የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንደሌሉ ገለፀ

• “የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል” 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ

• “የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው” 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ

አንዳርጋቸው ፅጌ

አንዳርጋቸው ፅጌ

በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንደሌሉ ማረሚያ ቤቱ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ ገልፆአል፡፡ 19ኛ ወንጀል ችሎት ሀምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም ለምስክርነት እንዲያቀርብ ለዛሬ ለጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡

ተከሳሾቹ ማረሚያ ቤቱ ሲያጉላላቸው ቆይቶ አሁን የለም ማለቱ ትክክል እንዳልሆነ የገለፁ ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ ማረሚያ ቤቱ ምላሽ የሰጠው በአራተኛው ትዕዛዝ መሆኑን ጠቅሶ የፍርድ ሂደታቸውን ከሚገባው በላይ እያጓተተ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ ገልፆአል፡፡ ‹‹መከላከል ከጀመርን አንድ አመት ከስድስት ወር ሆነ፡፡ በግዞት ነው ያለነው፡፡ የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው›› ያለው አቶ አሸናፊ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ‹‹ፌዝ ነው›› ብሎታል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ በበኩሉ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ሲጠቅሱ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኛ እንደሆኑ በመጠቆም ተቃውሞ አሰምቶ እንደነበር፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ ቃሊቲ እንደሚታሰር ገልፆ ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው እንደሌሉ መግለፁ ‹‹የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል›› ብሏል፡፡ ‹‹የእድሜ ልክ ወይንም የሞት ፍርደኛ የት ነው የሚታሰረው?›› ሲልም ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
3ቱ ተከሳሾች የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸውን እንደያዙ በቴሊቪዥን መግለፃቸውን አስታውሰው አሁንም ለሁለቱ አካላት ደብዳቤ እንደሚፅፉ ለፍርድ ቤቱ አሳውቀው የነበር ቢሆንም ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ሆኖም ግን 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱም 4ኛ ተከሳሽ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲቀርቡለት የሚያቀርበውን አቤቱታ ተመልክቶ ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ተላለፈበት

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲሁም በመፅሔት አሳታሚ ድርጅቱ ላይ የ200 ሺህ ብር ቅጣት ተወስኖበታል። ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ ከዓመት በፊት የሶስት ዓመት ከ3 ወር እስራት እንደተፈረደበት ይታወሳል።

ግዛው ታዬ

ግዛው ታዬ

ከ800 ሺህ ብር በላይ ታክስ በማጭበርበርና በሌሎች 14 ክሶች ጥፋተኛ የተባለው የሎሚ መጽሄት ዋና ስራ አስኪያጅ በ18 ዓመት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነ።
ውሳኔውን የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት ነው ያስተላለፈው።
ተከሳሾቹ ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ታዬ ግዛው ናቸው።
የፌደራል ገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፥ ድርጅቱም ሆነ ስራ አስኪያጁ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ክሱ እስከተመሰረተበት ድረስ ለተከታታይ 5 ዓመታት ኦዲት አልተደረጉም።
በዚህ ሂደትም ድርጅቱም ሆነ ግለሰቡ የታክስ ማጭበርበሮችን ሲያከናውን ቆይቷል ሲል የአቃቤ ህግ ክስ ያስረዳል።
የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የገቢ ግብር መሰወር የሚለውም በወንጀል ድርጊቱ ማስረጃዎች ጉዳይ ሲሆን፥ እንደ አቃቤ ህግ ገለጻ በዚህ ሂደት ውስጥ ድርጅቱ እና ስራ አስኪያጁ ለመንግስት መግባት የነበረበትን ከ800 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል ይላል።
በዚህ የክስ መዝገብም ግለሰቡ በችሎቱ አልቀረበም።
ይህን ተከትሎም የክስ ሂደቱ በሌሉበት እንዲቀጥል በተሰጠው በይን መሰረት አቃቤ ህግ የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
ጉዳዩን ሲመለክት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት በተከሳሾች ላይ የቀረበው ማስረጃ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ነው ሲል ቅጣቱን አስተላልፏል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንተኛ የወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ችሎት ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት በ200 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛውታዬ ላይ ደግሞ የ18 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ100 ሺህ የገንዘብ ቅጣት አስተላልፏል።
የድርጅቱ ሎሚ መፅሔት (ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንት) ባለቤትና ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ አቶ ግዛው ታዬ ከዚህ በፊት “አመጽ በማስነሳት እና መሰል የሽብርተኝነት ወንጀሎች” ክስ ተመስርቶበት በ50 ሺህ ብር ዋስ ከተለቀቀ በኋላ መሰደዱ ይታወቃል፡፡ የአሁኑ ክስና ፍርድም ተከሳሹ በሌለበት ተወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በተመለከተ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንን/ሬዲዮ ፋናን/ ዋቢ በማድረግ ቃልኪዳን ትዩብ ዘግቧል፡፡

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ ዓለም አቀፍ ተሸላሚ ሆነ

በሽብርተኝነት ተከስሶ 18 አመት የተፈረደበትና በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የፔን ካናዳ ደረጃ አንድ ሰብዓዊነት (PEN Canada’s One Humanity Award) ሽልማት ተሸላሚ መሆኑን ፔን ካናዳ ይፋ አድርጓል፡፡

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በፈረንጆቹ ግንቦት 2012 የባርባር ጎልድ ስሚዝ ሽልማት እንዲሁም በሰኔ 2014 የጎልደን ፔን ሽልማት ተሸላሚ እንደሆነ ይታወሳል፡፡ በካናዳ ቶሮንቶ እየተደረገ በሚገኘው 36ኛው ዓለም አቀፍ የፀሃፊዎች ፌስቲባል የፔን ካናዳ ደረጃ አንድ ሰብዓዊነት ሽልማትን ተሸልሟል፡፡
እ.ኤ.አ በ2011 የአረብ አብዮትን ተከትሎ መንግስት ለውጥ የማያደርግ ከሆነ ተመሳሳይ ህዝባዊ ንቅናቄ በኢትዮጵያም ሊከሰት ይችላል የሚል አስተያየቱን ማንጸባረቁን ተከትሎ ለእስር የተዳረገውና በፀረ ሽብር ህጉ ተከስሶ 18 አመት የተፈረደበት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ አምነስቲ ኢንተርናሽናልን ጨምሮ በበርካታ የሰብአዊ መብት ተቋማት ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ ዓለማቀፍ መብቱን መጠቀሙን በማስታወስ እስክንድር የህሊና እስረኛ እንደሆነ በመግለፅ ከእስር እንዲለቀቅ መጠየቃቸውን ቀጥለዋል፡፡ ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ከእስር እንዲለቅ ሲያሳስብ ቆይቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በእስር ቤቱ ከሚደረግበት ከፍተኛ ቁጥጥርና ጫና ባሻገር ከቤተሰብ ውጭ እንዳይጠየቅ ተከልክሎ ይገኛል፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ

በፍቃዱ ሀይሉ በ20 ሺህ ብር ዋስ ከእስር ተለቀቀ

ባለፈው ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም. አራቱ የዞን ዘጠኝ አባላት መካከል ናትናኤል ፈለቀ፣ አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና በሌለችበት ክስ የተመሰረተባት ሶሊያና ሽመልስ) በነፃ እንዲለቀቁ ሲወሰን፤ ዛሬ ጥቅምት 10 ቀን 2088 ዓ.ም. በዋለው ችሎት በወንጀለኛ መቅጫ ህግ 257/ሀ እንዲከላከል ተብይኖበት የነበረው በፍቃዱ ኃይሉ በ20 ሺህ ብር ዋስ ከእስር እንዲለቀቅ ተወሰነ፡፡

በፍቃዱ ኃይሉ

በፍቃዱ ኃይሉ

ብሎገርና ጋዜጠኛ በፍቃዱ ሀይሉ ጥቅምት 5 ቀን 2008 ዓ.ም ለልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት የዋስትና መብቱ እንዲከበርለት ጠይቆ በነበረው መሰረት ለዛሬ ጥቅምት 10/2008 ዓ.ም የዋስትናውን ጉዳይ ለማየት ቀጠሮ የሰጠው የልደታ ፍርድ ቤት በ20 ሺህ ብር ዋስ ወጥቶ ጉዳዩን በውጭ ሆኖ እንዲከታተል ወስኗል፡፡
አራቱ የዞን ዘጠኝ አባላት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ በተወሰነበት ወቅት ክሱ ከሽብርተኝነት ወጥቶ በማስረጃነት የቀረቡበት ፅሁፎች አመፅ ቀስቃሽ ናቸው በሚል በወንጀለኛ መቅጫ ህግ 257/ሀ እንዲከላከል የተወሰነበት በፍቃዱ ሀይሉ መከላከያ ምስክሮቹን እንዲያሰማ ለህዳር 27 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

በሳውዲ በተከሰው አደጋ ከ13 በላይ ኢትዮጵያውያን መሞታቸው ተገለፀ

ነብዩ ሲራክ
(ከሳውዲ ዓረቢያ)

መስከረም 13 ቀን 2008 ዓ.ም. የሐጅ ሥነ ሥርዓት ተከትሎ ሰይጣንን በድንጋይ በሚመታበት ክንዋኔ ምሳሌ፤በጀማራት ድልድይ በሚወስደው መንገድ በሀጅ ተጓዦች መካከል በመጨረሻው ሰዓት በተፈጠረ ግፊያና መጨናነቅ በተከሰተ አደጋ የሟ ቾች ቁጥር ወደ 1,100 ከፍ ያለ ሲሆን የቆሰሉት ቁጥርም ከፍተኛ መሆኑ ታውቋል፡፡ ከደረሰው አደጋ ውስጥ እስካሁን ከ13 በላይ ኢትዮጵያውያን ሲሞቱ ከ26 በላይ መቁሰላቸውን እና ከ204 በላይ መጥፋታቸውን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ለሒጅ ፀሎት ስነስርዓት የተጓዙ ኢትዮጵያውያንም 8 ሺህ ያህል እንደነበሩ ተጠቁሟል፡፡

Saudi Hajaj

ባለፈው ጳጉሜ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. በመካ ሳውዲ ዓረቢያ በደረሰው የክሬን መውደቅ አደጋ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ በርካታ ለሐጂና ፀሎት ስነስርዓት ወደስፍራው ባቀኑ ሀጃጆች ላይ ከህይወት መጥፋት እስከ አካል ማጉደል አደጋ ማድረሱ አይዘነጋም፡፡ በተለይ የመስከረም 13 ቱን አደጋ በተመለከተ ጋዜጠኛ ነብዩ ሲራክ እንደሚከተለው አቅርቦታል፡፡

ኢትዮጵያ…

* ኢትዮጵያ 13 በላይ ሞተውባታል ፣ 26 ቆስለውባታል
ከ204 በላይ ጠፍተውባታል ፣ ፍለጋው ቀጥሏል
* ጅዳ ከተላለፉት ቁስለኞች ኢትዮጵያዊ የለም
* ጅዳ ማህጀር የተላለፈው ሬሳ ማንነት ገና አልተጣራም
* ከማህጀሩ ሬሳ የአፍሪካውያን አለበት ተብሏል
* ኢትዮጵያውያን መካ ላይ ለፍለጋው በግል ተደራጅተዋል
* ማፈላለጉን በሁሉም ሆስፒታሎች መከዎን ገዷቸዋል
* ቤተሰብ ወይም የኢንባሲ ውክልና አምጡ ተብለዋል
* በመካው ክሬን የተጎዳች ኢትዮጵያዊት ሀጃጅ ተገኘች
* ኢትዮጵያቷ ሀጃጅ እስከዛሬ አልታወቀችም ነበር
* ልክ የዛሬ ሳምንት መሞቷ ተጠቁሟል

ህንድና ፖኪስታን …

* በማፈላልጉ የሳውዲ መንግስት አፋጣኝ እርዳታ ተጠየቀ
* የህንድን ፖኪስታን ቆንስሎች መግለጫ ሰጥተዋል
* ህንድ 46 ሞቶባታል 62 ቆስለዋል 82 ጠፍተውባታል
* ፖኪስታን 46 ሞተውባታል ፣ 8 ቆስለዋል 42 ጠፍተውባታል

የጠፉትን ፍለጋና ጭንቅ ድካሙ

ተቀማጭነታቸውን ሳውዲ ያደረጉ ፣ የተለያዩ ሀገራት ዜጎች ፣ በሀጅ ጸሎት ከአደጋው የተረፉ ሀጃጆችና ቤተሰቦቻቸው በሚና ጀማራት አደጋ የጠፉና የሞቱትን ሰዎች ለማፈላለግ ሌት ከቀን ወደ ሚና ፣ ጀማራትና መካ በመመላለስ አድካሚ የጭንቅ ሳምንት መግፋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው። የጠፉ ሃጅ ቤተሰቦች በግሩኘና በተናጠል ቢያፈላልጉም በርካታዎች እንዳልተሳካላቸው ይናገራሉ ። በአደጋው የሞቱ ኢትዮጵያውያን ቁጠር ገና ከአደጋ ቀን አንስቶ ከአምስት በላይ መሆኑ ግልጽ እያለ በኢትዮጵያ ኢንባሲ ፣ ቆንስልና የሀጅ ኮሚቴ የሚደረገው ፍለጋ የተቀናጀ ባለመሆኑ ዝርዝር መረጃው ቀርቶ የሞቱና የቆሰሉትን ዙሪያ ትክክለኛ መረጃ አልቀረበም ነበር ። ከብዙ ጉትጎታ በኋላም ትክክለኛውን መረጃ ለህዝብ ለማድረስ በርካታ ቀናት ወስዷል።
አሁንም በኢትዮጵያ ተወካዮች በኩል ቀናት የወሰደው የሞቱና የቆሰሉትን የማሳወቅ መረጃ ቅበላ ከቀናት በፊት ይፋ ቢደረግም አሁንም ቁጥሩ እየጨመረ ከመጣው የሟቾቸ ብዛት አንጻር የመረጃ ክምችቱን የማሻሻል ስራ እየተሰራ አይደለም በሚል ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ የመካና ጅዳ ነዋሪዎች ገልጸውልኛል፡፡

ኢትዮጵያን ወጣቶች በመካ ሚናው ፍለጋ

የሀጅ ኮሚቴ አካሄድ አዝጋሚ መሆን ያሳሰባቸው በመካ ዙሪያ የሚገኙ ወጣቶች ራሳቸውን በማደራጀት መካ ላይ በሚገኙ በ13 ሆስፒታሎች በአደጋው የተጎዱትን ለማግኘት ፍለጋ ጀምረዋል ። በትናንሽ ሆስፒታሎች ችግር ባይገጣማቸውም መሊክ ፈይሰል ፣ ሄራ ፣ ጀበለር ኑርና መሊክ አብደላ በተባሉ ትላልቅ ሆስፒታሎች እንዳይገቡ ተከልክለዋል ። ያም ቢሆን በቀሩት አንዳንድ ሆስፒታሎች ማፈላለጉን በተወሰነ መልኩ በማሳለጥ 15 ያህል ቁስለኞችን ማግኘታቸውን ጠቁመውኛል። መሊክ ፈይሰል ፣ ሄራ ፣ ጀበለር ኑርና መሊክ አብደላ በተባሉ ትላልቅ ሆስፒታል ሃላፊዎች “የቤተሰብ ወይም የኢንባሲ ውክልና አምጡ !” በማለት አንደከለከሏቸው ወጣቶች አጫውተ ኛል። ይህንን ችግር እንዳጋጠኛቸው ያጋጠማቸውን ለሀጅ ኮሚቴ በመጠቆም ተቀራርበው ለመስራት መሞከራቸው የገለጹልኝ የአፈላላጊ ቡድኑ አባላት አብሮ የመስራት ሙከራውም አለመሳካቱን ገልጸውልኛል! “ከጅዳ ለመጡ ኮሚቴ ነን ” ላሉን ሰዎች በሀጅ ኮሚቴ ወይም በጅዳ ቆንስሉ በኩል ውክልናውን ወይም መታወቂያ ቢሰጠን ብለን ጠይቀን ነበር ያሉኝ አንድ ወጣት በበኩላቸው ” መጣዎቂያ ይሰጣቹሃል!” የሚል ቃል ቢገባላቸውም እስካሁን ከኮሚቴውም ሆነ ከሌላ ወገን መልስ ባለ መሰጠቱ ጥረታቸው መሰናክል እንደገጠመው ገልጸውልኛል፡፡

በአንጻሩ የተመሳሳይ ችግር ያለባቸው የአንዳንድ ሀገራት የመንግስት ተወካዮችና ዲፕሎማቶች እንኳንስ ነዋሪው ተደራጅቶ መጥቶ ነዋሪዉን ለበጎ ስራና በማቀናጀትና በማቀዳጀት በሽዎች የሚቆጠሩ ልዩ የጠፉ ሃጃጆችን አፈላላ ግብረ ሃይል አቋቁመው በመካ ፣ ሚናና ጀናራት ማሰማራታቸው ይጠቀሳል ። የነዋሪውንና የሀጃጆችን ጭንቀት በመረዳትም የቆሰሉትንና የሞቱትን ፎቶ መረጃዎች ከሳውዲ መንግስት በመውሰድ ለዜጎቻቸው አቅርበዋል።

የመካ ወጣቶች በፍለጋው እንደ “አሳ ጎርጓሪ …”

አበው ” አሳ ጎርጓሪ…” የእኒሁ በመካ ዙሪያ ያሉ ወጣቶች በሚና ጀማራት የተጎዱ ሰዎችን ሲያፈላልጉ በመካው ክሬን ተጎድታ የሞተች ኢትዮጵያቷ ሀጃጅ ማግኘታቸው ታውቋል። እስከ ዛሬ የሀጅ ኮሚቴም ሆን የጅዳ ቆንስል ምንም መረጃ ስለሌላቸው ማንም ሳይደርስባት መሞታን ገልጸውልኛል። ይህችው ኢትዮጵያዊት ሃጃጅ በጉዳቱ በከባድ ቆስላ በህክምና ስትረዳ ከቆየች በኋላ ባሳለፍነው ሳምንት በተከበረው የኢድ አል አድሃ እለት ህይዎቷ ማለፉን ከዶክተሮች እንደተገለጸላቸው ሬሳውን አየሁ ያለ ጎልማሳ አስረድቶኛል። እኔም ጉዳዩን በተዘዋዋሪ መንገድ ለማጣራት ባደረግኩት ሙከራ የተባለችው እህት ሬሳ በሆስፒታሉ የሬሳ ክፍል እንደሚገኝ ማረጋገጥ ችያለሁ! በዚህች ሟች ሀጃጅ ዙሪያ የደረሰኝ መረጃ ለሃጅ ኮሚቴና ለጅዳ ቆንስል በተመሳሳይ ሁኔታ መቅረቡን አረጋግጫለሁ፡፡

ሀጃጆችን ፍለጋ በጅዳ ሆስፒታሎች

አደጋው ከደረሰ በኋላ ባሉት ቀናት የተጎጅዎች ቁጥር ከፍ እያለ በመምጣጡ ወደ 200 የሚጠጉ ቁስለኞች ወደ ጅዳ መተላለፋቸው ይታወሳል ። ይህንኑ ተከትሎ የጅዳ ቆንስል በሳምንቱ መጀመሪያ ዲፕሎማቶችን ከተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር በቡድን በማሰማራት ፍለጋ ጀምረው ነበር ። በዚሁ ፍለጋ ከተጋበዙት መካከል የሴቶች ማህበርና የጅዳ ኮሚኒቲ የሚገኙበት ሲሆን የሴቶች ማህበር አባላት ሲሳተፉ የጅዳ ኮሚኒቲ ግን በፍለጋው አልተሳተፈም ። ለሁለት ቀናት በተደረገው ፍለጋ አንድም ኡትዮጵያዊ አልተገኘም።

የተደረገው ፍለጋ ጅዳ ማህጀር የሚገኘውን የሬሳ ማቆያ ያካተተ ቢሆንም ወደ ማቆያው የተላለፈው ሬሳ ማንነት ገና ባለመጣራቱ መረጃ ማግኘት እንዳልተቻለ የጅዳ ቆንሰል ባወጣው መረጃ ጠቁሟል ። እስከ ዛሬ ረፋድ በዚሁ ሬሳ ማቆያ ተጨማሪ ሬሳዎች መግባታቸው ሲረጋገት ወደ ማህጀሩ ማቆያ አፍሪካውያን ሬሳ እንደሚኖርበት ተገምታል።

ሞተው መለየት ያልቻሉትን የማጣራቱ ስራ

በሳምንት የአደጋው አድሜ በዋናነት አሳሳቢ የሆነው ቁርጡ የታወቀው የሞቱትና የቆሰሉት ዜጎች አልሆነም። ሞተው ፎቷቸውና ቆሰለውም ከሆነ ዝርዝራቸው ያልተገኙት ጉዳይ ብዙ ዜጎችን በመንፈስ እያስጨነቀና እያንገላታ ይገኛል። መዳረሻቸው ” ጠፋ” ከሚባሉት መካከል በደረሰው አደጋ ፊታቸው መለየት ያስቸገረ ይገኙበታል የሚል ጥርጣሬ ቢኖርም የሟቾችን ሬሳ ለመለየት የተለያዩ እርንጃዎች ቀርበዋል። ሀጃጆች በገቡበት አሻራ ለመለየት እየተወሰደ ያለው ማጣራት ረዠም ጊዜ መውሰዱ ተቃውሞ እየቀረበበት መሆኑ ይጠቀሳል ። የሳውዲ መንግስት የየጤና ጥበቃና የፖስፖርት ክፍል ኃላፊዎች ስለመለየቱ ስራ ሲናገሩ በሶስት መንገድ እንደሚከወን ያስረዳሉ ። እስካሁን መለየት ያልተቻለውን ሬሳ ለመለየት የቀረቡት ዘዴዎችም 1ኛ / በገቡበት አሻራ 2ኛ / በገቡበት ፎቶ መለየት እና 3ኛው / የስጋ ዘመድ ቤተሰቦቻቸው እየቀረቡ DNA በመስጠት መለየቱ እንደሚከወን ይናገራሉ ! አሻራቸው የተነሱ ሬሳዎች ውጤት በከነገ ጀምሮ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ቢጠበቅም የተረጋገጠ መረጃ እስካሁን አላገኘሁም፡፡

የሟቾች ቁጥር ማሻቀብ

የሚና አረፋት አደጋ ከተከሰተ ሰባተኛ ቀኑን የደፈነ ቢሆንም በመቶዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ ዜጎች መዳረሻ እስካሁን ሊታወቅ አልቻለም ። ካሳለፍነው ሳምንት ጀምሮ በማህበራዊ መገናኛ መረቦች እስከ ታዋቂ መገናኛ ብዙሀን የዜና አውታሮች የጠፉና ያልተገኙት ዜጎች ጉዳይ አሳሳቢ እንደሂነ ቀጥሏል! ምንም እንኳን የሳውዲ መንግስት የሚቱትን ቁጥር ከ 769 ፈቀቅ ባያደርገውም ሞተየ ተብለው ፎቷቸው የተለጠፉት ቁጥር ከ1500 በላይ እየሆነ መጥቷል። የመንግስት ሃላፊዎች መሞታቸው ተረጋግጦ ፎቷቸው የሚለጠፉት ቁጥር እያደር አሳሳቢ ሆኗል። ለምን ቁጥሩ አደገ ተብለው ሲጠየቁ ” በፎቶው የተካተቱት ሀጅ ከተጀመረ ወዲህ በልብ ድካምና በተለያዩ አደጋዎች የሞቱት ከአደጋው ጊዜ ሰለባዎችን ጭምር ነው “ቢሉም የቁጥሩ በአፋጣኝ ማፈግ ብዙዎቹን አሳስቧል።

የህንድና ፖኪስታን ተሞክሮ

የሳውዲ መንግስት የጠፉትን በማፈላለግ ሂደቱን እንዲያፋጥንና የዜጎቻቸው እጣ ፈንታ እንዲያሳውቅ አጥብቀው እየጎተጎቱን ካሉት ሃገራት ዲፕሎማቶች መካከል ህንድና ፖኪስታን የሳውዲ መንግስት አስቸኳይ ጥሪና ተማጽኗቸውን በማቅረብ ላይ ናቸው፡፡

የፓኪስታን አምባሳደር መብዙር አለ ሀቅ እና ቆንስል ጀኔራል አፍታብ አህመድ በተገኙበት ሳውዲ የሀጅና ኡምራ ሚኒስትር በድር ሀጃር ጋር ምክክር ያደረጉት የፖኪስታን የሀይማኖት ጉዳዮች ተወካይ ሳድር መሀመድ በጠፉት ፣ በቆሰሉትና በሞቱት ፖኪስታን ሃጃጆች ዙሪያ መንግስታቸ ው አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጣቸው የሚኒስትሩን አሳስበዋል ። በአደጋው 46 የሞቱባት ፣ 8 የቆሰለባት እና 42 የጠፉባት ፖኪስታን የሀይማኖት ጉዳይ ተወካይ ሳድር መሀመድ ከሳውዲ ሃጅ ሚኒስትሩ ጋር ባደረጉት ውይይት በሚና ጀማራት አደጋ የቆሰሉት ፣ ሞተው ማንነታቸው ተጣርቶ ባልተነገረ ዜጎቻቸው ዙሪያ ጉዳይ ፖኪስታናውያን ን በእጅጉ ማሳሰቡን ገልጸው አስቸኳይ መፍትሔ እንደሚሹ ለሃላፊው በአጽንኦ አስታውቀዋል። በተለይም መዳረሻቸው የጠፉ ዜጎቻቸው ጉዳይ የሚወዷቸው ቤተሰቦች የጠፉባቸው ቤተሰቦችን በጣም ያጨናነቀ መሆኑን ጠቁመው የሳውዲ መንግስት ምለሽ እንዲሰጣቸው ተማጽኗቸውን አቅርበዋል፡፡

በአደጋው 46 በሞት ያጣችው 62 የቆስለባትና 82 የጠፉባት ህንድ ዲፕሎማቶች በበኩላቸው የሀጃጅ ዜጎቻቸው ጉዳይ ዜጎቹና መንግስትን እንቅልፍ እንደነሳቸው አሳስበዋል ። በጅዳ የሚገኘው የህንድ በቆንስል መስሪያ ቤቷ የጉዳዩን አሳሳቢነት ለሳውዲ መንግስት ለመሳሰብ ትናንት ሮብ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን በዋናነት የሰጡት የህንድ ሀጅ ኮሚቴ ዋና ኃላፊ መሀቡባ ሙፍቲ የመሩት ሲሆን ስጋራቸውንና የጠፉ ቤተሰብ አባላት ጉዳይ መጣራት መጓተት መንግስታቸውን እንዳሳሰበው በመጠቆም አስቸኳይ መፍትሔ ይፈለግ ዘንድ የሳውዲን መንግስት አሳስበዋል፡፡