ኦሮሞ ነኝ!! ኢትዮጵያዊ ነኝ!! አሸባሪ አይደለሁም!!
ገመቹ መረራ ፋና

*
ይኼንን የምፅፈው በብዙ ነገሮች ስለተረበሽኩ ነው፤ ጎኔን ከፍራሼ በጊዜ ባዋድድም እንቅልፍ ሊወስደኝ ስላልቻለ ከተጋደምኩበት ተነስቼ ነው። በየቀኑ የምሰማው እና የማየው ነገር እነ1984ን እና Hunger Gamesን አይነት ፊልሞች የምመለከት እንጂ የምር እየኖርኩት ያለሁት ነገር እየመሰለኝ አይደለም። መጪው ጊዜ ብሩህ አይደለም!!! ጭለማ እና አስፈሪ ሆኖብኛል።
* * *
ይሄ ሌሎች ሰዎች ላይ የደረሰ ሳይሆን በኔው በራሴው ላይ የደረሰና የኖርኩት ገጠመኝ ነው፦
አምቦ፣ ሕዳር 1998 ዓ/ም።
ከትምህርት ቤት ሲወጡ እዚያው ትምህርት ቤት በር ላይ ስለተገደሉት የ10ኛ ክፍል ተማሪዎች አላወራላችሁም። በሰላማዊ መንገድ ያለምንም ሁከት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ልጆች ላይ ፊት ለፊት ጥይት ስለሚተኩሱ «ሰላም አስከባሪዎች»ም አልተርክም። አዎ የተገደሉት ከተገደሉ በኋላ በአንድ ዝም ባለ ቀን የተደረገ ነገር ነው።
በዚህ ዕለት አሁን በሕይወት የሌሉ አያቴን እያስታመምኩ ለማደር ከሰፈር ወጥቼ አያቴ ወደተኙበት ወደ አምቦ ሆስፒታል እያመራሁ ነበር። ወደዋናው የአስፓልት መንገድ ልደርስ አንድ ቅያስ ሲቀረኝ በስፍራው የነበሩት ሁለት ፌዴራል ፖሊሶች ጠሩኝ። ምርጫ አልነበረኝም፤ እየቀፈፈኝ ወደቆሙበት ጥግ ሄድኩ።
«መታወቂያ!» ሲል ጮኸብኝ አንደኛው ፌዴራል ፖሊስ ዱላውን እያሽከረከረ። አረንጓዴዋን የቀበሌ መታወቂያዬን ከኋላ ኪሴ አውጥቼ ሰጠሁት። ያሽከረክረው የነበረውን ዱላውን ትከሻዬ ላይ አሳረፈው። «ማን ይሄን ጠየቀህ?! የኦነግ መታወቂያህን አውጣ!» ሲል ጮኸብኝ።
«ኧረ የለኝም…» ንግግሬን አልጨረስኩም። የሁለተኛው ፖሊስ ዱላ አረፈብኝ። የተለያዩ መልስ የማይፈልጉ ጥያቄዎች እየጠየቁ በእግራቸው ተቀባበሉኝ። ሲበቃቸው «ሂድ ከዚህ ጥፋ፣ እናንተ ናችሁ ያስቸገራችሁት..» አሉኝ። ተነስቶ ለመሄድ የሚያስችል አቅም ግን አልነበረኝም፤ ይሄም ለሌላ ዱላ ዳረገኝ። እንደምንም ታክሲ ይዤ ሆስፒታል ደረስኩና አደርኩ። ያንን ድብደባ የማልረሳበት ሌላም ምክንያት አለኝ።
* * *
ይሄ መንገድ እየሄድኩ ሳለሁ የገጠመኝ ነገር ነው። ለተቃውሞ ድምፁን ያሰማ ሰው ደግሞ ምን ሊደርስበት ነው? መገመት ነው። ኦሮሞ ስለሆንኩ፣ ጥያቄ ስለጠየቅኩ፣ አንገቴን ቀና አድርጌ ስለሄድኩ «ኦነግ» የሚል ታፔላ በማንም እንዲሰጠኝ አልፈልግም!!! ሰው ነኝ!!! ኢትዮጵያዊ ነኝ!!! ኦሮሞ ነኝ!!! አሸባሪ ግን አይደለሁም!!! አባቶቼ ለዚህች አገር እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ደምተዋል። ቅድም አያቴ ትግራይ ድረስ ሄደው ዘምተው የሃገራቸውን ዳር ድንበር ሲያስከብሩ ተሰውተዋል። ከማንም ያልበለጥኩ፣ ከማንም ያላነስኩ የዚህች አገር ዜጋ ነኝ።
* * *
ይሄንን እና ሌሎችም ነገሮችን በጭንቅላቴ እንደሰነግኩ ነው እንግዲህ ወደ መቐለ ዩኒቨርሲቲ ለትምህርት የሄድኩት። እዚያ እንደደረስኩም ብዙ ሳንቆይ ነበር የብሔር ግጭት የተነሳው። በኋላ ላይ ሲጣራ አንዲት ልጅ አፍቅሮ ራሱን ባጠፋ አንድ የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ምክንያት ነበር «እኛም አንድ ኦሮሞ መግደል አለብን» ተብሎ በጠራራ ፀሃይ የተዘመተብን። እኚህ ጥቂት የተማሩ ደደቦች የፈፀሙት ድብደባና ሌሎች አስፀያፊ ድርጊቶች የትግራይን ወይም የመቐለን ሕዝብ ይገልፁት ነበር? በፍጹም!!!
ለአራት አመታት የኖርኩበት ይህ የትግራይ ሕዝብ ከተማሪው ሸሽቶ ከዩኒቨርሲቲው ጊቢ በመውጣት በደመነፍስ ወደ ሃይማኖት ተቋማት እና ሌሎች ስፍራዎች የሸሸውን የሌላ ክልል ተማሪ ምግብና መጠለያ ሰጥቶ ክፉ ቀኑን ያሳለፈለት ደግ ሕዝብ ነው!! ታምሜ ለሳምንት በተኛሁበት አጋጣሚ በአካል እንኳን ሳታውቀኝ መታመሜን ስትሰማ «ወይኔ ልጄን» ብላ በልጇ ምግብና ማር የላከችልኝን እናት ያገኘሁበት ሕዝብ ነው!! ምንም የማያውቀኝን እኔን ተቀብሎ ቤቴ ያለው እንዲመስለኝ አድርጎ የተንከባከበኝ፣ ከአባቴ ያላነሰ ገንዘብና ሞራል እየሰጠ ለአራት አመታት ከአጠገቤ ያልተለየ አባት ያገኘሁበት ሕዝብ ነው!! የዚህን ሕዝብ ደግነት በጥቂቶች ድድብና በዜሮ ላባዛው? የተወሰኑ ፖለቲከኞች አሊያም «አክቲቪስቶች» ድርጊትና ንግግር ይሄንን እውነት ይሰውርብኝ? ፈጽሞ!!!!!!
አዎ እንዲህ አይነት የደግነት ታሪኮች በሌሎች አካባቢዎችም ብትሄዱ በብዙ ትሰማላችሁ። በተቸገረ ሰው ጨክኖ «ብሔሩ ምንድነው?» የሚል ሕዝብ የትም ቦታ የለም። ስለኖርኩብትና ስላሳደገኝ ስለደጉ የኦሮሞ ሕዝብ ሌላ ጨምሬ የምናገረው ነገር የለኝም። በተለያዩ ጊዜያትና አጋጣሚዎች በበቂ ሁኔታ ተነግሯል። በቅርቡ፣ በጣም በቅርቡ ግን በረባውም ባልረባውም በዘር መከፋፈል ነው የማየው። የሃይማኖት ጉዳይ ሆኖበት «የክርስቲያን/የሙስሊም ስጋ አልበላም» ይል የነበረው ማህበረሰባችን «የኦሮሞ/አማራ/ትግሬ ስጋ አልበላም» የሚልበት ጊዜ የመጣ እስኪመስል ድረስ ልዩነት በባትሪ ይፈለጋል። እርስ በርስ የሚያባላን የከፋ ችግር የለብንም። እንደሌላው ዓለም የዘር (race) ችግር የለብንም፤ ሁላችንም ጥቁር ነን። ተመሳሳይ ኑሮ የምንኖር፣ የመግባቢያ ችግር የሌለብን፣ ለዘመናት ስንጋባና ስንዋለድ የኖርን ሕዝቦች ነን። አንዱ «ብሔር» ከአንዱ «ብሔር» በከፋ ሁኔታ፣ አንዱ ሃይማኖት ከሌላኛዎቹ ሃይማኖቶች በተለየ ሁኔታ በተለያዩ ሥርዓቶች የተገፋበትን ሁኔታ አይተናል። አዎ ሥርዓቶች፣ መንግስታት/ገዢዎች ያልፋሉ፣ በሌላም ይተካሉ፤ ይህ ያለና የነበረ የተፈጥሮ ሥርዓት ነው። ሕዝቦች ግን አያልፉም።
ብሔር አጣርተው አይደለም ወላጆቻችን ለጎረቤታቸው ችግር ሲደርሱ እና ሲደረስላቸው የኖሩት። ብሔር ተጠያይቀን አይደለም እዚህ የደረስነው። ብሔር ቆጥረን አይደለም ምርጥ ጓደኞቻችንን ያፈራነው። ሰውነታችንን አስቀድመን ነው!!! ዛሬ በማወቅም ባለማወቅ የሚደረጉ የብሔር የርስ በርስ ግጭት ውስጥ መግባት የለብንም። ያ እንደ ብሔርም ሆነ እንደ ሃገር የማንወጣው አዘቅት ውስጥ ነው የሚከተን። አሁን ያለንበትንም ይሁን ያለፍንበትን ልዩነት በእጅጉ የሚያስመኝ ክፉ አዘቅት ውስጥ!!!
ተዋጠልንም አልተዋጠልን ተዋልደናል። ተዋደናል። ተዛምደናል። ተጋምደናል። የተሻለችዋን ነገኣችንን ልንፈልግና ልናገኝ የምንችለው አንዲት የሁሉንም ሰው መብት እና ሰብዓዊ ክብር በምትጠብቅ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነው። ከታሪክ ልንማር ይገባል ምናምን አልልም። አይናችንን አንስተን ደቡብ ሱዳንን ማየት በቂአችን ነው። ከሱዳን እስክትገነጠል ድረስ ፅኑና የሚገርም ትግል ለዓመታት አድርጋለች። ከተገነጠለች በኋላ ግን የሆነችውን ሆናለች። የኛም የተናጠል ጉዞ መድረሻው ያው ነው። አማራ ቢገነጠል ጎጃም፣ ጎንደር፣ ወሎ፣ ሸዋ እያለ ይናከሳል። ኦሮሚያ ብትገነጠል ሸዋ፣ ሐረርጌ፣ ወለጋ፣ አርሲ እያለ ይባላል። ትግራይ ቢገነጠል ተምቤን፣ እንደርታ፣ ዓድዋ፣ ሽሬ እያለ ይጫረሳል። «ታግሎ» ሲያበቃ «ነፃ» ባወጣት «ሃገር» የሚፈጠረው ቀውስ የዳር ተመልካች መሳቂያ ያደርገዋል።
* * *
አይን የሌለው ኢፍትሃዊነትን በሚተገብር እና ግፍ በሚፈፅመው አካል ሳይሆን ዳር ሆኖ ያንን ድርጊት በሚደግፈው ሰው ልቤ ትደማለች። ከክቡሩ የሰው ልጅ ሕይወት ይልቅ በተራ የንብረት መውደም የሚብሰከሰከውን ብኩን ሳይ ነፍሴ ክፉኛ ታዝናለች። ልጁን በሞት ካጣ ወላጅ ሃዘን ይልቅ ወደፊት ምናልባት ኪሴ ሊገባ ይችላል ብሎ ለሚያስበው ሽራፊ ሳንቲም በሚቆረቆር «ሰው» ንቀቴ ይበረታል። ትናንት እርሱ ላይ ሲጫን የነበረውን የበደል ቀንበር ዛሬ ባለቀን ሆኖ ሌላው ላይ አክብዶ በሚጭነው ላይ ጥላቻዬ ይከራል። አንድ ሕሊና ያለው ሰው እንዴት በባዶ እጅ በወጣ ሰልፈኛ ላይ ቀጥታ የተተኮሰን ጥይት ደግፎ ሊናገር ይችላል? አንድ ችግር የኛን ቤት እስኪያንኳኳ ድረስ የባለቤቱን ያህል ላይሰማን ይችላል፣ ነገር ግን እንዴት በተቃራኒ ያስቆማል? አላውቅም። የዚህ አይነት አስተሳሰብ አይገባኝም።
* * *
Rabindranath Tagore «Gitanjali» በተሰኘው መድብሉ ውስጥ በጣም የምወድለት እንዲህ የምትል የልመና/የፀሎት ግጥም አለችው፦
Where the mind is without fear and
the head is held high;
Where knowledge is free;
Where the world has not been broken
up into fragments by narrow domestic walls;
Where words come out from the depth of truth;
Where tireless striving stretches its arms towards perfection;
Where the clear stream of reason has not
lost its way into the dreary desert of
dead habit;
Where the mind is led forward by Thee
into ever-widening thought and action—
Into that heaven of freedom, my Father,
let my country awake.
አሜን!!
* * *
ኦሮሞ ነኝ!! አሸባሪ አይደለሁም!!
#OromoProtests
#StopKillingCivillians
#StopKillingUnarmedProtesters
በኦሮሚያ ያለው ተቃውሞ የቀጠለ ሲሆን፤ በመንግሥት የተገደሉ ሰዎች ቁጥርም 82 መድረሱ ተሰማ
በተለይ ከህዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ ምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ የተጀመረው የተማሪዎች የአዲስ አበባ እና የፊንፊኔ ልዩ ዞን ኦሮሚያ ክልል የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ትግበራን በመቃወም እስከ ታህሳሥ 3 ቀን 2008 ዓ.ም. 76 ሰዎች በመንግሥት በተወሰደ ሃይል እርምጃ መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ መድረክ በበኩሉ መግለጫውን እስኪሰጥ በረደሰው መደረጃ መሰረት በመንግሥት የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 32 ደረስው እንደነበር አስታውቋል፡፡ የሟቾቹ ቁጥር ዛሬም የጨመረ መሆኑን መረጃዎች የጠቆሙ ሲሆን፤ የሟጮች ቁጥር ከ82 በላይ መድረሱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከተገደሉት መካከልም ከ10ዓመት ህፃን የአንደኛ ደረጃ ተማሪ እስከ 78 ዓመት አዛውንትና የልጆች አባት እንደሚገኙበት መረጃዎች የጠቆሙ ሲሆን፤ በርካታ ሰዎችም መቆሰላቸውን እና መታሰራቸውም ታውቋል፡፡
መድረክ የመንግሥት እርምጃን በማውገዝ ታህሳሥ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. መግለጫ፤ ከሁለት ሳምናታት በላይ በዘለቀው የኦሮሚያ ክልል ከተሞች ተቃውሞ 32 ሰዎች በመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን አስታውቋል፡፡ መድረክ የተገደሉትን ሰዎች ስም ዝርዝር እና አካባቢም በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
በክልሉ በተለያዩ ከተሞች እየተካሄደ ባለው ህዝባዊ ተቃውሞ ዛሬ ረቡዕ ታህሳሥ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ እንደቀጠና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም የተገደሉ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ በተለይ የተቃውሞ ሰልፉ ዛሬም ከቀጠለባቸው ከተሞቸ መካከል በምዕራብ ሐረርጌ አሰቦት፣ በምበአርሲ አሰላ፣ በምዕራብ ሸዋ ኢጃጂ፣በኢሉባቦር መቱ፣ በምዕራብ ወለጋ ነጆ እና ቢላ፣ በምስራቀረ ጎጃም ነቀምት እንዲሁም በቡራዩ ጨምሮ በተለያዩ ከተሞችና ተቋማት ተቃውሞው ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል፡፡ ዛሬ በነጆ በነበረው ተቃውሞም 4 ሰዎች መገደላቸውንም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ የዛሬዎቹን ግድያዎች ጨምሮ ሶስተኛ ሳምንት ባስቆጠረው ህዝባዊ ተቃውሞ በመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች በተወሰደ የኃይል እርምጃ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር ከ82 በላይ መድረሱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡በክልሉ ባሉ ከተሞች ባሉ የተለያዩ ትምህርት ተቋማት ትምህርት መቋረጡ ታውቋል፡፡
ህዝባዊው ተቃውሞው ከክልሉ ተወላጆች በተጨማሪ በሀገር ውስጥ ከሀገር ውጭ ባሉ በርካታ ሰዎች የአጋርነትና ድጋፍ እንደተቸረው እየተገለፀ ሲሆን፤ በዚህም ምክንያት በተለይ በክልሉ ደቡብ ምዕራብ ሸዋ የአካባቢው የኢህአዴግ አመራሮችና ከየት እንደመጡ ባልታወቁ የስርዓቱ አካላት ባካባቢው ያሉ አማራና ኦሮሞን ለማጋጨት ተደጋጋሚ ሙከራ ማድጋቸውን እና በዚህም 4 የአካባቢው የአማራ ተወላጆች ሲገደሉ፣ ቤቶቻቸው የተቃጠሉና ንብረቶቻቸው ባልታወቁ ሰዎች እንዲዘረፍ በማድረግ በርካቶች መፈናቀላቸውን ከአካባቢው የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ተቃውሞውን ክህዝቡ ጥያቄ በተቃራኒ ወደ እርስ በርስ ብሔር ግጭት ለማድረግ የተሞከረውንም ድርጊት የአካባቢው የኦሮሞ ማኀበረሰብ አዛውንቶችና ወጣቶች እንዲቆም ማድረጋቸውን እና በድርጊቱም የተበሳጩ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል የርስ በርስ የብሔር ግጭት ለመፍጠር ሲሰሩ ከነበሩ የገዥው ስርዓት የአካባቢው የኦህዴድ/ኢህአዴግ አመራር አካላት መካከል አንዱ ወዲያው መገደሉንና ሌሎቹ ሸስተው ከአካባቢው ማምለጣቸውን የአዲስ ሚዲያ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ የተፈናቀለው ህዝብም ወደነበረበት አካባቢ እንዲመለስ የአካባው አዛውንቶችና ወጣቶች እየሰሩ እንደነበርም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት በሚኒስተሩ አቶ ጌታቸው ረዳ አማካኝነት በሰጠው መግለጫ በኦሮሚያ ከተሞች በተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ የመንግሥት አካላት ላይ ጉዳት መድረሱን በመግለፅ መንግሥት የኃይል እርምጃውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ሚኒስትሩ በታቀውሞው በመንግሥት አካላት ላይ ደረሰ ስላሉት ጉዳይ በዝርዝር የገለፀቱት ነገር ባይኖርም፤ በተቃውሞ ሰልፉ ስለተገደሉ ሰዎች ግን ያሉት ነገር የለም፡፡ በትናትነው ዕለት የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት፣ የፌደራሉ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል የመንግሥት የኃይል እርምጃ እንደሚቀጥል ማስጠንቀቂያ መስጠታቸው የሚታወስ ቢሆንም፤ የህዝቡ ተቃውሞ ግን ዛሬም በተለያዩ ከተሞች ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
በተለይ መንግሥት በሰላማዊ መንገድ ተቃውሞ እያደረጉ ባሉ ሰዎች ላይ መንግሥት እየወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ ከሀገር ውስጥ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ በመቃወምና በማውገዝ መግለጫ ማውጣታቸው አይዘነጋም፡፡ በተመሳሳይም ቢሮአቸውን በውጭ ያደረጉ እንደ ኦነግ እና አርበኞች ግንቦት ሰባትን ጨምሮ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች የመንግሥትን ድርጊት አውግዘዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ባሉ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ ከ5 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፤ በርካቶች ቆስለዋል
ህዳር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ጊኒጪ ከተማ እንደገና የተጀመረው አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞችን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ትግበራን የተቃወሙ ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ እስካሁን የ5 ሰዎች ህይወት መጥፋቱ እና በርካታ ተማሪዎችም መጎዳታቸው ታውቋል፡፡ በተለይ እንደ አዲስሚዲያ ምጮች ከሆነ፤ የተማሪዎች ተቃውሞ በምዕራብ ኢትዮጵያ በጊኒጪ፣ በአምቦ፣ በምዕራብ ወለጋ የተቀጣጠለው ተቃውሞ ሌሎችንም የምዕራብ ሸዋ ከተሞችን አዳርሶ ወደ ምስራቅ ኢትዮጵያ ሐረማያ ዩኒቨርስቲ መድረሱ ታውቋል፡፡

በተለይ በሐረማያ ዩኒቨርስቲ ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ጥያቄ ባነሱ ተማሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ 1 ተማሪ ሲገደል፣ ቁጥራቸው እስካሁን በውል ያልታወቁ በርካቶች ጉዳት እንደደረሰባቸው ታውቋል፡፡ በተለይ ህዳር 23 ቀን 2008 ዓ.ም. ሐረማያ ዩኒቨርስቲ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በዩኒቨርስቲው ክልኒክ እና በሐረር ሆስፒታል የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ከነበሩት መካከል በዩኒቨርስቲው ክልኒክ የህክምና እርዳታ ሲደረግለት የነበረ አንድ ተማሪ ህይወቱ ማለፉን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተማሪዎች ላይ እየወሰዱ ባሉት የኃይል እርምጃ በምዕራብ ወለጋ ግሊሶ ከተማ ሌላ አንድ ተማሪ መገደሉ የተጠቆመ ሲሆን፤ እስካሁን በፀጥታ ኃይሉ የተገደሉ ተማሪዎች ቁጥርም 5 መድረሱ ታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ በሱሉልታ ጫንጮ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ባነሱት ተመሳሳይ ጥያቄ በርካታ ተማሪዎች በመንግሥት በተወሰደባቸው የኃይል እርምጃ ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ ተቃውሞው በኦሮሚያ ክልል ካሉ አንደኛ ደረጃ እስከ ዩኒቨርስቲ የተቀጣጠለ ሲሆን፤ በተለይ በጫንጮ አንደኛ እና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መንግሥት በወሰደው የኃይል እርምጃ የአንደኛ ደረጃ ህፃን ተማሪዎች ላይ ሳይቀር ጉዳት መድረሱን ምስልን አስደግፈው የአካባቢው ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

መንግሥት በተማሪዎች ላይ እየወሰደ ባለው የኃይል እርምጃ ከክልሉ ተወላጆች በተጨማሪ በርካታ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ላይ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን፤ ተቃውሞው ወደክልሉ ሌሎች ከተሞች እና ዩኒቨርስቲዎችም እየተዛመተ በመሆኑ በየአካባቢው ከተሞች ባሉ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እና ዩኒቨርስቲዎች ከፍተኛ የፀጥታ ጥበቃ ቁጥጥር ላይ መሆናቸው ተሰምቷል፡፡ ተቃውሞው ወደባሌ መዳወላቡ ዪኒቨርስቲም መዛመቱ መዛመቱን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በደቡብ ምዕራብ ሸዋ በበቾ እና በቱሉቦሎ ከተማ እንደዚሁም በደቡብ ሸዋ ወሊሶ አካባቢ በዲላላ ከተማ ውስጥ ያሉ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተቃውሞ እያደረጉ እንደሆነም የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትወርክ ዘገባ አመልክቷል፡፡ የተቃውሞው ዋነኛ ምክንያትም መንግሥት ይፋ ያደረውና እስካሁንም ከህዝብ ጋር ያልተመከረበትና ተግባራዊ ለማድረግ ከመንቀሳቀስ በስተቀር በምስጢር ተይዟል የተባለለት አዲሱ የአዲስ አበባ እና የአካባቢው የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች የጋራ የተቀናጀ ማስተር ፕላን በአካባቢው ያሉ ገበሬዎችን ያለ በቂ ካሳ ያፈናቅላል፣ የአካባቢው ኦሮሞ ማኀበረሰብ ባህልና ቋንቋ ያጠፋል እና ኦሮሚያ ክልልን ለሁለት ይከፍላል የሚሉ ጥያቄዎች እንደሚገኙበት ለአዲስ ሚዲያ የደረሱ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና፤ አዲሱ የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ ባለፈው ግንቦት 2006 ዓ.ም. ተቀስቅሶ በነበረው ተመሳሳይ የተማሪዎች ተቃውሞ ከ40 በላይ ወጣቶች ሲገደሉ፤ በርካቶች መጎዳታቸው አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ ተቃውሞውን አነሳስታችኋል ተብለው የታሰሩ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች አሉ፡፡ በተለይ ዛሬ ህዳር 23 ቀን 2008 ዓ.ም. በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ልደታ ምድብ ችሎት ከግንቦት 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ከነበሩት 6 ተማሪዎች መካከል 5ቱን ጥፋኛ ሲል መበየኑን እና እንዲከላከሉ ለማክሰኞ ጥር 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ መስጠቱን ታውቋል፡፡ ጥፋተኛ ተብለው እንዲከላከሉ ከተበየነባቸው ተማሪዎች መካከል አበበ ኡርጌሳ፣ መገርሳ ወርቁ፣ አዱኛ ኬሶ፣ቢሊሱማ ዳመነ እና ተሾመ በቀለ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ከተማሪ ተሾመ በቀለ በስተቀር የቀሪዎቹ አራቱን ተከሳሾች የዋስትና መብት ጥያቄ ውድቅ መደረጉንም የአዲስ ስታንዳርድ ዘገባ አመልክቷል፡፡
በጎንደር የ17 ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን መንግሥት ሲያምን፤ አንዱን የገደልኩት እኔ ነኝ ብሏል
በጎንደር ህዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በእስር ቤት ላይ በደረሰ ቃጠሎ የበርካታ ሰዎች ሕይወት መጥፋቱ ተነገረ፡፡ መንግሥት ከቃጠሎው ወቅት አንድ ሰው መግደሉን ሲያምን ሌሎቹ 16 ሰዎች ህይወት የጠፋው በቃጠሎው ወቅት ከ እስር ቤቱ ለማምለጥ ሲጋፉ ነው ብሏል፡፡
የአማራ ክልል ፖሊስ ለመንግስት ሚድያ በሰጠው መግለጫው በህዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በጎንደር ወህኒ ቤት ከቀኑ 7፡30 ሰዓት አካባቢ በተነሳ የእሳት ቃጠሎ እስረኞች ከቃጠሎው ለመውጣት በተደረገው ግፊያ የ16 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ አንድ ሰው ሊያመልጥ ሲል ከፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መገደሉን አምኗል፡፡

እንደ ዓይን እማኞች ከሆነ ሕይወታቸው ያለፈው ሰዎች ቁጥር ከ42 በላይ እንደሚሆን እና መንግሥት ቁጥሩን ዝቅ በማድረግ በእጁ የጠፉትን ቁጥር ወደ አንድ ብቻ ማሳነሱ እንዳሳዘናቸው ተናግረዋል፡፡ እንደ ዓይን እማኞች ገለፃ ከሆነ በቃጠሎው ወቅት መንግሥት በእስረኞች ላይ ጠከታታይ ተኩስ ከፍቶ እንደነበርና የእስረኞችንም ህይወት ለማትረፍ ማንም ወደ አቅራቢያው እንዳይጠጋ የጥብቃ ኃይሎች እና ፖሊሶች ማንም የውጭ ሰው እንዳይጠጋ ሲያስፈራሩ እንደነበር ጠቁመው፤ ከሞቱት መካከል አብዛኛው በመንግሥት እጅ የተገደሉ እንጂ ከእስር ቤት ከእሳት ለማምለጥና ለመውጣት ሲጋፉ እንዳልነበረ ተናግረዋል፡፡
ከሞቱት በተጨማሪ በቃጠሎው በርካታ እስረኞች ጉዳት እንደደረሰባቸውና በጎንደር ሆስፒታል የህክምና እርዳታም እየተደረገላቸው የተጠቆመ ሲሆን፤ የቃጠሎውን መንስኤና የተጎዱትንም ሆነ የሞቱን በተመለከተ እስካሁን በገለልተኛ አካል የተጣራ ነገር አለመኖሩ ታውቋል፡፡
በተለይ በሰሜን ጎንደር ዞን ከቃጠሎው በፊት ባሉት ቀናት የቅማንት ማኀረሰብ ባነሱት የመብት ጥያቄ ፖሊስ በወሰደው የኃይል እርምጃ እስካሁን በገለልተኛ አካልም ሆነ በመንግሥት ተጣርቶ ይፋ ባይደርግም በርካታ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውና የተወሰኑትም ምስሎቻቸውም በማኀበራዊ ሚዲያ ይፋ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡
የወህኒ ቤቱ ኃላፊ በቃጠሎውም ሆነ በመንግሥት ኃይሎች እርምጃ የሞተ ሰው የለም በሚል ለመንግሥት መገናኛ ብዙኃን መግለጫ የሰጡ ሲሆን፤ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ 16ቱ በቃጠሎው ወቅት በተፈጠረ መገፋፋት ሲሞቱ አንዱ ግን ሊያመልጥ ሲል በወህኒ ቤቱ ጥበቃ አባላት መገደሉን በማመን እስካሁን 17 ሰዎች መሞታቸውን አምነዋል፡፡ በተለይ በዞኑ ሰሜን ጎንደር መንግሥት በህዝቡ ላይ እየወሰደ ስላለው የኃይል እርምጃ እና በጎንደር ወህኒ ቤት በቃጠሎው እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት ሰዎች ቁጥር መደበቅና መቀነስ የተበሳጩ የጎንደር ዩኒቨርስቲ በተለይ ማራኪ እየተባለ በሚጠራው ግቢ የተማሪዎች ተቃውሞ መቀስቀሱን ተሰምቷል፡፡ በአሁን ወቅትም ተቃውሞው ወደሌሎች የዩኒቨርስቲው ግቢ እና ወደ ሌሎች የክልሉ ተቋማት ሊስፋፋ ይችላል በሚል ስጋት ዩኒቨርስቲው በመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች ተከቦ ጥብቅ ቁጥር እየተደረገበት መሆኑንም የአዲስ ሚዲያ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከአስመራ የትግል ሜዳ ወደ አውሮፓ መዲና ቤልጀም ብራሰልስ መጠራት
ብስራት ወልደሚካኤል
ፕሮፌሰሩ ለረቡዕ ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. (December 2, 2015) ከአስመራ ወደ ቤልጄየም ብራሰልስ የተጠሩት በሀገራችን ኢትዮጵያ ድርቅን ተከትሎ በተከሰተው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ውድቀት ወለድ ርሃብ ጉዳይ ላይ ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ንግግር፣ ምክክር እና ውይይት ለማድረግ እንደሆነ ይነገራል፡፡ የኢህአዴግ የ11 በመቶ የቁጥር ኢኮኒሚ ዕድገት ጋጋታ ገደል የከተተውና በምግብ ራሳችንን ችለናል መዝሙር ከአዳራሹ ነፋስ እንደወሰደው የሚያሳብቀው ከ15 ሚሊዮን በላይ ህዝብ በርሃብ አለነጋ ከመገረፍ አልፎ አስቸኳይ የምግብ ርዳት እንደሚያስፈልገው የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅቶች እና የተባበሩት መንግሥታት ይፋ አድርገዋል፡፡ ይሄንን እውነታ ለመደበቅ መንግሥት ከፍተኛ ወጪ በማውጣት ለማስተባበልና በርሃቡ ወደተጎ ዜጎች አካባቢ ሚዲያ ድርሽ እንዳይል እና እንዳይዘገብ በውስጥ መመሪያ መተላለፉንም ከሰማን ሰነበትን፡፡

ይሄ ሁሉ የራስን የጥፋት ገመና ለመሸፈን ሲባል ህዝብ ርሃቡ ከእኛ ቁጥጥር ውጭ አይደለም ሲባል ለሀገሬው ዜጋ በቋንቋው ሲነገር፤ ለዓለም አቀፍ ለጋሽ ሀገሮች ደግሞ በእንግሊዘኛ በሀገሪቱ ከፍተኛ የርሃብ አደጋ መከሰቱን እና በሀገሪቱ የእርዳታ ማስተባበሪያ የጠገኘው እህል ከአንድ ወር እንደማያልፍ በመግለፅ ተማፅኖውን ማሰማቱን ቀጥሏል፡፡ ይህንን ስንሰማ የኢህአዴግ መንግሥት አስተዳደር ኃላፊነቱ ለነጮች ነው ወይስ ለኢትዮጵያውያን የሚል ጥያቄ ቢያጭርም ከተለመድ የተለየ ነገር ግን የለም፡፡ ለዓመታት የተለመደ የመረጃ (ዳታ) ጋገራ መግለጫና ፕሮፖጋንዳ በተጨማሪ በግልፅ መረጃ ለማፈን ከፍተኛ በጀት መድቦ መንቀሳቀስ ከጀመረ እነሆ ከ10 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ልዕለ ኃያሏ አሜሪካም ብትሆን ከስርዓቱ ያላትን የፀጥታ ጉዳይ ትብብር (ወታደሮችን ለአላስፈላጊ እልቂት ማገዳ ካላት ስምምነት) አኳይ እንደ ጥሩ አጋር ብትቆጥርም የስርዓቱን አምባገነንነት፣ ዘረኛ አገዛዝ፣ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት አለመኖር፣ የፍትህ እጦት፣ ሙስና እና ተጠያቂነት የሌለው አሰራር የሚከተለው ስርዓት እንደሆነ ልትሸሽገው አልቻለችም፡፡

ይሁን እንጂ የአውሮፓ ህብረት የተለመደ ሰብዓዊ እርዳታውን በስሱም ቢሆን መለገሱን ባያቆምም የምንጊዜም የስርዓቱ ቀኝ እጅ የሆኑት እንግሊዝ፣ ጣሊያን እና አየርላንድ እንደድሮ ለስርዓቱ ሰዎች ፊት መስጠቱን የቀነሱ ይመስላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያን በሚመለከት በአውሮፓ ህብረት አሊያም በአውሮፓ ኢኮኖሚ ቅንጅት የጋራ አባል ሀገሮች በኩል ውሳኔ እንዲያልፍ እየተደረገ መሆኑን እየታዘብን ነው፡፡ ወቅታዊውን ርሃብ ለማስታገስና ለተጎዱ ወገኖች የሚደረው ሰብዓዊ እርዳታ እንኳ እንደቀድሞ በቀጥታ ለመንግሥት ከመስጠት ይልቅ በእርዳታ መልክ የተሰጠው ገንዘብ በሌሎች በጎ አድራጎት ድርጅቶች በኩል በቀጥታ ለተጎጂዎች እንዲደርስ የሚያስችል አሰራር እየተከተሉ እንደሆነ የስርዓቱ አጋር አሜሪካ እና በቅርቡም ስውድን የወሰደችው እርምጃ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ስርዓቱ በተለያዩ ለጋሽ ሀገሮች እንኳ እምነት እንደታጣበት እና የተለመደው የመረጃ ጋገራ ሪፖርትና ጋጋታ ፋይዳቢስ መሆኑን የተገነዘቡ ይመስላል፡፡
እነሆ አሁን ደግሞ የኢትዮጵያውን ርሃብ በተመለከተ ህዝባዊ ዓመኔታና ቅቡልነት ባይኖረው ኃላፊነት ያለበት መንግሥት እያለ ስርዓቱን ለመገርሰስ ከሚታገሉት መካከል ተዓማኒና ትክክለኛ መረጃና ትንታኔ ይሰጣሉ ተብለው ከታመኑት መካከል በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አማካኝነት ከአስመራ የትግል ሜዳ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተጋብዘዋል፡፡ በርግጥ ፕሮፌሰሩ ካላቸው የፖለቲካ ስብዕና በተጨማሪ በሙያቸው ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት ባለሙያና ተመራማሪ እንደመሆናቸው መጠን በስፍራው መጋበዛቸው የህብረቱ ትክክለኛ ምርጫ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ይሄ ደግሞ የስርዓቱን ሰዎች የበለጠ ምክንያታዊ መሸሸጊያ የሚያሳጣ ወቅታዊ የመረጃ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የሚገርመው በኢትዮጵያ ስም ስርዓቱን ወክሎ በቤልጀየም ከፍተኛ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር እያሉ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ መረጃና ትንታኔ እንዲሰጡ ከበረሃ የትግል ሜዳ የፕሮፌሰሩ መጋበዝ ለስርዓቱ ትልቅ ራስምታት ነው፡፡ ምክንያቱም ፕሮፌሰሩን እና የሚመሩትን የፖለቲካ ድርጅትና አባላት በሽብርተኝነት ለማስፈረጅ ለዓመታት በተለመደ የመረጃ ጋገራ ቢሞከርም በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ተቀባይነት አላገኘምና፡፡
በተለይ በመረጃ እና ሐሳቡን ለመግለፅ ለታፈነው የኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ አጋጣሚ ሲሆን፤ ለፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና ለሚመሩት ድርጅት እንደ አንድእመረታ ሊታይ ይችላል፡፡ እንደ አንዳንድ የስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጥቆማ ከሆነ መንግሥት ርሃቡን ከሀገሬው ሰው በመደበቅ ለጋሽ ሀገራት በተማፅኞ በማጨናነቅ ዕርዳታቸውን በጥሬ ገንዘብ ወይም ዶላር እንዲሆን እየሰራ እንዳለ እና ለዚህም ያቀረበው ምክንያት ገንዘቡ ከተሰጠኝ ከሀገር ውስጥ ነጋዴዎች እህሉን ራሴ ገዝቼ በማከፋፈል ጊዜና ጉልበት መቆጠብ እችላለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡ ይህ ለተጎጂዎች ታስቦ ሳይሆን መንግሥት በሀገሪቱ ከደረሰበት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት የተነሳ አጋጣሚውንም እንደ ጥሩ ዕድል ሊጠቀምበት እንዳሰበና እስካሁንም እንዳልተሳካለት ለስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ተጠቁሟል፡፡
በአሁን ወቅት ከአስከፊው ርሃብ በተጨማሪ በሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት በመከሰቱ የተለያዩ አስመጪዎች እና ኢንዱስትሪዎች ለአብነትም ቴክኖ ሞባይል የስልክ መገጣጠሚያን የመሳሰሉት ስራ ማቆማቸውም መነገር ከተጀመረ ሰነባብቷል፡፡ በዚህ ሁሉ የስርዓቱ አጣብቂኝ ውስጥ ፕሮፌሰሩ የበለጠ ተዓማኒነትና ተቀባይነት አግኝነተው በአውሮፓ ህብረት መጋበዛቸው በቀጣይ ምን ሊያሳየን ይሆን የሚለውን ወደፊት አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡