Category Archives: Social and Culture

የእንግሊዝ የፓርላማ ልዑክ አባላት በአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ለመደራደር ወደ ኢትዮጵያ ሊገቡ ነው

አቶ አንዳርጋቸው ባለፈው ወር ከባለቤታቸው ጋር በስልክ ተነጋግረዋል

አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ

አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ

የእንግሊዝ የፓርላማ አባላትን የያዘ የልኡካን ቡድን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከእስር ማስፈታት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለመደራደር በቀጣዩ ወር ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጣ የዘ ኢንዲፔንደንት ዘገባ አመልክቷል፡፡

ሁሉንም የእንግሊዝ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአባልነት የያዘው የፓርላማ አባላት የሰብዓዊ መብቶች ቡድን ምክትል ሊቀመንበር ጀርሚ ኮርባይን የሚመሩት የልኡካን ቡድኑ፣ ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ጋር በመምከር የሞት ፍርዱ ተፈጻሚ እንዳይሆንና ግለሰቡ ከእስር እንዲፈቱ ለማስቻል እንደሚሰሩ ዘገባው አመልክቷል፡፡አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንግሊዛዊ ዜግነት ያላቸው እንደመሆኑ የእንግሊዝ መንግስት ጉዳዩን አጽንዖት ሰጥቶ መከታተልና ግለሰቡን ከሞት ማዳን ይጠበቅበታል ያሉት ኮርባይን፤ ቡድኑ አቶ አንዳርጋቸው ግልጽ ባልሆነና ተቀባይነት በሌለው የህግ አካሄድ ለእስር ተዳርገዋል ብሎ እንደሚያምን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ አቶ እንዳርጋቸው የአሸባሪ ቡድን አባል ቢሆኑም በእስር ላይ ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው ሲል በተደጋጋሚ መግለፁ ይታወሳል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ባለፈው ነሐሴና ታህሳስ ወር ላይ ከተደረጉት ሁለት የመንግስት ተወካዮች ጉብኝቶች ውጭ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ለመጎብኘት እንዳንችል አግዶናል ብለዋል፡፡

የእንግሊዝ መንግስት የአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳስበው ገልጸው፣ በግለሰቡ ላይ የተጣለው የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እንዳይሆን በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና ማድረጉን እንደቀጠለበትም አስረድተዋል፡፡በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የኢትዮጵያን መንግስት ለማፍረስ የሚሰራ አሸባሪ ቡድን አባል ናቸው፣ በእስር ላይ ሆነውም ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው ነው፤ እስረኞችን ማሰቃየት ኢሰብአዊ ድርጊት እንደመሆኑ በዛሬዋ ኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ የሚደረግ  አይደለም ሲሉ መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናል በቅርቡ ይፋ ያደረገው ሪፖርት ግን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ከቅርብ አመታት ወዲህ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች የሚፈጸምባቸው ስቃይ እያየለ መምጣቱን የሚያመላክት መሆኑን አክሎ ገልጿል፡፡

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፤ ባለፈው ወር እንግሊዝ አገር ወደምትገኘው ባለቤታቸው ስልክ ደውለው መገናኘታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በአብዛኛው ስለልጆቻቸው ጉዳይ እንዳወሩ፣ ደህንነታቸውን እንደገለጹላቸው፣ እንዲሁም ለልጆቼ የማይሆን ተስፋ መስጠት አልፈልግም ማለታቸውን ባለቤታቸው እንደተናገሩ አመልክቷል ሲል አዲስ አድማስ ዘግቧል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ “ግንቦት 7” የተባለ የተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርጅት ዋና ፀሐፊ መሆናቸውና በኢትዮጵያና በየመን የደህንነት ኃይሎች ከየመን ታግተው መታሰራቸው ይታወቃል፡፡

አንድነት ፓርቲ የምርጫ ቦርድ ውሳኔን እንደማይቀበለውና በሁለት ሳምንት ውስጥ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ አስታወቀ

ከግራ ወደቀኝ የአንድነት ፓርቲ የወቅቱ አመራሮች አቶ በላይ ፈቃዱ፣ አቶ ግርማ ሰይፉ እና አቶ ዘካርያስ የማነብርሃን

ከግራ ወደቀኝ የአንድነት ፓርቲ የወቅቱ አመራሮች አቶ በላይ ፈቃዱ፣ አቶ ግርማ ሰይፉ እና አቶ ዘካርያስ የማነብርሃን

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራና ሪፖርቱን እንዲያቀርብ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ባለፈው እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ አድርጎ አቶ በላይ ፈቃዱን በድጋሚ የፓርቲው ፕሬዘዳንት አድርጎ መርጧል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው በድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ የሁለት ሳምንት ጊዜ መስጠቱን ተከትሎ አንድነት በድጋሚ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ ፓርቲው ጥር 8 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡

በተያያዘ ዜና የመላው ኢትዮጵ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)ም እንዲሁ እስከ ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ ምርቻ ቦርድ በሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. አድርጎ አቶ ማሙሸት አማረን ፕሬዘዳንት አድርጎ መምረጡ ቢታወቅም፤ ምርጫ ቦርድ በበኩሉ ድርጅቱ ድጋሚ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ የሉለት ሳምንት ጊዜ መስጠቱን አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ መኢአድ ምርጫ ቦርድ ፓርቲው በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ የሰጠውን ትዕዛዝና ያስተላለፈውን ውሳኔ እንደማይቀበለውና በድጋሚም ጠቅላላ ጉባኤ እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡

aeup

መኢአድና አንድነት ለሁለተኛ ጊዜ ጥር 3 ቀን 2007 ኣ.ም. ያደረጉትን ጠቅላላ ጉባኤ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንዲታዘብ ህጉ በመደንገጉና ፓርቲዎቹ በደብዳቤ ጥሪ ቢያደርጉለትም ምርጫ ቦርድ በሁለቱም ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ተወካዩን አለመላኩ ታውቋል፡፡

በተለይ አንድነት ፓርቲ ድጋሚ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማይጠራ ይፋ ከማድረጉ በተጨማሪ “ይህ በማን አለብኝ ሰሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሻንፍ የሚያደረግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡” ብሏል፡፡

የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-

udj

የመድብለ ፓርቲ ስርዓት እንዳይፈጠር የምርጫ ቦርድ ታሪካዊ ወንጀል እየፈፀመ ነው፡፡
———-
ከአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
የተሰጠ መግለጫ
————————-
የአንድነት ፓርቲ በኢትዮጵያ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት እንዲፈጠር በምንም መለኪያ በገለልተኝነት የማንጠብቃቸውን የዲሞክራሲ ተቋማት በተግባር ለመፈተን እንዲቻል የሁለት ሺ ሰባት ምርጫን በሁሉም ሂደቶች ህዝቡን በማሳተፍ እንደሚወዳደር እና ህዝብን የስልጣን ባለቤት ለማድረግ እና የኢህአዴግ አገዛዝ የመጨረሻ እንዲሆን በቁርጠኝነት እንደሚሰራ መወሰኑ ይታወቃል፡፡ ይህን ስንወስን እነዚህ ተቋማት ገለልተኝነታቸውን አረጋግጠው ታሪክ የሚሰሩበት እድልም ያገኛሉ የሚል ተሰፋ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ይህን እድል ከመጠቀም እና በህግ የተሰጠውን ኃላፊነት በብቃት ከመወጣት ይልቅ ለገዢው ፓርቲ ያለውን ወገንተኝነት በምርጫው ሂደት ዋዜማ በይፋ እያረጋገጠ ይገኛል፡፡ አሁንም ቦርዱ ወሰነ ተብሎ በሚዲያ የተገለፀው እንዲሁም ለፓርቲያችን በፅሁፍ የተሰጠው “በአስራ አምስት ቀን ውስጥ በጋራ ጉባዔ አድርጉ” የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ በተደጋጋሚ ፓርቲያችንን ደንብ እንዲያከብር እየጠየኩ ነው በማለት ከደንብ ውጭ እንድንሰራ የአዛኝ ቂብ አንጓች ሆኖዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ የመጥራት ኃላፊትን ያለበት የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ወይም ደግሞ በአባላት ጥያቄ የጠቀላላ ጉባዔ አባላትን አንድ ሶስተኛ ፊርማ አስባስበው በኦዲትና ኢንስፔክሽን ትዕዛዝ መሆኑ በግልፅ እየታወቀ ከፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ ውጭ በ15 ቀን ውስጥ ጉባዔ ጥሩ የሚል ትዕዛዝ፤ ቦርዱ ከገዢው ፓርቲ ጎን ተሰልፉ እየተጫወተ አንድነትን ከጫወታ ለማስወጣት ካለሆነ ሌላ ምንም ትርጉም ልንሰጠው አንችልም፡፡ ይህ ደግሞ ቦርዱ እየሰራ ያለውን ታሪካዊ ወንጀል ይፋ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህ በማን አለብኝ ሰሜት የተሰጠ ውሳኔ ሳይታረም ቢቀርና ገዢው ፓርቲ ያለምንም ጠንካራ ተቀናቃኝ ብቻውን ሮጦ ብቻውን እንዲያሻንፍ የሚያደረግ ተቋማዊ ሴራ ቦርዱን በታሪክ ተጠያቂ ማድረግ ብቻ ሳይሆን በዚህች ሀገር ዘላቂ ሰላም ላይ ለሚፈጠረው አደጋ ቦርዱ ከተጠያቂነት እንደማይድን ለማስታወስ እንወዳለን፡፡

በዚህ አጋጣሚ አንድነት ፓርቲ የሰላማዊ ትግሉን ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ እና ህዝቡን የስልጣን ባለቤት የማድረግ እንቅስቃሴውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና በቀጣይ ሳምንታትም በመንግሰትና በቦርዱ ላይ ጫና ማሳደሩን እንደሚቀጥልበት እያረጋገጥን አንድነት ፓርቲ ወደ ህገወጥነት የሚወሰደውን “የጋራ ጉባዔ” አካሂዱ የሚለው የምርጫ ቦርድ ውሳኔ የማንቀበለው መሆኑን ለመላው አባላትና ደጋፊዎች ማረጋገጥ እንወዳለን፡፡

ጥር 8 ቀን 2007

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

አቶ ብርሃኑ አዴሎ በቀረበባቸው ቅሬታ በድጋሚ ተነሱ

ዮሐንስ አንበርብር

 አቶ ብርሃኑ አዴሎ ከአዕምሯዊ ንብረት ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተርነት ኃላፊነታቸው በሕዝብ ቅሬታ ምክንያት እንዲነሱ ተደረገ፡፡ አቶ ብርሃኑ በሕዝብ ቅሬታ ምክንያት ከኃላፊነታቸው ሲነሱ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡

 

አቶ ብርሃኑ አዲሎ

አቶ ብርሃኑ አዲሎ

የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ሆነው ላለፉት ስምንት ዓመታት ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ብርሃኑ፣ ታኅሳስ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከጠቅላይ ሚኒስትሩ በተጻፈ ደብዳቤ ከኃላፊነታቸው መነሳታቸውን ውስጥ አዋቂ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተጻፈው ደብዳቤ አቶ ብርሃኑ ከኃላፊነታቸው የሚነሱበትን ምክንያት ባያብራራም፣ ከታኅሳስ 24 ቀን ጀምሮ መነሳታቸውን ይገልጻል፡፡ ተቋሙን በተጠባባቂ ዋና ዳይሬክተርነት እንዲመሩም የተቋሙ የፓተንት ክፍል ዳይሬክተር አቶ ግርማ በጅጋ ተሹመዋል፡፡

አቶ ብርሃኑ በአሠራር ችግሮች ከሠራተኞች ቅሬታዎች ይነሱባቸው እንደነበር፣ ከተቋሙ ደንበኞች ማለትም የንግድ ምልክት የሚያወጡ ወይም ምልክቶቻቸው እንዲከበሩ የሚፈልጉ የንግድ ተቋማትና ግለሰቦች ቅሬታ ይቀርብባቸው እንደነበር ምንጮች አስረድተዋል፡፡

እነዚህ ቅሬታዎች በቀጥታ ለተወካዮች ምክር ቤት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት እንደቀረቡ ምንጮች አስረድተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ችግሮቹን የሚያጣራ ኮሚቴ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት ተዋቅሮ የማጣራት ተግባራት ሲከናወኑ እንደነበሩ የሚያስታውሱት ምንጮች፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሯ ወ/ሮ ደሚቱ አንቢሳና የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አሚን አብዱልቃድር ከአጣሪ ኮሚቴ አባላቱ መካከል እንደነበሩም ገልጸው፣ ከኃላፊነት የተነሱትም ከዚሁ ጋር በተያያዘ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

አቶ ብርሃኑ እስከ 1998 ዓ.ም. ድረስ የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ ሚኒስትርና የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ነበሩ፡፡ በወቅቱ ከተወለዱበት የደቡብ ክልል ካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች አዲስ አበባ ድረስ በመምጣት በአቶ ብርሃኑ ላይ የተፈራረሙትን የቅሬታ አቤቱታ (ፔቲሽን) ለቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ማስገባታቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር የተቋቋመ አጣሪ ኮሚቴ ባቀረበባቸው ሪፖርት ከካቢኔ ጉዳይ ሚኒስትርነታቸውና ከኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልነታቸው እንዲነሱ መደረጉም አይዘነጋም፡፡

ጉዳዩን በተመለከተ አቶ ብርሃኑ አዴሎን ለማነጋገር በተደጋጋሚ የግል ስልካቸው ላይ በመደወል ለማግኘት የተደረገው ጥረት አለመሳካቱን በመጥቀስ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡

በአዲስ አበባ ኮልፌ የሚገኙ የአባት ጡረተኛ አርበኞች መኖሪያቸው እንዲፈርስ ተደረገ

Ethiopian elders patrioties

በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 09 እና 10 ውስጥ ከኃይለስላሴ ዘመን ጀምሮ በቀድሞ መንግስት በተሰጣቸው ካምፕ ውስጥ ሲኖሩ የነበሩ ከ500 በላይ የአባት ጡረተኛ አርበኞች ቤታቸው በመንግስት እንዲፈርስ በመደረጉ ከነቤተሰቦቻቸው ሜዳ ላይ መበተናቸውን ገለፁ፡፡

በተለምዶ ኮልፌ ልኳንዳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የሚገኘውንና ከጥንት ጀምሮ የአባት ጡረተኞችና የአርበኞች መኖሪያ የሆነውን የወታደር ካምፕ ቦታው ተከልሎላቸው የሰሩት ራሳቸው አርበኞቹ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ የገለፁ ሲሆን፤ ፈጽሞ ባላሰቡበትና ባልተዘጋጁበት ሁኔታ መኖሪያ ካምፓቸው ያለ ምንም ተለዋጪ ማረፊያ መሳሪያ በታጠቁ ወታደሮች እንዲፈርስ መደረጉ እንዳስደነገጣቸው  መናገራቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡  ነዋሪዎቹ  ውሳኔውን በመቃወም እስከ ፍትህ ሚኒስቴር ድረስ አቤቱታ ቢያቀርቡም  ሰሚ እንዳላገኙ ተጠቁሟል።

ካምፕ የሚገነው ቤታቸው ፈርሶ ሜዳ ላይ ከተበተኑትና የላስቲክ ድንኳን ሰርተው ከተጠለሉት ነዋሪዎች መካከል የኤች አይ ቪ/ ኤድስ ህመምተኞችና በርካታ ህጻናት እንደሚገኙበት ኢሳት በዘገባው አስታውሷል። የአካባቢው መስተዳድር አካላት ነዋሪውን ሊያነጋግሩ ሲመጡ የአርበኞቹ  ልጆች ባንዲራ እያውለበለቡ አባቶቻቸው በሞቱላትና ወደነሱ ባስተላለፉዋት ሀገራቸው የመኖር መብት ሊነፈጉ እንደማይገባና ያለ አማራጭ መኖሪያ ሜዳ ላይ መውደቅ እንደሌለባቸው አቤቱታ ቢያቀርቡም፤ የመስተዳድሩ አካላት ወጣቶቹ ባንዲራ በመያዛቸው ቁጣቸውን በመግለፅ ያለምንም መፍትሔ መመለሳቸውን ነዋሪዎቹ በሀዘን መናገራቸው ተጠቁሟል። አሁንም ነዋሪው የመንግስት ያለህ፣ያገር ያለህ እያለ ተማፅኖውን እያሰማ እንደሚገኝ የጥር 7 ቀን 2007 ዓ.ም.የኢሳት ዘገባ አመልክቷል።

በምርጫ 2007 ዓ.ም. ዋዜማ በአንድነት ፓርቲና በምርጫ ቦርድ መካከል የተደረጉ የደብዳቤ ልውውጦች ማስረጃ

በግርማ ሰይፉ ማሩ

(ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም.)

የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዓርማ

ከታህሳስ 19-20፡
*********
አንድነት ፓርቲ ታህሳስ 19-20/2006 ዓ.ም ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ አካሄድ፡፡ ይህ ጠቅላላ ጉባዔ ልዩ የተባለበት ምክንያት የአንድነት አምስት ዓመት ስትራቴክ ዕቅድ ላይ በተቀመጠው መሰረት ፓርቲ ከ2007 ዓ.ም ምርጫ ቀደም ብሎ የአመራር ሽግሽግ በማድረግ ፓርቲውን በአዲሰ አመራር ወደ ምርጫ ይዞ ለመግባት በተቀመጠ ግብ መሰረት ነው፡፡ በዚህ ጠቅላላ ጉባዔ ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው የፓርቲው ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጠዋል፡፡ ይህ ጠቅላላ ጉበዔውም የተለያዩ ውሳኔዎች አሳልፎዋል ከዚህ ውስጥ መሰረታዊ ሊባል የሚችለው ጉባዔው በሌለበት ወቅት ፕሬዝዳንቱን ማንሳት የሚያስችል ስልጣን ለብሔራዊ ምክር ቤቱ መስጠቱ ሲሆን ሌሎችም ለምሳሌ የወጣቶች፣ የሴቶች ጉዳይ ኃላፊዎች በስራ አስፈፃሚ ውስጥ እንዲካተቱ ያደረገ ሲሆን የተቀደሚ ፕሬዝዳንት ቦታም እንዲኖረው አድርጎዋል፡፡
አንድነት ፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔውን ባካሄደ በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ አመራሩ በሚጠበቅበት ፍጥነት አልሄደም በሚል አለመስማማት የተፈጠረ ሲሆን በአጋጣሚ አንድነት ከመኢህአድ ጋር የሚያደርገው ውህደት ጉዳይ ውይይት በመጀመሩና ለመጠናቀቅ አፋፍ ላይ የደረሰ ሲሆን ይህንንም አጋጣሚ በመጠቀም የውህዱን ፓርቲ የሚመራ የአንድነት ተወካይ ዕጩ ፕሬዝዳንት በብሔራዊ ምክር ቤት ተሰይሞ ውሕደት ይጠናቀቃል ሲባል ውህደቱ እንደማይቻል በምርጫ ቦርድ በኩል ይፋ ተደረገ፡፡ ኢ/ር ግዛቸው ሸፈራው በዚህ አጋጣሚ ተጠቅመው ለወጣት አመራር ቦታ ይለቃሉ ሲባል ይህን ከማድረግ ይልቅ ለውህደት በሚጠራው ጉባዔ በዕጩነት ለመሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውን ይፋ አደረጉ፡፡
ሐምሌ 14-30፡
*********
በኢንጅነር ግዛቸው የሚመራው ስራ አስፈፃሚ በታህሳስ 19-20 የተካሄደውን ጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት ገቢ ያደረገው 7 ወር ዘግይቶ ሐምሌ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ነበር፡፡ ብዙ ሰዎች ይህ ሪፖርት እንዲዘገይ የተደረገው በአዲሱ አመራር ስለሚመስላቸው ነው ይህን ነጥብ መግለፅ የፈለኩት፡፡ ይህን ሪፖርት መሰረት አድርጎ ምርጫ ቦርድ ሐምሌ 25 ቀን ዘጠኝ ነጥቦችን አንስቶ ማብራሪያ እንዲሰጠው ጠይቆዋል እነዚህም፤

በጉባኤው ዕለት በቀረበው ሪፖርት የገቡት አላሰፈላጊ ቃላት እንዲወጡ፤
የፓርቲው ባንዲራ እንዲቀርብ፤
ፓርቲው አሻሽሎ ባቀረበው አንቀፅ 8 ንዑስ አንቀፅ 2 ሰር የተዘረዘረው ሃሳብ ግልፅ አለመሆኑ፤
የጉባዔተኛው ቁጥር አለመገለፁ፤
የፕሬዝዳንቱን በብሔራዊ ምክር ቤት መመረጥ ከህግ አንፃር ያለው ጉዳይ በሚመለከት፤
የፓርቲው የገቢ ምንጭ በአዋጅ ቁጥር 573/2000 መሰረት ያለመቀመጡ፤
የፓርቲ መፍረስ በተመለከተ በአዋጅ ቁጥር 573/2000 መሰረት ያለመቀመጡ
የፓርቲው አባልነት በውርስ እንደማይተላለፍ አለመገለፁ፤ እና
ፓርቲው ያቀረባቸው የፓርቲ አካላት ውስጥ የሚሳተፉ አባላት አድራሻና በኃላፊነት ለመስራ የተሰማሙበት ሰነድ ያለመቅረቡ፤

የሚሉት ናቸው፡፡ ለእነዚህ ለቀረቡት ጥያቄዎች ሐምሌ 30 ቀን 18 ገፅ ያለው ማብራሪያ ተሰጧዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የመኢህአድና የአንድነት ውህደት አሰመልክቶ ከምርጫ ቦርድ ጋር በሚደረግ ውይይት በአንድነት በኩል ምንም ችግር እንደሌለ ነገር ግን ቦርዱ ሲሰበሰብ ውሰኔ እንደሚሰጥ በተደጋጋሚ ሲነገር ቆይቶ የመኢህአድ ጠቅላላ ጉባዔ ኮረም ሳይሞላ የተካሄደ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም በሚል ሰበብ ውህደቱ እንደማይሳካ በምርጫ ቦርድ ተገለጠ፡፡ ይህንንም ተከትሎ የአንድነት ስራ አሰፈፃሚ ኮሚቴ አባላት የነበሩ አምሰት ከፍተኛ አመራሮች በሰራ አሰረፃሚነት ላለማገልገል መወሰናቸውን ገልፀው መልቀቂያ ደብደቤ አሰገቡ፡፡ ኢንጂነር ግዛቸውም በምትካቸው ሌሎች አመራሮቸን በመሰየም ስራቸውን ለመቀጠል ሞከሩ፡፡
ጥቅምት 3፤
********
ኢንጂነር ግዛቸው ሸፈራው የብሔራዊ ምክር ቤቱን ጠርተው በጥቅምት ሁለት ካቢኔያቸውን ማሰናበታቸውን በመግለፅ ከውስጥና ከውጭ በደረሰባቸው ጫና ለፓርቲው እልውና ሲሉ ጠቅላላ ጉባዔ የሰጣቸውን ኃላፊነታቸውን ለመልቀቅ እንደወሰኑ ለምክር ቤት አቀረቡ፡፡ ምክር ቤቱም ኃላፊነት ለመልቀቅ መወሰናቸው ተቀብሎ ፓርቲው አመራር በቀጣይ እንዴት መሆን አለበት በሚል ባደረገው ከፍተኛ ውይይት ፓርቲው ለአንድ ቀንም ያለ አመራር ማድር እንደማያስፈልግ ታምኖበት ከዚህ በፊት የመኢህአድና አንድነት ውሕደት አስመልክቶ ለዕጩነት ሲንቀሳቀሱ የነበሩትን ጨምሮ ሌሎች ተጨማሪ ዕጩዎች በፈቃደኝነት ቀርበው ውድድር ተደርጎ በሚስጥር ደምፅ አስጣጥ በተደረገ ምርጫ አቶ በላይ ፍቃዱን በፕሬዝዳንትነት ሰየመ፡፡ በሳምንቱ ጥቅምት 10 ደግሞ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴውን ሰይሞ ስራውን በይፋ ጀመረ፡፡
ጥቅምት 19-21፤ የምርጫ ቦርድ ፅ/ቤት ምክትል ኃለፊ ጥቅምት 19 በተፃፈ ደብዳቤ አንድነት ፓርቲ ያደረገው የፕሬዝዳንት ምርጫ በታሕሳስ 19-20 በተደረገው ጉባዔ የተሻሻላው ደንብ በቦርዱ ባለፀደቀበት ሁኔታ ስለሆነ ተቀባይነት የለውም የሚል ስሜት ያለው ደብዳቤ ሲፃፍልን፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር ጥቅምት 20 የቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊ ጋር ለመነጋገር የፓርቲ ወኪሎች ስንሄድ የቦርዱን ጥቅምት 19 ያደረገውን 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ውሳኔ ደረሰን፡፡ ፓርቲያችን ሁለቱን ደብዳቤዎች መሰረት አድርገን ከቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊ ጋር ባደረግነው ውይይት ቦርዱ በጥቅምት 20 ላቀረባቸው ጥያቄዎች መልስ ስጡ ዋናውም የቦርዱ ጥያቄ ነው ተብለን በመግባባት መንፈስ ተለያየን፡፡ ቦርዱ ጥቅምት 19 ተሰብስቦ ለፓርቲያችን ያቀረበልን ጥያቄዎች፤
1. ሪፖርቱ ለምን 7 ወር ዘገየ፤
2. የጠቅላላ ጉበዔ አባላት ቁጥር በደንቡ ውስጥ የለም እና
3. የፕሬዝዳንት መረጣ ለማድረግ ጠቅላላ ጉባዔ ለብሔራዊ ምክር ቤት ውክልና የሰጠበት አግባብ ከዲሞክራሲያዊነት እና ከአባላት ተሳትፎ አንፃር ማብራሪያ ይፈልጋል፤
የሚሉት ናቸው፡፡
ለእነዚህ የቦርዱ ጥየቄዎች እና ጥቅምት 19 በቦርዱ ምክትል ኃላፊ ለቀረቡት ህገወጥ ጥያቄዎች መልስ አዘጋጅተን ጥቅምት 21 2007 ዓ.ም ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ አደረገን፡፡
ህዳር 10 -19/2007፤
*************
የምርጫ ቦርድ በጥቅምት 20 ላቀረባቸው ጥያቄዎች በጥቅምት 21 ለሰጠነው መልስ ገምግሞ የሚከተሉትን ውሳኔዎች የያዘ ደብዳቤ ህዳር 10 2007 ዓ. ም ለፓርቲያችን እንዲደርስ አደረገ፡፡ እነርሱም
1. ሪፖርት መዘግየቱ አግባብ ያለመሆኑን ጠቅሶ ለወደፊት ሪፖርቶች በወቅቱ ገቢ እንዲደረግ፤
2. የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር ተወስኖ በደንብ ውስጥ መግባት እንደሚያስፈልግ እና
3. የፕሬዝዳንቱን ምርጫ አስመልክቶ ጠቅላላ ጉባዔው ለብሔራዊ ምክር ቤት ውክልና የሰጠበትን አግባብ በቅንንት እንደሚያየው ገልፆ፤
በተራ ቁጥር 2 ለተጠየቀው ጥያቄ መልስ ሲቀርብ ውሳኔ እንደሚሰጥ የሚጠቅስ ነበር፡፡
ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር 320 እንደሆነ እና ከዚህ ውስጥ 161 ሲገኝ (ሃምሳ ከመቶ በላይ)ምልዓተ ጉባዔ እንደሆነ ገልፀን ለቦርዱ አስገባን፡፡ በዚሁ መሰረት መልስ ይሰጡናል ብለን ስንጠብቅ፣ በቦርዱ በኩል ደግሞ ዝምተው ስበረታብን የቦርዱን ፅ/ቤት ኃላፊ እንዲሁም የቦርዱን ሰብሳቢ ሰናነጋግር ደንብ የሚሻሻላው በደብዳቤ ሳይሆን ይህን ማድረግ በሚችለው በጠቅላላ ጉባዔው መሆኑን በተዘዋዋሪ ገለፁልን፡፡ በዚህ ውይይት ዘወትር የሚሰጠን ምክር አርፋችሁ ለምርጫ ዝግጅት አድርጉ እኛ በቅንንት ነው የምናየው የሚሉ የማግባቢያ ንግግሮች ነበሩት፡፡ ይህንን ግን በፅሁፍ እንዲያደርጉት ባደረግነው ጉትጎታ ህዳር 19 ቀን ቦረዱ ያለውን የመጨረሻ ጥያቄ በፅሁፍ ሰጠን፡፡ ይኽውም የጠቅላላ ጉባዔ አባላትን ቁጥር በደንብ ውስጥ አካቱና አምጡ የሚል ነው፡፡ ቦርዱ ከዚህ በኋላ ባደረገው የደብደቤ ልውውጥ የህዳር 10 እና ህዳር 19 ደብዳቤ ሆን ተብሎ አይጠቅስም፡፡ የቦርዱን ቅንነትና ሆደ ሰፊነት የሚለውን አባባል ያልተመቻቸው አባላት ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ተጠርተው ለጉዳዩ መቋጫ ለመስጠት በመወሰን ጉባዔ እንዲጠራ ተወሰነ፡፡
ታህሳስ 3-4፤
*********
የአንድነት ፓርቲ በቦርዱ በቀረበለት ጥያቄ መሰረት የጠቅላላ ጉባዔ ኮረም በደንብ ውስጥ ለማስገባት ብቻ መጥራት ተገቢ አይደለም በሚል እምነት ከጉባዔ አባላት ቁጥር ከማካተት በተጨማሪ ያሉ የዞን አመራሮችን ጨምሮ በምርጫ ጉዳይ ላይ ሰፊ ውይይት የሚያደርግበት በፓርቲያችን ላይ በምርጫ ቦርድ በኩል በሚዲያ እየተፈጠረ ያለውን ብዥታ ለማጥራት የሚያሰችል ደማቅ ጉባዔ ተካሄደ፡፡ መፈክራችንም “ምርጫ 2007 ለለውጥ” የሚል ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የተቃዋሚዎች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ያሸበረቀ ጉበዔ አካሄደን የሚከተሉትን ውሳኔዎች ጉባዔ አሳለፈ፤
1. የጠቅላላ ጉባዔ አባላት ቁጥር 320 እንዲሆን እና ኮረም 50 ከመቶ ሲደመር አንድ እንዲሆን፤
2. የብሔራዊ ምክር ቤቱ የፓርቲውን ፕሬዝዳንት ለመምረጥ የሄደበት መንገድ ህገ ደንባዊ መሆኑን፤
3. በቀጣይ ምርጫ ቦርድ በጠቅላላ ጉባዔው ውሳኔ ላይ ጥያቄ የሚያነሳ ቢሆን ብሔራዊ ምክር ቤቱ የጠቅላላ ገባዔውን ወክሎ ምላሽ እንዲሰጥ የሚሉት፤
ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ታህሳስ 10፤
**********
የጠቅላላ ጉበዔውን ሪፖርት ታህሳስ 10 ቀን 2007 ዓ.ም ለቦርዱ ፅ/ቤት ገቢ የተደረገ ሲሆን ቦርዱ ይህንን ችላ በማለት ፍፁም ኃላፊነት በጎደለው ሁኔታ በዕለቱ ምሽት የቦርዱ ኃላፊዎች በሚዲያ ቀርበው በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ችግር እንዳለ የሚገልፅ መግለጫ ይሰጣሉ፡፡ በማግስቱ ቅዳሜ ደውለው ደብዳቤ እንድንወስድ ይነግሩናል፡፡ በታህሳስ 10 ቦርዱ ተሰብስቦ በወሰነው መሰረት የጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት በ7 ቀን ውስጥ እንድታስገቡ የሚል ነበር፡፡ ይህን ደብዳቤ አስመልክቶ እና በሚዲያ የሰጡትን መግለጫ አስመልክቶ ከቦርዱ ስብሳቢ ጋር ባደረግነው ውይይት ያቀረብነውን ሪፖርቱን በአጭር ጊዜ ተሰብሰበው ውሳኔ እንደሚሰጡት መግለጫ በክፋት ሳይሆን በቅንንት እንደሆነ ይገልፁልናል፡፡ ይህ እንደማይሆን ግን ምልክቶች እያየን ነበር፡፡ የቦርዱ ፅ/ቤት ኃላፊና ምክትላቸው በተለያየ መልኩ ከፓርቲያችን ውስጥ ቅሬታ ተሰምቶናል የሚሉ ህገወጦች ጋር በቢሮዋቸው እንደሚዶልቱ እየሰማን ነበር፡፡ በግንባርም በኃላፊው ቢሮ ከግለሰቦቹ ጋር ሲመክሩ አግኝተናቸዋል፡፡
ታህሳስ 27 -30፡
***********
ቦርዱ ተሰብሰቦ ያቀረብነውን ሪፖርት መርምሮ መልስ ይሰጣል ብለን በቅንንት ስንጠብቅ ታህሳስ 26 እሁድ በስልክ ተደውሎ የቦርዱ ኃላፊዎች ለውይይት እንደሚፈልጉን ይነገረናል፡፡ የዚያኑ እለት እሁድ በፓርቲያችን ለሆዳቸው ያደሩ ባንዳዎች አራት ኪሎ በሚገኝ ካፍቴሪያ ተሰብሰበው ፊርማ ተፈራርመው ለቦርዱ ገቢ አድርገዋል፡፡ በእሁድ ቀን ማለት ነው፡፡ ታታሪው ምርጫ ቦርድ አንድነትን ለማናጋት እሁድን ጨምሮ ሌት ከቀን ይሰራል፡፡ ታህሳስ 27 ቀን 2007 ዓ.ም ቦርዱ ፅ/ቤት ስንገኝ ካሜራ ደቅነው ከአቶ የማነአብ አሰፋ እና ከአቶ አየለ ሰሜነህ ጋር “ውይይት” እንድናደርግ ግብዣ ያደርጉልናል፡፡ ዓላማው በምሽት ቦርዱ ሊሰጠው ላሰበው ውዥንብር መፍጠሪያ መግለጫ የቪዲዮ ግብዓት ለማግኘት የነበረ ሲሆን መኢህአዶች በየዋህነት በቪዲዮ ተቀርፀው ሲቀርቡ እኛ ከእነዚህ ሰዎች ጋር በምርጫ ቦርድ መድረክ የምናደርገው ውይይት እንደሌለ፤ ቦርዱ ያሰገባነውን ሪፖርትና ግለሰቦች ያቀረቡትን ሪፖርት መርምሮ ውሳኔውን እንዲያሳውቅ ብቻ መሆኑን ገልፀን ተመለስን፡፡ በምሽቱ የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ የውስጥ ችግራቸውን እንዲፈቱ ልናስማማቸው ሞክረን አልተሳካም፤ የታህሳስ 19-20 ሪፖርት 7 ወር አዘግይተው አስገብተዋል፤ የፕሬዝዳንቱ ምርጫ ህገወጥ ነው፤ የሚሉ መግለጫዎችን በመስጠት ህዝቡን ብዥታ ውስጥ ለመክተት ሞከሩ፡፡ ይህን ሲያደርጉ ቦርዱ ስብሰባ የተጠራው ለታህሳስ 28 ሲሆን ቦርዱ ከመሰብሰቡ በፊት በቅድሚያ በማን አለብኝነት የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ የግል ውሳኔያቸውን አስታውቀው ለቀሪዎቹ የቦርድ አባላት ዋጋ ቢስነት በህዝብ ፊት አረጋገጡ፡፡
በታህሳስ 28 በምሳ ሰዓት ተደውሎ የቦረዱን ውሳኔ ለመስማት በ9፡00 ሰዓት እንድንገኝ ጥሪ ተደርጎልን ስንሄድ ገዛኽኝ አዱኛ የሚባል የወረዳ ስድሰት አባል እና እራሱን የወረዳ ሰድስት ዕጩ አድርጎ ያቀረበ 10+1 ያጠናቀቀ እና ሰፊው የሚባል የወረዳ 7 አባልና አራሱን ለ2007 ምርጫ የወረዳ 7 ዕጩ አድርጎ አቅርቦ ያልተሳካለት አኩራፊ አኩራፊ የአንድነት አባላትን ወክለው እንዲገኙ በአኩራፊዎች ተወክለው ነበር፡፡ ይህ ቡድን ምርጫ ቦርድ ከመምጣቱ በፊት በአምባሳደር መናፈሻ ድራፍት ቢራ እየተጎነጩ በአቶ ትዕግሰቱ አውሎም መመሪያ ሲሰጣቸው ነበር፡፡
ቦርዱ ፅ/ቤት ያለውን ሁኔታ ስንረዳው አሁንም ለኢቲቪ የቪዲዮ ግብዓት ለማግኝት ካልሆነ ትርጉም እንደሌለው በመረዳታችን የቦርዱ ውሳኔ በፅሁፍ እንዲሰጠን ጠይቀን ወደ ቢሮዋችን ተመለስን፡፡ በምሽት ዜና እና በቅርቡ በከፍተኛ ወኔ ገዢውን ፓርቲ ለመከላከል የቆመው የኢህአዴግ ሚዲያ የሆነው ሬዲዮ ፋና የቦርዱ ውሳኔ ነው ያሉትን ነገር ግን ቦርዱ ከመሰብሰቡ በፊት በቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ በሚዲያ የተነገረውን ውሳኔ በትንተና አቀረቡት፡፡ የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጊያም ከንፈራች እስኪደርቅ ድረስ አንድነት ላይ አለ የሚሉትን ክስ ሁሉ አዘነቡት፡፡ ታህሳስ 29 የገና በዓል በመሆኑ ታህሳስ 30/ 2007 ዓ.ም ጠዋት ማልደን ምርጫ ቦርድ ተገኘተን በሚዲያ የነዙትን ክስ በፅሁፍ እንዲሰጡን ስንጠይቅ ደብዳቤ እየተዘጋጀ እንደሆነ ገልፀውልን በ5፡00 ሠዓት ደብዳቤ ሰጡን፡፡ አባላቶቻችን ቁጭ ብሎ ተረቆ የተፃፈ ደብዳቤ አስገራሚው በሆነ ሁኔታ በታህሳስ 28 ተደርጎ ወጭ እንዲሆን ተደርጎ ቀን ተፃፈበት፡፡ እዚህ ጋ የቦርድ ኃላፊዎች የበታች ሰራተኞችን ምን ያህል ከህግ ውጭ እንደሚያሰሩ ነው፡፡ የቦርዱ ፅ/ቤት ምን ያህል ለመዋረድ እንደተዘጋጀ የሚያሳይ ነው፡፡ ለማነኛውም ታህሳስ 30 የደረሰን ደብዳቤ አራት ነጥቦች ያሉት ለማስመስል ቢሞክርም ሁለት ጥያቄዎች ናቸው ያሉት፡፡ እነርሱም
1. የታህሳስ 19-20 ሪፖርት ለምን ዘገየ የሚል እና
2. የፕሬዝዳንቱ ምርጫ የፓርቲውን ህገ ደንብ የተከተለ አይደለም የሚል ነው፡፡
የሚያሳዝነው ነገር ቦርዱ የታህሳስ 3 ቀን 2007 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባዔ ሪፖርት ለመመርመር ተሰብሰቦ የታህሳስ 19-20/2006 ዓ.ም ሪፖርት ለምን ዘገየ ማለቱ ብቻ ሳይሆን በቅንንት ተቀብዬዋለሁ ያለውን የፕሬዝደንት ምርጫ በድጋሚ ማንሳቱ ነው፡፡ በግልፅም ቦርዱ የአንድነትን ሪፖርት በጥልቀት ገመገምኩ ይበል እንጂ እንዳልገመገመው ማሳያ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቦርዱ ወሰነ የተባለው እና የቦርዱ ምክትል ሰብሰቢ ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ የሰጡት መግለጫ መመሳሰል ብቻ ሳይሆን ቦርዱ ሊመረምረው ከተቀመጠው ሪፖርት ይዘት የወጣ ውሳኔ አሳለፈ መባሉ ነው፡፡
ስለዚህ የታህሳስ 19-20/2006 ዓ.ም ሪፖርት ለምን ዘገየ ከአሁን በፊት በቂ መልስ ተሰጥቶታ ቦርዱ እንደተቀበለው ማስታወስ እና አንድነትም በተከታይ ባደረገው ጠቅላላ ጉባዔ በሰባት ቀን ሪፖርት ማስገባቱ ነው፡፡
ጥር 1-3፤
********
አንድነት ፓርቲ ለመጨረሻ የደረሰው ደብደቤ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ 11፡45 (ከሰራ ሰዓት ውጭ) የደረስን ህገወጥ ደብዳቤ በጥር 3/2007 ዓ.ም ለሚደረገው ጠቅላላ ጉባዔ የምርጫ ቦርድ ታዛቢ መላክ እንደማይችሉ ገልፀው ለዚህም የሰጡት ሰበብ በእነ አየለ ሰሜነህ የሚመሩ አባላት ሌላ ጠቅላላ ጉባዔ በሳሬም ሆቴል በመጠራቱ ሁለት ቦታ ጉባዔ ታዛቢ መላክ አልችልም የሚል ነው፡፡ በመሰረቱ የምርጫ ቦርድ በእጁ በሚገኝው የፓርቲያችን ደንብ አባላት ጠቅላላ ጉባዔ ሊጠሩበት የሚችሉበት ስርዓት በግልፅ ተቀምጦ እያለ ከዚህ ውጭ የፓርቲውን ጉባዔ ለማደናቀፍ ምን ያህል እየተሰራ እንደሆነ ግልፅ ማሳያ ነው፡፡ አንድነት በማግስቱ መገኘት ባይፈልጉም ጉባዔው በተያዘለት ፕሮግራም መሰረት እንደሚቀጥል ጥር 2/2007 ዓ.ም እንዲያውቁት ተደርጎዋል፡፡ በዚሁ መስረት አድነት ጥር 3/2007 ዓ.ም በደማቅ ሁኔታ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ ይህን መስመር የፃፍኩት ጉባዔዬው አመስራጭ ኮሚቴ ሰይሞ ሲያጠናቅቅ ነው፡፡ ትግሉ ይቀጥላል……….. የደብዳቤው ልውውጥም ይቀጥላል፡፡ ይህ ታሪካዊ ዘገባ ይሆናል፡፡