Tag Archives: Human Rights

በኬንያ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ በአል-ሸዓባብ በተፈፀመ ጥቃት የሟቾች ቁጥር 147 ደርሷል

Garissa-University-College attack

በኬንያ ሰሜን ምስራቅ  በምትገኘው ጋሪሳ የሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ ሐሙስ ጠዋት መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ግቢ ውስጥ በመግባት በከፈተው ጥቃት ሁለት የዩኒቨርስቲው ጠባቂዎችን፣ሶስት የፖሊስ ኦፊሰሮችን እና 142 ተማሪዎች በአጠቃላይ 147 ሰዎች መገደላቸውን የሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ጆሴፍ ነካይዘሪ ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርገዋል፡፡ በጥቃቱ ከሟቾች በተጨማሪ 79 ተማሪዎች የቆሰሉ ሲሆን፤ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቀ በታጣቂው ኃይል ታግተው እንደነበር ተጠቁሟል፡፡

ይህንንም ተከትሎ የሀገሪቱ ፕሬዘዳንት ኡሁሩ ኬኒያታ በፖሊስ እጥረት ምክንያት አላስፈላጊ ዋጋ መክፈል የለብንም በማለት ከፍተኛ የፖሊስ ቁጥር እንዲጨምርና ወደስልጠና እንዲገቡ  ትዕዛዝ መስጠታቸውን አደጋው በደረሰ ቀን ባስተላለፉት የሀዘን መግለጫ ላይ አስታውቀዋል፡፡ የሶማሊው ታጣቂ አልሸዓባብ በኬንያ ንፁሃን ላይ የሚያደርሰው ጥቃት እየተበራከተ ሲሆን፤ ከዚህ በፊት በናይሮቢ ዌስትጌት የንግድ ማዕከል ውስጥ በፈፀመው ጥቃት 67 ሰዎች መግደሉ ይታወሳል፡፡ ከዛም በኋላ የሐሙሱን የጋሪሳ ዩኒቨረድስቲ ኮሌጅን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በርካታ ጥቃቶችን መፈፀሙ ይታወቃል፡፡ የጥቃቲ ኢላማዎችም ሙስሊም ያልሆነ ማንኛውም አካል ሲሆን፤ በተለይ ክርስቲያኖች ላይ ጥቃቱ መጨመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

እንደ ሀገሪቱ ፖሊስ መጃ መሰረት ከ2004 ዓ.ም. እስከ ታህሳሥ 2007 ዓ.ም. ብቻ የአልቃይዳ ክንፍ በሆነው በሶማሊያው እስላማዊ ታጣቂ አልሸዓባብ የተገደሉ ኬኒያውያን ቁጥር 312 ደርሶ ነበር፡፡ በጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ የተፈፀመውን የጅምላ ግድያ ጨምሮ በሶማሊያው ታጣቂ አል-ሸዓባብ የተገደሉ ኬንያውያን  459 ደርሷል፡፡

Garissa-University-College attack

በዩኒቨርስቲ ኮሌጁ ተማሪዎች ላይ ታጣቂው  ከፈፀመው የጅምላ ግድያ በኋላ አራት የታጣቂ ቡድኑ አባላት ሲገደሉ፣ አምስት ተጠርጣሪ የቡድኑ አባላት በቁጥጥር  መዋላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ጋሪሳ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ ውስጥ የተገደሉ ሰዎችን ማንነት ለመለየትና ወደ የቤተሰቦቻቸው ለመላክ አሰከሬናቸው ወደ ናይሮቢ መላኩም ታውቋል፡፡

ጋሪሳ ከናይሮቢ ሰሜን ምስራቅ 367 ኪሎ ሜትር ስትርቅ፤ ከኬንያ ሶማሊያ ድንበር ያላት ርቀት  ደግሞ 147 ኪሎ ሜትር ነው፡፡ የታጣቂ ቡድኑ በተመሳሳይ መልኩ በዩጋንዳ የትምህርት ተቋማት ላይ ጥቃት ለመፈፀም ዕቅድ እንዳለው ተጠቁሞ፤ የዩጋንዳ የደህንነትና ፀጥታ አካላት የሀገሪቱን ደህንነት ከመቼውም ጊዜ በላቀ በተጠንቀቅ ላይ ሆነው እንዲጠብቁ መደረጉንም የዩጋንዳ ከፍተኛ ፖሊስ ኦፊሰርን ጠቅሶ የአውስትራሊያው ኤቢሲ ዘግቧል፡፡

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በኬንያ መንግሥት ተፈላጊው መሐመድ መሐሙድ

በተለይ ከጥቃቱ በስተጀርባ ዋና አቀናባሪና በጋሪሳ ከተማ የእስላማዊ ትምህርት ቤት መምህር እንደነበር የተጠቆመው መሐመድ መሐሙድ የገደለ ወይም ያለበትን የጠቆመም እንዲሁም ይዞ ለሚያስረክብ የኬንያ መንግሥት ፖሊስ 215 ሺህ የአሜሪካን ዶላር (200 ሚሊዮን የኬንያ ሽንልንግ)እንደሚሰጥ ቃል ገብቷል፡፡ ጥቃቱን በተመለከተ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋነ ፀሐፊ ባን ኪ ሙንን ጨምሮ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ማኀበረሰቦች ያወገዙት ሲሆን፤ ታጣቂው አልሸዓባብ በበኩሉ ድርጊቱ የፈፀመው ከኬንያ ጋ ጦርነት ውጊያ ላይ ስለሆንን ነው ማለቱን የቢቢሲ ዘገባ አመልክቷል፡፡

በጉጂ ዞን ያለው ውጥረት እስካሁንም አለመብረዱ ተገለፀ

በደቡብ ኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል በሚገኘው ጉጂ ዞን ባለፈው መጋቢት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. በኦዶ ሻኪሶ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች እና ከዞኑ ከተማ መስተዳደር ጋር በተፈጠረው አለመግባባት ሁለት ወጣቶች በፌደራል ፖሊስ መገደላቸውን ተከትሎ የፈጠረው ውጥረት እስካሁንም አለመብረዱ ተገለፀ፡፡ እንደምንጮች ገለፃ ከሆነ የ9ኛ ክፍል ተማሪ የሆነችው ብስራት ኃይሌ እና በግብርና ሙያ የሚተዳደረው ወጣት ሀለቄ ሮባ በከተማው የዕለት ስራውን ለማከናወን እየተንቀሳቀሰ ሳለ በፌደራል ፖሊስ በተወሰደ የጥይት ተኩስ እርምጃ ወዲያው ህይወታቸው አልፏል፡፡

በፌደራል ፖሊስ ተገደሉ ከተባሉት ተማሪዎች በተጨማሪ በከተማው ማንነቱ ባልታወቀ አካል በተተኮሰ ጥይት አንድ የፌደራል ፖሊስ ላይ ከፍተኛ አደጋ በመድረሱ ወዲያው ወደ አዲስ አበባ ለህክምና መላኩን እና በከተማውም ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሌሎች ነዋሪዎች ላይ በፖሊስ በተወሰደ የኃይል እርምጃ ቆስለው በከተማው ሆስፒታል ህክምና እርዳታ ያገኙም እንዳሉበት የአዲስሚያ ምንጮች ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በጉጂ ዞን ባሉ 15 ወረዳዎች እና በሶስቱ ከተማ መስተዳደሮች ነጌሌ ቦረና፣ ክብረ መንግስትና ኦዶሻኪሶ በነዋሪውና በመንግስት ኃላፊዎች መካከልበተፈጠረ አለመግባባት እስካሁን ውጥረቱ አለመርገቡ እና ችግሩ በዞኑ ባሉ ገጠሮች ድረስ መዛመቱም ተጠቁሟል፡፡ የግጭቱ መንስኤም ተማሪዎቹ ለአስተዳዳሪዎቹ ባነሱት የመጠጥ ውሃ፣ የመብራትና ተያያዥ የመብት ጥያቄዎች መሆኑንም መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በዚህ ዙሪያ የመንግስት ኃላፊዎች እስካሁን ምንም ሰጡት ማስተባበያም ሆነ መልስ ባይኖርም፤ በወጣቶቹ መገደል በተፈጠረው ውጥረት የአካባቢው የመንግስት ሹማምንት ዛሬ እሁድ መጋቢት 7 ቀን 2006 ኣ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት በጉጂ ዞን አንድነት ፓርቲ የገንዘብና ንብረት ክፍል ኃላፊ የሆኑትን አቶ ዮሐንስ ኢብሶን ተማሪዎቹ ላነሱት ጥያቄ ምክንያት ናቸው በማለት መንግስት ማሰሩ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡

በኦሮሚያ ሻኪሶ ሁለት ተማሪዎች በፌደራል ፖሊስ በመገደላቸው ውጥረት መንገሱ ተሰማ

 

በደቡብ ኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል በሚገኘው ጉጂዞን ኦዶ ሻኪሶ ከተማ በተማሪዎችና በከተማው አስተዳደር መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የፌደራል ፖሊስ ጣልቃ በመግባት በወሰደው የኃይል እርምጃ አንዲት ሴት እና አንድ ወንድ በአጠቃላይ ሁለት ተማሪዎች ህይወት በማለፉ እና ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በመቁሰላቸው የኦዶ ሻኪሶ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ተቃውሟቸውን ማሰማታቸው ተጠቁሟል፡፡ pic

የግጭቱ መንስኤ ተማሪዎቹ “በከተማውና አካባቢው የመጠጥ ውሃ አገልግሎት የለም፣ አንድ ባለ 25 ሊትር ጀርካን ውሃ በ 7 ብር እየተሸጠ ነው፣ በቂ የመብራት አገልግሎትም የለም፣ ከህዝቡ ሚሰበሰበው ግብር እና ከመንግስት የሚመደበው በጀት እስካሁን ምን ላይ እየዋለ ነው? ህብረተሰቡም እኛ ምበውሃጥም እየተጎዳን አስተዳደሩ እስከዛሬ ለምን ዝም አለ?” የሚሉ ጥያቄዎች በመነሳታቸው፤ የአስተዳደር አካላት ተማሪዎቹን “እናንተ ምን አገባችሁ፣ አርፋችሁ ተማሩ፤ካልሆነ እርምጃ እንወስዳለን” የሚልምላሽ በመሰጠቱ ተማሪዎችን እንዳስቆጣ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ በዚህም ምክንያት የፌደራል ፖሊስ ድንገት ጣልቃ በመግባት ተቃውሞ በሚያሰሙ ተማሪዎች ላይ እርምጃ በመውሰዱ የከተማው ነዋሪዎችም ተቃውሞውን መቀላቀላቸው የአዲስሚዲያ ምንጮች ከስፍራው ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የከተማውና የአካባቢው ነዋሪ ከፌደራል ፖሊስ ጋር መፋጠጡን፣ ይህ እስከተዘገበበት ሰዓት ድረስም በከተማው የጦር መሳሪያ ተኩስ ሁሉ እየተሰማ መሆኑንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሟቾቹ ሁለቱ ተማሪዎች አስከሬን በሆስፒታል እንደሚገኝ እና ወላጆችም ወደሆሲፒታሉ እንዳይገቡ በፌደራል ፖሊስ መከልከላቸው እንዲሁም በከተማው ተወስኖ የነበረው ቁጣም ወደ ገጠሩ ነዋሪበ መስፋፋት በርካቶች በቁጣወደ ከተማው እየገቡ መሆኑንም ምንጮች አስረድተዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ በከተማው ከፍተኛው ጥረት መንገሱም ተጠቁሟል፡፡

እንደምንጮች ገለፃ ከሆነ ችግሩ የተፈጠረው የኦዶ ሻኪሶ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የመብት ጥያቄ በማንሳታቸው አስተዳደሩ ጥያቄያቸውን በቀጥታ ወደ ፖለቲካ በመቀየር የፌደራል ፖሊስ ተጠርቶ በቀጥታ የኃይል እርምጃ በመውሰዱ የሁለት ተማሪዎች ህይወት ወዲያው በማለፉ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ በአሁን ሰዓትም በከተማው በተለያዩ ቦታዎች የእሳት ቃጠሎ፣ የህንፃዎች መስታወት መሰባበር፣ ሌሎች ንብረቶች እየወደሙ መሆናቸውን እንዲሁም ከፍተኛ የተኩስ ድምፅ እየተሰማ መሆኑንም ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ አዲስሚዲያ ይህንን ለማጣራት የኦሮሚያ ፖሊስ አዛዥ ናቸው ወደተባሉት ኮማንደር አበበ እና የጉጂ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ገዳ ሮቤ ጋር ተደጋጋሚ ጥረት ቢደረገም ለጊዜው አልተሳካም፡፡ ኦዶ ሻኪሶ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የወርቅ ማዕድን ከሚመረትባቸው አካባቢዎች ዋነኛው መሆኑ ይታወቃል፡፡