Category Archives: News

በሊቢያ ዓለም አቀፉ አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው አሸባሪ ድርጅት 28 ኢትዮጵያውያንን በሊቢያ መግደሉን አስታወቀ

በኢራቅና በሶሪያ በሚፈፅማቸው አሰቃቂ ድርጊቶች የሚታወቀው አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው አሸባሪ ድርጅት አካል ዛሬ ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. 28 ኢትዮጵያውያንን በለመደው አሰቃቂ ግድያ መፈፀሙን የሚገልፅ ቪዲዮና ምስል ለቋል፡፡ 29 ደቂቃ የፈጀው ቪዲዮ መረጃ መሰረት 12ቱ በምስራቃዊ ሊቢያ ባህር ዳርቻ አንገታቸውን ሲቀላ፤ከ16 ያላነሱትን ደግሞ በደቡባዊ ሊቢያ በረሃ ላይ በጥይት ደብድቦ መግደላቸውን ይፋ መደረጉን ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡ ቡድኑም አሰቃቂ ግድያውን ሲፈፅም የጠላታችን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የመስቀሉ ተከታዮች የሚል ግልፅ ፅሑፍና ንግግር አድርጓል፡፡

ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ስለጉዳዩ ከሮይተርስ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ለቀረበላቸው ጥያቄ በቡድኑ የተገደሉት ኢትዮጵውን ስለመሆናቸው በግብፅ ከሚገኘው የኢትዮጵ ኤምባሲ ማረጋገጫ አላገኘንም የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡ አሸባሪ ቡድኑ ግድያውን የፈፀመው ሊቢያ ውስጥ እንጂ ግብፅ እንዳልሆነ ይታወቃል፡፡ የሟቾችም የቪዲዮ ምስል ቡድኑ ከገለፀው በተጨማሪ የተለመደው ኢትዮጵያዊ ገፅታ በግልፅ ይታያል፡፡ ቡድኑም ግድያውን የፈፀመበትን ሲናገር ሟቾቹ የነበሩትን የክርስትና ኃይማኖት ክደው እስልምናን እንዲቀበሉና በሊቢያ ለሚገኘው የአሸባሪው ቡድን አካል ልዩ ግብር ቢከፍሉ እንደሚለቀቁ የቀረበባቸው አስገዳጅ ጥያቄ ባለመቀበላቸው እርምጃውን መውሰዱን አስታውቋል፡፡

Ethiopian killed by ISIL

ቡድኑ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ መልኩ ከ30 ያላነሱ የግብፅ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችን መግደሉን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ፤ ግብፅ ብሔራዊ የሀዘን ቀን በማወጅ በሊቢያ የቡድኑ ይዞታ ነው በተባለ ቦታ በአየር ኃይሏ ተደጋጋሚ ድብደባ በማድረግ ፈጣን የአፀፋ መልስ መስጠቷ ይታወቃል፡፡ አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው ይህ አሸባሪ ቡድን በኢራቅና በሶሪያ በተመሳሳይ መልክ የበርካታ ክርስቲያኖችን እና ከሱ ወገን አይደሉም ያላቸው ሙስሊሞች ላይ ተመሳሳይ አሰቃቂ ግድያ መፈፀሙና አሁንም በዚህ ተግባሩ ላይ መሆኑ ይታወቃል፡፡

በተያያዘ ዜና አሁንም አሸባሪ ቡድኑ በቅርብ ከሚገኝበት ሊቢያ ከ90 በላይ ኢትዮጵያውያን ተሸሽገው የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ መሆኑን እና፤ ተደብቀው ምግብ ሳይበሉ ከተቆለፈባቸው 3 ቀናት እንደሞላቸው የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከ40 የማያንሱ ኢትዮጵውያን በዛው ሊቢያ የወደብ ከተማ በሆነችው ትሪፖሊ ወደ አውሮፓ ለመሻገር መርከብ በመጠባበቅ ላይ ሲሆኑ፤ በስፍራው በርካታ ኢትዮጵውን ሴቶችና ህፃናትም እንደሚገኙበትና በአቅራቢያቢያው የአሸባሪው ቡድን አካላት ስለሚንቀሳቁ ስጋት ላይ በመውደቃቸው እነሱም የአስቸኳይ የድረሱልን ጥሪ ማሰማታቸው ታውቋል፡፡በትናንትናው ዕለትም ከዚህ ከትሪፖሊ ወደ አውሮፓ 700 አፍሪካውያንን ስደተኞች የያዘች መርከብ መስጠሟን እና እስካሁን በአውሮፓ የነፍስ አድን ሰራተኞች የ28 ሰዎች ህይወት ብቻ ማትረፍ መቻሉ የተዘገበ ሲሆን፤ ተጓዦች ውስጥ ኢትዮጵያውያንም እንደሚኖሩበት ይገመታል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በየመን ባለው ጦርነት ምክንያት ባለፈው መጋቢት 2007 ዓ.ም. በስደተኛ መጠለያ ያሉ 46 ኢትዮጵያውን በሳውዲ ዓረቢያ የቶር አውሮፕላን መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ በርካታ ኢትዮጵያውያን የሚታደጋቸው አጥተው አሁንም በየመን ስቃይ ላይ በመሆናቸው የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ ይገኛሉ፡፡

በደቡብ አፍሪካ የ7 ሰዎችን ህይወት ያጠፋው የጥላቻ አመፅ ወደሌሎች ከተሞችም መዛመቱ እየተነገረ ነው

በደቡብ አፍሪካ በያዝነው ሚያዝያ ወር 2007 ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ በወደብ ከተማዋ ደርባን ጥቁር የውጭ አፍሪካውያን ነጋዴዎች ላይ የተቀሰቀሰው ጥላቻ የ6 ሰዎች ህይወትን እንዳጠፋ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያ ዘገባ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በሌሎች የአፍሪካ ጥቁር ዜጎች ላይ የተጀመረው ጥላቻ ከደርባን ከተማ ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የተዛመተ ሲሆን፤ ትናንት ቅዳሜ ጆሃንስበርግ ከተማ ላይ አንድ ሞዛምቢካዊ መግደላቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡

south africa 3

በጥቃቱ በብዛት ሰለባ የሆኑት የኢትዮጵያ፣ የሶማሌ፣የናይጄሪያ፣የሞዛምቢክ፣የዙምባቤና የማላዊ ዜጎች የገለፀ ሲሆን፤ ከተገደሉት መካከልም 3ቱ ኢትዮጵውን መሆናቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጥቃቱ ምክንያት ኬንያ፣ ማላዊ እና ዙምባቤ ወዲያውኑ ዜጎቻቸውን ከደቡብ አፍሪካ ለማስወጣት የሞከሩ ሲሆን፤ በተለይ ዙምባቤ እና ቦትስዋና ዜጎቻቸው በሰላም እስኪወጡ ድረስ ከጥቃቱ ለመከላከል ልዩ የጦር ኃይል ወደስፍራው መላካቸው ተሰምቷል፡፡ ሞዛምቢክ በበኩሏ ዜጎቿና የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ሌሎች ጥቁር አፍሪካውያንን ለመታደግ ድንበሯን የከፈተች ስትሆን፤ ጥቃቱ ወዳለበት ስፍራ ድረስ በመሄድ ዜጎቻቿን ለመታደግ ትራስፖርትና አስፈላጊውን ነገር ሁሉ ስታቀርብ ተስተውሏል፡፡

በተለይ ናይጄሪያና የሶማሊያ መንግሥት ድርጊቱን ከማውገዝ አልፎ፤ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት የተፈጠረውን ቀውስ በአስቸኳይ እንዲቆጣጠርና እንዲያቆም ማስጠንቀቂያ ጠይቀዋል፡፡ በናይጄሪያ በዓለም አቀፍ አሸባሪነት የተፈረጀው ቦኮ ሃራም በበኩሉ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት በናይጄሪያውያን ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በ24 ሰዓታት ውስጥ ማስቆም ካልቻለ በምዕራብ አፍሪካ ባሉ የደቡብ አፍሪካ ኤምባሲና ዜጎቿ ላይ እርምጃ እንደሚወስድ ከመዛት በተጨማሪ የደቡብ አፍሪካዋን ጆሃንስ በርግን ባግዳድ አደርጋታለሁ ሲል ማስጠንቀቁ አነጋግሯል፡፡

south africa2

የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ በደቡብ አፍሪካ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አገኘሁት ባለው መረጃ መሰረት በጥቃቱ የሞተው አንድ ኢትዮጵዊ መሆኑን በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮረፖሬሽን አስታውቋል፡፡

በደርባን የተቀሰቀሰው በተለምዶ የውጭ ሀገር ዜጋን የመጥላት “ዜኖፎቢያ” ዘመቻ በአሁን ሰዓት ጋብ ያለ ቢመስልም፤ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች መዛመቱንና ችግሩ ከከተማ ውጭ የሚሰሩ ሌሎች ጥቁር የአፍሪካ ዜጎች አደጋ ላይ መሆናቸውንና እስካሁንም የደረሰባቸውን ችግር ለማወቅ እንዳልተቻለም ተጠቁሟል፡፡ ድርጊቱንም የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ፕሬዘዳንት ጃኮብ ዙማና የተለያዩ የሀገሪቱ ዜጎች በይፋ ቢቃወሙም፤የአመፁ ዋና ቀስቃሽ ተደርገው የተወሰዱት በደርባን ያሉት የዙሉ ጎሳ ንጉስ ጉድዊል በወቅቱ በአንድ መድረክ ባደረጉት የጥላቻ ንግግር መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የፕሬዘዳንቱ ጃኮብ ዙማ ልጅም ድርጊቱን የሚያበረታታ ነገር ከዚህ በፊት በሌላ መድረክ መናገራቸው እየተጠቆመ ይገኛል፡፡ በጥቃቱም ሁለት ጥቁር አፍሪካውያን ከነ ህይወታቸው በደቡብ አፍሪካውያን የተቃጠሉ ሲሆን ሌሎቹ ስለት ባላቸው መሳሪያዎችና በድንጋይ ተደደብድበው መገደላቸው ታውቋል፡፡

በተቀሰቀሰው የጥላቻ አመፅም የኢትዮጵያውንን ጨምሮ የበርካታ የጥቁር አፍሪካውያን ሱቆች ተዘርፈዋል፣ ከዝርፊው የተረፉትም ተቃጥለዋል፡፡ ድርጊቱን ዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ቢያወግዘውም ወደሌሎች ከተሞች መዛሙቱ አሁንም ስጋትን ጭሯል፡፡ በርካቶችም የንግድ ሱቆቻቸውን ጥለው በተለይ በደርባን ከተማ ጊዘየያዊ የስደተኛ መተጠለያ ጣቢያና በፖሊስ ጣቢያዎች እንደተጠለሉም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ በጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በተፈፀመ ተመሳሳይ ጥቁር አፍሪካውያን ስደተኞች በተሰማሩበት የንግድ ስራ ጥላቻ ከ60 ያላነሱ ሰዎች መገደላቸውንና የበርካቶች ሱቆችና ሌሎች የንግድ ተቋማት መዘረፋቸውን መረጃዎች አመለክተዋል፡፡

ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን አነስተኛ የንግድ ሱቅ በሚሰሩ አፍሪካውያን ላይ በጥላቻ ቢዘምቱም፤ለዛሬው ነፃነታቸው ያበቋቸው በዋናነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች አፍሪካውያን ትልቅ ሚና እንደነበራቸው አይዘነጋም፡፡

በኬንያ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ በአል-ሸዓባብ በተፈፀመ ጥቃት የሟቾች ቁጥር 147 ደርሷል

Garissa-University-College attack

በኬንያ ሰሜን ምስራቅ  በምትገኘው ጋሪሳ የሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ ሐሙስ ጠዋት መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ግቢ ውስጥ በመግባት በከፈተው ጥቃት ሁለት የዩኒቨርስቲው ጠባቂዎችን፣ሶስት የፖሊስ ኦፊሰሮችን እና 142 ተማሪዎች በአጠቃላይ 147 ሰዎች መገደላቸውን የሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ጆሴፍ ነካይዘሪ ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርገዋል፡፡ በጥቃቱ ከሟቾች በተጨማሪ 79 ተማሪዎች የቆሰሉ ሲሆን፤ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቀ በታጣቂው ኃይል ታግተው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡

ይህንንም ተከትሎ የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ በፖሊስ እጥረት ምክንያት አላስፈላጊ ዋጋ መክፈል የለብንም በማለት ከፍተኛ የፖሊስ ቁጥር እንዲጨምርና ወደስልጠና እንዲገቡ  ትዕዛዝ መስጠታቸውን አደጋው በደረሰ ቀን ባስተላለፉት የሀዘን መግለጫ ላይ አስታውቀዋል፡፡ የሶማሊው ታጣቂ አልሸዓባብ በኬንያ ንፁሃን ላይ የሚያደርሰው ጥቃት እየተበራከተ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በናይሮቢ ዌስትጌት የንግድ ማዕከል ውስጥ በፈፀመው ጥቃት 67 ሰዎች መግደሉ ይታወሳል፡፡ ከዛም በኋላ የሐሙሱን የጋሪሳ ዩኒቨረድስቲ ኮሌጅን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በርካታ ጥቃቶችን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ የጥቃቲ ኢላማዎችም ሙስሊም ያልሆነ ማንኛውም አካል ሲሆን፤ በተለይ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃቱ መጨመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

እንደ ሀገሪቱ ፖሊስ መጃ መሰረት ከ2004 ዓ.ም. እስከ ታህሳሥ 2007 ዓ.ም. ብቻ የአልቃይዳ ክንፍ በሆነው በሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አልሸዓባብ የተገደሉ ኬኒያውያን ቁጥር 312 ደርሶ ነበር፡፡ በጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ የተፈፀመውን የጅምላ ግድያ ጨምሮ በሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ የተገደሉ ኬንያውያን  459 ደርሷል፡፡

Garissa-University-College attack

በዩኒቨርስቲ ኮሌጁ ተማሪዎች ላይ ታጣቂው  ከፈፀመው የጅምላ ግድያ በኋላ አራት የታጣቂ ቡድኑ አባላት ሲገደሉ፣ አምስት ተጠርጣሪ የቡድኑ አባላት በቁጥጥር  መዋላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ውስጥ የተገደሉ ሰዎችን ማንነት ለመለየትና ወደ የቤተሰቦቻቸው ለመላክ አሰከሬናቸው ወደ ናይሮቢ መላኩም ታውቋል፡፡

ጋሪሳ ከናይሮቢ ሰሜን ምስራቅ 367 ኪሎ ሜትር ስትርቅ፤ ከኬንያ ሶማሊያ ድንበር ያላት ርቀት  ደግሞ 147 ኪሎ ሜትር ነው፡፡ የታጣቂ ቡድኑ በተመሳሳይ መልኩ በዩጋንዳ የትምህርት ተቋማት ላይ ጥቃት ለመፈፀም ዕቅድ እንዳለው ተጠቁሞ፤ የዩጋንዳ የደህንነትና ፀጥታ አካላት የሀገሪቱን ደህንነት ከመቼውም ጊዜ በላቀ በተጠንቀቅ ላይ ሆነው እንዲጠብቁ መደረጉንም የዩጋንዳ ከፍተኛ ፖሊስ ኦፊሰርን ጠቅሶ የአውስትራሊያው ኤቢሲ ዘግቧል፡፡

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በተለይ ከጥቃቱ በስተጀርባ ዋና አቀናባሪና በጋሪሳ ከተማ የእስላማዊ ትምህርት ቤት መምህር እንደነበር የተጠቆመው መሐመድ መሐሙድ የገደለ ወይም ያለበትን የጠቆመም እንዲሁም ይዞ ለሚያስረክብ የኬንያ መንግሥት ፖሊስ 215 ሺህ የአሜሪካን ዶላር (200 ሚሊዮን የኬንያ ሽንልንግ)እንደሚሰጥ ቃል ገብቷል፡፡ ጥቃቱን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋነ ፀሐፊ ባን ኪ ሙንን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ማኀበረሰቦች ያወገዙት ሲሆን፤ ታጣቂው አልሸዓባብ በበኩሉ ድርጊቱ የፈፀመው ከኬንያ ጋ ጦርነት ውጊያ ላይ ስለሆንን ነው ማለቱን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ 28 ቀን ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

ከግራ ወደቀኝ  ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

ከግራ ወደቀኝ ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ትናንት መጋቢት 21 አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ እነ ብርሃኑ ተክለያሬድን ‹‹ለግንቦት 7 አባላትን መልምለው ወደ ኤርትራ በመላክና ቡድኑን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ተይዘዋል›› ብሏል፡፡

ጠበቃው እነ ብርሃኑ ተ/ክለያሬድ ለግንቦት ሰባት ሲመለምሉም ሆነ አባል ሲሆኑ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ እንደሌለ በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምመረምራቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ሌሎች የምንይዛቸው ግብረ አበሮችም አሉ፡፡ መረጃ ያጠፉብናል፡፡›› በሚል ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆ 28 ቀን ተፈቅዶለታል፡፡ ሚያዚያ 19 ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡

ፖሊስ ሌሎች ሰዎች ይዘውት የተነሱትን መሳሪያ በማሳየትም እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ እንደነበር ለማሳየት በመረጃነት አቅርቧል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹የማህበራዊ ሚዲያ ላይ ምርመራ ለማድረግና መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተጠርጣዎቹን ማሰር ተገቢ አልነበረም፡፡ ሌሎች ሰዎች የያዙትን መረጃ እነሱን ለመክሰስ መጠቀም ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ ተቃውመዋል፡፡

በሌላ በኩል ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ የታሰረበት ቤት መብራት ስለማይጠፋ አይኑ ላይ ለከፍተኛ ችግር እንዳደረሰበት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ለ15 ደቂቃ ፀኃይ እንዲሞቁ ከሚፈቀድላቸው ውጭ ወደ ከታሰሩበት ቤት ውጭ መውጣት እንደማይፈቀድላቸውና ቤተሰቦቻቸውም እንዲጠይቋቸው እየተደረገ አለመሆኑን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡

የዞን9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን የአቃቤ ህግ ምስክሮች ቃል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በ19ኛው ወንጀል ችሎት እየታየ ያለው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የክስ ጉዳይ ለሁለተኛ ቀን ምስክሮችን አሰምቶ በአወዛጋቢ መልኩ ለሚቀጥለው መጋቢት 30 ቀጠሮ ይዞ ተጠናቋል፡፡

ከእለቱ ዋዜማ ቃለ መሃላ ፈጽመው ሳይሰሙ የቀሩት ምስክሮች የተሰሙ ሲሆን ቃለ መሃላ በቀደመው ቀን በመግባታቸው ቀጥታ ወደ ምስክርነት ቃላቸው ተገብቷል፡፡ በሃያ ስድስተኛው የፍርድ ቤት ውሎ ተሰሙት ምስክሮች

7ተኛ ምስክር -ተስፋዬ መንግስቴ የመሰከሩት አቤል ዋበላ ላይ ሲሆን ከመንገድ ላይ ፓሊስ ሲፈትሹ አንዲታዘቡ ጠይቋቸው ቤቱ እና መስሪያ ቤቱ የተገኘው ሲዲ መጽሄቶች እና መጸሃፍት ላይ ሲገኙ አይቼ ፈርሜያለው አቤልም ፈርሟል ብለዋል፡፡

8ተኛ ምስክር- አቶ በረከት ጌታቸው በተመሳሳይ መንገድ ላይ ፓሊስ ታዘቡልኝ ብሎ የበፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ መታዘባቸውን በፍቃዱ የፈረመባቸው ነገሮች ላይም መፈረማቸውን ተናግረዋል፡፡ ጽሁፎቹ አማርኛ እና አንግሊዘኛ ከመሆናቸው ውጪ የሚያስታውሱት ይዘት አንደሌለ ተናግረዋል፡፡

9ኛ ምስክር – አቶ አንድነት ስሜ ይባለሉ አጥናፍ ብርሃኔ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ቤቱ የተገኙ ወረቀቶች ላይ እሱም ፈርሟል አኔም ፈርሜያለው ብለዋል፡፡ የተገኙት ወረቀቶች አማርኛ እና እንግሊዘኛ ሲሆኑ ሴኩሪቲ ኢን ኤቦክስ የሚል መጽሃፍ አለበት ብለዋል፡፡ በይዘቱ ላይ አቃቤ ህግ አንዲመሰክሩ ቢጠይቅም ጠበቆች በይዘቱ ላይ ለመመስከር ስላልተመዘገቡ አንዳይመሰክሩ ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ እንዲመሰክሩ ቢፈቅድም ምስክሩ ምንም ይዘት አንደማያስታውሱ ተናግረዋል፡፡

10ኛ ምስክር -አቶ ታምራት ዓለሙ የሚባሉ ሲሆን አቤል ዋበላ ቤት ሲፈተሽ እንደነበሩ በመግለጽ ምስክርነታቸውን አሰምተዋል፡፡ አቤል የፈረመባቸው ነገሮች ላይ ፈርመናል ያሉ ሲሆን የነጻነት ጎህ ሲቀድ መጽሃፍ እስልምና በኢትዬጲያ የሚል መጽሃፍ አዲስ ጉዳይ መጽኄቶች አና እምነት እና ተስፋ በኢትዬጲያ የሚሊ ጽሁፎች ተገኝተዋል፡፡ ሲዲም ተገኝቷል ብለዋል፡፡ የፍተሻውን ቀን ሚያዝያ 11 ነው ብለዋል፡፡ ( ጦማሪ አቤል የታሰረው ሚያዝያ 17 አንደሆነ ይታወቃል)

11ኛ ምስክር አቶ ፋሲል ግርማ ሲሆኑ በፍቃዱ ሃይሉ ቤት ሲፈተሽ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ቤት ውስጥ ተገኙት እቃዎች እና ሰነዶች ላይ ተከሳሹ ሲፈርም እኛም ፈርመናል ብለዋል፡፡ የተገኙትን ሰነዶች ብዛትና ይዘት እንደማያሰታውሱም ተናግረዋል፡፡

12ኛ ምስክር አቶ ደረጀ አበበ የኮንስትራክሽን እና ቢዝነስ ባንክ ባልደረባ ሲሆኑ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ቢሮ ሲፈተሽ ፓሊስ ታዘቡ ብሏቸው አንደነበሩ እና ተገኙት ወረቀቶች ላይ ፈርመው ቢሮውን ዘግተው መውጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የፈረሙበትን ወረቀት ይዘት የማያስታውሱት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

13ኛ ምስክር አቶ አክሊሉ ሃይለማርያም ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ላይ የመሰከሩ ሲሆን ስሙን ብቻ ነው የማስታውሰው በማለት ያዬትን ተናግረዋል፡፡ ፈረንሳይ ለጋሲዬን አካባቢ ያለው ቤቱ ሲፈተሽ የተገኙ አማርኛ እና እንግሊዘኛ ጽሁፎች የግል ማስታወሻዎች ሲም ካርድ እና መጽሃፍት የተገኙ ሲሆን ሁሉም ላይ በፍቃዱም ሲፈርም እኔም ፈርሜያለሁ ብለዋል፡፡

በ14ኛ ምስክርነት አቶ የማነ ብርሃኔ የተባሉ ግለሰብ ቀርበው የነበር ቢሆንም አቃቤ ህግ ‹የተለየ ነገር አያስረዱልኝም› በሚል ምስክሩ ሳይደመጡ እንዲመለሱ ፍርድ ቤቱን ጠይቆ ምስክርነታቸው ሳይሰማ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ አጠቃላይ 41 ምስክሮችን እንዳስመዘገበ በመጥቀስ ትናንት ካስመዘገባቸው 17 ምስክሮች ውጭ ሌሎቹን ፖሊስ በአድራሻቸው ፈልጎ እንዳጣቸው በመግለጽ ማቅረብ አለመቻሉን አስረድቷል፡፡ በሌላ በኩል ግን 8ኛ፣ 9ኛ እና 27ኛ ላይ አቃቤ ህግ ያስመዘገባቸው ምስክሮች መጥሪያ ደብዳቤ ደርሷቸው እንዳልተገኙለት ገልጹዋል፡፡

Ethiopia-Federal-High-Court-300x194

ፍርድ ቤቱ የጠበቆችን (የተከሳሾችን) አስተያየት ጠይቆ ነበር፡፡ በዚህም ጠበቆቹ አሉ የተባሉትን ምስክሮች ፌደራል ፖሊስ ሌሎችን በአድራሻቸው ፈልጎ ማቅረብ ይገባው እንደነበር፣ እግዚቢት ላይ የተመሰከሩት ቃሎችን ፍ/ቤቱ እንዳይመዘግባቸው ማመልከት፣ እንዲሁም ያልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ምስክር መስማቱ ተገቢ እንዳልሆነ በአስተያየታቸው አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም አቃቤ ህግ ቀሪ ምስክሮችን ማሰማት ካለበትም ምስክሮቹን በተሰጠው ቀን ( የማስረጃ መስማት ለሶሰት ተከታታይ ቀናት አንደተቀጠረ ይታወሳል) እንዲያቀርብ በማሳሰብ የደንበኞቻቸው የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት በፍርድ ቤቱና በአቃቤ ህግ በኩል እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡ በተለይ ባልተካዱ ዶክሜንቶች ላይ ይህን ያህል ጊዜ መውሰዱ ተገቢ አይደለም ብለዋል ጠንካራ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹አቃቤ ህግ ያቀረበውን ሰምተናል፤ እኛ ብቻችንን አይደለም የታሰርነው፤ ቤተሰቦቻችንና ጓደኞቻችንም አብረውን ታስረዋል፡፡ በህሊና እና በኢኮኖሚ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰብን ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ ሁሉ ‹ውሳኔው ላይ አብሮ እንዲታይልን እናመለክታለን ብሏል፡፡

ፍርድ ቤቱ የጠዋት ምስክር መስማቱን ሂደት አጠናቆ ለከሰአት ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ ከሰአት በኋላ ሁለት ጉዳዬች ብይን ሰጥቷል፡፡ የመጀመሪያው የምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር አንዲያያዝ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ቀሩ የተባሉት ሶስት ምስክሮች ታስረው ለመጋቢት 30 አንዲቀርቡ እና አቃቤ ህግ ተጨማሪ ምስክሮች አሉኝ ካለም አንዲያቀርብ ነው፡፡በዚህም መሰረት ለሶስት ቀን የታቀደው ምስክሮችን መስማት በአንድ ቀን ከግማሽ ተጠናቋል፡፡ ጠበቆች አቃቤ ህግ ቀድሞ በተወሰነው ቀን ምስክሮችን ሊያቀርብ ሲገባ ሌላ ቀነ ቀጠሮ መሰጠት የለበትም በማለት ያቀረቡትን ተቃውሞ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ ምስክሮቹን በፌደራል ፓሊስ እያስፈለኩ ስለሆነ ተከሳሾ ማረሚያ ቤት እንዳሉ ለፍለጋው ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ነበር ፡፡

ጠበቆቹ አቃቤ ህግ የእግዚቢት ሰነዶችን በተመለከተ የመዝገብ ቁጥሩን ገልጾ እንዲቀርብ በጠየቁት መሰረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ በትዕዛዙ መሰረት አቃቤ ህግ ዛሬ የመዝገብ ቁጥሩን ይዞ መቅረብ የነበረበት ቢሆንም፣ ጠበቆቹ ይህንኑ ጉዳይ በማንሳት ሲጠይቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ አልሰጠንም በሚል ክዷል፡፡

ምንጭ፡- ዞን 9 ማኀበራዊ ገፅ