ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የቀረበበት ክስ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት አመልክቷል
ከሽብር ቡድን አመራሮች ጋር በፌስቡክና በስልክ ግንኙነት በመፍጠር መረጃዎችን አስተላልፏል በሚል የሽብር ክስ የቀረበበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ክሱ ተሰርዞለት በነጻ እንዲሰናበት በክስ መቃወሚያው አምልክቷል፡፡

ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረበው ጋዜጠኛ ጌታቸው አራት ገጽ ያለው የክስ መቃወሚያውን ለችሎቱ አስገብቷል፡፡
ተከሳሹ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አንቀጽ 7(1)ን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበበት ክስ “በማናቸውም መልኩ በሽብር ተግባር መሳተፍ” የሚለው፣ አንድ ሽብርተኛ ተብሎ የተሰየመን ድርጅት ስም መጥራት፣ የሽብር ድርጅቱ በሚጠቀምበት ሚዲያ መጠቀም ወይም የሽብር ድርጅት አባል ነው የተባለን ሰው ለሽብር ድርጅቱ አንዳችም ፋይዳ በሌለው ነገር ላይ ማነጋገር ሁሉ ይጨምራል በሚል ተለጥጦ መቅረብ እንደሌለበት በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡
ተከሳሽ አቃቤ ህግ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ስለነበሩ ክስተቶች የሽብር ድርጅት አመራር ናቸው ላላቸው ሰዎች መረጃ ማስተላለፍን በሽብር ድርጅቱ ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ እንደሆነ አድርጎ ማቅረቡ ስህተት ብቻ ሳይሆን ከህጉ አላማም በእጅጉ የራቀ ነው ሲል ተከሳሹ ተቃውሟል፡፡
ስለሆነም የአዋጁን አንቀጽ 7(1) ጠቅሶ ክሱን ማቅረብ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕጉ አንቀጽ 112 ላይ በወንጀል ጉዳይ በሚቀርብ ክስ ስለ ወንጀሉ እና የወንጀሉ ሁኔታ ስለሚሰጠው ዝርዝር ወንጀለኛው የፈጸመውን ተግባር ወንጀል ከሚያደርገው ሕግ አነጋገር ጋር የተቀራረበ መሆን አለበት የሚለውን አስገዳጅ ድንጋጌ የሚጥስ በመሆኑ የአዋጁ አንቀጽ መጠቀሱ አግባብ አይደለም ተብሎ ክሱ እንዲሰረዝለት አመልክቷል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው በሁለተኛነት ያቀረበው መቃወሚያ የህጋዊነት መርህን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ ህገ-ወጥነቱ በህግ ያልተደነገገን ድርጊት ወይም ግድፈት እንደወንጀል ሊቆጥረውና ቅጣት ሊወስንበት እንደማይገባ በማስታወስ በክሱ ዝርዝር ላይ የተመለከቱ በህግ ወንጀል ናቸው ተብለው ያልተደነገጉ ድርጊቶችን ጠቅሶ ክሱ እንዲሰረዝለት የሚጠይቀውን መቃወሚያ አስገብቷል፡፡
ተከሳሹ በሦስተኝነት ያቀረበው የመቃወሚያ ነጥብ የተከሰሰበትን ወንጀል ለይቶ በማወቅ መልስ ለመስጠት እንዲያስችለው ግልጽ ሊሆኑለት የሚገቡ ነጥቦችን በመጥቀስ ነው፡፡ በዚህ መቃወሚያ ስር ተከሳሹ ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ እንደተቀበለ ከመጠቀሱ በቀር ተልዕኮው ምን እንደሆነ፣ መቼ፣ ከማን እና በምን አይነት መንገድ ተልዕኮውን እንደተቀበለ ከሳሽ ግልጽ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡ ተከሳሹ ‹‹የሽብር ቡድኑ በሚጠቀምበት ሚዲያ›› በሚል የቀረበበት ክስ በህግ ቋንቋ ምን ማለት እንደሆነም አልተገለጸም ሲል ጠቃውሟል፡፡
በመሆኑም ከሳሽ እነዚህና ሌሎች በመቃወሚያው ላይ የተመለከቱ ነጥቦችን ግልጽ እንዲያደርግ፣ ይህን ማድረግ የማይችል ከሆነ ግን ክሱ ተሰርዞ በነጻ እንዲሰናበት ተከሳሹ ለችሎቱ በመቃወሚያው ላይ አመልክቷል፡፡
ችሎቱ አቃቤ ህግ ተከሳሹ ያቀረበውን የክስ መቃወሚያ ተመልክቶ መልስ እንዲሰጥበት ለመጠባበቅ ለሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡-EHRP
ኦብነግ የኢትዮጵያን መንግሥት በጭፍጨፋ ከሰሰ
በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ውስጥ የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይል ጥቃት አድርሰው ሃምሣ አንድ ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ) ሰኔ 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ስሞታ አሰምቷል፡፡

ሶማሌ ክልል ውስጥ ጃማ ዱባድ በሚባል መንደር ሰሞኑን የመንግሥት ወታደሮችና የክልሉ ልዩ ፖሊስ ኃይሎች በመንደርተኞች ላይ ጥቃት አድርሰው 51 ሰው ገድለዋል ሲል የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር – ኦብነግ ከስሷል፡፡
“የመንግሥቱ የፀጥታ ኃይሎች በሌሎች አካባቢዎችም በተለያዩ የቅርብ ጊዜያት ከሦስት መቶ በላይ ሰላማዊ ሰዎችን ገድለዋል” ያሉት የኦብነግ ቃል አቀባይ አቶ ሃሰን አብዱላሂ ድርጅታቸው ጉዳዩን ለዓለምአቀፍ ተቋማት ለማድረስ ማስረጃዎችን እያጠናቀረ መሆኑን ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የቪኦኤ የሶማሊኛ ዝግጅት ክፍል ወደ አካባቢው ደውሎ ያነጋገራቸው የጎሣ መሪ ወታደሮቹ ስድስት ሕፃናትና ሴቶችንም ጨምሮ ሃያ አራት ሰዎችን መግደላቸውን አመልክተዋል፡፡ ሌሎች ምንጮች ደግሞ ወታደሮቹ መንደሪቱን ማቃጠላቸውንና አሥር ሰዎች የገበቡበት እንደማይታወቅ ጠቁመዋል፡፡ ስለጉዳዩ ከክልሉም ሆነ ከፌደራል መንግሥቱ የተሰጠ መግለጫ የለም፡፡
ምንጭ፡- VOA Amharic service
የኢትዮጵያ መንግሥት በአሜሪካን ሀገር የፈፀመውን ህግወጥ የቦንድ ሽያጭ ገንዘብ ከነወለዱ እንዲመልስ ተወሰነበት
(አዲስ ሚዲያ) የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካን ህገወጥ የቦንድ ሽያጭ በማድረግ የሰበሰበውን ገንዘብ እንዲመልስ ተወሰነበት። የአሜሪካን የቦንድ ሽያጭና ግዥን የሚቆጣጠረው ኮሚሽን ባቀረበው ክስ መሰረት፤ የኢትዮጵያ መንግስት መብራት ኃይል ኮርፖሬሽን በአሜሪካን ባልተመዘገበ የቦንድ ሽያጭ የሰበሰበውን 5.8ሚሊዮን ዶላር እና 6 መቶ ሺህ ዶላር ወለድን ጨምሮ በድምሩ 6.45 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንዲከፍል ተስማምቷል።

የኢትዮጵያ መንግሥት ከ2004 ዓ.ም. እስከ 2006 ዓ.ም. በህገወጥ መንገድ ገንዘቡን ሰብስቦት የነበረው ነዋሪነታቸው በአሜሪካን ሀገር ከሆኑ 3,100 ኢትዮጵያውያን ነበር፡፡ ስለሆነም በቦንድ ግዥ የተሰበሰበው ገንዘብ በሙሉ ከነ ወለዱ እንዲመለስ የተደረገው፤ የአሜሪካን ሴኩዩሪቲ ኤንድ ኤክስቼንጅ ኮሚሽን (SEC) ህግን ተላልፎ በመገኘቱ መሆኑን የኮሚሽኑ መግለጫ አስታውቋል። የኢትዮጵያ መንግሥትም የአሜሪካን ህግ በመጣስ የቦንድ ሽያጭ ማካሄዱን በማመን፤ የቦንድ ሙሉ ሽያጩን ከነ ወለዱ ለአሜሪካ መንግሥት ለሚመለከተው አካል ለመክፈል መስማማቱን ኮሚሽኑ በዋሸንግተን ዲሲ ሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል፡፡
እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ መከላከል አትችሉም ተባሉ
ማህሌት ፋንታሁን
የካቲት 4 ቀን 2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል በዋለው ችሎት እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ( ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ኢየሩሳሌም ተስፋው፣ ፍቅረማርያም አስማማው እና ደሴ ካህሳይ) አቃቢ ህግ ያቀረበባቸውን ክስ በሰነድና በአንድ የሰው ምስክር ማስረጃዎች አስረድቷል በሚል ተከሳሾች መከላከል ይገባቸዋል ሲል ፍርድ ቤቱ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

ውሳኔውን ተከትሎም መከላከያ ማስረጃዎች ያቀርቡ እንደሆነ በሚል ፍርድ ቤቱ ጠይቆ፣ ተከሳሾች 200 የሰው ምስክሮችና የሰነድ ማስረጃዎች በጋራ እንደሚያቀርቡ አሳውቀው ነበር፡፡ ከዛ በኋላ በነበሩ ቀጠሮዎችም ምስክሮቻቸውን በዝርዝር አስገብተው ነበር፡፡ እንዲሁም ከዛሬ ግንቦት 30 እስከ ሰኔ 8 ቀን 2008ዓ.ም. ድረስ ምስክሮቻቸውን እንዲያሰሙ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው የነበረ ቢሆንም፤ የቀጠሯቸው ቀን ሳይደርስ፤ ባለፈው ሳምንት ፍርድ ቤት ቀርበው ጭብጥ እንዲያሲዙ ተጠይቀዋል። እነሱም የምስክርነት ጭብጥ ምስክሮች መሃላ ሳይፈፅሙ መያዝ እንደሌለበት ለፍቤቱ አስረድተው ውሳኔውን ለመስማት ለዛሬ ተቀጥረው ነበር።

ይሁን እንጂ አራት ወር ሙሉ ፍርድ ቤቱ ሲሰጥ ከነበረው ትዕዛዝ በተለየ “መከላከያ ምስክር ማሰማት የለባችሁም ስለዚህ ለፍርድ ብይን ሃምሌ 13, 2008 ቅረቡ” የሚል ውሳኔ አስተላልፏል።
ምንጭ፡-ከማህሌት ፋንታሁን ፌስቡክ ገፅ የተወሰደ
በጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው የሽብር ክስ በንባብ ተሰምቷል
*ተከሳሹ ጥቁር ልብስ ለብሰሃል በሚል በቀጠሮው ሰዓት አለመቅረቡ ታውቋል

የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ በሆነው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. የመሰረተው የሽብር ክስ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡
ተከሳሹ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርቦ ክሱ ሊነበብለት የነበር ቢሆንም ከጠበቃው ጋር ሳይመካከር ክሱ እንዲነበብለት እንደማይፈልግ በመግለጹ በቀጠሮ ሰንብቶ ዛሬ ተነቦለታል፡፡ ከክስ ዝርዝሩ መረዳት እንደተቻለው ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ላይ የቀረበው ክስ የጸረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ሆኗል፡፡
አቃቤ ህግ በክሱ ላይ እንዳመለከተው ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል ጠቅሷል፡፡
ተከሳሹ ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡
ችሎቱ ክሱን በንባብ አሰምቶ ሲያጠናቅቅ በተከሳሹ ላይ የተጠቀሱ የአቃቤ ህግ የማስረጃ ዝርዝሮችን በተመለከተ እንደገለጸው፣ ተከሳሹ የተጠቀሰበት ማስረጃ የሰነድ ማስረጃ ብቻ መሆኑ ተገልጹዋል፡፡
ተከሳሹ ከግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ ቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኝ ሲሆን፣ በዛሬው የችሎት ቀጠሮ በጠዋት እንዲቀርብ የሚል ቢሆንም የእስር ቤቱ አስተዳደር ‹‹ጥቁር ልብስ ለብሰህ ፍርድ ቤት መሄድ አትችልም›› በሚል ጠዋት ሳያቀርቡት ከቆዩ በኋላ ከሰዓት ሊያቀርቡት ችለዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሽ የክስ መቃወሚያን ለመቀበል ለሰኔ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- EHRP