በውዝግብ የተጠናቀቀው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የችሎት ውሎ
በጌታቸው ሺፈራው
~ተከሳሾቹ ጆሯቸውን በእጃቸው ደፍነው፣ ጀርባቸውን ለዳኞ ሰጥተው ችሎቱን “አንሰማም! አናይም!” ብለዋል
~ የዐቃቤ ሕግ ምስክር ነኝ ብሎ የቀረበውን ግለሰብ ዐቃቤ ሕጉ ክዶታል።ዐቃቤ ሕጉ በሀሰት እንድመሰክር ተገድጃለሁ ያለውን ግለሰብ የእኔ ሳይሆን የጠበቃ ምስክር ነው ብሎታል።
~ጨለማ ቤት የታሰሩት መነኩሴ በቀጠሯቸው አልቀረቡም
~ እነ ተሻገር ወ/ሚካኤል ለሁለተኛ ጊዜ በዳኛው ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል። ብይኑ በማረሚያ ቤት ይደርሳቸዋል ተብሏል። ታዳሚ ወደ ችሎት እንዳይገባ ተከልክሏል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ውሎ በውዝግብ ተጠናቅቋል። በጠዋቱ የፍርድ ቤቱ የስራ ሰዓት ተከሳሾች ችሎቱን አንሰማም፣ አናይም ብለው ተቃውሞ አሰምተዋል። ከሰዓት በነበረው የችሎቱ ሰዓት የቀረቡት እነ ተሻገር ወልደሚካኤል ባሰሙት ተቃውሞ ችሎቱ ብይን ማንበብ ባለመቻሉ ብይኑን ባሉበት ለማድረስ ተገዷል። ፍርድ ቤቱ ለእነ ተሻገር በችሎት ቀጠሮ እንዳልሰጠ ታውቋል።
ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት እነ ጎይቶም ርስቃይ ጆሯቸውን በእጃቸው በመድፈን እና ፊታቸውን በማዞር ችሎቱን አንሰማም አናይም ብለው ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።
እነ ጎይቶም ዛሬ ታህሳስ 11/2010 ዓም ቀጠሮ የተያዘላቸው በክሱ ላይ ያቀረቡትን መቃወሚያ ብይን ለመስማት ሲሆን ተከሳሾቹ ብይኑ ከመነበቡ በፊት ዳኛ ዘርዓይ ወ/ሰንበት ከችሎት እንዲነሱ አቤቱታ አቅርበው፣ ብይኑ ዳኛው ከተነሱ በኋላ እንዲሰራ ጠይቀዋል።
ይሁንና ፍርድ ቤቱ ብይኑን ማንበብ በመቀጠሉ ተከሳሾቹ ጆሯቸውን በእጃቸው በመድፈን አንሰማም ብለዋል። በተጨማሪም ፊታቸውን በማዞር ጀርባቸውን ለችሎቱ ሰጥተው ብይኑ ተነቧል። ብይኑን ያነበቡት ተከሳሾቹ ከችሎት እንዲነሱ አቤቱታ እናቀርብባቸዋለን ያሏቸው ዳኛ ዘርዓይ ወ/ሰንበት ናቸው።
~ከሰዓት በነበረው የፍርድ ቤቱ የስራ ሰዓት ፍርድ ቤት የቀረቡት በእነ ተሻገር ወ/ሚካኤል የክስ መዝገብ ስር የተከሰሱ 35 እስረኞች ለ2ኛ ጊዜ በዳኛ ዘርዓይ ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል። ተከሳሾቹ ባለፈው ቀጠሮ ዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት ሊዳኙን አይገባም የሚል ተቃውሞ በማሰማታቸው ችሎት ደፍራችኋል በሚል እንደተፈረደባቸው በመግለፅ በክሱ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ብይን ከመነበቡ በፊት ዳኛው ሊነሱ እንደሚገባ መግለፃቸው ታውቋል።
ይሁንና ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹ የዳኛ ይነሳልን አቤቱታ በፅሁፍ ያልደረሰው መሆኑን ገልፆ ብይኑን ለማንበብ በመሞከሩ ተቃውሞ ገጥሞታል። የተከሳሾቹ መዝገብ የያዙትና ብይኑንም ለማንበብ የሞከሩት ከችሎት እንዲነሱ ተቃውሞ የቀረበባቸው ዳኛ ዘርዓይ መሆናቸው ተገልፆአል። ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን ስም ሲጠራ ተከሳሾቹ “አቤት” ባለማለታቸው እንዳልቀረቡ (እንደሌሉ) ተደርጎ ተመዝግቧል።
1ኛ ተከሳሽ ተሻገር ወ/ሚካኤል ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኘን አይገባም ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። አቶ ተሻገር ” እኔ ወልቃይቴ ነኝ። አማራ ነኝ። እኛን በፌስቡክ ሲዘልፍ የነበረ፣ ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ ነው እያለ ሊዳኘን አይገባም። እኛ ትናንትም፣ ዛሬም ነገም አማራ ነን። ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኘን አይገባም። ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኝ ከፈለገ ከፖለቲካው ገለልተኛ ሆኖ ሌላ ቦታ ሄዶ ይዳኝ” የሚል ይዘት ያለው አስተያየት ሰጥተዋል።
በሌላ በኩል ቂሊንጦ እስር ቤት ያለው ጨለማ ቤት ውስጥ የሚገኙት አባ ገብረስላሴ ወልደሐይማኖት በዛሬው ቀጠሮ አልቀረቡም። ወደ ችሎቱ መግባት የተከለከለ ሲሆን ፖሊሶችን እንድንገባ ስንጠይቅ ዳኞቹ ታዳሚ እንዳያስገቡ ትዕዛዝ እንደሰጧቸው ገልፀውልናል። ቀድመው ወደ ችሎት ገብተው የነበሩ የተከሳሾች ቤተሰቦች ከችሎት እንዲወጡ ተደርጓል። እነ ተሻገር ሲናገሩ ችሎቱ በር አካባቢ ሆነን ስናዳምጥ ፖሊሶች ከችሎት እንድንርቅ አድርገዋል። ከችሎት እንድንርቅ ያደረጉት በዳኞች ትዕዛዝ እንደሆነም ገልፀውልናል።
~ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዐቃቤ ሕግ ራሱ የቆጠረውን ምስክር የእኔ አይደለም ብሏል። በእነ ክንዱ መሃመድ የክስ መዝገብ ላይ በዐቃቤ ሕግ 1ኛ ምስክር ሆኖ የተቆጠረውን አቶ ሸዋንግዛው የሽጥላ ዐቃቤ ሕግ “የእኔ ምስክር አይደለም” ሲል ክዷል። ምስክሩ በጠዋቱ የችሎት ሰዓት በችሎት ቀርቦ በተከሳሾች ላይ በሀሰት እንዲመሰክር መገደዱን ገልፆአል። በወቅቱ ዐቃቤ ሕጉ አቶ ሓፍታሙ ቸኮለ ምስክሩን እንደማያውቀው ገልፆ የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ 1ኛ የዐቃቤ ምስክር መሆኑን በማረጋገጡ ዐቃቤ ሕጉም እንደገና 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን አምኖ ነበር።
አቶ ሸዋንግዛው የሽጥላ ከሰዓት ምስክርነቱን እንዲሰጥ ቀጠሮ በተያዘው መሰረት ከሰዓት ሲቀርብ፣ ዐቃቤ ሕጉ “የተከሳሾች ጠበቃ ምስክር እንጅ የእኔ ምስክር አይደለም” ብሎ ክዷል።
የተከሳሾች ጠበቃ አዲሱ ጌታነህ በበኩሉ ምስክሩ ዐቃቤ ሕግ በማስረጃ ዝርዝር ላይ ያስቀመጠው፣ ጠዋትም ማንነቱን ለፍርድ ቤቱ የገለፀ፣ ዐቃቤ ሕግ በጠራው መሰረት በቀጠሮው የቀረበ እና በመታወቂያውም መለየት የሚቻል መሆኑን በመግለፅ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን አስረድቷል።
ዐቃቤ ሕግ ዛሬ የቀረበው ሳይሆን ሌላና በምስክርነት ቆጥሬዋለሁ የሚለው ሸዋንግዛው ቀርቦ እንዲመሰክር ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠኝ ብሏል። ፍርድ ቤቱ 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን ገልፆ በቀጠሮ መሰረት የቀረበውን አቶ ሸዋንግዛው በጠዋቱ ችሎት ከተናገረው፣ ከዐቃቤ ሕግና ከተከሳሾች ጠበቃ የራሱን ግምት እንደሚወስድ በመግለፅ 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር እንዲቀርብ ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ ክስ በቀረበባቸው እስረኞች ላይ የተፈፀመ በደል
ጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ያሬድ ሁሴን ኢብራሂም የክስ መዝገብ ክስ የቀረበባቸው 25 ተከሳሾች በአዲስ አበባ ቀጠሮ ማረፊያ ቤት( ቂሊንጦ) ቃጠሎ ሰበብ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው የደረሰባቸው የሰብአዊ መብት ጥሰትን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽ አጣርቶ እንዲያቀርብ በማዘዙ ኮምሽኑ ምርመራውን ለፍርድ ቤት ልኳል።
ተከሳሾቹ ያቀረቡት አቤቱታ:_
የቀጠሮ ማረፊያ ቤት ላይ በተፈጠረው ቃጠሎ ምክንያት በቃጠሎው እጃችሁ አለበት ተብለን ነሃሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለይተን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን ኢሰብአዊ ድርጊት ተፈፅሞብናል። በሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ያልፈፀምነውን ድርጊት እመኑ እየተባልን ለሰው ልጅ በማይመጥን፣ ኢሰብአዊ የሆነ ድርጊት ተፈፅሞብናል። ለአንድ ወር ያህል በካቴና ከአልጋ ጋር ታስረናል። ተገልብጠን ተገርፈናል። የውስጥ እግራችን ተገርፈናል። አንጠልጥለው በማሰር ውሃ እየደፉብን፣ በኤሌክትሪክ ሾክ እየተደረግን ተመርምረናል። በእምነትና ማንነታችን ጥቃት ደርሶብናል። በደረሰብን ድብደባና ስቃይ ብዛት ያልፈፀምነውን ድርጊት ፈፅመናል ብለን ለማመን ተገደናል።
ወደ ቀጠሮ ማረፊያ ቤት (ቂሊንጦ) ከተመለስን በኋላ ቢሆን በደረሰብን ድብደባ ብዛት ላጋጠመን ጉዳት ህክምና አላገኘንም። በቃጠሎው ወቅት አልባሳትን ጨምሮ ንብረቶቻችን በማረሚያ ቤቱ የተወረስን ሲሆን እንዲመለሱልን ስንጠይቅ ተቃጥለዋል የሚል ምላሽ ተሰጥቶናል።
በምርመራ ወቅት ጉዳት የደረሰባቸው ተከሳሾች:_
1) ፀጋዬ ዘውዱ:_ቀኝ እግር ከጉልበቱ በታች ጠባሳ፣ ግራ እግር ላይ የግርፋት የሚመስል ጠባሰ፣ ጀርባ ላይ ጠባሳ ፣ የአውራ ጣት ጥፍር መነቀል፣ የካቴና የታሰረበት ምልክት
2) ያሬድ ሁሴን:_ ግራ እግር ላይ ጠባሳ፣ቀኝ እጅ ላይ ጠባሳ፣ የካቴና እስር ምልክቶች፣
3) ኃይለ መስቀል ፀጋዬ:_ ሁለት እጆቹ ላይ ጠባሳ
4) ሁሴን አህመድ:_ የግራ እጅ ጠባሳ
5)ሰለሞን ጫኔ:_የቀኝ እጅ የመሃል ጣት ስብራት፣ የቀኝ እግር ደም ስር መዛባት
6)ስማቸው አርጋው:_ የግራ እጅ የመጀመርያ ጣት ስብራት፣ ሁለት እጆቹ ላይ ጠባሳ፣ ሁለት እግር ታፋዎች ላይ የግርፋት ጠባሳ ምልክቶች
7)ዋሲሁን አየለ:_ በካቴና የመታሰር ምልክቶች
8) ሀቢብ ከድር:_ሁለት እጅ ላይ የጠባሳ ምልክቶች፣ ቀኝና ግራ ክንድ ላይ የጠባሳ ምልክቶች፣
9) ግሩም አስቀናው:_ ሁለት እጆቹ ላይ በካቴና የታሰረበት ጠባሳ ምልክቶች፣ ከቀኝ ታፋ በላይ ትልቅ ጠባሳ
10) ሻሾ አድማሱ:_ ወገቡ ላይ ትልቅ ጠባሳ
11)ማናዬ መንገሻ:_ የአውራ ጣት ጥፍር መነቀል
12) ቢንያም አሰፋ:_ የቀኝና ግራ እጅ ላይ በካቴና መጥበቅ ምክንያት የጠባሳ ምልክቶች
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ከላይ የተጠቀሱት እስረኞች ወደ እስር ቤት ሲገቡ የተጠቀሱት ጉዳቶችና ምልክቶች እንዳልነበረባቸው አረጋግጧል። የኮምሽኑ ምርመራው የተካሄደው ድብደባው ከተፈፀመ 10 ወር በኋላ ቢሆንም የግርፋት ምልክቶች በግልፅ እንደሚታዩ በሪፖርቱ ላይ ተገልፆአል። በመሆኑም ተከሳሾች ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው በአቤቱታው ላይ የተጠቀሰው ለሰው ልጅ የማይመጥንና ኢ ሰብአዊ የሆነ ድርጊት እንደተፈፀመባቸው ተረጋግጧል።
ይሁንና አቤቱታ ያቀረቡት 25 ተከሳሾች ሆነው ኮምሽኑ የጠቀሰው የ12 ተከሳሾችን በደል ብቻ ነው። በሌሎች መዝገቦችም ተመሳሳይ አቤቱታ ቀርቦ ኮምሽኑ ሪፖርት ያቀረበ ሲሆን በእስረኞች ላይ የተፈፀመውን በደል በሚገባ በሪፖርቱ አላጠቃለለም ተብሏል።
በደል የተፈፀመባቸው እስረኞች ካለመጠቀሳቸውም በተጨማሪ በሪፖርቱ የተጠቃለሉ እስረኞች የደረሰባቸው በደል በሚገባ አልተጠቀሰም ተብሏል። በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ክስ መዝገብ የተከሰሱ 38 ተከሳሾች ሸዋሮቢት ተወስደው በደል በተፈፀመባቸው 175 እስረኞች ላይ ከተፈፀመው በደል መካከል ኮምሽኑ 6 በመቶውን ብቻ በሪፖርቱ ማጠቃለሉን ተከሳሾቹ በችሎት ተናግረዋል። ኮምሽኑ የተፈፀመውን በደል በሚገባ በሪፖርቱ ባለማጠቃለሉና ገለልተኛ አይደለም በሚል ሌላ ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ የተፈፀመባቸውን አስከፊ በደል እንዲያጣራ እስረኞቹ አቤቱታቸውን ለፍርድ ቤት እያቀረቡ ነው።
ኮምሽኑ በእስረኞች ላይ በደል ፈፀሙ የተባሉ አካላትን ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲያጣራ በምክረ ሀሳብ ያስቀመጠ ሲሆን እነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ኃላፊዎች ድብደባ እንደፈፀሙባቸውና እንዳስፈፀሙባቸው የኃላፊዎችን ስም ጭምር በመጥቀስ ገልፀዋል። በመሆኑም በደል የፈፀመው አካል ጉዳዩን እንዲያጣራ መታዘዙ የደረሰብን በደል ተሸፋፍኖ እንዲቀር ስለተፈለገ ነው የሚል ቅሬታ አቅርበዋል። ከተከሳሾቹ ባሻገር ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ ያቀረባቸውና ያዘጋጃቸው ምስክሮች በምርመራ ወቅት በደረሰባቸው ድብደባ ምክንያት ተገደው ለምስክርነት እንደቀረቡና ተገደው ምስክር በሆኑት ላይ የተፈፀመው በደልም እንዲጣራ ተከሳሾች ለፍርድ ቤት አመልክተዋል።
ፍርድ ቤቱ ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጣ
በጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእስር ላይ የምትገኘው ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጥቷል። በእነ ደቻሳ ሞሲሳ የክስ መዝገብ 4 ተከሳሽ ጫልቱ ታከለ “እናንተ ኢህአዴግ ናችሁ፣ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አልጠብቅም” ብላ ተናግራለች በሚል በችሎት መድፈር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።

ፎቶ፡- ጫልቱ ታከለ
ህዳር 28 ቀን 2010 ዓም እነ ደቻሳ ሞሲሳ ተከላከሉ የሚል ብይን በተሰጠባቸው ወቅት 3ኛ ተከሳሽ የሆነችው ጫልቱ በሰነድ ማስረጃነት የቀረበባት የደህንነት ሪፖርት ወደ ኤርትራ ስለመሄድ የጠቀሰው ነገር ሳይኖር ብይን ላይ ወደ ኤርትራ ልትሄድ እንደነበር ተጠቅሶ ተከላከይ መባሏ እንዳሳዘናት ገልፃለች።
ጫልቱ ታከለ በወቅቱ “ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አንጠብቅም። ወደፊትም ፍትህ እንደማናገኝ ነው የምናስበው።” ብላ በመናገሯ በችሎት መድፈር ጥፋተኛ ተብላ በአዳር ዛሬ ህዳር 29 ቀን 2010ዓ.ም. የ500 ብር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።
ጫልቱ ታከለ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ክስ ተፈርዶባት ፍርዷን ጨርሳ እንደወጣች ተገልጿል።
አባ ገብረ-ኢየሱስ ዘዋልድባ፤ ተደብድበውና አካላቸው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶ ጭለማ እንደሚገኙ ተጠቆመ
በጌታቸው ሺፈራው
#የፌደራልከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ውሎ
” #አባገ/እየሱስ ዘ _ዋልድባ ተደብድበው፣ ተሰባብረው እኔ ጋር ጨለማ ቤት ነው ታስረው ያሉት” አስቻለው ደሴ
#እስረኞች ለህይወታቸው እንደሚሰጉ ገልፀዋል
#የዐቃቤሕግ ምስክር ስሙን እየቀያየረ በተለያዩ መዝገቦች እየመሰከረ ነው ተብሏል
#የአማራክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ ዛሬም የከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣኑን አጥቷል የሚል ብይን ተሰጥቶበታል

ፎቶ:- አባ ገብረ-ኢየሱስ ዘ-ዋልድባ
~የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬም (ህዳር 28/2010) የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣኑን አጥቷል የሚል ብይን ሰጥቷል። ፍርድ ቤቱ ብይን የሰጠው በእነ አስቻለው ደሴ መዝገብ የተከሰሱ 4 ግለሰቦች ወንጀል ፈፅማችኋል የተባልነው በአማራ ክልል በመሆኑ ጉዳያችንን ሊያየው የሚገባው የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ነው ብለው ላቅቡት የክስ መቃወሚያ ነው።
ብይኑን በአብላጫ ድምፅ የሰጠው ፍርድ ቤቱ በአዲስ አበባና ድሬዳዋ እንዲሁም ሶማሊ፣ አፋር፣ ሀረሪ(?)፣ ደቡብና ቤንሻንጉል ክልሎች የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶችየፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትን ስራ ደርበውና ወክለው እንዲሰሩ ስልጣን ስለተሰጣቸው የአማራ ክልልን ጨምሮ ሌሎች ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች የከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣንን አጥተዋል ተብሏል።
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ለቀረቡለት የክስ መቃወሚያዎች ከአዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ፣ ሶማሊ፣ አፋር፣ ቤንሻንጉልና ሀረሪ(?) ክልሎች ውጭ ያሉ የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች የከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣንን አጥተዋል ብሎ በተደጋጋሚ ብይን ሰጥቷል።
~ብይኑ የተሰጠው በአብላጫ ድምፅ ሲሆን የመሃል ዳኛው ዮሃንስ ጌስያብ ለሌሎች ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ስልጣን በሕግ መሰጠቱ፣ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይህን ስልጣን እንዲያጣ አያደርገውም በሚል የልዩነት ሀሳባቸውን አስመዝግበዋል። መሃል ዳኛው ለብይኑ መንስኤ በሆነው ምክንያት ልዩነት ቢያስመዘግቡም የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የ”ሽብር” ጉዳይን የማየት “ተፈጥሯዊ መብት” አለው በሚል በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ሊታይ አይገባም በማለት በብይኑ ውጤት ከሌሎች ዳኞች ላይ ተስማምተዋል።
~ በእነ አስቻለው ደሴ ክስ መዝገብ አንደኛ ተከሳሽ እና ህዳር 14/2010 ሱሪውን አውልቆ በምርመራ ወቅት ብልቱ መኮላሸቱን ያሳየው አስቻለው ደሴ አሁንም ህይወቱ አደጋ ውስጥ መሆኑን ተናግሯል። አስቻለው ደሴ ምንም አይነት ጥፋት ሳያጠፋ ጨለማ ቤት ታስሮ እንደሚገኝና አሁን የታሰረበት ሁኔታ ለህይወቱ አስጊ መሆኑን ለፍርድ ቤቱ ተናግሯል። አባ ገ/ እየሱስ ኪዳነ ማርያም ጨለማ ቤት መታሰራቸውን ገልፆአል። ” አባ ገ/እየሱስ ዘ ዋልድባ ተደብድበው፣ ተሰባብረው እኔ ጋር ጨለማ ቤት ነው ያስረው ያሉት” ሲል አባ ገ/እየሱስ ስለታሰሩበት ሁኔታ ገልፆአል።
~ ከክፍለ ሀገር የመጡ ቤተሰቦቹ ፍርድ ቤቱ ግቢ ውስጥ በፖሊስ መያዛቸውን ገልፆ፣ ለምን እንደተያዙና የት እንደሚገኙ እንዲጣራ በጠየቀው መሰረት ቤተሰቦቹን የያዘችው ፖሊስ የአስቻለው ቤተሰቦች እጃቸውን አጣምረው ለተከሳሹ ሰላምታ ሲሰጡ በማየቷ እንደያዘቻቸውና መክራ እንደለቀቀቻቸው ገልፃለች። አስቻለው ደሴ “ካላየኋቸው አላምንም” በማለቱ ፍርድ ቤቱ “ዘመነኛውን የተቃውሞ ምልክት አሳይተው መለስኳቸው ብላለች። ከዚህ ግቢ ውስጥ እንዲህ አይነት ነገር አይደረግም” ብሏል።
~በአስቻለው የክስ መዝገብ 4ኛ ተከሳሽ ማዕከላዊ በደረሰበት ድብደባ ምክንያት አንድ ጉድን፣ ኩላሊት እና ልቡ ላይ ጉዳት እንደደረሰበት ገልፆአል። በዚህም ምክንያት በአንድ ጉኑ ብቻ ለመተኛት መገደዱን፣ በቂ ህክምናም እያገኘ እንዳልሆነ ገልፆ “በቅርቡ ህይወቴ ያልፋል ብየ እሰጋለሁ” ሲል ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል። ማዕከላዊ የደበደቡት ቸርነት እና ተስፋዬ የተባሉ መርማሪዎችም እንዲጠየቁ አቤቱታ አቅርቧል።
~በእነ አብዱ አደም ክስ መዝገብ የተከሰሱ 7 ግለሰቦች አንድ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት በሚል 6 ጊዜ እንደተቀጠረባቸው በመግለፅ ምስክርነቱ እንዲታለፍ ጠይቀዋል። አድራሻው ሻሸመኔ ነው የተባለውን ምስክር ለመስማት በተደጋጋሚ እንደተቀጠረባቸው የገለፁት ተከሳሾቹ ምስክርነቱ ታልፎ እንዲበየንላቸው ጠይቀዋል።
~ 1ኛ ተከሳሽ :_
” ከታሰርን አንድ አመት ከአራት ወር ሆኖናል። እኔ ተማሪ ነኝ። ከትምህርት ቤት ነው የተያዝኩት። አባቴ የ70 አመት አዛውንት ናቸው። በሌላ መዝገብ ተከሰው ቂሊንጦ ታስረው ነበር። የተለያየ ዞን ታስረን ነበር። ለቤተሰብ ጥየቃ ስለማይመች በደብዳቤ ጠይቄ ከእኔ ጋር ታስረው ነበር። ነገር ግን ካቦ(የእስረኞች ኃላፊ) ይቀየር ብለው ስለጠየቁ ትናንት ማታ ወዳልታወቀ ቦታ ተወስደዋል። የት እንደሄዱ አላውቅም። ያሉበትን ሁኔታ ማወቅ እፈልጋለሁ።”
~እነ አበራ ለሚ ክስ መዝገብ ስር የተከሰሱ የመከላከያ ምስክር አሰምተዋል። ለ3ኛ ተከሳሽ ሆራ ከበደ የመከላከያ ምስክርነቱን የሰጠው ቡልቲ ተሰማ በእነ አበራ ለሚ መዝገብ ያሉ ተከሳሾች ላይ የመሰከረው ግለሰብ ስም እየቀየረ በተለያዩ መዝገቦች ክስ የቀረበባቸው እስረኞች ላይ እንደሚመሰክር አስረድቷል። ምስክሩ ሀምሌ 13/2009 ዓም በእነ አበራ ለሚ ክስ መዝገብ ሀብታሙ ፈይሳ፣ እንዲሁም ነሃሴ 6/2009 ደግሞ ጋድጌዳ ግርማ ብሎ በራሱ በአቶ ቡልቲ ላይ እንደመሰከረ ተገልፆአል።
~እነ መልካሙ ክንፉ ክሳቸው እንዲሻሻል በጠየቁት መሰረት ሁለት ጊዜ ተሻሻለ ተብሎ ሳይሻሻል መቅረቱን ገልፀዋል። በዛሬው እለት ለ3ኛ ጊዜ የተሻሻለ ነው የተባለ ክስ ተነቦላቸዋል። ፍርድ ቤቱ የአንደኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፉ ክስ መሻሻሉን ገልፆአል። ሆኖም ክሱ ከተነበበ በኋላ ተከሳሾች ይሻሻል የተባለው የ1ኛ እና 4ኛ ተከሳሾች መሆኑን አስታውሰው የተነበበላቸው የመጀመርያው ክስ እንጅ የተሻሻለ ነገር እንደሌለው ገልፀዋል። ባለፈው ቀጠሮ ፍርድ ቤት አቃቤ ህግ ክሱን አሻሽሎ በቶሎ ካላመጣ ተከሳሾቹን በነፃ አሰናብታለሁ እንዳለ አስታውሰው ቃሉን እንዲጠብቅ ገልፀዋል።
~ፍርድ ቤቱ የሟች አየለ በየነ ክስ እንዲቋረጥ በመወሰን ለአቃቤ ህጉ ትዕዛዝ ባስተላለፈበት ወቅት አቃቤ ህጉ አቶ መኩሪያ አለሙ “ተከሳሽ መሞቱን ሳላረጋግጥ ክሱን ማቋረጥ አልችልም” ብለዋል። ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መስጠቱን በማስታወስ፣ የአስከሬን ምርመራ ማስረጃም መዝገቡ ጋር መያያዙን ገልፆአል። አቃቤ ሕጉ ይህን መረጃ ካገኘ ክሱን እንደሚያቋርጥ ገልፆአል። ፍ/ ቤቱ መዝገቡን አይቶ ክሱ ተሻሽሏል አልተሻሻለም የሚለውን አይቶ ለመበየን ለታህሳስ 10/2010 ዓም ቀጠሮ ይዟል።
~ በማስተር ፕላኑ ምክንያት የተነሳውን የህዝብ ተቃውሞ አስተባብሯል፣ የኦነግ አባላትን አደራጅቶ አመፅ መርቷል የሚል የ”ሽብር” ክስ የተመሰረተበት ጃራ ሃዋዝ 5 አመት ተፈርዶበታል።
የፖለቲካ እስረኞች በኢትዮጵያ እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትን አስመልክቶ የድረሱልን ጥሪ አቀረቡ
በመቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ ላይ ያሉ 38ቱ ተከሳሾች አቤቱታ
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን(ኢሰመኮ) ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!

ፎቶ፡- ማስረሻ ሰጤ
~ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የተሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።
~አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።
እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተከሰን በነበርንበት ክስ የዋስትና መብተችንን ተከልክለን እንደማንኛውም እስረኛ ክሳችንን በቀጠሮ እየተከታተልን ሳለን ነሃሴ 28/ 2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ውስጥ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ ምክንያት “ሊያመልጡ ሞክረዋል!” በሚል ሰበብ፣ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥያቄ የሚጠይቁ ወንድሞቻችን (ጓደኞቻችንን) እኛ ፊት በጥይት ገድለው እሳት ውስጥ ጨምረው አቃጥለዋቸዋል።
እንዲህ ያለ አረመኔያዊ ድርጊት ከፈፀሙ በኋላ ገና ለገና ይህንን እውነት ያጋልጡብናል ብለው በመስጋት እኛን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት በመውሰድ ለ3ወራት ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ በማፈን፣ ለምርመራ በሚል ሰበብ በዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ በሚመራው ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሰማዕታት ሙዝዬም ውስጥ ሀውልት የተሰራለት የ”ቶርች” ገረፋ ተፈፅሞብናል።
በካቴና ታስረን፣ ተሰቅለን ተገርፈናል። ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። በኤሌክትሪክ ሾክ ተደርገናል። በሚስማር ውስጥ እግራችንና ጀርባችን ተበሳስቷል። ጭንቅላታችንን በሰደፍ ፈንክተውናል። የተወሰንን ታራሚዎች ተለይተን ብልታችን ላይ ሁለት ሊትር ሀይላንድ ውሃ ተንጠልጥሎብናል። ሌሎችም ተዘርዝረው የማያልቁ ብዙ በደሎች ተፈፅመውብናል።
ይህ የደረሰብን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ታህሳስ 14/2009 ዓ•ም ለፍርድ ቤት በማሳየትና በማስረዳት ፎቶ መነሳት አለብን ብንልም ፍርድ ቤቱ ጥያቄያችን ሊቀበለን አልቻለም። ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ስንመለስ ደግሞ “ፍርድ ቤት ሄዳችሁ ብትለፈልፉ ምንም አታመጡም!” በማለት እስከ መጋቢት 12/2009 ዓ•ም ድረሰ ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ውስጥ ከተው የቤተሰብ ግንኙነት ከልክለውን በፀሀይ ብርሃን እጦት መልካችን ቢጫ እስኪሆንና አይናችን ብርሃን ማየት እስኪያቅተው ድረስ ተቆልፎብን ተሰቃይተናል።
እንደዚህ አይነት ግፍ የተፈፀመብን በወቅቱ የነበሩ በጣት የሚቆጠሩ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችን ከተጠያቂነት ለማዳን በጣም ደካማ አስተሳሰብ ያላቸው የመንግስት ኃላፊዎች እኛን የፖለቲካ መልስ ለማድረግ የወሰኑት ውሳኔ ነው። ህሊናቸውን ሸጠው በእኛ በንፁሃን ላይ እንዲህ አይነት ስቃይ የፈፀሙብን፣ ያስፈፀሙብን እንዲሁም ሀሳት የተቀነባበረ ክሰ የከሰሱን።
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት የኮምሽኑ መርማሪዎች ከ10 ወራት ቆይታ በኋላም ቢሆን በአይናቸው ያዩትን እውነት በዝርዝር በሪፖርት ለፍርድ ቤት አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱም ሰብአዊ መብት ኮምሽን ሪፖርት ላይ ብይን ለመስጠት ለህዳር 29/ 2010 ዓ•ም ቀጠሮ ይዟል።
#የኢትዮጵያሰብአዊመብትኮምሽን ስላቀረበው ሪፖርት ያለን አስተያየት:_
1) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን (ኢሰመኮ) የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ሙሉ ለሙሉ አላካተተም።
2)የኢሰመኮ ኢ _ሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ በማለት ቁርጥ ያለ ሪፖርት ማቅረብ ሲገባው እና የኮምሽን መስርያ ቤቱ ጉዳዩን ተከታትሎ በዜጎች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት ያደረሱ አካላት በሕግ ማስቀጣት ሲገባው ምክረ ሀሳብ በማለት የተለሳለሰ የፍራቻ የሚመስል ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል። መስርያ ቤቱ እውነቱን እያወቀ እንዲህ ያለ ሪፖርት በማቅረቡ ምን ያህል የደህንነት ቢሮ ተፅዕኖ እንዳለበት እና በራስ መተማመን የጎደለው መስርያ ቤት መሆኑን የሚያሳይ ነው።
3) ኢሰመኮ በእኛ ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙ አካላትን እንዲመረምር ወይም እንዲያጣራ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽንና ለህክምና ቡድን አባላት በመፃፉ ቅር ተሰኝተናል። ምክንያቱም ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ነው። ውሻ ነከሰን ብለን ለጅብ እንድንናገር መደረግ የለበትም።
4) ኢሰመኮ በዚህ መልክም (በጥቂቱም) ቢሆን የተፈፀመብንን ግፍ በሪፖርት በማቅረቡ ምስጋና እናቀርባለን። ምክንያቱም ምን ያህል ተገደን ለፖሊስ ቃል እንደሰጠንና ለዶክመንተሪ ፊልማቸው በቪዲዮ እንደተቀረፅን የሚያሳይ ነው። በፍርድ ቤቱም በ27(2) ቃላችን ውድቅ እንዲደረግ የሚጠቅመን የሰነድ ማድረጃ በመሆኑ ነው።
#የህዝብተወካዮች ምክር ቤት እና የፌደራል ማረሚ ያ ቤቶች ላይ ያለን አስተያየት:-
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ነን፣ ለምርመራ ነው የመጣነው ብለው በግልና በጋራ አናግረው መርምረው ምንም አይነት መፍትሄ አልሰጡንም። ምንም አይነት ሪፖርትም አላቅረቡም። በዚህም በጣም ቅር ተሰኝተናል። እንዲህ ነው እንጅ የህዝብ ተወካይ መሆን፤
1) የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር እውነቱን እያወቀ፣ እኛ እንድንከሰስ በማቀነባበር፣ በህግ ጥላ ስር እያለን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን ያ ሁሉ ኢሰብአዊ ድርጊት እንዲፈፀምብን ማድረጉ፣
~ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ያሉ እስረኞችን በማስፈራራትና በማባበል ወደ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት በመውሰድ በእኛ ላይ እንዲመሰክሩብን በማድረጉ፣
~መርማሪዎች ነን ከሚሉ አካላት ጋር በመተባበር እኛን በመደብደብና በማስደብደብ ጨለማ ቤት አስገብቶ፣ ቤተሰብ ግንኙነት ከልክሎ በማሰቃየት በተፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት ቅር ተሰኝተናል።
2) በዚህ ኢትዮጵያዊነት በጎደለው በዘራችንና በሀይማኖታችን ተመርጠን፣ በሀሰት ተከሰን ለአመታት እንዲህ ያለ ስቃይ እንድንሰቃይ መደረጋችን ታሪክ የማይሽረው ጠባሳ በልባችን ላይ ጥላችሁብናል። የሞቱት ጓደኞቻችን! ገዳይ እናንተ! በሀሰት ተከሰን የምንሰቃየው እኛ! ፈጣሪን አትፈሩም? ግፍ አይደለም? ነገ በልጆቻችሁ አይደርስም? ከትግራይ ተወላጆች ውጭ ሌላው ዘር ጠላት ነው? ያሳዝናል!
3) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከትግሬ ውጭ ሌላ አመራር የለም። አንድም የተማረ ወይም የበሰለ አስተዳደር የለም። ተናዳጅ፣ ተቆጭ፣ መሃይሞች ብቻ ናቸው። አብዛኛዎቹ ታጋይ የነበሩና በዘረኝነት ያበዱ ከትግሬ ውጭ ሌላው ዘር ሰው የማይመስላቸው ያልሰለጡ ናቸው። ይህ ደግሞ ለጭካኔና አረሜኔያዊ ተግባር ለመፈፀም አግዟቸዋል። ለዚህ ነው ፍርድ ቤት ሄደን ስንናገር የምንደበደበው። ጨለማ ቤት የምንገባው ማገናዘብ በማይችሉ አመራሮች ስለምንመራ ነው።
ቂሊንጦ ማረፊያ የሆኑት ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አሰፋ ኪዳነ ቃጠሎው ሲደርስ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ነበርኩ ብለው ተጠርጣሪዎች በቆይታቸው ምንም ጉዳት አልደረሰባቸውም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። ሰብአዊ መብት ኮምሽን መርማሪዎች የደረሰብንን ጉዳት እያወቀ! በምን አይነት ሰዎች እጅ ተይዘን እንዳለን ማሳያ ነው።
#በ19ኛወንጀልችሎት ዳኞች ላይ ያለን ቅሬታ
ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ቀጠሮ የተያዘ ቢሆንም ሌሎች መዝገቦችን በተደራቢ በመስራት በጠዋቱ ፕሮግራም ላይ ዳኞች ከ4 ሰዓት በፊት ባለመግባት ጉዳያችን ተጓትቶብናል።
ይህ ሳያንስ ቀሪ የዐቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በሚል ነሃዴ 12/2009 ዓም፣ ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3 /2010 ዓም ድረስ የግማሽ አመት ቀጠሮ ተቀጥሮብናል። በዚህም ቅር ተሰኝተናል። “የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል” የሚለውን መርህ የጣሰ ተግባር ነው።
2) በፍርድ ቤቱ ውስጥ ለሟች ቤተሰቦች፣ ለእኛ ቤተሰቦችና የእኛን ጉዳይ መከታታል እና መታዘብ ለሚፈልጉ የትኛውም ወገኖች በችሎት ውስጥ በቂ የመቀመጫ ወንበር አለመኖር፣ የችሎት መጥበብ፣ በምስክር አሰጣጥ ወቅት ዳኞች ገለልተኛ አለመሆን ቅር አሰኝቶናል።
#ለኢትዮጵያሕዝብና #ለዓለምአቀፍ ማህበረሰብ የምናቀርበው የድረሱልን ጥሪ!
1) ይህ ክስ ባለቤት አለው። ክሱ ለባለቤቶቹ ይሰጥ! ክሱ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችና ፖሊሶች ነው።
2) ኢትዮጵያ ውስጥ እውነት መንግስትና ሕግ ካለ በእኛ ላይ የቀረበው ክስ ሊቋረጥ ይገባዋል። የምናውቀው ብዙ ሚስጥር አለን። ከፍተኛ የመንግስት አካላት መጥተው ሊነጋግሩን ይገባል።
3) የብሔራዊ ደህንነት ስብሰባ ላይ በቴሌቪዝን ያየነው ዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ ኃይሉ የተባለው የማዕከላዊ መርማሪ ፖሊስ የሚመራው ቡድን ለፈፀመብንና ላስፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት በህግ ይጠየቅልን።
4) ኢሰመኮ ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!
5) ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ የሚያሰማቸውን የሀሰት ምስክሮችና የሀሰት ሁኔታ እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።
6) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ቃጠሎ ምክንያት ከእኛ ከ38ቱ ተከሳሾች ውጭ 121 ተጠርጣሪዎች በዚሁ ወንጀል ከ20 እስከ 25 ተከፋፍለው በሌላ መዝገብ መከሰሳቸው ይተወቃል። ከእነሱ ውስጥ አርማዬ ዋቄ በማረሚያ ቤት ፖሊሶች ተደብድቦ የተገደለ በመሆኑ ጉዳዩ በሕግ ተይዞ እየተመረመረ ይገኛል። ሌሎቻችን ሰውነታችን በድብደባ በልዞ፣ ዝለን፣ ከነገ ዛሬ ገደሉን እያለን ስጋት ላይ ስለሆንን ይህ ግፍ እንዲቆም እንጠይቃለን።
#ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን
#ጀኔባ
እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተጠርጥረን በታሰርንበት ክስ የዋስትና መብታችን ተከልክለን ክሳችን በመከታተል ላይ እያለን ነሃሴ 28/2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በደረሰበት የእሳት ቃጠሎ ሊያመልጡ ሞክረዋል በሚል ምክንያት በእስር ቤት ውስጥ የመብት ጥያቄ ይጠይቁ የነበሩ በርካታ ወንድሞቻችን ተነጥለው በማረሚያ ቤተ ፖሊሶች በጥይት እኛ ፊት ተገድለውብናል። ይህ ሳያንሳቸው ራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን እኛ ለምርመራ በሚል ሰበብ ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን በዘራችን ብቻ ተመርጠን የአማራ፣ የኦሮሞና የጉራጌ ተወላጆች ብቻ ከፍተኛ የሆነ ኢሰብአዊ ድርጊት ተፈፅሞብናል።
ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የየሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።
አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። ይህን ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጥቅምት 20/2010 መርምሬ አረጋግጫለሁ ባለው ሪፖርት ላይ በመጠኑም ቢሆን ተፈፀመብንን ኢ ሰብአዊ ድርጊት አቅርቧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።
1)አሁንም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከፍተኛ የሆነ ድብደባ፣ ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰብን ስለሆነ፣ አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ ነው። በዚሁ በቃጠሎ ምክንያት በሌላ መዝገብ ከተከሰሱ ወንድሞቻችን ውስጥ አርማዬ ዋቄ የተባለ ተከሳሽ በማረሚያ ቤት ፖሊስ ተደብድቦ ተገድሎ ቤተሰቦቹ በክስ ላይ ይገኛሉ
2) ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ በሀሰት ያሰለጠናቸውን ምሰረክሮች ያሰማ ሲሆን ቀሪ ምስክሮችን ለማሰማት በሚል ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ተቀጥረናል። እስካሁንም ፍርድ ቤት ቀርበው የመሰከሩ ምስክሮች በተፅዕኖ ስር ሆነው ዐቃቤ ሕግ ባሰለጠናቸው መሰረት የመሰከሩ ናቸው። ቀሪ ምስክሮችም እንደ ቀድሞ ምስክሮች የታሰሩና በተፅዕኖ ስር ሆነው የሚመሰክሩ ናቸው። አንዳንድ በዋስት እና በነፃ የተፈቱ ምስክሮችን በዐቃቤ ሕግና ፖሊስ “እኛ በምንላችሁ መሰረት ነው የምትመሰክሩት” እየተባሉ ፣”ይህን ካደረጋችሁ ከቀድሞ ክሳችሁ ነፃ ትባላላችሁ” እያሉ በመደለል እንዲሁም፣ የተለያየ ማስፈራሪያና ዛቻ እየደረሰባቸው እንደሆነ አረጋግጠናል። ይህንን በተፅዕኖና ምስክሮችን በማስገደድ የሚደረግ አመሰካከር እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።
3) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ባቀረበው ሪፖርት መሰረት በእኛ በተከሳሾች ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ግፊት እንድታደርጉልን እንጠይቃለን። ነገር ግን ኢሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን በመሆኑ በሌላ ገለልተኛ ወገን ምርመራው እንዲካሄድ እንጠይቃለን።
4) ኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ ኤምባሲዎች ይህንን በሀገራችን እየተፈፀመብን ያለውን ኢሰብአዊ ድርጊት እንድትቃወሙልንና አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ በመሆኑ የድረሱልን ጥሪ እናቀርባለን።
5) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ምርመራ አረጋግጫለሁ ብሎ ባቀረበው ሪፖርት ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ማድረግ ሲገባው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን የወንጀል ምርመራ ክፍልና የህክምና ባለሙያዎች አስፈላጊ ምርመራ በማድረግ ውጤቱን ለሚመለከተው አካል አስተላልፈው የተደረሰበትን ድምዳሜ ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን እንዲያቀርቡ ምክረ ሀሰብ ቀርቧል በማለት ያቀረበው ሪፖርት ላይ በጣም ቅር ተሰኝተናል።
ምክንያቱም በሕግ ሊጠየቁ የሚገባቸው አካላት በሕግ ሊጠየቁ ይገበል ማለት ሲገባው፣ ጉዳዩን ተከታትሎ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ሲገባው በጣም ተለሳልሶ የፍራቻ የሚመስል መደምደሚያ ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል።
#ግልባጭ:_
#ለአፍሪካ ህብረት
#ለአሜሪካ፣ ለብሪታኒያ፣ ስውይድን፣ ካናዳ፣ ኖርዎይ ኤምባሲዎች
#ለማህበራዊ ሚዲያ፣ ለራዲዮ ጣቢያዎች፣ ኢቢሲና ሌሎች ሚዲያዎች ይድረስልን
#ወደእንግሊዝኛና አረብኝ ተተርጉሙ ለዓለም ህዝብ ይድረስልን