሰው፣ የኢሕአዴግ ደጋፊ ናቸው ብሎ ያሰባቸው ብዙ ሰዎችን ጉዳት እንዳደረሰባቸው ተናግሯል፡፡ ‹‹አሁን ብትሄዱ ወረዳውን አልነግራችሁም ራሳችሁ ድረሱበት፤›› ካለ በኋላ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ውስጥ የአንድ ወረዳ የፀጥታ ኃላፊ እንደሆነ በመግለጽ፣ ‹‹ያን ጊዜ ያላዳረሳቸውን አሁን ለማዳረስ እንዲመቸው ይሁን እኔ አልገባኝም፡፡ ይኼ ሰው በሌላ ማልያ እንዲጫወት ተፈቅዶለታል፡፡ በትክክል ሥራቸውን ሲሠሩ የነበሩ ሰዎች ደግሞ ችግር ደርሶባቸው ሌላ ችግር ላይ የወደቁ አሉ፤›› በማለት እንዲህ ዓይነት ችግሮች እንዲስተካከሉ አሳስቧል፡፡

እንደ ጋዜጠኛ በ2004 ዓ.ም. ተንዳሆ መሄዱን አስታውሶ ቦታው ላይ የነበረው ሥራ የሚያስደስት እንደነበር ይናገራል፡፡ ‹‹25 ሺሕ ቶን ስኳር ማምረት ይችል ነበር፡፡ በአፍሪካ ሁለተኛ መሆን ይችል ነበር፡፡ ያኔ መጠናቀቅ ነበረበት፡፡ ዛሬም ድረስ ግን አልተጠናቀቀም፡፡ ስኳር ፋብሪካው ሲወድቅ በሒደት ነው፡፡ በአንድ ጊዜ ግንድስ አላለም፡፡ በአንድ ጊዜ ግንድስ ቢል ይሰማ ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ነው ዛሬ የተገነደሰው፡፡ የት ነበራችሁ? 88 ሕንፃዎች ጠፉ ሲባል የት ነበራችሁ? የተረከበውና ያስረከበውን የት ገቡ? ምን ዓይነት ሰዎች ናቸው ፈርመው ያስረከቡት? ስለዚህ ችግሮቹ በአንድ ጊዜ የመጡ አይደሉም፡፡ ፀረ ሙስና ጠንካራ ነው ስትሉን ሳቄ ነው የሚመጣው፡፡ የሚከሰው የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ነው፡፡ ፀረ ሙስና ይዞ የሚለቃቸው ሰዎች አሉ እሱም ተከፋይ ነው፤›› በማለት ጋዜጠኛው ምሳሌዎችን በመደርደር ወቀሳውን ደርድሯል፡፡

ወ/ሮ ፍሬሕይወት በሰጡት ምላሽ ያቀረቡት ሪፖርት ሚዛኑ የጠበቀ መሆኑን ተናግረው፣ የቀረቡትን ቅሬታዎች ማጣራት ያስፈልግ ይሆናል በማለት አልፈዋቸዋል፡፡

የኪራይ ሰብሳቢነት ምሽግ የተባሉ ዘርፎች ተለይተው በዚያ መሠረት ዕርምጃ እየተወሰደ እንደሆነ፣ እያንዳንዱ ተቋም በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ የሚገመገምበት ቋሚ አሠራር መዘርጋቱን ተናግረዋል፡፡ ከቀበሌ ጀምሮ ላይ ያሉት ዥንጉርጉር አሠራሮች መስተካከል እንዳለባቸው አስረድተዋል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን በተመለከተ ግን፣ ‹‹መንግሥት ሊፈጥረው አይችልም፡፡ ሕዝብን አገለግላለሁ የሚል መንግሥት ሙስናን ሊፈጥር አይችልም፤›› በማለት ተመጣጣኝ ዕርምጃ አይወሰድም የሚለውን አልተቀበሉትም፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች ግን መንግሥትን ጨምሮ የማይረባ ሥራ እንደሚሠራ ተቀብለዋል፡፡

‹‹ዋናውን ጉዳይ ግን መንግሥት ሕዝባዊ ነው፣ ያነሳችኋቸው ችግሮች የሉም ማለት አይቻልም፣ ጨለማ ግን አይታየኝም፤›› ብለዋል፡፡
አቶ ዘርአይ በሰጡት የማጠቃለያ ሐሳብ፣ ‹‹ሥርዓቱ 100 ሺሕ፣ 200 መቶ ሺሕ መስዋዕትነት ተከፍሎበት የመጣ ነው፡፡ ሥርዓቱ በቃኝ ይኼን ሠርቼያለሁ ብሎ ከቆመ የሞተ ነው ማለት ነው፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ የራሱን ሌቦችም እየቆረጠ የሚጥል ነው፡፡ ታጋይ የነበሩ በኃላፊነት ላይ ሆነው ሲባልጉ ቆርጦ የሚጥል ቆራጥ ነው፡፡ ኢሕአዴግ እንደ ኢሕአዴግ ሌባ አይደለም፡፡ አሁንም ቦታው ላይ ነው ያለው፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡

በቅርቡ በጋምቤላ በተፈጸመው ጥቃትና በኤርትራ በተፈጸሙ ተደጋጋሚ ጥቃቶች ላይ ዕርምጃ ለምን አይወሰድም ተብሎ ጥያቄ ቀርቧል፡፡ አቶ ዘርዓይ፣ ‹‹የኤርትራ መንግሥት በ1993 ዓ.ም. አይደለም የገደልነው፡፡ አሁን ነው የገደልነው ጦርነት ባለመግጠም፤›› በማለት ሐሳባቸውን ደምድመዋል፡፡ ከዚህ ውጪ የመንግሥት ሚዲያን በተመለከተ በርከት ያሉ ትችቶች ቀርበዋል፡፡ ሚዲያው ራሱ ነፃና ሳይሆን የሕዝብ ሳይሆን፣ ሚዲያ ሳይያዝ ሙስናን እንዴት መታገል ይቻላል የሚሉ ጥያቄዎችም ቀርበዋል፡፡

ባለፈው ዓመት ሕወሓት 40ኛ ዓመቱን ሲያከብር አርቲስቶችና ጋዜጠኞች ወደ ድርጅቱ ታሪካዊ ቦታዎች እንዲሄዱ ባደረገበት ወቅት፣ ለድርጅቱ ሹማምንት ተመሳሳይ ጥያቄዎች ቀርበው እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ