Category Archives: Social and Culture

“ክርስትና ዘውድ ሰጣቸው፥ ክርስትና ነጠቃቸው” ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

ያሬድ ሹመቴ

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

በምስጋናው ታደሰ የተደረሰውን “ሚካኤል ንጉሰ ወሎ ወትግሬ” የተሰኘውን አዲስ መጽሐፍ ለመመረቅ ጥቅምት 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በደሴ አይጠየፍ አዳራሽ የተገኙ ምሁራን ማራኪ ሀሳቦቻቸውን በመድረኩ አቅርበዋል። ከአቅራቢዎቹ መሀል ለዛሬ የዶክተር ዳኛቸውን ውብ ገለፃ ለንባብ እንዲመች አድርጌ በማቀናበር እነሆ በዝርዝር አቅርቤላችኋለሁ።(ያሬድ ሹመቴ)

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ “እንግዲህ ንግግሬን የምጀምረው እንደ ጥሩ “ወሎዬ” በግጥም ነው። ገጣሚ ስላልሆኩ የኔን ሀሳብ የሚገልጸውን የቀኝ አዝማች ምስጋናው አዱኛን የተወሰነ ስንኝ ተውሼ ልጀምር።
‘በጣሙን ጨነቀኝ ልቤ ተበትኖ፥
እንጀራዬ ሸዋ ቤቴ ጎንደር ሁኖ።’
የዚህ ስንኝ መንፈስ የኔን አመለካከት ይገልጽልኛል ብዬ ስለማምን የሳቸውን ትከሻ ተንተርሼ እጀምራለሁ።
‘በጣሙን ጨነቀኝ ልቤ ተበትኖ፥
ውሎዬ ሸዋ ላይ ልቤ ወሎ ሁኖ።’
ብዬ እጀምራለሁ።

አልፎ አልፎ ከምስጋናው ጋር ስለዚህ መጽሐፍ በስልክ ስናወራ እኔ “ራስ ማይክ” ብዬ ስጠራው እሱ ደግሞ “የሰገሌው” ብሎ ይጠራኛል። ሁለቱም ምክንያት አላቸው። እሱ ስለ ራስ (የኃላው) ንጉስ ሚካኤል ስለጻፈ፥ ራስ ገብረየስ የተባሉ የኔ ቅድመ አያት ከዚች ቦታ [አይጠየፍ] ተነስተው ከራስ ሚካኤል ጋር አብረው ሰገሌ ዘምተው [በኃላ በራስ ካሳ ስር እስረኛ ሁነው ቢመለሱም] ወሎየነቴ ሰገሌን ያልፋል ለማለት ነው እንጂ እንዲያው በዚህ ሳልፍ እግረ መንገዴን ወሎዬ ነኝ አላልኩም ለማለት ነው።
ወሎዬ ነኝ ስል፥ አደራችሁን፥ ሰሜን ወሎ ነኝ አላልኩም። ደቡብ ወሎ አላልኩም። አርጎባም አላልኩም። ከሚሴ ነኝም አላልኩም። ሚሌም ነኝ አላልኩም። በደፈናው ወሎዬ ነኝ ነው ያልኩት።

እንግዲህ እንጀምር፡-
ትልቁ የጀርመን ፈላስፋ ሄግል አንድ ቦታ ላይ ስለ ታሪክ እንዲህ ይላል። ‘አፍሪካ በደፈናው ታሪክ የላትም። ይህንንም ስል ምክንያቴ ስለማትጽፍ ነው’ ይላል። በሱ አነጋገር ‘እንዲያውም ትንሽ ታሪክ ላይ የደረሱት አረቦቹ ናቸው። እነሱ ይጽፋሉና’ ይላል። እኛ ኢትዮጵያዊያን እንደምንጽፍ ሄግል አያውቅም። የምስጋናው መጽሐፍ ለዚህ መልሱ ነው። የንጉስ ሚካኤልና የወሎ ታሪክ ባይፃፍ ኖሮ ተረት ተረት ሆኖ ነበር የሚቀረው።

ሁላችንም ቤት ውስጥ [ይህ ታሪክ] የአፍ ብቻ ታሪክ ሆኖ ተቀምጦ ኖሯል። “ካልተጻፈ ታሪክ የለም።” መጻፍ መዘገብ ካልቻለ በአፍ ያለው ጠፍቶ ተረት ተረት ሆኖ ይቀራል። ታሪክ ከጽሁፍ ጋር የተቆራኘ በመሆኑ መፃፍ አለበት። ለዚህ ደግሞ ምስጋናው ተገቢ መልስ በመስጠቱ ባለውለታችን ነው የሚል እምነት አለኝ።
ሌላው ከክርስቶስ ልደት 600 ዓመት በፊት የነበረው ታላቁ ግሪካዊው የታሪክ ቀመር መስራች ሱሲዲየስ ምን ይላል? ‘ታሪክን ለመፃፍ የሚነሳ ሰው ቢያንስ ቢያንስ አርባ አመት ቢሞላው ይመረጣል’ ይላል። ‘ፀሀፊው እድሜው የጠና ካልሆነ እንዲሁ የሆነውን ያልሆነውን እየጻፈ ህዝብ ያበጣብጣል።’ ሲል ያክላል።

በአንድ በኩል እውነቱን ነው። ባለፉት ከ25 እስከ 30 ዓመታት ውስጥ የወጡትን “የታሪክ ድርሳናት” ስንመለከት መርዶ አቅራቢዎች ናቸው። ‘በእንዲህ ያለ ጊዜ እንዲህ እና እንዲያ ተደርገሀል፥ በእንዲህ ያለ ቦታ እንዲህ ተደርጎብሀል’ እየተባለ ይፃፋል። ታሪክ የተወሳሰበ ዲሲፕሊን ነው። ከመርዶ ነገራ በእጥፉ ይለያል።

በተጨማሪም ታሪክ ከመርዶ ነገራ አልፎ የርዕዮተ ዓለም እና የፖለቲካ አሽከር በሚሆንበት ጊዜ ብዙ ጣጣ ይመጣል። ርዕዮተ አለሙ ይቀድምና ታሪክ የበታችነትን ቦታ ትይዛለች። ይሄን ልጅ (ምስጋናው) ከዚህ አንፃር ስናየው 40 ዓመት ገና አልሞላውም። እንዲያውም አንድ ሰው ለአንድ ጓደኛዬ ’40 አመት ያልሞላው ሰው ታሪክ መፃፍ የለበትም ብሏል ዳኛቸው። እድሜው ያልደረሰውን ምስጋናው የፃፈውን መጽሀፍ ለመመረቅ ለምን ሄደ?’ ብሎ ጠይቋል። ስለ ታሪክ አረዳድ፥ ስለታሪክ ምርምር እና ስለ ታሪክ ትንተና እስከ ከፍተኛ ትምህርት ደርሶ የተማረው ምስጋናው፥ ትምህርቱ ባበረከተለት እውቀት የእድሜውን ማነስ ተሻግሮታል ብዬ አምናለው። እውቀት የእድሜን ክፍተት ይሞላልና።

የዚህ መጽሀፍ ንባብ ሲጀመር ገና ከጠዋቱ ጥያቄዎች ተጀምረዋል። አንዱ ‘የኔን አያት በደንብ አልፃፋቸውም’ ሲል ሌላው ደግሞ ‘የኔ ቅድም አያት ሊቀ መኳስ እከሌን አሳንሶ ጽፏቸዋል’ [እንዲህ እንዲያ] ወዘተርፈ ይላል። ለዚህ ደግሞ አጭሩ መልስ፥ የታሪክ ጸሀፊ ሊዘግበው በተነሳው ርዕስ ዙሪያ ሁሉንም ምንም ሳይተው አጠቃላይ ዘገባ ማቅረብ በፍፁም አይቻለውም። በመሆኑም የታሪክ ዘገባ የሚከናወነው ወሳኝ የሚላቸውን ጉዳዮች በመምረጥ እንጂ ሁሉንም በማካተት ሊፃፍ አይችልም።

[ሌላው ጉዳይ] ታሪክን ከአንድ ከማይላወስ እና ከማይነቃነቅ መድረክ ላይ ሆነን የምንረዳው እውነታ አይደለም። ታሪክ ምን ግዜም ተለዋዋጭ እና ፈሳሽ መሆኑን ማጤን ተገቢ ነው። ለምሳሌ የመንግስቱ ነዋይን ግርግር ደርግ ከመምጣቱ በፊት ያጠና ሰው የወታደር መፈንቅለ መንግስትን የሚያይበት አተያይ አለው። ከነመንግስቱ ነዋይ በኋላ የወታደር መንግስት 17 ዓመት በስልጣንከቆየ በኋል የመንግስቱ ነዋይን ታሪክ የሚያጠና ሰው አተያዩ በጭራሽ እንደ መጀመሪያው አይሆንም። ስለዚህ ታሪክን ከተለዋዋጭነቱ ሁኔታ አንጻር ማየት የግድ ይላል።

በሌላ መልኩ ደግሞ ዋናው የቀደመ ታሪክን ለመረዳት፥ የጀርመን ፈላስፋዎች እንደሚሉት አሁን ባለንበት በኛ ዘመን እና ባለፈው ዘመን መካከል የአተያይ አድማሳት ዑደትን ማግኘት ተገቢ ነው። (fusion of horizon)በመሆኑም 21ኛው ክፍለ ዘመን ላይ ሆነን 19ኛውን ክፍለ ዘመን ለመረዳት ሀሳባችንን መንፈስና ቀልባችንን ወደ ዘመኑ መላክ ተገቢ ነው። ያለፈውን እሴት ወግ እና መቼት በሚገባ ካላጠናን፥ የኛን ዘመን የአመለካከት ዘይቤ ብቻ ይዘን ያንኛውን ዘመን ልንረዳው አንችልም። በመንፈስ ልናጠናው ወደ ፈለግነው ዘመን እስካልተጠጋን ድረስ ያ ዘመን ለኛ ምን ግዜም ባይተዋር ሆኖ ይቀጥላል።

ከዚህ አኳያ ስንመለከት የምስጋናው ታደሰ መጽሐፍ ከመቶ አመታት በፊት የተካሄደውን የታሪክ ሂደት ከውጭ ሆኖ ሳይሆን በጊዜው እንዴት ያስቡ እንደ ነበርና የአመለካከት አድማሳቸውን በተገቢ አውድ በማስቀመጥ አቅርቦታል።
ወደ ሌላ ነጥብ ስናልፍ፥ ስለ መሪዎቻችን በምናወሳበት ጊዜ በአንድ ወጥ ትረካ መሪዎቹን አናገኛቸውም። እንደ ምሳሌም መምህር አለማየሁ ሞገስ ‘መልክዓ ኢትዮጵያ’ ላይ ከሰበሰቧቸው ስነ ቃሎች መሀል አፄ ቴውድሮስ ሲሞቱ የተገጠመላቸውን ሙሾ ላንሳላችሁ።

“ከመላክ ከሰይጣን እግዜር የሰራው…
….ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ
የመጨረሻው ቀን ግስላ ሆኑና ታነቁና ሞቱ’
‘ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ’ የሚለውን ያዙልኝ።

ሁሉም መሪዎቻችን ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ ናቸውና። በአንድ ቁንጠራ አንፍረዳቸው። ሚካኤል ስንል የዓድዋውን ሚካኤል ማስታወስ ሊኖርብን ይገባል። ሚካኤል ስንል ይህንን ወሎ የተባለውን ሀገር ያቆሙልንን ልናወሳ ይገባል። ሚካኤል ስንል ደግሞም ከአፄ ዮሀንስ ጋር ሆነው በኃይማኖት ጉዳይ ችግር የፈጠሩትን ልናነሳ እንችላለን። ይሄንን መቀበል ይኖርብናል። አንዷን ብቻ ይዘን ሚካኤል ይሄ ነው ለማለት በጣም አስቸጋሪ ይሆንብናል።

አፄ ቴውድሮስ ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ እንደተባሉት ማለት ነው። እዚህ መሀል ጎንደሬዎች ካላችሁ እንዳትቀየሙ። ስለሳቸው ከጀግንነት ውጪ ያወራ ሰው ሊሰዋ ይችላል ተብሏል አሉ። (ከፍተኛ ሳቅ)
ወደ ሌላ ወሳኝ ጉዳይ ስናመራ፥ ከወሎ ባህል ያፈነገጠውን ሙስሊሞችን ክርስቲያን የማድረግ ዘመቻ – የአፄ ዮሐንስ ፖሊሲን እናገኛለን። ምስጋናው በመጽሀፉ ምንም የደበቀው ነገር የለም። እንዲያውም ‘አራት እና አምስት አመታት ለወሎ ሙስሊሞች የጭንቅ አመታት ነበሩ’ ይላል። ትልልቅ ሸሆች ተጋድለው መስዋዕትነት መክፈላቸውንም ይተነትናል።

እኔ ንጉስ ሚካኤል ከአፄ ዮሐንስ ጋር አብረው ስህተት ሰርተዋል ነው የምለው። በወሎ ሙስሊሞች ላይ ትልቅ ጫና እና ሰቆቃ ደርሶባቸዋል። ከፊሉ ለስደት ሲዳረግ ከፊሉ ተቃውሞ ጀሀድ አውጆ ለሀይማኖቱ ተጋድሎ ተሰውቷል። ቀሪው ደግሞ ክርስትናን የተቀበለ መስሎ ህይወቱን አትርፏል። ምንም የሚያስደብቅ ነገር የለም። መሪዎች በሁሉ ነገር ልክ ናቸው ማለት አንችልም።
በምስጋናው መጽሐፍ ውስጥ ሙስሊሞቹ በጉልበት እንዲጠመቁና የክርስቲያን ስጋ እንዲመገቡ ሲገደዱ ቅሬታቸውን በሚያንፀባርቅ ስነ ቃል ስሜታቸውን ገልፀዋል እንዲህ ሲሉ ገልፀዋል።

“ታላቅ ታናሽ በላን ከርካ አደባባይ
አለ ልብ ስጋ ይጣፍጣል ወይ”
እንደዚሁም ሸህ ሁሴን ጅብሪል፡-
“ለጥቂት ቀን ብዬ አልበላም ነጃሳ
ወንዝ ለወንዝ ሄጄ እበላለሁ አሳ″

በሌላ በኩል ደግሞ ‘ሰው ያላመነበትን እንዲቀበል ማስገደል ልክ አይደልም’ ሲሉ ሊቁ ክርስቲያን መምህር አካለ ወልድ ይህን ዘመቻ አለመውደዳቸውን ገልፀዋል።

ይህ ሁሉ መዓት ከወሎ ህዝብ ከራሱ የመጣ አለመሆኑንም ማረጋገጥ ከፈለግን፥ አፄ ዮሐንስ አልፈው አፄ ምኒልክ ሲነግሱ፥ የክርስትና ሀይማኖትን በኃይል የመጫን ፖሊሲ ሲያበቃ፥ በወሎ ሙስሊም እና ክርስቲያን መሀል የነበረው የቀደመ ፍቅር መልሶ ቀጥሏል።
ንጉስ ሚካኤልን በኃይማኖት ጉዳይ የነበራቸውን ክፉ ጥላ ትንሽ ይቅር ለማለት የምንችለው የአፄ ዮሐንስ ስርዓት ሲያከትም ይኸው ተግባርም በዚያው በማክተሙ ነው። እንዲያውም ልጃቸው አቤቶ እያሱ ኢትዮጵያን የማስተዳደር ስልጣን ሲያገኙ፥ “ሙስሊምና ክርስቲያኑ እኩል ሊታይ ይገባል” ባሉ ጊዜ ንጉስ ሚካኤል አልተቃወሟቸውም ። ይሄ እሳቸውን ትንሽ ይቅር ለማለት ያስችለናል።
ከማመዶቹ ስርዐት ጋር ተፋልመው ከአፄ ዮሐንስ እና አፄ ምኒልክ ዘመን ጋር ተፋልመው ወሎ የፖለቲካ ወሳኝ ማዕከልነትን ቦታ እንድትይዝ ሲያደርጓት ደግሞ ታያላችሁ። አፄ ምኒልክ እንዳረፉ የአቤቶ እያሱን አልጋ ወራሽነት ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ሲያውጁ ‘ሸዋ ተስማምቷል፥ ወሎ ተስማምቷል’ ብለው ነው የሚጀምሩት። ይህ አዋጅ ከአጀማመሩ የወሎን የፖለቲካ ማዕከላዊነት ያሳያል። በነገራችን ላይ አሁን በያዝነው ዘመን ሸዋ ተስማማ ወሎ ተስማማ ምንም ለውጥ ያለው አይመስለኝም። (ከፍተኛ ሳቅ) ነገሮች ተለዋውጠዋል።

ሌላው የኔ ልብ የሚመታው ሰገሌ ላይ ነው። ሰገሌን የሚመለከት ያለኝ ምክረ ሐሳብ (thesis) ፥ ንጉስ ሚካኤልን “ክርስትና ዘውድ ጫነላቸው በአንፃሩ ደግሞ የክርስትና እምነታቸው ዘውዳቸውን ነጠቃቸው” ነው እኔ የምለው። ክርስቲያን ባይሆኑ ኖሮ አይነግሱም ነበር። ደግሞ ደንበኛ አማኝ ክርስቲያን ባይሆኑ ኖሮ ሰገሌ ላይ አይሸነፉም ነበር። “የፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ደብዳቤ አታለላቸው” የሚለው የልጆች ተረት ተረት ነው ለኔ። መስቀል ተልኮ ትልልቅ ቀሳውስት አባቶች ካህናት ተልከው እንዴት እምቢ ይበሉ? አማኝ ናቸዋ።
እዚህ ላይ የኒኮሎ ማኪያቬሊን አስተምህሮት ማስታወስ ጠቃሚ ይሆናል። ለማኪያቬሊ ሁለት አይነት የሞራል አድማስ አለ። አንደኛው “የክርስቲያን ሀይማኖታዊ ‘ሞራሊቲ′ (ግብረ ገብ)” ይለዋል። ሁለተኛውን “ማህበረሰባዊ የፖለቲካ ሞራሊቲ″ ይለዋል። በመሆኑም ፖለቲካል አለም ውስጥ መጠቀም ያለብን የማህበረሰባዊ የፖለቲካ ሞራሊቲን እንጂ የክርስቲያን ሀይማኖታዊ ሞራሊቲ አይደለም” ይላል።

ለመሆኑ በሁለቱ የሞራሊቲ መርሆች መካከል ልዩነቱ ምንድን ነው?

ለማኪያቬሊ የክርስቲያን ስነ ምግባራት እንደ ርህራሄ፥ ለቃል መታመን፥ መሀላ፥ መማለድ እና ወዘተርፈ ሲሆኑ። በአንፃሩ የፖለቲካ ሞራሊቲ ማለት የወጠንከው ግቡ ላይ ለመድረስ ማናቸውንም አማራጮች የሞራል መስፈርት ጥሶ ያለ ገደብ መጠቀም ማለት ነው። ለምሳሌ፡- ሀይማኖትን እንደ መሸምገኛ መጠቀም፥ የማያከብሩትን ቃል መግባት፥ በውሸት መማል፥ ወዳጅነትን እንደ ማዘናጊያ ማቅረብ እና ወዘተርፈ።

ወደ ሰገሌ ስንመጣ ሸዋ የፖለቲካ ሞራሊቲ ይዞ መጣ። ወሎ የክርስቲያን ሞራሊቲ ይዞ ቀረበ። የምስጋናው መጽሐፍ እንደሚያስተምረን፥ ንጉስ ሚካኤል፥ ከሸዋ ቀድሞ የመጣውን የራስ ልዑል ሰገድን ጦር ቶራ መስክ ላይ ከደመሰሱ በኋላ ገስግሰው ወደ አዲስ አበባ ሳይገቡ ለምን እንደ ቀሩ እና የሸዋው ኃይል ከየጠቅላይ ግዛቱ ጦሩን እስኪያሰባስብ ድረስ ለምን ሰገሌ ላይ እንደቆዩ ብዙ ጊዜ የሚሰጠው መልስ የሚከተለው ነው።

“ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ በተለመደው ብልሀታቸው ከንጉስ ሚካኤል ጋራ እንደሆኑ እና አቤቶ እያሱን እንዳልከዱ በመግለጽ ለጊዜው አሉበት ቦታ ሆነው እንዲቆዩላቸው መልዕክት ልከው ስላታለሏቸው ነው።” ይባላል። ይሔ ለኔ ተረት ተረት ነው።
የአሸናፊዎቹ ተረት ተረት የሆነው ደብዳቤ ተጽፏል ወይ? አዎ ተጽፏል። ግን ከልባቸው አምነው የተታለሉት ለመስቀሉ ነበር። የክርስትናን እውነታ ፀንተው ስለያዙ ተታለሉ። ‘ክርስቲያ አይዋሽም። ክርስቲያን ቃሉን ይጠብቃል’ ከሚል እምነታቸው ተነስተው ዘውድ የሰጣቸው ክርስትና በእምነታቸው ምክንያት ዘውዱን መልሶ ነጠቃቸው።

ንጉስ ሚካኤል በእመነታቸው ፀኑ። ሀብቴ አባ መላ ግን “መስቀልም አውጥተን ታቦትም አውጥተን ይሄን ሰው ማሸነፍ አለብን” አሉ። ይሄ ማለት ከላይ ለማሳየት እንደሞከርነው ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ የማኪያቬሊን የፖለቲካ ሞራሊቲ ይዘው ሲመጡ፥ እኚህ ደግሞ የክርስቲያን ሞራሊቲ ይዘው ስለቀረቡ ለኃብተ ጊዮርጊስ “ክርስቲያናዊ” ጥሪ ታምነው የፖለቲካዊ ሞራሊቲ ሰለባ ሆኑ።
ዕምነቱን እንደ መሰሪያ የተጠቀሙት ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ብልህ ብልጥ ሲባሉ፥ በሀይማኖታቸው መርህ የፀኑት ንጉስ ሚካኤል ግን ገራገር ተባሉ። ይኸው እስካሁን ወሎ ገራገሩ እየተባለ ይዘፈናል። (ሳቅ) ወይ ሀብቴ አባ መላ… ይሄ መቼስ የሚገርም ነው። (ሳቅ)
በመጨረሻም፡-
አደራ እምለው፥ ከወሎ ባህል ያፈነገጠና አስከፊ የሆነው የእምነት ጫና እና ግፊት ህዝቡ ተሻግሮ እንዳለፈው ሁሉ፥ የወሎን ህብረ ብሔራዊነት ተፃፈ ከተባለው ህገ መንግስት እና ፌዴሬሽን በፊት በወሎ የኖረውን የሀይማኖት መደጋገፍ እና ተቻችሎ በፍቅር የመኖርን ባህል አንግሶ መቀጠል ይገባናል ስል ንግግሬን እጨርሳለሁ። አመሰግናለሁ።” (ታላቅ ጭብጨባ)
ዶክተር ዳኛቸው ጋር የቀረቡ ሌሎች ጥናቶችን በሌላ ጽሁፍ እመለስባቸዋለሁ። በእለቱ ከተሳታፊዎች ጥያቄዋች እና አስተያየቶች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

አንድ መንፈሳዊ አባት በንግግራቸው ንጉስ ሚካኤል በእምነታቸው ጥልቀት አማካኝነት መሸነፋቸው የሀይማኖት ሰማዕት እንዳደረጋቸው በመግለጽ ዘውትር ስመ ክርስትናቸውን በቤተ ክርስቲያን እየተነሳ ፀሎተ ፍትሀት ይደረግላቸዋል” ሲሉ የምሁሩን ሀሳብ አጠናክረዋል።
በተሳታፊዎች “ታሪክን ወደ ኋላ ሂዶ መዘገብ ስለምን በመንግስት በኩል አስፈሪ ሊሆን ቻለ?” የሚል እና የንጉስ ሚካኤልን ሀውልት ማቆም የተመለከቱ ጥያቄዋች ቀርቦ፥ ዶክተር ዳኛቸው ሲመልሱ “የንጉስ ሚካኤልን ሀውልት በሚመለከት፥ ሲታሰብ የሳቸውን ብቻ ሳይሆን ሌሎችንም ለሀይማኖታቸው ሲሉ የወደቁ ኢማሞች አሉና ለነሱም ሀውልት ሊቆም ይገባል። ምን አልባት በእስልምና ሀይማኖት ሀውልት የማይፈቀድ ከሆነ በስማቸው የጥናት ማዕከላት ሊገነቡ ይችላል። የራሳችን ታሪክ አካል ስለሆነ ተቻችለን ተሳስበን መዘከር ይገባናል።

ታሪኩ ለምን አልወረደም ላልሽው፥ እኔ እምልሽ ታሪክ በጣም ከባድ ነገር ነው። አንድ አንድ ጊዜ ታሪክ የፖለቲካ አሽከር የምትሆንበት ጊዜ አለ። የፖለቲካ ሀይሉ ጠምዝዞ ይመራዋል። በአፄ ኃይለ ስላሴ ጊዜ ስለ ልጅ እያሱ መፃፍ በጣም አስቸጋሪ ነበር። በደርግ ጊዜ ስለ አፄ ኃይለ ስላሴ መፃፍ አስቸጋሪ ነበር። አሁን ደግሞ አንድ አንድ ሁኔታዎች መፃፍ አስቸጋሪ ነው። ከዚህ አልተላቀቅንም።
እንዲያውም “ሀቅ ሀቁን ለህፃናት” የሚል የፕሮፖጋንዳ መጽሀፍ ተለቋል አሁን። እሚገርም ነው መቼም። አስቸጋሪ ነው። አረ ተመስገን ነው። አይጠየፍ ሁነን እንዲህ ያለ ውይይት ማድረጋችንም ተመስገን ነው። (በከፍተኛ ሳቅ እና ጭንጨባ ተቋጨ)

ምንጭ፡- ቋጠሮ ድረ-ገፅ

የኢትዮጵያ ድርቅና ርሃብ ትናንት እና ዛሬ

ብስራት ወልደሚካኤል

በርግጥ ድርቅ በተፈጥሮ ሊከሰት የሚችል የአየር መዛባት አደጋ ውጤት ነው፡፡ ድርቅ ባለፀጋም ሆነ እንደኛ ባሉ ደሃ ሀገራት ሊከሰት ይችላል፡፡ የድርቁ መንስኤም ተፈጥሯዊ አሊያም ሰው ሰራሽ ሊሆን ይችላል፡፡

Ethiopia_drought_cows

ርሃብ በምግብ እጥረት የሚከሰት ሲሆን፤ መንስዔውም የምርት አቅርቦት ማነስ አሊያም የምግብ ፍላጎት ከምርት አቅርቦት ጋር አለመጣጣም ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ዋነኛ ምክንያት ደግሞ ፍላጎት እና አቅርቦትን አሊያም የሀገር ምርት ለማሳደግ ሀገሪቱ የምትከተለው ፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡ በኢትዮጵያም በተለያዩ መንግሥታትም ሆነ ዘመን ድርግቅን ተከትሎም ይሁን ያለድርቅ ለተከሰቱት እና እየተከሰቱ ላሉ ችግሮች ዋነኛ መንስዔው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡

ርሃብ በተፈጥሮ የሚከሰት ሳይሆን የሀገሪቱ መንግሥት ስርዓት በሚከተለው የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡ ደካማ ወይም ተፈጥሮንና የሀገሪቱን ህዝብ አቅምና ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ፖሊሲ ትግበራ ባለበት ሀገር ድርቅ ከተከሰተ ምንጊዜም ርሃብ አለ፡፡ ርሃቡ ምንም እንኳ ድርቅን ተከትሎ የመጣ ቢሆንም ዋነኛ ምክንያቱ ግን የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡

በሀገራችን በተከታታይ የተከሰተውም ርሃብ ዋነኛ ምክንያት ድርቁ ሳይሆን የደካማ ፖሊሲ ውጤት ነው፡፡ ምክንያቱም ድርቅ የተከሰተባቸው ሀገሮች ሁሉ ርሃብ አይከሰትም፡፡ ደካማ ፖሊሲ ያለባቸው ሀገሮች ግን ድርቅ ካለ ምንም ጊዜም ርሃብ አለና፡፡

በዘመናዊ ኢትዮጵያ የመንግሥት ታሪክ ጎልቶ መታወቅ የጀመረው በዳግማዊ አጼ ምኒልክ ዘመን ቢሆንም እስከዛሬም ይህን ችግር የሚቀርፍ የመንግሥት ፖሊሲና ተግባር አልታየም፡፡ አሳዛኙ ነገር በዘመነ ዳግማዊ ምኒልክ የነበረውን ርሃብ ለዓለም ማኀበረሰብ አሳውቆ ተገቢውን ርዳታ ይቆ ለተጎጂዎች በማድረስ ህይወት ለማትረፍ ቴክኖሎጂው ችግር ነበረብን፡፡ ቢሆንም ግን ይህን ክፍተት ንጉሱን ጨምሮ ባለሟሎቹ (አመራሮቹ) የተፈጠረውን ርሃብ በድርቅ ላይ ሳያመሃኙ ወዲያው ለህዝቡ በማሳወቅ ወገን ለወገን በሚችለው አቅም እንዲረዳዳ እና የመንግሥት ካዝና (ለችግር ጊዜ የተቀመጠ የእህል ጎተራ) ሳይቀር በይፋ ተከፍቶ ለተጎጂዎች ወዲያው እንዲደርስ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ ይህ በጎ አስተሳሰብ ቢሆንም ከነበረው የእህል ክምችት አናሳነት እና የትራንስፖርት ችግር አኳያ ለሁሉም ተጎጂ እኩል ማድረስ ባይቻልም መንግሥት ችግሩን አምኖ የህዝቡን ድጋፍ ጤቆ ተገቢውን ምላሽ አግኝቶ ነበር፡፡ ቢሆንም ግን ብዙ ወገኖቻችንን በርሃቡ አጥተናል፡፡

Ethiopian famine 2015

በዘመነ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ የነበረው በ1965/66 ዓ.ም. ርሃብ ግን ንጉሱም ህዝቡም እንዳያውቁ መኳንንቱ ለመሸፋፈን ሞክረዋል፡፡ በዚህም መኳንንቱ ጠግበው እየበሉ በርካታ ወገኖቻችን በወቅቱ በተከሰተው ርሃብ ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ይሄ በተለይ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍለክ እጅግ የከፋ የታሪክ ጠባስም ጥሎልን አልፏል፡፡

በዘመነ ደርግ በተለይ በ1977 ዓ.ም. የተከሰተውን ልብ ይሏል፡ የተከሰተውን ርሃብ የሀገሪቱ መራሄ መንግሥት መንግሥቱ ኃይለማርያምና ሁሉም ሹማምንት ቢያውቁም ከሀገሪቱ ህዝብ (ርሃብ ካልነካቸውን) እና ከዓለሙ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ተሞክሯል፡፡ በዚህም ብዙ ወገኖቻችን በጊዜ ማዳን ሲቻል በሞት ተነጥቀናል፤የበለጠ ክብራችንም እንዲዋረድ በር ከፍቷል፡፡

በዘመነ ኢህአዴግ ከአንዴም ሶሰት ጊዜ፤በተለይ በ1985ዓ.ም.፣ 1986/87 ዓ.ም. እና የአሁኑን የ 2007/08 ዓ.ም. ርሃብ መንግሥት ከሀገሬው ህዝብና ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ሞክሯል፤ባይችልም፡፡ በቅርቡ በተለይም ባለፈው ክረምት በምስራቁ የሀገራችን ክፍል የተጀመረው ርሃብ ወደ ሰሜኑ እና መካከለኛው የሀገራችን ክፍል በፍጥነት ቢዛመትም መንግሥት በምግብ ራሳችንን ችለናል፣ ርሃብ አልተከሰተብ፣ …ወዘተ የሚለው ፈሊጥ አንድ ወር እንኳ አልሞላውም፡፡ ርሃቡ ልክ እንደሰደድ እሳት እና አውሎ ነፋስ ማዕበል ምስራቁን፣ ሰሜኑን እና ከፊል መሐከለኛ የሀገራችን አካባቢ በፍጥነት ተዛመተ፡፡ ርሃብ የለም፣ በምግብ ራሳችንን ችለኛል፣…የክፉዎች ወሬ ነው ሲባል የነበረው ርሃብ፤ አሁን መንግሥት በህዝብ ላይ እና በእንሰሳቶቻቸው ላይ ከፍተኛ እልቂ ከደረሰ በኋላ “ኢሊኖ በሚባለው ድርቅን ተከትሎ በነሳው ርሃብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር 5 ሚሊዮን አካባቢ ደርሷል፣ ከዓለም አቀፉ ለጋሽ ድርጅቶች እና ሀገራት አፋጣኝ እና በቂ ድጋፍ አላገኘንም,…” የሚል ይፋ ልመናዊ መግለጫ ተሰጠ፡፡ የተራቡ ወገኖቻንን ቁጥር መገመትና መናገር ቢከብድም አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ግን ከ 10 ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ይገመታል፡፡

በጣም የሚያሳዝነው ሁሉም ስርዓቶች በተፈጥሮ ሃብትና በግብርና ላይ ያላቸው ፖሊሲ የአንዳቸው ከአንዳቸው የማይሻል፣ ያልተለየ ቢሆንም በዳግማዊ ምኒልክ ጊዜ ግን ርሃብ ለመደበቅ አልተሞከረም፤ ይልቁንም ከመንግሥት ካዝና በተጨማሪ ህዝቡ እንዲረዳዳ የጠማፅኞ ጥሪ ተደረገ እንጂ፡፡ በኃይለስላሴ ዘመንም ቢሆን ሹማምንቱ ከንጉሱ እና ርሃብ ካልደረሰበት ህዝብ ለመደበቅ ቢሞከርም መደበቁ አልቻሉም፡፡ የደርግና ኢህአዴግ ስርዓት ክፋት ግን ከበታች ሹም እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ድረስ ርሃቡን እያወቁ ለመደበቅ መሞከራቸው የፖሊሲ ችግራቸውን ለመደበቅ ከመሞከራቸው ይልቅ በሰብዓዊ ፍጡር ህይወት ላይ ያላቸውን ጭካኔ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ርሃብ ቀን አይሰጥምና፡፡ ርሃብ የሰውንም ሆነ የእንሰሳትን ህይወት ሲቀጥፍ ዳግም አናገኛቸውምና፡፡

አሁን ርሃቡ በዋነኛነት የተከሰተው ውሃ ቅዳ ውሃ መለስ የሆነው የመንግሥት ስርዓትና በመሪዎች ቸልተኝነት፤ የተፈጥሮ ሃብት፣ የመሬት፣ ስነ ህዝብ፣የምግብ እና የመረጃ ጥንቅር ፖሊሲ ችግር ነው፡፡ ባለፈው ከነበረው ችግር ለነገው አለመማራችን እና ለመማር አለመዘጋጀታችን ውጤትም ነው፡፡ ስለዚህ ርሃብን እና የተራበውን ህዝብ ቁጥር በመደበቅና በማዛበት ርሃብን ማቆም እንደማይቻል ልናውቅ ይገባል፡፡ ስለዚህ በርሃብ የተጎዱ ወገኖቻችንን በተመለከተ የውጭ መንዛሪ እጠረት ለመሸፈን ባለመ የውጭ ለጋሽ ሀገሮችን ተማፅኞ ብቻ ሳይሆን ዜጎች ወገኖቻችንን እንዲረዳዳ ዕድሉ ሊሰጥና በይፋ የምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ ማሰባሰብ ስራ በማድረግ የወገኖቻችንን ህይወት መታደግ ይቻላል፡፡ ለዚህም ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፤ ርሃብ ጊዜ አይሰጥምና፡፡

ከፖሊሲ ችግር አንዱ ከዝናብ ጥገኝነት ለመውጣት የሚያስችል መስኖ አለማስፋፋት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሜትሪዮሎጂ ተቋም ብቃት ባላቸው የአየር ትንበያ ባለሙያዎች አለመዋቀር እና አለመጠናከር፣ መስኖ በሌለባቸውና ዓመታዊ የዝናብ መጠናቸው ዝቅተኛ የሆኑ ቆላማ አካባቢዎች የተለየ ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲሁም በቂ የእንሰሳትና የሰው ህክምና እና የምግብ ቅድመ ዝግጅት ክምችት አለማድረግን መጥቀስ ይቻላል፡፡

ከአስቸኳይ ርስበርስ የመረዳዳት እና ዓለም አቀፍ ድጋፍ ጥየቃ እንቅስቃሴው እንዳለ ሆኖ፤ ለ24 ዓመታት ተሰርቶበት ለውጥ ያላመጣውን ፖሊሲም ማሻሻል አሊያም መቀየር ዋነኛው ቁልፍ ተግባር መሆን አለበት፡፡ አለበሊያ በኢህአዴግ ዘመን ለ4ኛ እና 5ኛ ጊዜ መከሰቱ እንደማይቀር የአሁኑን ጨምሮ ያለፉት ጊዜያት ከበቂ በላይ አስተማሪዎች ናቸውና ከፖለቲካ ጋጋታ ትርፍ ይልቅ ሕይወት የማዳኑ ተግባር ሊፈጥን ይገባዋል፡፡

አዳማ የኤድስ ተጠቂዎች ማደርያን ወደ መቅዲ ባርና ሬስቶራንት ቀየረች?!

የትነበርክ ታደለ
ይህ የምስራች እንዳይመስላችሁ! እጅግ ዘግናኝ አሳፋሪና አሳዛኝ የሀገራችን እውነታ ነው። ከአመታት በፊት ሀገር በኤች አይቪ የደረሰባትን የጭለማ ድባብ አንረሳውም! እርግጥ አሁንም ገና ከሀዘኑ ሙሉ በሙሉ አልተላቀቅንም። በዝያ የጭለማ ዘመን፣ መፍትሄ ከሀገር ውስጥም ከውጭም ሲፈለግ፣ ወጣቱ በየቦታው ሲረግፍ፣ ቤተሰብ ሲበተን አዳማ ውስጥ አንድ ሰው ተገኘ።

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

ይህ ሰው መስፍን ፈይሳ ይባላል። መስፍን ራሱም የቫይረሱ ተጠቂ መሆኑን ይፋ አውጥቶ በመናገር የሱ ቢጤ ወገኖቹን ለመርዳት ቆርጦ ተነሳ። እሱ እንደሚናገረው ማዳበርያ ከረጢት አንገቱ ላይ አስሮ በየደጃፉ እየዞረ ምግብ እየለመነ የሰበሰባቸውን ወገኖቹን መመገብ ያዘ።

እየቆየ ጥረቱ ፍሬ አፍርቶ በሀገር አቀፍ ደረጃ እውቅና የተሰጠውና ከ5000 ሰዎች በላይ የተረዱበት “መስፍን ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት” ተቋቋመ።

ይህ ተቋም አሁን “መቅዲ ባርና ሬስሮራንት ተብሎ ወጣቶች ቀንና ለሊት የሚጨፍሩበት፣ በሺሻ ጢስ የሚታጠኑበትና ህልማቸውን የሚነጠቁበት ቦታ ሆኗል።

ከሰአታት በፊት ግለሰቡ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ በለቀቀው ቪዲዮ እንዳስታወቀው በጉልበት ከሀገር እንድወጣ ካደረጉኝ በኋላ ተቋሙን አፈራርሰው አራት ሚሊየን የሚገመት ንብረት ዘርፈው ጉዳተኞቹን በትነው ህንጻውን ከኤች አይቪ መከላከያነት ወደ ማሳራጫነት አዙረውታል ብሏል።

እጅግ የሚደንቀው ደግሞ ይህ ተቋም (አሁን መቅዲ ባር) የሚገኘው ከአዳማ ዩኒቨርስቲ አጠገብ መሆኑ ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ አለማቀፍ ሚዲያዎች እንደሚዘግቡት ሀገራችን ውስጥ ዝሙት በርካሽ የሚሸጥባቸው ስፍራዎች ዩኒቨርስቲዎች ባሉበት አካባቢ ነው።

በተለይ ደግሞ አዳማ ናዝሬት በዚህ ግምባር ቀደም ተጠቃሿ ናት። አንድ የቅርብ ጊዜ መረጃ እንደሚያሳየው አዳማ 230.000 ነዋሪዎች ያላት ስትሆን ከዚህም ውስጥ ካሉት ሴቶች 5000 ዝሙት አዳሪዎች ናቸው። ይህም ማለት ከመቶ አምስት ፐርሰንቱ በዚሁ ስራ የሚተዳደሩ ናቸው። ልብ በሉ ይህ ቁጥር የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን አይጨምርም።

እንግዲህ ይህንን አይነት ጉድ የተሸከመች ከተማ እንዴት ባለ አስተዳደር እጅ ብትወድቅ ነው የህዝብን ሁለንተናዊ ጤንነት ከመጠበቅ ሀላፊነቱ እየሸሸ በግለሰብ የተቋቋመ ተቋም ለማፈረስ የተደፈረው?

እጅግ በጣም የሚገርመው ደግሞ ይህ ተቋም ሲጀመር የመሰረት ድንጋይ የጣሉት በአሁን ሰአት የክልሉ ፕሬዚዳንት የሆኑት ኦቦ ሙክታር ከድር መሆናቸው ነው። (አቡነ ጳውሎስም በቦታው ነበሩ)

Mesfin Feyisa Initiative adama-nazereth

እና ምነው? ኦቦ ሙክታር አዳማ ውስጥ ምን እየተካሄደ ማወቅ አይችሉም ማለት ነው? ለአንድ ትልቅ አላማ ራሳቸው በቦታው ድረስ ሄደው መሰረት የጣሉለት ተቋም እጅግ በሚያሳፍርና በሚያዋርድ ሁኔታ ተሽቆልቁሎ ሲጠፋ ምንም አልሰሙም ማለት ነው? አዳማ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ነች! ይህንን ሳይስሙና ሳያዩ ወለጋ ጫፍ ወይም አርሲ ቦረና ስላለው እንዴት ሊሰሙ ይችላሉ? ነው ወይስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሳቸው ይሁንታ አለበት? እውነት ለመናገር መልስ ሊሰጡበት የሚገባ ጥያቄ ነው።

የአዳማ ህዝብስ ቢሆን በራሱ ጉዳይ ላይ ከሱ የተሻለ ማን ሊጠይቅለት ይችላል? ግለሰቡ እንደተናገሩት ወደዚህ ባርና ሬስቶራንት ልጆቻችሁ እየሄዱ እያያችሁ ዝም ብትሉ በልጆቻችሁ ህይወት ላይ ፈርዳችኋል።

መንግስትም ቢሆን እነ መቄዶኒያን የመሳሰሉ ወገንን ከጎዳና የሚሰበስቡ ተቋማት ነገ በተመሳሳይ መንገድ እንደማይፈርሱና ወደ ሺሻ ቤትነት እንደማይቀየሩ ምን ማስተማመኛ ይሰጠናል? ትውልድ እየጠፋ ነው! ህግ እየተጣሰ ነው! የምንፈልገውን እያጣን የማንፈልገው እየተጫነብን በዚህ ላይ ለጩሀታችን ዝምታ እየተመለሰልን ነው! ነገ አጣብቂኙ ለሀገር ነውና መቅዲ ባር በአስቸኳይ ወገኖቻችን ወደ ሚረዱበት ተቋምነት ይመለስልን! ወገን በጭፈራ ቤት አይታከምም!

በሳውዲ በተከሰው አደጋ ከ13 በላይ ኢትዮጵያውያን መሞታቸው ተገለፀ

ነብዩ ሲራክ
(ከሳውዲ ዓረቢያ)

መስከረም 13 ቀን 2008 ዓ.ም. የሐጅ ሥነ ሥርዓት ተከትሎ ሰይጣንን በድንጋይ በሚመታበት ክንዋኔ ምሳሌ፤በጀማራት ድልድይ በሚወስደው መንገድ በሀጅ ተጓዦች መካከል በመጨረሻው ሰዓት በተፈጠረ ግፊያና መጨናነቅ በተከሰተ አደጋ የሟ ቾች ቁጥር ወደ 1,100 ከፍ ያለ ሲሆን የቆሰሉት ቁጥርም ከፍተኛ መሆኑ ታውቋል፡፡ ከደረሰው አደጋ ውስጥ እስካሁን ከ13 በላይ ኢትዮጵያውያን ሲሞቱ ከ26 በላይ መቁሰላቸውን እና ከ204 በላይ መጥፋታቸውን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ለሒጅ ፀሎት ስነስርዓት የተጓዙ ኢትዮጵያውያንም 8 ሺህ ያህል እንደነበሩ ተጠቁሟል፡፡

Saudi Hajaj

ባለፈው ጳጉሜ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. በመካ ሳውዲ ዓረቢያ በደረሰው የክሬን መውደቅ አደጋ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ በርካታ ለሐጂና ፀሎት ስነስርዓት ወደስፍራው ባቀኑ ሀጃጆች ላይ ከህይወት መጥፋት እስከ አካል ማጉደል አደጋ ማድረሱ አይዘነጋም፡፡ በተለይ የመስከረም 13 ቱን አደጋ በተመለከተ ጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ እንደሚከተለው አቅርቦታል፡፡

ኢትዮጵያ…

* ኢትዮጵያ 13 በላይ ሞተውባታል ፣ 26 ቆስለውባታል
ከ204 በላይ ጠፍተውባታል ፣ ፍለጋው ቀጥሏል
* ጅዳ ከተላለፉት ቁስለኞች ኢትዮጵያዊ የለም
* ጅዳ ማህጀር የተላለፈው ሬሳ ማንነት ገና አልተጣራም
* ከማህጀሩ ሬሳ የአፍሪካውያን አለበት ተብሏል
* ኢትዮጵያውያን መካ ላይ ለፍለጋው በግል ተደራጅተዋል
* ማፈላለጉን በሁሉም ሆስፒታሎች መከዎን ገዷቸዋል
* ቤተሰብ ወይም የኢንባሲ ውክልና አምጡ ተብለዋል
* በመካው ክሬን የተጎዳች ኢትዮጵያዊት ሀጃጅ ተገኘች
* ኢትዮጵያቷ ሀጃጅ እስከዛሬ አልታወቀችም ነበር
* ልክ የዛሬ ሳምንት መሞቷ ተጠቁሟል

ህንድና ፖኪስታን …

* በማፈላልጉ የሳውዲ መንግስት አፋጣኝ እርዳታ ተጠየቀ
* የህንድን ፖኪስታን ቆንስሎች መግለጫ ሰጥተዋል
* ህንድ 46 ሞቶባታል 62 ቆስለዋል 82 ጠፍተውባታል
* ፖኪስታን 46 ሞተውባታል ፣ 8 ቆስለዋል 42 ጠፍተውባታል

የጠፉትን ፍለጋና ጭንቅ ድካሙ

ተቀማጭነታቸውን ሳውዲ ያደረጉ ፣ የተለያዩ ሀገራት ዜጎች ፣ በሀጅ ጸሎት ከአደጋው የተረፉ ሀጃጆችና ቤተሰቦቻቸው በሚና ጀማራት አደጋ የጠፉና የሞቱትን ሰዎች ለማፈላለግ ሌት ከቀን ወደ ሚና ፣ ጀማራትና መካ በመመላለስ አድካሚ የጭንቅ ሳምንት መግፋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው። የጠፉ ሃጅ ቤተሰቦች በግሩኘና በተናጠል ቢያፈላልጉም በርካታዎች እንዳልተሳካላቸው ይናገራሉ ። በአደጋው የሞቱ ኢትዮጵያውያን ቁጠር ገና ከአደጋ ቀን አንስቶ ከአምስት በላይ መሆኑ ግልጽ እያለ በኢትዮጵያ ኢንባሲ ፣ ቆንስልና የሀጅ ኮሚቴ የሚደረገው ፍለጋ የተቀናጀ ባለመሆኑ ዝርዝር መረጃው ቀርቶ የሞቱና የቆሰሉትን ዙሪያ ትክክለኛ መረጃ አልቀረበም ነበር ። ከብዙ ጉትጎታ በኋላም ትክክለኛውን መረጃ ለህዝብ ለማድረስ በርካታ ቀናት ወስዷል።
አሁንም በኢትዮጵያ ተወካዮች በኩል ቀናት የወሰደው የሞቱና የቆሰሉትን የማሳወቅ መረጃ ቅበላ ከቀናት በፊት ይፋ ቢደረግም አሁንም ቁጥሩ እየጨመረ ከመጣው የሟቾቸ ብዛት አንጻር የመረጃ ክምችቱን የማሻሻል ስራ እየተሰራ አይደለም በሚል ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ የመካና ጅዳ ነዋሪዎች ገልጸውልኛል፡፡

ኢትዮጵያን ወጣቶች በመካ ሚናው ፍለጋ

የሀጅ ኮሚቴ አካሄድ አዝጋሚ መሆን ያሳሰባቸው በመካ ዙሪያ የሚገኙ ወጣቶች ራሳቸውን በማደራጀት መካ ላይ በሚገኙ በ13 ሆስፒታሎች በአደጋው የተጎዱትን ለማግኘት ፍለጋ ጀምረዋል ። በትናንሽ ሆስፒታሎች ችግር ባይገጣማቸውም መሊክ ፈይሰል ፣ ሄራ ፣ ጀበለር ኑርና መሊክ አብደላ በተባሉ ትላልቅ ሆስፒታሎች እንዳይገቡ ተከልክለዋል ። ያም ቢሆን በቀሩት አንዳንድ ሆስፒታሎች ማፈላለጉን በተወሰነ መልኩ በማሳለጥ 15 ያህል ቁስለኞችን ማግኘታቸውን ጠቁመውኛል። መሊክ ፈይሰል ፣ ሄራ ፣ ጀበለር ኑርና መሊክ አብደላ በተባሉ ትላልቅ ሆስፒታል ሃላፊዎች “የቤተሰብ ወይም የኢንባሲ ውክልና አምጡ !” በማለት አንደከለከሏቸው ወጣቶች አጫውተ ኛል። ይህንን ችግር እንዳጋጠኛቸው ያጋጠማቸውን ለሀጅ ኮሚቴ በመጠቆም ተቀራርበው ለመስራት መሞከራቸው የገለጹልኝ የአፈላላጊ ቡድኑ አባላት አብሮ የመስራት ሙከራውም አለመሳካቱን ገልጸውልኛል! “ከጅዳ ለመጡ ኮሚቴ ነን ” ላሉን ሰዎች በሀጅ ኮሚቴ ወይም በጅዳ ቆንስሉ በኩል ውክልናውን ወይም መታወቂያ ቢሰጠን ብለን ጠይቀን ነበር ያሉኝ አንድ ወጣት በበኩላቸው ” መጣዎቂያ ይሰጣቹሃል!” የሚል ቃል ቢገባላቸውም እስካሁን ከኮሚቴውም ሆነ ከሌላ ወገን መልስ ባለ መሰጠቱ ጥረታቸው መሰናክል እንደገጠመው ገልጸውልኛል፡፡

በአንጻሩ የተመሳሳይ ችግር ያለባቸው የአንዳንድ ሀገራት የመንግስት ተወካዮችና ዲፕሎማቶች እንኳንስ ነዋሪው ተደራጅቶ መጥቶ ነዋሪዉን ለበጎ ስራና በማቀናጀትና በማቀዳጀት በሽዎች የሚቆጠሩ ልዩ የጠፉ ሃጃጆችን አፈላላ ግብረ ሃይል አቋቁመው በመካ ፣ ሚናና ጀናራት ማሰማራታቸው ይጠቀሳል ። የነዋሪውንና የሀጃጆችን ጭንቀት በመረዳትም የቆሰሉትንና የሞቱትን ፎቶ መረጃዎች ከሳውዲ መንግስት በመውሰድ ለዜጎቻቸው አቅርበዋል።

የመካ ወጣቶች በፍለጋው እንደ “አሳ ጎርጓሪ …”

አበው ” አሳ ጎርጓሪ…” የእኒሁ በመካ ዙሪያ ያሉ ወጣቶች በሚና ጀማራት የተጎዱ ሰዎችን ሲያፈላልጉ በመካው ክሬን ተጎድታ የሞተች ኢትዮጵያቷ ሀጃጅ ማግኘታቸው ታውቋል። እስከ ዛሬ የሀጅ ኮሚቴም ሆን የጅዳ ቆንስል ምንም መረጃ ስለሌላቸው ማንም ሳይደርስባት መሞታን ገልጸውልኛል። ይህችው ኢትዮጵያዊት ሃጃጅ በጉዳቱ በከባድ ቆስላ በህክምና ስትረዳ ከቆየች በኋላ ባሳለፍነው ሳምንት በተከበረው የኢድ አል አድሃ እለት ህይዎቷ ማለፉን ከዶክተሮች እንደተገለጸላቸው ሬሳውን አየሁ ያለ ጎልማሳ አስረድቶኛል። እኔም ጉዳዩን በተዘዋዋሪ መንገድ ለማጣራት ባደረግኩት ሙከራ የተባለችው እህት ሬሳ በሆስፒታሉ የሬሳ ክፍል እንደሚገኝ ማረጋገጥ ችያለሁ! በዚህች ሟች ሀጃጅ ዙሪያ የደረሰኝ መረጃ ለሃጅ ኮሚቴና ለጅዳ ቆንስል በተመሳሳይ ሁኔታ መቅረቡን አረጋግጫለሁ፡፡

ሀጃጆችን ፍለጋ በጅዳ ሆስፒታሎች

አደጋው ከደረሰ በኋላ ባሉት ቀናት የተጎጅዎች ቁጥር ከፍ እያለ በመምጣጡ ወደ 200 የሚጠጉ ቁስለኞች ወደ ጅዳ መተላለፋቸው ይታወሳል ። ይህንኑ ተከትሎ የጅዳ ቆንስል በሳምንቱ መጀመሪያ ዲፕሎማቶችን ከተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር በቡድን በማሰማራት ፍለጋ ጀምረው ነበር ። በዚሁ ፍለጋ ከተጋበዙት መካከል የሴቶች ማህበርና የጅዳ ኮሚኒቲ የሚገኙበት ሲሆን የሴቶች ማህበር አባላት ሲሳተፉ የጅዳ ኮሚኒቲ ግን በፍለጋው አልተሳተፈም ። ለሁለት ቀናት በተደረገው ፍለጋ አንድም ኡትዮጵያዊ አልተገኘም።

የተደረገው ፍለጋ ጅዳ ማህጀር የሚገኘውን የሬሳ ማቆያ ያካተተ ቢሆንም ወደ ማቆያው የተላለፈው ሬሳ ማንነት ገና ባለመጣራቱ መረጃ ማግኘት እንዳልተቻለ የጅዳ ቆንሰል ባወጣው መረጃ ጠቁሟል ። እስከ ዛሬ ረፋድ በዚሁ ሬሳ ማቆያ ተጨማሪ ሬሳዎች መግባታቸው ሲረጋገት ወደ ማህጀሩ ማቆያ አፍሪካውያን ሬሳ እንደሚኖርበት ተገምታል።

ሞተው መለየት ያልቻሉትን የማጣራቱ ስራ

በሳምንት የአደጋው አድሜ በዋናነት አሳሳቢ የሆነው ቁርጡ የታወቀው የሞቱትና የቆሰሉት ዜጎች አልሆነም። ሞተው ፎቷቸውና ቆሰለውም ከሆነ ዝርዝራቸው ያልተገኙት ጉዳይ ብዙ ዜጎችን በመንፈስ እያስጨነቀና እያንገላታ ይገኛል። መዳረሻቸው ” ጠፋ” ከሚባሉት መካከል በደረሰው አደጋ ፊታቸው መለየት ያስቸገረ ይገኙበታል የሚል ጥርጣሬ ቢኖርም የሟቾችን ሬሳ ለመለየት የተለያዩ እርንጃዎች ቀርበዋል። ሀጃጆች በገቡበት አሻራ ለመለየት እየተወሰደ ያለው ማጣራት ረዠም ጊዜ መውሰዱ ተቃውሞ እየቀረበበት መሆኑ ይጠቀሳል ። የሳውዲ መንግስት የየጤና ጥበቃና የፖስፖርት ክፍል ኃላፊዎች ስለመለየቱ ስራ ሲናገሩ በሶስት መንገድ እንደሚከወን ያስረዳሉ ። እስካሁን መለየት ያልተቻለውን ሬሳ ለመለየት የቀረቡት ዘዴዎችም 1ኛ / በገቡበት አሻራ 2ኛ / በገቡበት ፎቶ መለየት እና 3ኛው / የስጋ ዘመድ ቤተሰቦቻቸው እየቀረቡ DNA በመስጠት መለየቱ እንደሚከወን ይናገራሉ ! አሻራቸው የተነሱ ሬሳዎች ውጤት በከነገ ጀምሮ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ቢጠበቅም የተረጋገጠ መረጃ እስካሁን አላገኘሁም፡፡

የሟቾች ቁጥር ማሻቀብ

የሚና አረፋት አደጋ ከተከሰተ ሰባተኛ ቀኑን የደፈነ ቢሆንም በመቶዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ ዜጎች መዳረሻ እስካሁን ሊታወቅ አልቻለም ። ካሳለፍነው ሳምንት ጀምሮ በማህበራዊ መገናኛ መረቦች እስከ ታዋቂ መገናኛ ብዙሀን የዜና አውታሮች የጠፉና ያልተገኙት ዜጎች ጉዳይ አሳሳቢ እንደሂነ ቀጥሏል! ምንም እንኳን የሳውዲ መንግስት የሚቱትን ቁጥር ከ 769 ፈቀቅ ባያደርገውም ሞተየ ተብለው ፎቷቸው የተለጠፉት ቁጥር ከ1500 በላይ እየሆነ መጥቷል። የመንግስት ሃላፊዎች መሞታቸው ተረጋግጦ ፎቷቸው የሚለጠፉት ቁጥር እያደር አሳሳቢ ሆኗል። ለምን ቁጥሩ አደገ ተብለው ሲጠየቁ ” በፎቶው የተካተቱት ሀጅ ከተጀመረ ወዲህ በልብ ድካምና በተለያዩ አደጋዎች የሞቱት ከአደጋው ጊዜ ሰለባዎችን ጭምር ነው “ቢሉም የቁጥሩ በአፋጣኝ ማፈግ ብዙዎቹን አሳስቧል።

የህንድና ፖኪስታን ተሞክሮ

የሳውዲ መንግስት የጠፉትን በማፈላለግ ሂደቱን እንዲያፋጥንና የዜጎቻቸው እጣ ፈንታ እንዲያሳውቅ አጥብቀው እየጎተጎቱን ካሉት ሃገራት ዲፕሎማቶች መካከል ህንድና ፖኪስታን የሳውዲ መንግስት አስቸኳይ ጥሪና ተማጽኗቸውን በማቅረብ ላይ ናቸው፡፡

የፓኪስታን አምባሳደር መብዙር አለ ሀቅ እና ቆንስል ጀኔራል አፍታብ አህመድ በተገኙበት ሳውዲ የሀጅና ኡምራ ሚኒስትር በድር ሀጃር ጋር ምክክር ያደረጉት የፖኪስታን የሀይማኖት ጉዳዮች ተወካይ ሳድር መሀመድ በጠፉት ፣ በቆሰሉትና በሞቱት ፖኪስታን ሃጃጆች ዙሪያ መንግስታቸ ው አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጣቸው የሚኒስትሩን አሳስበዋል ። በአደጋው 46 የሞቱባት ፣ 8 የቆሰለባት እና 42 የጠፉባት ፖኪስታን የሀይማኖት ጉዳይ ተወካይ ሳድር መሀመድ ከሳውዲ ሃጅ ሚኒስትሩ ጋር ባደረጉት ውይይት በሚና ጀማራት አደጋ የቆሰሉት ፣ ሞተው ማንነታቸው ተጣርቶ ባልተነገረ ዜጎቻቸው ዙሪያ ጉዳይ ፖኪስታናውያን ን በእጅጉ ማሳሰቡን ገልጸው አስቸኳይ መፍትሔ እንደሚሹ ለሃላፊው በአጽንኦ አስታውቀዋል። በተለይም መዳረሻቸው የጠፉ ዜጎቻቸው ጉዳይ የሚወዷቸው ቤተሰቦች የጠፉባቸው ቤተሰቦችን በጣም ያጨናነቀ መሆኑን ጠቁመው የሳውዲ መንግስት ምለሽ እንዲሰጣቸው ተማጽኗቸውን አቅርበዋል፡፡

በአደጋው 46 በሞት ያጣችው 62 የቆስለባትና 82 የጠፉባት ህንድ ዲፕሎማቶች በበኩላቸው የሀጃጅ ዜጎቻቸው ጉዳይ ዜጎቹና መንግስትን እንቅልፍ እንደነሳቸው አሳስበዋል ። በጅዳ የሚገኘው የህንድ በቆንስል መስሪያ ቤቷ የጉዳዩን አሳሳቢነት ለሳውዲ መንግስት ለመሳሰብ ትናንት ሮብ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን በዋናነት የሰጡት የህንድ ሀጅ ኮሚቴ ዋና ኃላፊ መሀቡባ ሙፍቲ የመሩት ሲሆን ስጋራቸውንና የጠፉ ቤተሰብ አባላት ጉዳይ መጣራት መጓተት መንግስታቸውን እንዳሳሰበው በመጠቆም አስቸኳይ መፍትሔ ይፈለግ ዘንድ የሳውዲን መንግስት አሳስበዋል፡፡

የታክሲዎች ፖለቲካ

ጌታቸው ሺፈራው

ታክሲ ውስጥ በብዛት ከሚፃፉት ጥቅሶችም በላይ አንዳንዴ ታክሲ ውስጥ ካሉት ሰዎች ጣል የሚደረጉት የምሬት አሊያም ሌሎች የፖለቲካ ወጎች የማህበረሰቡን አመለካከት በግልፅ ያሳያሉ፡፡ መጀመሪያ ከጎናቸው ያለውን ሰው የሚጠራጠሩት ተሳፋሪዎች ሁኔታውን አይተው ብሶታቸውን ያወራሉ፡፡ አንዳንዶቹ ወሬ የሚያስጀምር ሳያስፈልጋቸው በከተማው የሚታዘቡትን በግልፅ ይቃወማሉ፡፡ ስርዓቱን የሚደግፉ፣ የሚያስመስሉም እንደሚገኙበት ሁሉ፡፡

tavxi politics

ዛሬ ያጋጠመኝ ግን ትንታኔ ነው፡፡ በቀልድም ቢሆን ደንበኛ የፖለቲካ ትንታኔ፡፡ ህዝቡ ፖለቲካን በደንብ እንደሚከታተልና እንደሚረዳ የሚያሳይ ትንታኔ ነው፡፡ በየ ሰዓቱ የሚነገረውን ፕሮፖጋንዳ ህዝብ ገልብጦ እንደሚያነበው የሚያሳይ አጋጣሚ፡፡

ከአራት ኪሎ ወደ ስድስት ኪሎ ከዛም ወደ ፈረንሳይ እየሄድን ነው፡፡ የፈረንሳይ ህዝብ ‹‹በወንበር›› የሚጫነው ከአራት ኪሎ እስከ ስድስት ኪሎ ብቻ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ከሰው ላይ ሰው ይደራረብበታል፡፡ ሰው እንደ ሽንኩርት ነው የሚጭኑት፡፡ ታክሲው እስከ አፍ ጢሙ ሞልቶ ‹‹ሁለት ሰው የቀረው›› እያለ የሚጠራን አንድ የታክሲ ረዳት ለቀልድ ‹‹ለምን ከላይ አትጭንም?›› ብዬው ‹‹ቢፈቀድ እንዴት አሪፍ ነበር መሰለህ! ጥሩ ሀሳብ ነበር›› ብሎኛል፡፡ ሰውን እንደበግ አስሮ ጭኖ ብር ከሀምሳ ሊያስከፍል!

አብዛኛዎቹ ረዳቶች በግድ ነው አጠጋግተው የሚጭኑት፡፡ ካልሆነ አልጠጋም ያለውን ‹‹ውረድ!›› ለማለትም ይዳዳቸዋል፡፡ ዛሬ የመጣንበት ታክሲ ረዳት ግን ተጫዋች ነው፡፡ ያስቃል እንጅ አያስገድድም፡፡ ‹‹ተጠጉ›› ሲልም እያባበለና በቀልድ ነው፡፡ ስድስት ኪሎ ስንደርስ ተሰብስቦ ታክሲ የሚጠብቀውን ሰው ‹‹ፈረንሳይ ፈረንሳይ!›› ብሎ የታክሲውን መዳረሻ ካሳወቀው በኋላ ‹‹ይኸው ቤታችሁ ነው ግቡ፡፡ ለሁላችሁም ይበቃል፡፡ ዋናው ፍቅር ነው!›› እያለ ጎረምሳ የ70 አመት ሽማግሌ፣ ነፍሰ ጥሩ ሴትና ህፃናት ጋር ሲጋፋ ፈንጠር ብሎ ይታዘባል፡፡ ምን አልባት ሊያሳዝነውም፣ ሊያስደስተውም ይችላል፡፡ ለምዶት ምንም ላይመስለው ይችላል፡፡ አብዛኛው ሰው ተገፍትሮም፣ ቦታ አይኖርም ብሎ ተስፋ ቆርጦም ተመልሷል፡፡ ቦታ ይኖራል ብለው ታክሲው በር ላይ ቆመው የቆዩት ሰዎች ቦታ እንደሌለ አውቀው ወደ ኋላ ሲመለሱ እሱ ወደ ታክሲው በር ተጠጋ፡፡ መቀመጫ አጥተው መተላለፊያው ላይ አጎንብሰው የቆሙ መንገደኞች አሉ፡፡ ታክሲዋ ወስጥ በግምት ከ19- 20 ያህል ሰዎች ተጠጋግተው ተቀምጠዋል፡፡ እድል የቀናቸውም አአንዳሚው ወንበር ላይም ተደርድረዋል፡፡ ያን ያህል ተጋፍቶ ወንበር ማግኘት ደስታ የሚፈጥርባቸው አሉ፡፡ በግፊያው ወቅት በነበረው ትይንት የሚስቀም፣ የሚናደደም አለ፡፡ እንዲህም ሆኖ ሶስት ያህል ሰዎችጠባቧ መተላለፊያ ላይ በሰው ተጣብቀው ‹‹ቆመው›› ቦታ እየፈለጉ ነው፡፡
የታክሲው ሚኒስቴር ዴኤታ (ረዳቱ) ቦታ እንደሌለ ቢያውቅም ‹‹ተጠጉላቸው፡፡ ተጠጉላቸው እንጅ!›› እያለ ያባብላል፡፡ ሁለቱ ወንበሮች ሶስት ሶስት ሰው ይዘዋል፡፡ አግዳሚው ወንበርም ሞልቷል፡፡ ሶስቱ ሰዎች አሁንም አልወረዱም፡፡ የታክሲ ሚንስቴር ዴኤታም ‹‹ኧረ ተጠጉ!›› ቢል የሚሰማው አላገኘም፡፡ ቦታ የለማ! እሱ እራሱኮ ቦታ ስለሌለ አልገባም፡፡ አንዱ ወረደ፡፡ ሁለቱ ተስፋ አልቆረጡም፡፡ ረዳቱን ታስፋ አድርገው እንጅ ቦታ እንደሌለስ አይተዋል፡፡

አሁን ረዳቱ ቢያንስ ለመቆሚያ ቦታ አግኝቷል፡፡ ከበሩ ትንሽ ወደ ታክሲው ገብቶ ‹‹ቤታችሁ ነው፡፡ ቆማችሁም ቢሆን ትሄዳላችሁ፡፡›› ይላቸዋል ሁለቱን መንገደኞች፡፡ ግን ማባበሉንም አላቆመም፡፡ ‹‹ተጠጉላቸው! ወገን ተጠጉላቸው! እነሱም እንደኛው መሄድ ይፈልጋሉ፡፡ የሀገራችን ሰዎች ናቸውኮ፡፡ አቅፈንም ቢሆን እንወስዳቸዋለን፡፡ ቻይና እንኳን በታክሲያችን ይሄድ የለ፡፡ ያው በሳምንት የሚፈራርስ መንገድ ቢሰራም ….›› እሱ የተናገረውን ሁሉ ለመያዝ ከባድ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ እሱ በላይ በላይ ስለሚናገር ከማዳመጥ በሳቅ ነው ያሳለፍነው፡፡ አሁን ቦታ እንደሌለ እሱም አውቋል፡፡ ግን ቀልዱን ቀጥሏል፡፡ እየሳኩም ቢሆን አንዱ ቀልዱ ግን ትንተና ሆነብኝ፡፡ ሳቄን አስቆመኝ፡፡ አስገረመኝ!

Taxi-Politics Ethiopia

ሰው መጠጋት ተስኖታል፡፡ የት ይሄዳል? እየቀለደ የሚጭነው ልጅ ግን በዛው ፖለቲካም ያወራል፡፡ ሰው አልጠጋለት ሲል ‹‹ተጠጉላቸው! ተጠጉላቸው እንጅ! ያው ከዚህ ሀገር መጠጋጋት እንጅ መተካካት የሚባል ነገር የለም፡፡ ተጠጉላቸው….›› ብሎ ሰውን ከታክሲዋ ጣራ በላይ አሳቀው፡፡ ግሩም ትንታኔ ነው፡፡ ‹‹ምሁራን›› በ10ና በ20 ገፅ ‹‹ጥናታዊ ፅሁፍ›› ሲገልፁት ያልሰማሁት ትንታኔ፡፡

እውነቱን ነው፡፡ መጠጋጋት እንጅ መተካካት የሚባል ነገር ብዙም አይታይም፡፡ እኔን የገረመኝ የእሱ ቀልድና ትንታኔ ብቻ አይደለም፡፡ የሰው ሳቅ ጭምር እንጅ፡፡ የታፈነው ህዝብ የሚቀልድለት ወይንም የሚናገርለት ሲያገኝ ፍርስ እስኪል ይስቃል፡፡ የሚፈራራው፣ የሚጠራጠረው መንገደኛ አይን ገላጭ ሲያገኝ ከጎኑ ምን እንዳለም ጭምር ይረሳዋል፡፡ በሬዲዮና በቴሊቪዥን ስለ መተካካት ብዙ ቢወራም ከልቡ አልገባም፡፡ ምክንያቱም ህዝቡ በውል የሚያውቀው መጠጋጋትን እንጅ መተካካት የሚባል ነገር እንደሌለ ነው፡፡ ታክሲም ውስጥ በፖለቲካውም!