Tag Archives: Ethiopian Justice

በእስር ላይ የሚገኙት መምህር ግርማ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄም ወድቅ ተደረገ

ጥላሁን ካሳ
ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት መምህር ግርማ ወንድሙ ዛሬ ጥቅምት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፖሊስ መርማሪ ቡድን ዛሬ ግለሰቡን በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት አቅርቧቸዋል።

መምህር ግርማ ወንድሙ

መምህር ግርማ ወንድሙ

ፖሊስ ግለሰቡ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ቀሪ የምርመራ ስራ ስላሉብኝ ተጨማሪ 14 ቀን ይፈቀድልኝ ብሏል።
ተጠርጣሪው በራሳቸውና በጠበቃቸው በኩል ፖሊስ የጠየቀውን ተጨማሪ ጊዜ በመቃወም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል።
የፖሊስ የምርመራ ቡድን በበኩሉ እሳቸው ቢለቀቁ ሌሎች ተፈላጊዎችን እና የተለያዩ ሰነዶችን ስለሚያሸሹብን ጥያቄያቸው ውድቅ ይሁን ብሏል።
ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ አብዛኛውን የምርመራ ስራ ያካሄደ በመሆኑ ለቀሪ የምርመራ ስራዎቹ ይረዳል በማለት ከጠየቀው የ14 ቀን ጊዜ ውስጥ 7 ቀን ብቻ ፈቅዷል።
ውጤቱን ለመጠባበቅም ለጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
የወንጀሉ ዝርዝር
ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ.ም ነው ብሏል።
በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው።
እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።
እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል።
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ800 ሺህ ብር ይሸጡታል።
ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው የሚለው የምርመራ መዝገቡ።
ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው።
ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።
የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው።
ተጠርጣሪው እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።
ጠበቃቸውም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል አይደለም፤ ፖሊስም የሚጠበቁ ምርመራዎቹን አጠናቋል፤ ደንበኛዬ የዋስትና መብታቸው ይከበርልኝ በማለት ጠይውቋል።
ይሁን እንጂ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጓል።
ምንጭ፡- ሬዲዮ ፋና (ኤፍቢሲ)

እነ ዘመነ ምህረት የእምነት ክህደት ቃላቸው ሰጡ

• “ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ አሸባሪ አይደለሁም”
• “ፍትህ ቢኖር ኖሮ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ እዚህ መቆም የነበረባቸው” አቶ ጌትነት ደርሶ
• “የተከሰስኩት ድርቡሽ እንኳ ያልደፈረውን የጎንደር ጥምቀት ላይ ፈንጅ ልታፈነዳ ነበር ተብዬ ነው፡፡ ምርመራ ላይ ግን ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ ይሉኛል” አቶ ዘመነ ምህረት

Zemene Kassie

ዘመነ ምህረት የክስ መዝገብ በሽብርተኝነት የተከሰሱት የቀድሞው መኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረትና ሌላኛው የመኢአድ አባል የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ ዛሬ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ለዛሬ ቀጠሮ የሰጠው አቶ ዘመነ ምህረት ማረሚያ ቤቱ ውስጥ በደል እየደረሰበት መሆኑን ባመለከተው መሰረት ማረሚያ ቤቱ ጉዳዩን አጣርቶ እንዲያቀርብ፣ እንዲሁም በዚሁ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ የነበረው የመኢአድ አባል መለሰ መንገሻ ክስ የተለየ ይዘት ስላለው ክሱ ተለጥሎ እንዲታይና የቀሪዎቹን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ነው፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የእምነት ክህደት ቃል እንዲሁ እየሰማሁ እመዘግባለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹በድምፅ እንዲቀዳልኝ እፈልጋለሁ›› በማለቱ የሁለቱም ተከሳሾች የእምነት ክህደት ቃል በድምፅ እንዲቀረፅ ተደርጓል፡፡1ኛ ተከሳሽ አቶ ዘመነ ምህረት የጎንደር ጥምቅት ላይ ፈንጅ ሊያፈነዳ እንደነበር መከሰሱን ሲገልፅ ‹‹ሰው አይደለም እንሰሳት እንኳን የማይደፍሩትን፣ ድርቡሽ እንኳን ያልደፈረውን ጥምቀት እኔ በክስትና ሀይማኖትና ባህል ተኮትኩቼ ያደኩትን ሰው ፈንጅ ልታፈነዳበት ነበር መባሌ ያሳዝናል›› ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ግን በምርመራ ወቅት ‹‹ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ? ለምን የኢህአዴግ አባል አልሆንክም?›› እንደተባለ የገለፀው አቶ ዘመነ ይህም ‹‹ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ዥግራ ነሽ ይሏታል ነው›› ሲል እሱን ለማሰር የተቀነባበረ ሴራ መሆኑን ገልፆል፡፡ አቶ ዘመነ ምህረት አክሎም የታሰረው ኤርትራ እንዳትገነጠል ሲታገሉ የኖሩትን፣ እንዲሁም የሰላማዊ ትግሉ ፈር ቀዳጅ የሆኑት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ያስጀመሩትን ትግልን የመኢአድ አመራር ሆኖ እያስቀጠለ በመሆኑ እንደሆነ ገልፆል፡፡ በመሆኑም ወንጀሉን እንዳልፈፀመው የገለፀ ሲሆን ‹‹ከተጠቀሰው መካከል ግን የማምነው አለኝ፡፡ ኢህአዴግን ዛሬም ነገም እታገለዋለሁ›› ብሏል፡፡
2ኛ ተከሳሽ የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ በበኩሉ ‹‹ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ እኔ አሸባሪ አይደለሁም›› ብሏል፡፡ አቶ ጌትነት አክሎም ‹‹ፍትህ ቢኖር ኖሮ እዚህ መቆም የነበረኝ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ ነበሩ፡፡ እዚህ መቆም የነበረበት መሳሪያን ተገን አድሮጎ ለ3 ወር ጨለማ ቤት ዘግቶ ጭካኔ የፈፀመብኝ ወያኔ ነበር›› ሲል ወንጀሉን እንዳልፈፀመው ክዶ ተከራክሯል፡፡
ምንም እንኳ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ቀጠሮ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዘመነ ምህረት ተፈፀመብኝ ያለውን በደል አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ‹‹የደረሰኝ መረጃ የለም›› ብለዋል፡፡ ዛሬም በድጋሜ አቤቱታውን ያቀረበው አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹እኛ እየራበን ነው፡፡ ምግቡን እንሰሳት እንኳን ሊበሉት አይችሉም፡፡ ቤተሰቦቼ እንዳይጠይቁኝ ተደርጓል፡፡›› በማለት ከተያዙበት ጥር 10 ቀን 2007 ጀምሮ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈፀመባቸው መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ የዘር መድሎ እየደረሰባቸው እንደሆነ እና ሽንት ቤት ጥግ እንዲተኙ መደረጋቸውንም ለፍርድ ቤቱ አመልክቷል፡፡ ዛሬ ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ በማቅረቡም ከማረሚያ ቤቱ ስቃይ ሊገጥመው እንደሚችል ስጋቱን የገለፀው አቶ ዘመነ ጉዳያቸው በተዘዋዋሪ ችሎት እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የ3ኛ ተከሳሽ ክስ ከእነ ዘመነ ምህረት ክስ ተነጥሎ በሌላ ችሎት እንዲታይ ብይን የሰጠ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በማረሚያ ቤቱ ላይ ያሰማቸው አቤቱታዎችን ማረሚያ ቤቱ አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የሰው ምስክር ለማቅረብም ለህዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች ምስጋና አቀረቡ

በድንገት ከያለንበት ተይዘን እንደታሰርነው አፈታታችንም ግራ የሚያጋባ ነበር፡፡ ተመሳሳይ ክሶች ቀርበውብን እያለ ግማሾቻችን ‹ክስ ተቋርጦላችኋል› ተብለን ተፈታን፣ ግማሾቻችን ደግሞ ‹ነፃ ናችሁ› (ከሳሽ በነፃነታችን ላይ ይግባኝ መጠየቁ እንዳለ ሁኖ) ተብለን ይሄው ወጥተናል፡፡ ቀሪ ክስ ይዘን በዋስ ወጥተን እየተከራከርንም ያለን አለን፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የሁላችንም ዕምነት ግን አንድም ቀን ሊያሳስረን የሚገባ ወንጀል አለመፈፃችን ማመናችን ነው፡፡ መፈታታችን ጥሩ ሁኖ፤ መታሰር በፍፁም የማይገባን ነበርን፡፡ መፃፋችን እና ሕግ እንዲከበር መጠየቃችን ሀገሪቱ አገራችን እንድትሻሻል እና ሁላችንም ዜጎች የተሻለ ህይወት አንዲኖራቸው ከመሻት ባለፈ ሌላ ነገር አልነበረውም/የለውም፡፡ ነገር ግን ይህን በማድረጋችን ተገርፈናል፣ ተዘልፈን-ተሰድበናል፣ ታስረናል ተሰደናልም፡፡ ይህ በፍጹም አይገባንም ነበር፡፡

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

ከእስር የተለቀቁት የዞን 9 ብሎገሮች እና ጋዜጠኞች

የእኛ መታሰር ፖለቲካዊ ንቃት የፈጠረላቸው ሰዎች እንዳሉ ሲነግሩን ደስ ይለናል፡፡ በእኛ መታሰር ምክንያት ለመጠየቅና ለመፃፍ በጣም እንደሚፈሩ የሚነግሩን ሰዎች ስናገኝ ደግሞ እናዝናለን፡፡ የመታሰራችን ጉራማይሌ ስሜት እንደዚህ ነው፡፡ ሳይገባን በመታሰራችን የነቁ መኖራቸውን በማወቃችን የምነደሰተውን ያክል፤ ሳይገባን በመታሰራችን የተሰበሩና ከተዋስኦ መድረኩ የራቁ እንዳሉ ስናውቅ እጅግ እናዝናለን፡፡
መታሰር በደል ነው፡፡ ብዙ ነገር ያጎድላል፡፡ መታሰር መልካም ነው፡፡ ብዙ ነገር ያስተምራል፡፡ እኛ በመታሰራችን ሀገራችን የበለጠ እንድናውቃት ሁነናል፡፡ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ነፃነት አሁንም ብዙ ዋጋ እንደሚያስከፍል ተረድተናል፡፡ ሕግን መከታ አድርገው የኖሩ ‹ስም የለሽ› ዜጎች ሕጉ ሲከዳቸውና እነሱ ላይ ‹በላ› ሲያመጣባቸው ታዝበናል፡፡ ከሁሉም በላይ ፍትህ የሌለባት ሀገር ለዜጎቿ የማትመችና አገር እንደሆነች አይተናል፡፡
በእስራችን ወቅት የተለያዩ በደሎች በተቋም ደረጃ ደርሰውብናል፡፡ ግን አገር ነውና ከይቅርታ የሚያልፍ አይደለም፡፡ ለበደላችሁን አካላት እናንተ ይቅርታ ባትጠይቁንም፤ እናንተ የፈለጋችሁትን ባለማድረጋችንና ሕግን መሰረት አድርገን በመኖራችን ስላስከፋናችሁ እባካችሁ ይቅር በሉን፡፡
በዚህ ሁሉ መሃል ግን እናንተ አላችሁ፡፡ ጓደኞቻችንም ናችሁ፤ ዘመቻ አድራጊዎችም ናችሁ፤ ቤተሰቦቻችንም ናችሁ፤ ጠያቂዎቻችንም ናችሁ፤ ጠበቆቻችንም ናችሁ፣ የመንፈስ አጋሮቻችንም ናችሁ ርቀት ሳይገድባች የጮሃችሁልን አለም አቀፍ የመብት ጠያቂዎችም ናችሁ … በመታሰራችን የተረዳነው አንዱ ትልቅ ነገር የናንተን መልካምነት፣ የናንተን አጋርነት እና የናንተን የማይሰለች ድካምና ፍቅር ነው፡፡ እናንተ ባትኖሩ ‹አጭሩ› የእስር ጊዜያችን ይረዝምብን ነበር፤ ‹ቀላሏ› እስር ትከብድብን ነበር፡፡ ምስጋና ለናንተ፤ እስራችን ‹አጭር› – ፈተናችን ‹ቀላል› እንዲሆን አድርጋችሁልናልና፡፡
እናንተ ወዳጆቻችን ለሁሉም ነገር – እልፍ ምስጋና፡፡
እናመሰግናለን!
የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች

የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንደሌሉ ገለፀ

• “የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል” 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ

• “የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው” 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ

አንዳርጋቸው ፅጌ

አንዳርጋቸው ፅጌ

በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንደሌሉ ማረሚያ ቤቱ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ ገልፆአል፡፡ 19ኛ ወንጀል ችሎት ሀምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም ለምስክርነት እንዲያቀርብ ለዛሬ ለጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡

ተከሳሾቹ ማረሚያ ቤቱ ሲያጉላላቸው ቆይቶ አሁን የለም ማለቱ ትክክል እንዳልሆነ የገለፁ ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ ማረሚያ ቤቱ ምላሽ የሰጠው በአራተኛው ትዕዛዝ መሆኑን ጠቅሶ የፍርድ ሂደታቸውን ከሚገባው በላይ እያጓተተ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ ገልፆአል፡፡ ‹‹መከላከል ከጀመርን አንድ አመት ከስድስት ወር ሆነ፡፡ በግዞት ነው ያለነው፡፡ የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው›› ያለው አቶ አሸናፊ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ‹‹ፌዝ ነው›› ብሎታል፡፡

3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ በበኩሉ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ሲጠቅሱ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኛ እንደሆኑ በመጠቆም ተቃውሞ አሰምቶ እንደነበር፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ ቃሊቲ እንደሚታሰር ገልፆ ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው እንደሌሉ መግለፁ ‹‹የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል›› ብሏል፡፡ ‹‹የእድሜ ልክ ወይንም የሞት ፍርደኛ የት ነው የሚታሰረው?›› ሲልም ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
3ቱ ተከሳሾች የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸውን እንደያዙ በቴሊቪዥን መግለፃቸውን አስታውሰው አሁንም ለሁለቱ አካላት ደብዳቤ እንደሚፅፉ ለፍርድ ቤቱ አሳውቀው የነበር ቢሆንም ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ሆኖም ግን 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱም 4ኛ ተከሳሽ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲቀርቡለት የሚያቀርበውን አቤቱታ ተመልክቶ ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ተላለፈበት

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲሁም በመፅሔት አሳታሚ ድርጅቱ ላይ የ200 ሺህ ብር ቅጣት ተወስኖበታል። ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ ከዓመት በፊት የሶስት ዓመት ከ3 ወር እስራት እንደተፈረደበት ይታወሳል።

ግዛው ታዬ

ግዛው ታዬ

ከ800 ሺህ ብር በላይ ታክስ በማጭበርበርና በሌሎች 14 ክሶች ጥፋተኛ የተባለው የሎሚ መጽሄት ዋና ስራ አስኪያጅ በ18 ዓመት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነ።
ውሳኔውን የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት ነው ያስተላለፈው።
ተከሳሾቹ ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ታዬ ግዛው ናቸው።
የፌደራል ገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፥ ድርጅቱም ሆነ ስራ አስኪያጁ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ክሱ እስከተመሰረተበት ድረስ ለተከታታይ 5 ዓመታት ኦዲት አልተደረጉም።
በዚህ ሂደትም ድርጅቱም ሆነ ግለሰቡ የታክስ ማጭበርበሮችን ሲያከናውን ቆይቷል ሲል የአቃቤ ህግ ክስ ያስረዳል።
የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የገቢ ግብር መሰወር የሚለውም በወንጀል ድርጊቱ ማስረጃዎች ጉዳይ ሲሆን፥ እንደ አቃቤ ህግ ገለጻ በዚህ ሂደት ውስጥ ድርጅቱ እና ስራ አስኪያጁ ለመንግስት መግባት የነበረበትን ከ800 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል ይላል።
በዚህ የክስ መዝገብም ግለሰቡ በችሎቱ አልቀረበም።
ይህን ተከትሎም የክስ ሂደቱ በሌሉበት እንዲቀጥል በተሰጠው በይን መሰረት አቃቤ ህግ የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
ጉዳዩን ሲመለክት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት በተከሳሾች ላይ የቀረበው ማስረጃ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ነው ሲል ቅጣቱን አስተላልፏል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንተኛ የወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ችሎት ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት በ200 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛውታዬ ላይ ደግሞ የ18 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ100 ሺህ የገንዘብ ቅጣት አስተላልፏል።
የድርጅቱ ሎሚ መፅሔት (ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንት) ባለቤትና ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ አቶ ግዛው ታዬ ከዚህ በፊት “አመጽ በማስነሳት እና መሰል የሽብርተኝነት ወንጀሎች” ክስ ተመስርቶበት በ50 ሺህ ብር ዋስ ከተለቀቀ በኋላ መሰደዱ ይታወቃል፡፡ የአሁኑ ክስና ፍርድም ተከሳሹ በሌለበት ተወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በተመለከተ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንን/ሬዲዮ ፋናን/ ዋቢ በማድረግ ቃልኪዳን ትዩብ ዘግቧል፡፡