በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ እንደቀጠለ ነው፤ በመንግሥት የኃይል እርምጃ የተገደሉ ዜጎች ቁጥርም ከ140 በላይ ደርሷል
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ አሁንም በተለያዩ ከተሞች እንደቀጠለ ነው፡፡ በርካታ ትምህርት ቤቶች ተዝግተዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት ዜጎች ቁጥር ከ140 በላይ መድረሱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል እርምጃ ከሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ ከተሳተፉት እና በቤታቸው እንዲሁም በመንገድ ላይ ሲጓዙ የተገደሉትን 140 ዜጎችን ጨምሮ ከ350 በላይ ሰዎች ሲቆስሉ ከ4 ሺህ በላይ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተለይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በጅምላ እየወሰዱት ባለው እስር በድጋሚ የታሰሩት የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባ ልጅ የሆነው እና በአዳማ ዩኒቨርስቲ የ5ኛ ዓመት የህግ ተማሪ የሆነው ናዖል በቀለ ገርባን ጨምሮ በርካታ ተማሪዎች ከሚማሩበት የትምህርት ተቋም ተይዘው መታሰራቸውም ተሰምቷል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞው አሁንም በተለያዩ ከተሞች በተለይም በምዕራብ ኢትዮጵያ በወለጋ፣ ምዕራብ ሸዋ፣ በምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል በምስራቅ እና ምዕራብ ሐረርጌ፣ በአርሲ ፣ በምስራቅ ሸዋ በሚገኙ የተለያዩ ከተሞች እንደቀጠለ ነው፡፡ በመንግሥት የሚገደሉ፣ የሚታሰሩና የሚጎዱ ዜጎችም ቁጥር እየጨመረ እንደሆነ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
የኦፌኮ/መድረክ ዋና ፀሐፊ አቶ በቀለ ነጋዓ እስካሁን በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ከደረሰባቸው ተደጋጋሚ ማስፈራሪያና ዛቻ በኋላ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ የተንቀሳቃሽ ስልካቸው ተነጥቆ ፣ ከመኖሪያ ቤታቸው እንዳይወጡ ተደርጎ እስካሁንም በቁም እስር ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ህዝባዊው ተቃውሞ ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ትግበራን በመቃወም መጀመሩ ይታወሳል፡፡
መንግሥት በበኩሉ ለተቃውሞ የወጡትን ፀረ-ህዝብ፣ ፀረ-ሰላም፣ አሸባሪዎች ብሎ መወንጀሉን እና ህዝባዊው ተቃውሞውን በቁጥጥር ስር አውየዋለሁ በሚል ተደጋጋሚ መግለጫ ቢሰጥም፤ ተቃውሞው በያዝነው ሳምንት በተለያዩ የሀገሪቱ ኦሮሚያ ክልሎች ተጠናክሮ መቀጠሉ የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ በሐረርጌ አካባቢ ከአዲስ አበባ ድሬዳዋ እና ሐረር የሚወስዱ ዋና መንገዶች በተቃውሞው ተዘግተው እንደነበር ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ህወሓት እና የእነ ሓጎስ ፖለቲካ
ተክሌ በቀለ
(የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)

በተቃውሞ እንቅስቃሴዉ ዉስጥ አንድ ያልተፈታ መምታታት ይታያል፡፡ ህዝብንና ድርጅትን መለየት አለመቻል፡፡ አንዳንዴ እንደስልትም ሆን ተብሎ ይሰራበታል፡፡ ግን አክሳሪ ስልት እንደሆነ ትምህርት ሊወሰድ አልተቻለም፡፡ ህወሓት በትግራይ ህዝብ ውስጥ የተፈጠረ ድርጅት ሲሆን ህዝቡ ብዙ ታሪክ እየሰራ ለብዙ ዘመናት እንደኖረ የምንስማማ ይመስለኛል፡፡ ለወደፊቱም ይኖራል፡፡ እነ ሓጎስ ድርጅቱ ውስጥ በአባልነትና በደጋፊነት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በህዝቡ መሃል እየተረገጡም ሊኖሩ ይቻላሉ፡፡ በተቃዋሚው ጎራም ይኖራሉ፡፡ ከሃገር እንዲወጡና እንዳይመለሱ የተደረጉም ይኖራሉ፡፡ ተሰፋ ቆርጠው አንገት ደፍተዉ የተቀመጡም ይኖራሉ፡፡ እነሓጎስ ብዙ ናቸው፡፡ እነ ሓጎስን ከህወሓት ጋር ስንቀላቅላቸው ለደህንነታቸው ይሰጋሉ፡፡ እናም ልዩነታቸውን ረስተው አብረው ይቆማሉ፡፡ በዚህኛው ወገን ያለው ደጋፊም አቅም ያጣል፡፡የወገኖቹን ደህንነት ይፈልጋልና ነው፡፡
የህወሓቶቹን እነ ሃጎስ ያገኘን(ለማሸማቀቅም ይሁን ለማስፈራራት) መስሎን ቀላቅለን ስናያቸው በተቃራኒ ያሉትን ሓጎሶች(ለምሳሌ የዓረና አመራሮችና አባላትን) ሁሉ አቅም እያሳጣናቸዉ ነው፡፡ መሰረታቸውን እያናጋነው ነው፡፡ በህዝባቸው ፊት በህወሓት እንዲቀጠቀጡ ዱላ እያቀበልን ነዉ፡፡ ሲሆን እንሰልጥንና የሁሉም ሓጎሶች ምርጫ ህወሓት ከሆነ ሌሎቻችን እኛን ራሳችንን ነጻ እናውጣና ያገሪቱ ህግ በሚፈቅደዉ መሰረት አብረናቸዉ ለመስራት ዝግጁ እንሁን፡፡ እነሱን ከነሓጎስ ጋር ለማጥፋት ከመስራት እዛው ራሳቸዉን እንዲያስተዳድሩ ራስን ማሳመን ዋጋው ይቀላል፡፡ ሁሉን አቀፍ ድርድር (inclusive negotiation) እኮ አንዱ እፊታችን የሚኖር አማራጭ ይመስለኛል፡፡ ራሳችንን ነጻ ለማዉጣት ከህወሓት ጋር ያሉትን ድጋፍ መጠበቅ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ግን እስኪ ሌሎቻችን በወጉ እንስማማ፡፡ መንግሰትን የሚያክል ግዙፍ ተቋም ለመለወጥና አገር ለመምራት የተናጠል አመጽ ብቻውን በቂ አይመስለኝም፡፡ ህዝብን እንወክላለን የሚሉ ቡድኖች ቢስማሙ፤ቅስቀሳና አስተምህሮቶች ሁሉ ባንድነት ቢቆሙ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ አመጽ ለመቀስቀስ መስራት አይጠበቅም፡፡ ለዚህ ኢህኣዴግ ራሱ ተግቶ እየሰራ ነው፡፡ የተቃውሞው ጎራ አንድነቱን ጠብቆ አማራጭነቱን ከሳየ ህዝባዊ አመጽ ከሆነ ቦታ በሆነ ምክንያት ተነስቶ ስርዓት እንደሚለውጥ በዓለም ላይ በቂ ተሞክሮ አለ፡፡ እኛ የተለየን አንሆንም፡፡
ሳጠቃልለው፤ እነ ሓጎስን ከህወሓት አለመለየት ለትግሉ መዳከምና ለመከራችን መራዘም አስተዋጽኦ ማበርከት ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ በተናጠልም ቢሆን እየተከፈለ ያለውን ውድ መስዋዕትነት ማራከስ ነው፡፡ እነ ሓጎስን በሙሉ ከራሱ ጋር መቀላቀልና የተቀላቀሉ ማስመሰል የሚፈልገዉ ህወሓት ብቻ ነው፡፡ ህዝብና ድርጅት የመለየት ጥበብ ይኑረን፡፡ ልቦናችን ካላሰበው ካፋችን አይጣምና ልቦና ይስጠን፡፡ ተገቢ ቃላትን መጠቀም ለትግሉ ወሳኝነት ይኖረዋል፡፡ ህወሓትና ወያኔም አንድ አይደሉም! ለዚህም ነው ገዥው ቡድን ህዝባዊ ጥያቄዎችን ሁሉ ረብሻ እያስመሰለ የሚያቀርበውና ህይወት እየበላ እንዲቀጥል እድል እተሰጠው ያለው፡፡ በእውነት ያማል!!!!
እነ ዘመነ ምህረት የእምነት ክህደት ቃላቸው ሰጡ
• “ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ አሸባሪ አይደለሁም”
• “ፍትህ ቢኖር ኖሮ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ እዚህ መቆም የነበረባቸው” አቶ ጌትነት ደርሶ
• “የተከሰስኩት ድርቡሽ እንኳ ያልደፈረውን የጎንደር ጥምቀት ላይ ፈንጅ ልታፈነዳ ነበር ተብዬ ነው፡፡ ምርመራ ላይ ግን ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ ይሉኛል” አቶ ዘመነ ምህረት
ዘመነ ምህረት የክስ መዝገብ በሽብርተኝነት የተከሰሱት የቀድሞው መኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረትና ሌላኛው የመኢአድ አባል የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ ዛሬ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ለዛሬ ቀጠሮ የሰጠው አቶ ዘመነ ምህረት ማረሚያ ቤቱ ውስጥ በደል እየደረሰበት መሆኑን ባመለከተው መሰረት ማረሚያ ቤቱ ጉዳዩን አጣርቶ እንዲያቀርብ፣ እንዲሁም በዚሁ መዝገብ 3ኛ ተከሳሽ የነበረው የመኢአድ አባል መለሰ መንገሻ ክስ የተለየ ይዘት ስላለው ክሱ ተለጥሎ እንዲታይና የቀሪዎቹን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ነው፡፡
ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የእምነት ክህደት ቃል እንዲሁ እየሰማሁ እመዘግባለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹በድምፅ እንዲቀዳልኝ እፈልጋለሁ›› በማለቱ የሁለቱም ተከሳሾች የእምነት ክህደት ቃል በድምፅ እንዲቀረፅ ተደርጓል፡፡1ኛ ተከሳሽ አቶ ዘመነ ምህረት የጎንደር ጥምቅት ላይ ፈንጅ ሊያፈነዳ እንደነበር መከሰሱን ሲገልፅ ‹‹ሰው አይደለም እንሰሳት እንኳን የማይደፍሩትን፣ ድርቡሽ እንኳን ያልደፈረውን ጥምቀት እኔ በክስትና ሀይማኖትና ባህል ተኮትኩቼ ያደኩትን ሰው ፈንጅ ልታፈነዳበት ነበር መባሌ ያሳዝናል›› ብሏል፡፡ በሌላ በኩል ግን በምርመራ ወቅት ‹‹ለምን የመኢአድ አባል ሆንክ? ለምን የኢህአዴግ አባል አልሆንክም?›› እንደተባለ የገለፀው አቶ ዘመነ ይህም ‹‹ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ዥግራ ነሽ ይሏታል ነው›› ሲል እሱን ለማሰር የተቀነባበረ ሴራ መሆኑን ገልፆል፡፡ አቶ ዘመነ ምህረት አክሎም የታሰረው ኤርትራ እንዳትገነጠል ሲታገሉ የኖሩትን፣ እንዲሁም የሰላማዊ ትግሉ ፈር ቀዳጅ የሆኑት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ያስጀመሩትን ትግልን የመኢአድ አመራር ሆኖ እያስቀጠለ በመሆኑ እንደሆነ ገልፆል፡፡ በመሆኑም ወንጀሉን እንዳልፈፀመው የገለፀ ሲሆን ‹‹ከተጠቀሰው መካከል ግን የማምነው አለኝ፡፡ ኢህአዴግን ዛሬም ነገም እታገለዋለሁ›› ብሏል፡፡
2ኛ ተከሳሽ የሆነው አቶ ጌትነት ደርሶ በበኩሉ ‹‹ሽብር ተፈፅሞብኛል እንጅ እኔ አሸባሪ አይደለሁም›› ብሏል፡፡ አቶ ጌትነት አክሎም ‹‹ፍትህ ቢኖር ኖሮ እዚህ መቆም የነበረኝ እኔ ሳልሆን ወያኔና ግብረ አበሮቹ ነበሩ ነበሩ፡፡ እዚህ መቆም የነበረበት መሳሪያን ተገን አድሮጎ ለ3 ወር ጨለማ ቤት ዘግቶ ጭካኔ የፈፀመብኝ ወያኔ ነበር›› ሲል ወንጀሉን እንዳልፈፀመው ክዶ ተከራክሯል፡፡
ምንም እንኳ ፍርድ ቤቱ ባለፈው ቀጠሮ የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዘመነ ምህረት ተፈፀመብኝ ያለውን በደል አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም የማረሚያ ቤቱ ተወካይ ‹‹የደረሰኝ መረጃ የለም›› ብለዋል፡፡ ዛሬም በድጋሜ አቤቱታውን ያቀረበው አቶ ዘመነ ምህረት ‹‹እኛ እየራበን ነው፡፡ ምግቡን እንሰሳት እንኳን ሊበሉት አይችሉም፡፡ ቤተሰቦቼ እንዳይጠይቁኝ ተደርጓል፡፡›› በማለት ከተያዙበት ጥር 10 ቀን 2007 ጀምሮ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየተፈፀመባቸው መሆኑን ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ የዘር መድሎ እየደረሰባቸው እንደሆነ እና ሽንት ቤት ጥግ እንዲተኙ መደረጋቸውንም ለፍርድ ቤቱ አመልክቷል፡፡ ዛሬ ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ በማቅረቡም ከማረሚያ ቤቱ ስቃይ ሊገጥመው እንደሚችል ስጋቱን የገለፀው አቶ ዘመነ ጉዳያቸው በተዘዋዋሪ ችሎት እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የ3ኛ ተከሳሽ ክስ ከእነ ዘመነ ምህረት ክስ ተነጥሎ በሌላ ችሎት እንዲታይ ብይን የሰጠ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በማረሚያ ቤቱ ላይ ያሰማቸው አቤቱታዎችን ማረሚያ ቤቱ አጣርቶ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የሰው ምስክር ለማቅረብም ለህዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ-ኢትዮጵያ
የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንደሌሉ ገለፀ
• “የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል” 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ
• “የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው” 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ
በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንደሌሉ ማረሚያ ቤቱ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ ገልፆአል፡፡ 19ኛ ወንጀል ችሎት ሀምሌ 29 ቀን 2007 ዓ.ም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም ለምስክርነት እንዲያቀርብ ለዛሬ ለጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ የነበር ቢሆንም ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ቃሊቲ እንደሌሉ በደብዳቤ አሳውቋል፡፡
ተከሳሾቹ ማረሚያ ቤቱ ሲያጉላላቸው ቆይቶ አሁን የለም ማለቱ ትክክል እንዳልሆነ የገለፁ ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ አቶ አሸናፊ አካሉ ማረሚያ ቤቱ ምላሽ የሰጠው በአራተኛው ትዕዛዝ መሆኑን ጠቅሶ የፍርድ ሂደታቸውን ከሚገባው በላይ እያጓተተ እንደሆነ ለፍርድ ቤቱ ገልፆአል፡፡ ‹‹መከላከል ከጀመርን አንድ አመት ከስድስት ወር ሆነ፡፡ በግዞት ነው ያለነው፡፡ የሚቀርብልን ምግብ ለእንሰሳትም መቅረብ የማይገባው ነው›› ያለው አቶ አሸናፊ የማረሚያ ቤቱን ምላሽ ‹‹ፌዝ ነው›› ብሎታል፡፡
3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛ በበኩሉ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት ሲጠቅሱ አቃቤ ህግ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የሞትና የእድሜ ልክ ፍርደኛ እንደሆኑ በመጠቆም ተቃውሞ አሰምቶ እንደነበር፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ ቃሊቲ እንደሚታሰር ገልፆ ማረሚያ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው እንደሌሉ መግለፁ ‹‹የስርዓቱን ሽፍትነት ያመላክታል›› ብሏል፡፡ ‹‹የእድሜ ልክ ወይንም የሞት ፍርደኛ የት ነው የሚታሰረው?›› ሲልም ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
3ቱ ተከሳሾች የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉና ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ አንዳርጋቸውን እንደያዙ በቴሊቪዥን መግለፃቸውን አስታውሰው አሁንም ለሁለቱ አካላት ደብዳቤ እንደሚፅፉ ለፍርድ ቤቱ አሳውቀው የነበር ቢሆንም ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡
ሆኖም ግን 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ፍርድ ቤቱም 4ኛ ተከሳሽ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲቀርቡለት የሚያቀርበውን አቤቱታ ተመልክቶ ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት ለጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ መሰጠቱን ነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ላይ የኢህአዴግ እስር እና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ ቀጥሏል
በኢትዮጵያ የሰላማዊ ፖለቲካ ትግል ትልቅ ተስፋ ተጥሎበት የነበረውና በመላ ሀገሪቱ ፅህፈት ቤቶች ከፍቶ ሲንቀሳቀስ የነበረው የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ላይ የኢህአዴግ እስር እና ማስፈራሪያ ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለፀ፡፡ በተለይ ምርጫ ቦርድ ባለፈው የካቲት 2007 ዓ.ም. ፓርቲው የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ዋነኛ የኢህአዴግ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቅረብ መወሰኑን እና ለዚህም ይፋ የምርጫ እንቅስቃሴ መጀመሩን ተከትሎ ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን በማፍረሱ የቀድሞው የአንድነት አመራሮች እና አባላት ከፖለቲካው እንቅስቃሴ እንዲታቀቡ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡
ይሁን እንጂ የተወሰኑ የአንድነት ፓርቲ አመራሮች እና አባላት ፓርቲያቸው በኢህአዴግ እና በምርጫ ቦርድ በይፋ ተነጥቆ እንዲፈርስ በመደረጉ የተወሰኑ አመራሮች እና አባላት ሰማያዊ ፓርቲን በይፋ ተቀላቅለው የፖለቲካ ትግሉን ቢጀምሩም አሁንም ከኢህአዴግ እስርና ማስፈራሪያ መዳን አልቻሉመ፡፡ በዚህም በርካታ የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ወጣት አመራሮች እና አባላት ሰማያዊ ፓርቲን ከተቀላቀሉ በኋላ እነ ስንታየሁ ቸኮል በእስር ላይ ይገኛሉ፡:
ይህ በእንዲህ እንዳለ ፓርቲያቸው በምርጫ ቦርድ ፈርሶ፤ ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን ለእኔ ለሚታዘዙልኝ በሚል ራሱ ቦርዱ ለመረጣቸው አካላት ቢያስተላልፍም በርካታ የቀድሞ የአንድነት አመራሮች ከፖለቲካ ድርጅት ትግል እንዲታቀቡ ቢደረግም፤ ማስፈራሪያና እስሩ ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡ በዚህም ትናንት ግንቦት 7 ቀን 2007 ዓ.ም. የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ አባልና የማኀበራዊ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አለነ ማፀንቱ ያለምንም የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ከመኖሪያ ቤቱ በደህንነት እና በፖሊስ ኃይል ታፍኖ ከተወሰደ በኋላ ከፍተኛ ድብደባ በመፈፀም የኢሜይል አካውንቱን የይለፍ ቃል በግድ በደህንነቶች ከተወሰደ በኋላ በአዲስ አበባ ጉለሌ ፖሊስ ጣቢያ መታሰሩ ታውቋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ፓርቲው ፕሬዘዳንት የነበረው አቶ በላይ ፈቃዱ እና ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት የነበረው አቶ ተክሌ በቀለም በተመሳሳይ ዕለት በደህንነት ኃይሎች ከፍተኛ ማስፈራሪ እና ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፓርቲው በምርጫ ቦርድ ከፈረሰ በኋላ የስራ አስፈፃሚ አባል የነበረው አቶ ዳዊትአስራደን ጨምሮ በርካታ ወጣቶች እስማኤል ዳውድ፣ ስንታየሁ ቸኮል፣ መሳይ ትኩዕ፣ ፋንቱ ዳኜ በደህንነት እና ፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸውና መደብደባቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲው ወጣት ከፍተኛ አመራሮች የነበሩት አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ ዳንኤል ሺበሺ እና ሀብታሙ አያሌው በእስር ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ አንድነት የፊታችን እሁድ ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሚደረገው ሀገራዊ ምርጫ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከ450 በላይ ዕጩ ተወዳዳሪዎችን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ በቀጠለው ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል እንቅስቃሴ ምክንያት የካቲት 2007 ዓ.ም. ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን አፍርሶ “ለእኔ ለሚታዘዙልኝ…” በሚል ጋዜጣዊ መግለጫ ራሱ ቦርዱ ለመረጠው አመራር የፓርቲውን ስም መስጠቱን ይፋ ማድረጉ አያዘነጋም፡፡





