Tag Archives: Ethiopia

የኢትዮጵያ ድርቅና ርሃብ ትናንት እና ዛሬ

ብስራት ወልደሚካኤል

በርግጥ ድርቅ በተፈጥሮ ሊከሰት የሚችል የአየር መዛባት አደጋ ውጤት ነው፡፡ ድርቅ ባለፀጋም ሆነ እንደኛ ባሉ ደሃ ሀገራት ሊከሰት ይችላል፡፡ የድርቁ መንስኤም ተፈጥሯዊ አሊያም ሰው ሰራሽ ሊሆን ይችላል፡፡

Ethiopia_drought_cows

ርሃብ በምግብ እጥረት የሚከሰት ሲሆን፤ መንስዔውም የምርት አቅርቦት ማነስ አሊያም የምግብ ፍላጎት ከምርት አቅርቦት ጋር አለመጣጣም ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ዋነኛ ምክንያት ደግሞ ፍላጎት እና አቅርቦትን አሊያም የሀገር ምርት ለማሳደግ ሀገሪቱ የምትከተለው ፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡ በኢትዮጵያም በተለያዩ መንግሥታትም ሆነ ዘመን ድርግቅን ተከትሎም ይሁን ያለድርቅ ለተከሰቱት እና እየተከሰቱ ላሉ ችግሮች ዋነኛ መንስዔው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡

ርሃብ በተፈጥሮ የሚከሰት ሳይሆን የሀገሪቱ መንግሥት ስርዓት በሚከተለው የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡ ደካማ ወይም ተፈጥሮንና የሀገሪቱን ህዝብ አቅምና ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ፖሊሲ ትግበራ ባለበት ሀገር ድርቅ ከተከሰተ ምንጊዜም ርሃብ አለ፡፡ ርሃቡ ምንም እንኳ ድርቅን ተከትሎ የመጣ ቢሆንም ዋነኛ ምክንያቱ ግን የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡

በሀገራችን በተከታታይ የተከሰተውም ርሃብ ዋነኛ ምክንያት ድርቁ ሳይሆን የደካማ ፖሊሲ ውጤት ነው፡፡ ምክንያቱም ድርቅ የተከሰተባቸው ሀገሮች ሁሉ ርሃብ አይከሰትም፡፡ ደካማ ፖሊሲ ያለባቸው ሀገሮች ግን ድርቅ ካለ ምንም ጊዜም ርሃብ አለና፡፡

በዘመናዊ ኢትዮጵያ የመንግሥት ታሪክ ጎልቶ መታወቅ የጀመረው በዳግማዊ አጼ ምኒልክ ዘመን ቢሆንም እስከዛሬም ይህን ችግር የሚቀርፍ የመንግሥት ፖሊሲና ተግባር አልታየም፡፡ አሳዛኙ ነገር በዘመነ ዳግማዊ ምኒልክ የነበረውን ርሃብ ለዓለም ማኀበረሰብ አሳውቆ ተገቢውን ርዳታ ይቆ ለተጎጂዎች በማድረስ ህይወት ለማትረፍ ቴክኖሎጂው ችግር ነበረብን፡፡ ቢሆንም ግን ይህን ክፍተት ንጉሱን ጨምሮ ባለሟሎቹ (አመራሮቹ) የተፈጠረውን ርሃብ በድርቅ ላይ ሳያመሃኙ ወዲያው ለህዝቡ በማሳወቅ ወገን ለወገን በሚችለው አቅም እንዲረዳዳ እና የመንግሥት ካዝና (ለችግር ጊዜ የተቀመጠ የእህል ጎተራ) ሳይቀር በይፋ ተከፍቶ ለተጎጂዎች ወዲያው እንዲደርስ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ ይህ በጎ አስተሳሰብ ቢሆንም ከነበረው የእህል ክምችት አናሳነት እና የትራንስፖርት ችግር አኳያ ለሁሉም ተጎጂ እኩል ማድረስ ባይቻልም መንግሥት ችግሩን አምኖ የህዝቡን ድጋፍ ጤቆ ተገቢውን ምላሽ አግኝቶ ነበር፡፡ ቢሆንም ግን ብዙ ወገኖቻችንን በርሃቡ አጥተናል፡፡

Ethiopian famine 2015

በዘመነ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ የነበረው በ1965/66 ዓ.ም. ርሃብ ግን ንጉሱም ህዝቡም እንዳያውቁ መኳንንቱ ለመሸፋፈን ሞክረዋል፡፡ በዚህም መኳንንቱ ጠግበው እየበሉ በርካታ ወገኖቻችን በወቅቱ በተከሰተው ርሃብ ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ይሄ በተለይ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍለክ እጅግ የከፋ የታሪክ ጠባስም ጥሎልን አልፏል፡፡

በዘመነ ደርግ በተለይ በ1977 ዓ.ም. የተከሰተውን ልብ ይሏል፡ የተከሰተውን ርሃብ የሀገሪቱ መራሄ መንግሥት መንግሥቱ ኃይለማርያምና ሁሉም ሹማምንት ቢያውቁም ከሀገሪቱ ህዝብ (ርሃብ ካልነካቸውን) እና ከዓለሙ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ተሞክሯል፡፡ በዚህም ብዙ ወገኖቻችን በጊዜ ማዳን ሲቻል በሞት ተነጥቀናል፤የበለጠ ክብራችንም እንዲዋረድ በር ከፍቷል፡፡

በዘመነ ኢህአዴግ ከአንዴም ሶሰት ጊዜ፤በተለይ በ1985ዓ.ም.፣ 1986/87 ዓ.ም. እና የአሁኑን የ 2007/08 ዓ.ም. ርሃብ መንግሥት ከሀገሬው ህዝብና ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ሞክሯል፤ባይችልም፡፡ በቅርቡ በተለይም ባለፈው ክረምት በምስራቁ የሀገራችን ክፍል የተጀመረው ርሃብ ወደ ሰሜኑ እና መካከለኛው የሀገራችን ክፍል በፍጥነት ቢዛመትም መንግሥት በምግብ ራሳችንን ችለናል፣ ርሃብ አልተከሰተብ፣ …ወዘተ የሚለው ፈሊጥ አንድ ወር እንኳ አልሞላውም፡፡ ርሃቡ ልክ እንደሰደድ እሳት እና አውሎ ነፋስ ማዕበል ምስራቁን፣ ሰሜኑን እና ከፊል መሐከለኛ የሀገራችን አካባቢ በፍጥነት ተዛመተ፡፡ ርሃብ የለም፣ በምግብ ራሳችንን ችለኛል፣…የክፉዎች ወሬ ነው ሲባል የነበረው ርሃብ፤ አሁን መንግሥት በህዝብ ላይ እና በእንሰሳቶቻቸው ላይ ከፍተኛ እልቂ ከደረሰ በኋላ “ኢሊኖ በሚባለው ድርቅን ተከትሎ በነሳው ርሃብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር 5 ሚሊዮን አካባቢ ደርሷል፣ ከዓለም አቀፉ ለጋሽ ድርጅቶች እና ሀገራት አፋጣኝ እና በቂ ድጋፍ አላገኘንም,…” የሚል ይፋ ልመናዊ መግለጫ ተሰጠ፡፡ የተራቡ ወገኖቻንን ቁጥር መገመትና መናገር ቢከብድም አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ግን ከ 10 ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ይገመታል፡፡

በጣም የሚያሳዝነው ሁሉም ስርዓቶች በተፈጥሮ ሃብትና በግብርና ላይ ያላቸው ፖሊሲ የአንዳቸው ከአንዳቸው የማይሻል፣ ያልተለየ ቢሆንም በዳግማዊ ምኒልክ ጊዜ ግን ርሃብ ለመደበቅ አልተሞከረም፤ ይልቁንም ከመንግሥት ካዝና በተጨማሪ ህዝቡ እንዲረዳዳ የጠማፅኞ ጥሪ ተደረገ እንጂ፡፡ በኃይለስላሴ ዘመንም ቢሆን ሹማምንቱ ከንጉሱ እና ርሃብ ካልደረሰበት ህዝብ ለመደበቅ ቢሞከርም መደበቁ አልቻሉም፡፡ የደርግና ኢህአዴግ ስርዓት ክፋት ግን ከበታች ሹም እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ድረስ ርሃቡን እያወቁ ለመደበቅ መሞከራቸው የፖሊሲ ችግራቸውን ለመደበቅ ከመሞከራቸው ይልቅ በሰብዓዊ ፍጡር ህይወት ላይ ያላቸውን ጭካኔ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ርሃብ ቀን አይሰጥምና፡፡ ርሃብ የሰውንም ሆነ የእንሰሳትን ህይወት ሲቀጥፍ ዳግም አናገኛቸውምና፡፡

አሁን ርሃቡ በዋነኛነት የተከሰተው ውሃ ቅዳ ውሃ መለስ የሆነው የመንግሥት ስርዓትና በመሪዎች ቸልተኝነት፤ የተፈጥሮ ሃብት፣ የመሬት፣ ስነ ህዝብ፣የምግብ እና የመረጃ ጥንቅር ፖሊሲ ችግር ነው፡፡ ባለፈው ከነበረው ችግር ለነገው አለመማራችን እና ለመማር አለመዘጋጀታችን ውጤትም ነው፡፡ ስለዚህ ርሃብን እና የተራበውን ህዝብ ቁጥር በመደበቅና በማዛበት ርሃብን ማቆም እንደማይቻል ልናውቅ ይገባል፡፡ ስለዚህ በርሃብ የተጎዱ ወገኖቻችንን በተመለከተ የውጭ መንዛሪ እጠረት ለመሸፈን ባለመ የውጭ ለጋሽ ሀገሮችን ተማፅኞ ብቻ ሳይሆን ዜጎች ወገኖቻችንን እንዲረዳዳ ዕድሉ ሊሰጥና በይፋ የምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ ማሰባሰብ ስራ በማድረግ የወገኖቻችንን ህይወት መታደግ ይቻላል፡፡ ለዚህም ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፤ ርሃብ ጊዜ አይሰጥምና፡፡

ከፖሊሲ ችግር አንዱ ከዝናብ ጥገኝነት ለመውጣት የሚያስችል መስኖ አለማስፋፋት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሜትሪዮሎጂ ተቋም ብቃት ባላቸው የአየር ትንበያ ባለሙያዎች አለመዋቀር እና አለመጠናከር፣ መስኖ በሌለባቸውና ዓመታዊ የዝናብ መጠናቸው ዝቅተኛ የሆኑ ቆላማ አካባቢዎች የተለየ ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲሁም በቂ የእንሰሳትና የሰው ህክምና እና የምግብ ቅድመ ዝግጅት ክምችት አለማድረግን መጥቀስ ይቻላል፡፡

ከአስቸኳይ ርስበርስ የመረዳዳት እና ዓለም አቀፍ ድጋፍ ጥየቃ እንቅስቃሴው እንዳለ ሆኖ፤ ለ24 ዓመታት ተሰርቶበት ለውጥ ያላመጣውን ፖሊሲም ማሻሻል አሊያም መቀየር ዋነኛው ቁልፍ ተግባር መሆን አለበት፡፡ አለበሊያ በኢህአዴግ ዘመን ለ4ኛ እና 5ኛ ጊዜ መከሰቱ እንደማይቀር የአሁኑን ጨምሮ ያለፉት ጊዜያት ከበቂ በላይ አስተማሪዎች ናቸውና ከፖለቲካ ጋጋታ ትርፍ ይልቅ ሕይወት የማዳኑ ተግባር ሊፈጥን ይገባዋል፡፡

አዳማ የኤድስ ተጠቂዎች ማደርያን ወደ መቅዲ ባርና ሬስቶራንት ቀየረች?!

የትነበርክ ታደለ
ይህ የምስራች እንዳይመስላችሁ! እጅግ ዘግናኝ አሳፋሪና አሳዛኝ የሀገራችን እውነታ ነው። ከአመታት በፊት ሀገር በኤች አይቪ የደረሰባትን የጭለማ ድባብ አንረሳውም! እርግጥ አሁንም ገና ከሀዘኑ ሙሉ በሙሉ አልተላቀቅንም። በዝያ የጭለማ ዘመን፣ መፍትሄ ከሀገር ውስጥም ከውጭም ሲፈለግ፣ ወጣቱ በየቦታው ሲረግፍ፣ ቤተሰብ ሲበተን አዳማ ውስጥ አንድ ሰው ተገኘ።

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

መስፍን ፈይሳ (የመስፍነ ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት መስራች)

ይህ ሰው መስፍን ፈይሳ ይባላል። መስፍን ራሱም የቫይረሱ ተጠቂ መሆኑን ይፋ አውጥቶ በመናገር የሱ ቢጤ ወገኖቹን ለመርዳት ቆርጦ ተነሳ። እሱ እንደሚናገረው ማዳበርያ ከረጢት አንገቱ ላይ አስሮ በየደጃፉ እየዞረ ምግብ እየለመነ የሰበሰባቸውን ወገኖቹን መመገብ ያዘ።

እየቆየ ጥረቱ ፍሬ አፍርቶ በሀገር አቀፍ ደረጃ እውቅና የተሰጠውና ከ5000 ሰዎች በላይ የተረዱበት “መስፍን ፈይሳ ኢኒሼቲቭ በጎ አድራጎት” ተቋቋመ።

ይህ ተቋም አሁን “መቅዲ ባርና ሬስሮራንት ተብሎ ወጣቶች ቀንና ለሊት የሚጨፍሩበት፣ በሺሻ ጢስ የሚታጠኑበትና ህልማቸውን የሚነጠቁበት ቦታ ሆኗል።

ከሰአታት በፊት ግለሰቡ በፌስ ቡክ ገጹ ላይ በለቀቀው ቪዲዮ እንዳስታወቀው በጉልበት ከሀገር እንድወጣ ካደረጉኝ በኋላ ተቋሙን አፈራርሰው አራት ሚሊየን የሚገመት ንብረት ዘርፈው ጉዳተኞቹን በትነው ህንጻውን ከኤች አይቪ መከላከያነት ወደ ማሳራጫነት አዙረውታል ብሏል።

እጅግ የሚደንቀው ደግሞ ይህ ተቋም (አሁን መቅዲ ባር) የሚገኘው ከአዳማ ዩኒቨርስቲ አጠገብ መሆኑ ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ አለማቀፍ ሚዲያዎች እንደሚዘግቡት ሀገራችን ውስጥ ዝሙት በርካሽ የሚሸጥባቸው ስፍራዎች ዩኒቨርስቲዎች ባሉበት አካባቢ ነው።

በተለይ ደግሞ አዳማ ናዝሬት በዚህ ግምባር ቀደም ተጠቃሿ ናት። አንድ የቅርብ ጊዜ መረጃ እንደሚያሳየው አዳማ 230.000 ነዋሪዎች ያላት ስትሆን ከዚህም ውስጥ ካሉት ሴቶች 5000 ዝሙት አዳሪዎች ናቸው። ይህም ማለት ከመቶ አምስት ፐርሰንቱ በዚሁ ስራ የሚተዳደሩ ናቸው። ልብ በሉ ይህ ቁጥር የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን አይጨምርም።

እንግዲህ ይህንን አይነት ጉድ የተሸከመች ከተማ እንዴት ባለ አስተዳደር እጅ ብትወድቅ ነው የህዝብን ሁለንተናዊ ጤንነት ከመጠበቅ ሀላፊነቱ እየሸሸ በግለሰብ የተቋቋመ ተቋም ለማፈረስ የተደፈረው?

እጅግ በጣም የሚገርመው ደግሞ ይህ ተቋም ሲጀመር የመሰረት ድንጋይ የጣሉት በአሁን ሰአት የክልሉ ፕሬዚዳንት የሆኑት ኦቦ ሙክታር ከድር መሆናቸው ነው። (አቡነ ጳውሎስም በቦታው ነበሩ)

Mesfin Feyisa Initiative adama-nazereth

እና ምነው? ኦቦ ሙክታር አዳማ ውስጥ ምን እየተካሄደ ማወቅ አይችሉም ማለት ነው? ለአንድ ትልቅ አላማ ራሳቸው በቦታው ድረስ ሄደው መሰረት የጣሉለት ተቋም እጅግ በሚያሳፍርና በሚያዋርድ ሁኔታ ተሽቆልቁሎ ሲጠፋ ምንም አልሰሙም ማለት ነው? አዳማ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ነች! ይህንን ሳይስሙና ሳያዩ ወለጋ ጫፍ ወይም አርሲ ቦረና ስላለው እንዴት ሊሰሙ ይችላሉ? ነው ወይስ በዚህ ጉዳይ ላይ የሳቸው ይሁንታ አለበት? እውነት ለመናገር መልስ ሊሰጡበት የሚገባ ጥያቄ ነው።

የአዳማ ህዝብስ ቢሆን በራሱ ጉዳይ ላይ ከሱ የተሻለ ማን ሊጠይቅለት ይችላል? ግለሰቡ እንደተናገሩት ወደዚህ ባርና ሬስቶራንት ልጆቻችሁ እየሄዱ እያያችሁ ዝም ብትሉ በልጆቻችሁ ህይወት ላይ ፈርዳችኋል።

መንግስትም ቢሆን እነ መቄዶኒያን የመሳሰሉ ወገንን ከጎዳና የሚሰበስቡ ተቋማት ነገ በተመሳሳይ መንገድ እንደማይፈርሱና ወደ ሺሻ ቤትነት እንደማይቀየሩ ምን ማስተማመኛ ይሰጠናል? ትውልድ እየጠፋ ነው! ህግ እየተጣሰ ነው! የምንፈልገውን እያጣን የማንፈልገው እየተጫነብን በዚህ ላይ ለጩሀታችን ዝምታ እየተመለሰልን ነው! ነገ አጣብቂኙ ለሀገር ነውና መቅዲ ባር በአስቸኳይ ወገኖቻችን ወደ ሚረዱበት ተቋምነት ይመለስልን! ወገን በጭፈራ ቤት አይታከምም!

እነ ዘመነ ምህረት የእምነት ክህደት ቃላቸው ሰጡ

• “ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ አሸባሪ አይደለሁም”
• “ፍትህ ቢኖር ኖሮ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ እዚህ መቆም የነበረባቸው” አቶ ጌትነት ደርሶ
• “የተከሰስኩት ድርቡሽ እንኳ ያልደፈረውን የጎንደር ጥምቀት ላይ ፈንጅ ልታፈነዳ ነበር ተብዬ ነው፡፡ ምርመራ ላይ ግን ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ ይሉኛል” አቶ ዘመነ ምህረት

Zemene Kassie

ዘመነ ምህረት የክስ መዝገብ በሽብርተኝነት የተከሰሱት የቀድሞው መኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረትና ሌላኛው የመኢአድ አባል የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ ዛሬ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ለዛሬ ቀጠሮ የሰጠው አቶ ዘመነ ምህረት ማረሚያ ቤቱ ውስጥ በደል እየደረሰበት መሆኑን ባመለከተው መሰረት ማረሚያ ቤቱ ጉዳዩን አጣርቶ እንዲያቀርብ፣ እንዲሁም በዚሁ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ የነበረው የመኢአድ አባል መለሰ መንገሻ ክስ የተለየ ይዘት ስላለው ክሱ ተለጥሎ እንዲታይና የቀሪዎቹን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ነው፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የእምነት ክህደት ቃል እንዲሁ እየሰማሁ እመዘግባለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹በድምፅ እንዲቀዳልኝ እፈልጋለሁ›› በማለቱ የሁለቱም ተከሳሾች የእምነት ክህደት ቃል በድምፅ እንዲቀረፅ ተደርጓል፡፡1ኛ ተከሳሽ አቶ ዘመነ ምህረት የጎንደር ጥምቅት ላይ ፈንጅ ሊያፈነዳ እንደነበር መከሰሱን ሲገልፅ ‹‹ሰው አይደለም እንሰሳት እንኳን የማይደፍሩትን፣ ድርቡሽ እንኳን ያልደፈረውን ጥምቀት እኔ በክስትና ሀይማኖትና ባህል ተኮትኩቼ ያደኩትን ሰው ፈንጅ ልታፈነዳበት ነበር መባሌ ያሳዝናል›› ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ግን በምርመራ ወቅት ‹‹ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ? ለምን የኢህአዴግ አባል አልሆንክም?›› እንደተባለ የገለፀው አቶ ዘመነ ይህም ‹‹ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ዥግራ ነሽ ይሏታል ነው›› ሲል እሱን ለማሰር የተቀነባበረ ሴራ መሆኑን ገልፆል፡፡ አቶ ዘመነ ምህረት አክሎም የታሰረው ኤርትራ እንዳትገነጠል ሲታገሉ የኖሩትን፣ እንዲሁም የሰላማዊ ትግሉ ፈር ቀዳጅ የሆኑት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ያስጀመሩትን ትግልን የመኢአድ አመራር ሆኖ እያስቀጠለ በመሆኑ እንደሆነ ገልፆል፡፡ በመሆኑም ወንጀሉን እንዳልፈፀመው የገለፀ ሲሆን ‹‹ከተጠቀሰው መካከል ግን የማምነው አለኝ፡፡ ኢህአዴግን ዛሬም ነገም እታገለዋለሁ›› ብሏል፡፡
2ኛ ተከሳሽ የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ በበኩሉ ‹‹ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ እኔ አሸባሪ አይደለሁም›› ብሏል፡፡ አቶ ጌትነት አክሎም ‹‹ፍትህ ቢኖር ኖሮ እዚህ መቆም የነበረኝ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ ነበሩ፡፡ እዚህ መቆም የነበረበት መሳሪያን ተገን አድሮጎ ለ3 ወር ጨለማ ቤት ዘግቶ ጭካኔ የፈፀመብኝ ወያኔ ነበር›› ሲል ወንጀሉን እንዳልፈፀመው ክዶ ተከራክሯል፡፡
ምንም እንኳ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ቀጠሮ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዘመነ ምህረት ተፈፀመብኝ ያለውን በደል አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ‹‹የደረሰኝ መረጃ የለም›› ብለዋል፡፡ ዛሬም በድጋሜ አቤቱታውን ያቀረበው አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹እኛ እየራበን ነው፡፡ ምግቡን እንሰሳት እንኳን ሊበሉት አይችሉም፡፡ ቤተሰቦቼ እንዳይጠይቁኝ ተደርጓል፡፡›› በማለት ከተያዙበት ጥር 10 ቀን 2007 ጀምሮ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈፀመባቸው መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ የዘር መድሎ እየደረሰባቸው እንደሆነ እና ሽንት ቤት ጥግ እንዲተኙ መደረጋቸውንም ለፍርድ ቤቱ አመልክቷል፡፡ ዛሬ ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ በማቅረቡም ከማረሚያ ቤቱ ስቃይ ሊገጥመው እንደሚችል ስጋቱን የገለፀው አቶ ዘመነ ጉዳያቸው በተዘዋዋሪ ችሎት እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የ3ኛ ተከሳሽ ክስ ከእነ ዘመነ ምህረት ክስ ተነጥሎ በሌላ ችሎት እንዲታይ ብይን የሰጠ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በማረሚያ ቤቱ ላይ ያሰማቸው አቤቱታዎችን ማረሚያ ቤቱ አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የሰው ምስክር ለማቅረብም ለህዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ምስጋና አቀረቡ

በድንገት ከያለንበት ተይዘን እንደታሰርነው አፈታታችንም ግራ የሚያጋባ ነበር፡፡ ተመሳሳይ ክሶች ቀርበውብን እያለ ግማሾቻችን ‹ክስ ተቋርጦላችኋል› ተብለን ተፈታን፣ ግማሾቻችን ደግሞ ‹ነፃ ናችሁ› (ከሳሽ በነፃነታችን ላይ ይግባኝ መጠየቁ እንዳለ ሁኖ) ተብለን ይሄው ወጥተናል፡፡ ቀሪ ክስ ይዘን በዋስ ወጥተን እየተከራከርንም ያለን አለን፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የሁላችንም ዕምነት ግን አንድም ቀን ሊያሳስረን የሚገባ ወንጀል አለመፈፃችን ማመናችን ነው፡፡ መፈታታችን ጥሩ ሁኖ፤ መታሰር በፍፁም የማይገባን ነበርን፡፡ መፃፋችን እና ሕግ እንዲከበር መጠየቃችን ሀገሪቱ አገራችን እንድትሻሻል እና ሁላችንም ዜጎች የተሻለ ህይወት አንዲኖራቸው ከመሻት ባለፈ ሌላ ነገር አልነበረውም/የለውም፡፡ ነገር ግን ይህን በማድረጋችን ተገርፈናል፣ ተዘልፈን-ተሰድበናል፣ ታስረናል ተሰደናልም፡፡ ይህ በፍጹም አይገባንም ነበር፡፡

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

የእኛ መታሰር ፖለቲካዊ ንቃት የፈጠረላቸው ሰዎች እንዳሉ ሲነግሩን ደስ ይለናል፡፡ በእኛ መታሰር ምክንያት ለመጠየቅና ለመፃፍ በጣም እንደሚፈሩ የሚነግሩን ሰዎች ስናገኝ ደግሞ እናዝናለን፡፡ የመታሰራችን ጉራማይሌ ስሜት እንደዚህ ነው፡፡ ሳይገባን በመታሰራችን የነቁ መኖራቸውን በማወቃችን የምነደሰተውን ያክል፤ ሳይገባን በመታሰራችን የተሰበሩና ከተዋስኦ መድረኩ የራቁ እንዳሉ ስናውቅ እጅግ እናዝናለን፡፡
መታሰር በደል ነው፡፡ ብዙ ነገር ያጎድላል፡፡ መታሰር መልካም ነው፡፡ ብዙ ነገር ያስተምራል፡፡ እኛ በመታሰራችን ሀገራችን የበለጠ እንድናውቃት ሁነናል፡፡ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ነፃነት አሁንም ብዙ ዋጋ እንደሚያስከፍል ተረድተናል፡፡ ሕግን መከታ አድርገው የኖሩ ‹ስም የለሽ› ዜጎች ሕጉ ሲከዳቸውና እነሱ ላይ ‹በላ› ሲያመጣባቸው ታዝበናል፡፡ ከሁሉም በላይ ፍትህ የሌለባት ሀገር ለዜጎቿ የማትመችና አገር እንደሆነች አይተናል፡፡
በእስራችን ወቅት የተለያዩ በደሎች በተቋም ደረጃ ደርሰውብናል፡፡ ግን አገር ነውና ከይቅርታ የሚያልፍ አይደለም፡፡ ለበደላችሁን አካላት እናንተ ይቅርታ ባትጠይቁንም፤ እናንተ የፈለጋችሁትን ባለማድረጋችንና ሕግን መሰረት አድርገን በመኖራችን ስላስከፋናችሁ እባካችሁ ይቅር በሉን፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል ግን እናንተ አላችሁ፡፡ ጓደኞቻችንም ናችሁ፤ ዘመቻ አድራጊዎችም ናችሁ፤ ቤተሰቦቻችንም ናችሁ፤ ጠያቂዎቻችንም ናችሁ፤ ጠበቆቻችንም ናችሁ፣ የመንፈስ አጋሮቻችንም ናችሁ ርቀት ሳይገድባች የጮሃችሁልን አለም አቀፍ የመብት ጠያቂዎችም ናችሁ … በመታሰራችን የተረዳነው አንዱ ትልቅ ነገር የናንተን መልካምነት፣ የናንተን አጋርነት እና የናንተን የማይሰለች ድካምና ፍቅር ነው፡፡ እናንተ ባትኖሩ ‹አጭሩ› የእስር ጊዜያችን ይረዝምብን ነበር፤ ‹ቀላሏ› እስር ትከብድብን ነበር፡፡ ምስጋና ለናንተ፤ እስራችን ‹አጭር› – ፈተናችን ‹ቀላል› እንዲሆን አድርጋችሁልናልና፡፡
እናንተ ወዳጆቻችን ለሁሉም ነገር – እልፍ ምስጋና፡፡
እናመሰግናለን!
የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች

የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንደሌሉ ገለፀ

• “የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል” 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ

• “የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው” 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ

አንዳርጋቸው ፅጌ

አንዳርጋቸው ፅጌ

በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንደሌሉ ማረሚያ ቤቱ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ ገልፆአል፡፡ 19ኛ ወንጀል ችሎት ሀምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም ለምስክርነት እንዲያቀርብ ለዛሬ ለጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡

ተከሳሾቹ ማረሚያ ቤቱ ሲያጉላላቸው ቆይቶ አሁን የለም ማለቱ ትክክል እንዳልሆነ የገለፁ ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ ማረሚያ ቤቱ ምላሽ የሰጠው በአራተኛው ትዕዛዝ መሆኑን ጠቅሶ የፍርድ ሂደታቸውን ከሚገባው በላይ እያጓተተ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ ገልፆአል፡፡ ‹‹መከላከል ከጀመርን አንድ አመት ከስድስት ወር ሆነ፡፡ በግዞት ነው ያለነው፡፡ የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው›› ያለው አቶ አሸናፊ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ‹‹ፌዝ ነው›› ብሎታል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ በበኩሉ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ሲጠቅሱ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኛ እንደሆኑ በመጠቆም ተቃውሞ አሰምቶ እንደነበር፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ ቃሊቲ እንደሚታሰር ገልፆ ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው እንደሌሉ መግለፁ ‹‹የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል›› ብሏል፡፡ ‹‹የእድሜ ልክ ወይንም የሞት ፍርደኛ የት ነው የሚታሰረው?›› ሲልም ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
3ቱ ተከሳሾች የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸውን እንደያዙ በቴሊቪዥን መግለፃቸውን አስታውሰው አሁንም ለሁለቱ አካላት ደብዳቤ እንደሚፅፉ ለፍርድ ቤቱ አሳውቀው የነበር ቢሆንም ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ሆኖም ግን 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱም 4ኛ ተከሳሽ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲቀርቡለት የሚያቀርበውን አቤቱታ ተመልክቶ ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡