በሜዴትራኒያን ባህር ላይ በደረሰ የጀልባ አደጋ ከ16 በላይ ኢትዮጵያውያን ህይወታቸው አለፈ
ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሜዴትራኒያን ባህር ከሊቢያ ወደ አውሮፓ በስደት ሲጓዙ ከነበሩ 700 ሰዎች መካከል በርካቶች መሞታቸውንና የ28 ሰው ህይወት ብቻ በጣሊያን ባህር ኃይሎች ማትረፍ ቢቻልም፤ የአብዛኛው ተጓዥ ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡ ህይወታቸው ካለፉት ውስጥ በርካታ ኤርትራውያን እንዳሉበት ቀደም ሲል የተገለፀ ቢሆንም፤ አሁን እየወጡ ባሉ መረጃዎች በተለይም ከሞት በተረፉ ኢትዮጵያውያን እንደተገለፀ ከሆነ ከ16 በላይ ኢትዮጵያውውን መሞተታቸው ታውቋል፡፡ በጉዞ ጀልባዋ ላይ በደረሰ የመስጠም አደጋ ህይወታቸው ካለፉት መካከል 8 ወጣቶች ከአዲስ አበባ መርካቶ ልዩ ስሙ አባኮራን በሚባል አካባቢ፣ 8 ወጣቶች ከባሌ እንዲሁም የድሬዳዋ ልጆች ህይወታቸው ማለፉን ቢቢኤን እና ፍትህ ሬዲዮን ጨምሮ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ከሀገር ቤት ቤሰቦቻቸውን ዋቢ በማድረግ ያሰራጩት ዘገባ አመልክቷል፡፡
በተለይ ከአዲስ አበባ መርካቶ አባኮራን አካባቢ በጋራ ከተጓዙ 10 ወጣቶች መካከል 9ኙ በአደጋው ህይወታቸው ማለፉን እና አንዱ ከአደጋው የተረፈው ኢትዮጵያዊ ወጣት ጣሊያን እንደገባ ሀገር ቤት ደውሎ ማርዳቱ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም መሰረት የ8ቱ ቤተሰቦች ሀዘን ሲቀመጡ የአንዱ ወጣት ወላጆች ግን እስካሁን የልጃቸው ህይወት አልፏል መባሉን እንዳላመኑ እና እንዳልተቀበሉም የአካባቢው ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ሜዲትራኒያን ባህር በደረሰው አደጋ ህይወታቸው ካለፈ የአዲስ አበባ አባኮራን ሰፈር ወጣቶች መካከል አብዱ ጅላል ወጉ (ሙራድ)፣የሐዋሳ ዩኒቨርስቲ ተማሪ የነበረው ኑሩ መሐመድ፣አብዱልከሪም ዘይኒ፣ ሰይድ ይመር፣ አሊ መሐመድ፣ ነጃ ሳቢር አወል እና የኢንፎኔት ኮሌጅ ተመራቂ የነበረው ኢድሪስ አደም እና ወጣት ሸበቴ ህይወታቸው በማለፉ ቤተሰቦቻቸው ተረድተው ሀዘን መቀመጣቸው ተጠቁሟል፡፡ በሰጠመችው ጀልባ ከባሌ አካባቢ ህይወታቸው ካለፉት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች መካከል አብዱረዛቅ አቡበክር፣ በሪሲና አብዱልወሃብ፣ ሰይፈዲን አሊዪ፣ ሬድዋን ሙሃመድ፣ አሊይ ረሻድ፣ ኢሳ አማን፣ ኑእማን ሁሴን እና ሲራጅ ሙሃመድ እንደሚገኙበት ተጠቁሟል፡፡ በዚህ አደጋ ከድሬዳዋ አካባቢም ህይወታቸው ያለፈ ወጣቶች እንደሚገኙበትና ቤተሰብም ተረድቶ ሀዘን መቀመጣቸውን የቢቢኤን ዘገባ አመልክቷል፡፡
በዚህ አደጋ ከኢትዮጵያውያን በተጨማሪ ከ350 ያላነሱ ኤርትራውያንን ጨምሮ በርካታ የሶማሊያ እና የተለያዩ የአፍሪካ ሀገር ዜጎች ህይወታቸው ማለፉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ ባለፈውበደደቡብ አፍሪካ፣ በየመን እንዲሁም በሊቢያ በረሃ በዓለም አቀፉ አሸባሪው አይ ኤስ አይ ኤል 28 ኢትዮጵያውያን መገደላቸው ተከትሎ በመላ ሀገሪቱ ያለው የሀዘን ድባብ ሳያባራ አሁን ደግሞ በሊቢያ ሜዴትራኒያን ባህር ሰጥመው መሞታቸው ህዝቡን የበለጠ ሀዘን ውስጥ መክተቱ ታውቋል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ መጨረሻ 2007 ዓ.ም. በሊቢያ ታስረው የነበሩ 27 ኢትዮጵያውያን በግብፅ መንግሥት ጥረት እንዲለቀቁ ተደርገው ወደ ካይሮ ሲገቡ የግብፁ ፕሬዘዳንት አብዱል ፈታህ ኤል ሲሲ በአውሮፕላን ማረፊያው ድረስ በመሄድ አቀባበል ማድረጋቸው አይዘነጋም፡፡
የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
በአብዛኛዎቻችን ኢትዮጵያዉያን አንድ ጥሩ ባህል አለን፡፡የምንወደዉንና የሚመቻንን ሰዉ በሞት ስናጣ እርም የማዉጣት ባህል፤ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሆኖ አገኘሁት፡፡ሠዉና የፖለቲካ ድርጅ ባይገናኙም በጉልበተኛ ሃይል እንዲገናኙ ሲደረግ ከማገናኘት ዉጪ ምርጫ የለንምና እናገናኛቸዋልን፡፡
አቅምና ሁኔታዎች በፈቀዱት መጠን የወቅቱን ያገራችን ችግር በመፍታት በኩል የራሱን አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት፤ የኢህአዴግ ሰዎችን ጨምሮ ያብዛኛዉ ተራማጅ ኢትዮጵያዊ ቤት እንዲሆን አድርገን ስንገነባዉ(ሲፈጥሩትም ለዚህ ኣላማ ነበር ተብሎ ይታመናል) የነበረዉን አንድነት ፓርቲን በፖለቲካዊ ዉሳኔ የሆነዉ እንዲደርስበት ተደርጓል፡፡አማራጭ እንዲኖር የማይፈልጉት በከፍተኛ የመንግስት ሃላፊነት የተመደቡቱ ጥቂት የህወሓት ቡድኖች የማይጠቅማቸዉን ዉሳኔ እንደወሰኑ ይታወቃል፡፡ ተዉኔቱ በማን ተዘጋጅቶ እነማን እንደተጫወቱትና እነማን ደግሞ ለህዝቡ እንዳደረሱት በተደጋጋሚ ገልጸነዋል፡፡
ፓርቲዉን በተለያዩ ስሞች ሲከሱና ሲፈርጁ ቆይተዉ አመራሩንም በእስርና ድብደባ እያሹ እንዳልተንበረከከና ይበልጥ መጠናከሩን ሲያረጋግጡ ለዚህ ዉሳኔ በቅተዋል፡፡ በ40 ዓመታት ታሪኩ ፓርቲዎችን በመብላትና ከዉስጥና ከዉጭ የሚነሳ ልዩነትን በማቻቻል ሳይሆን በማጥፋት የሚታቀወቀዉ ጥቂት የህወሓት ቡድን አንድነት ፓርቲን ከማጥፋት አሁን ወደ መረጠዉ ደረጃ እንዲወርድ አድርጓል፡፡ታሪክ ሁሉን ይፈርዳል፡፡በጨለማዉ ዘመን ግፍ የተፈፀሞባቸዉ ቡድኖችና የፈሰሰዉ ደምም ተደብቆ ኣልቀረም፡፡ፖለቲካችንን ለማዘመንና ያለፈዉ ግፍ ሁሉ ባይረሳም በይቅር መታለፍ አለበት ብለን ለተነሳን ሃይሎችም እድሉን (በጉልበት በህዝብ ሃብትና በያዙት ስልጣን ተጠቅመዉ) ዘግተዉብናል፡፡ በደም መጨማለቅ በዚህ ያበቃ ዘንድ አሁንም እንታገላለን፡፡የፖለቲካ ትግሉ ሂደትም አይቆምም፡፡ያዉም ይብልጥ የመጠናከር እድል አግኝቷል ተብሎ ይታመናል፡፡የሚያቆመዉ ሃይል የለም፤መጪዉ ግዜ የለዉጥ ነዉ፡፡ለዉጡ እንደይሰረቅና ለሁሉም ይመች ዘንድ የጋራ ትስስርን እንደሚጠይቅ እሙን ነዉ፡፡
ለግዜዉ ከጀርባ ያለዉን ፖለቲካዊ ግፊት ለሌላ ፖለቲካዊ ትግል ትተን የምርጫ ቦርድ ዉሳኔን በመቃወም ክስ መስርተን ወደ ፍርድ ቤት ተብየዉ ወስደንዋል፡፡ ወደ ህግ ለመዉሰድ ስንወስን የፓርቲ ስምና አርማ አስጨንቆን አይደለም፡፡ የደጋፊዎችና አባላት ንብረት ለይምሰልም ቢሆን ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ፖለቲካዊ ዉሳኔ እንግበዉ በመጡ ከህዝብ ግብር በተሰበሰበ ደሞዝ የሚተዳደሩ የክፍለ ከተማ ፖሊስ ሃይሎች ( ህዝባዊ ሃለፊነትን የተሸከመ ተቋም በፖለቲካ እዝና ዉሳኔ የፓርቲን ንብረት ይዘርፋል የሚል እምነት አልነበረንም) ስለተዘረፈብን ሃላፊነታችንን ለመወጣትና ታሪካዊ እልባት እንዲኖረዉ ለማስቻል ነዉ፡፡እንጂማ ራእያችን በእያነዳንዳችን ዉስጥ ቢሆንም የወቅቱ ትግል ግን የነፃነት መሆኑን አጥተነዉ አይደለም፡፡
በወቅቱ የብሔራዊ ስራ አስፈፃሚዉ የወሰነዉ ዉሰኔ የመድብለ ፓርቲ ስርኣቱ ከምን ግዜዉም በላይ ፈተና ላይ መዉደቁና አዲስ ፓርቲ መመስረት ችኮላና ህዝቡን ስርአቱ ለመድብለ ፓርቲ አሁንም ይመቻል፤ጥፋቱ የኛ ነዉ ብሎ መዋሸት መሆኑ፤እስኪያጠፋቸዉ ድረስ ሌሎች ፓርቲዎች ጋ መቀላቀል በተላይም ከምርጫዉ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ተስፋ ያላቸዉ አባላት የግል ምርጫቸዉ መሆኑንና አመራሩም ይህን እንደማይቃወም፤የፓርቲዉ አባላት ጉዳዩ በፍ/ቤት እስኪቋጭ ድረስ አመራሩን እንዲጠብቁ ይሀም ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ከሰዓት እንዲቀርብና ተወያይቶ ዉሰኔ እንዲሰጥበት የተስማማ ሲሆን በወቅቱ ሁለት አባላት ብቻ አልተገኙም፡፡ከሰኣት ቢሮዉ የፖሊስ ደንብ በለበሱ የመንግስት አካላት ተዘረፈ፡፡ይህ ደግሞ አእላፍ ወንድሞቻችን ላለፉት 40-50 አመታት በተለያየ ጉራ ተሰልፈዉ በተሰዉለት በተላይም በትግረዋይ ደም/ የትግል ዉጢት ሌላዉ ቀልድ እንደመሆኑ ጉዳዩ አብዛሃዉ የአንድነት ደጋፊና አባል በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንወስደዋለን ባልነዉ መሰረትእየታየ ይገኛል፡፡በመሆኑም ጉዳዩን መከታተል የእያነዳንዱ የአንድነት አባልና ደጋፊ የህሊና እዳ ይመስለኛል፡፡በአንድነት ቀብር ላይ አሁንም አንድነታችንን በማረጋገጥ ባብዛሃ ዉሳኔ ቀጣዩን መንድ መጓዝ እንጂ ልንለያይ የሚጋብዝን መንገድ መከተል ያለብን አይምስለኝም፡፡ካለፉት የተቃዉሞ ጎራ በጎዉን ትምህርት መቅሰም የሚኖርብን እንዳለ ይሰማኛል፡፡በችኮላ ፓርቲ ለመመስረት የሚደረግ ሩጫ የስልጣን ሀይልነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለህዝባችን ፋይዳ አለዉ ብየ አልገምትም፡፡ ምርጫቸዉ ላደረጉት ጓዶቼ ግን ስህተት ቢሆን ምርጫቸዉን አከብራለሁ፡፡
ጉዳያችንን ወደ ፍርድ ቤት ስንወስደዉ በፍትህ ተቋማቱ ምናልባትም በሰላማዊ ትግል ስልት ስርኣቱን ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች መካከል ከቀድሞዉ ቅንጅት ቀጥሎ የግፍ ፍርድ ሲበየንበት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት እንደሆነ ስተነዉም አይደለም፡፡ ዱባና ቅል አበቃቀሉ ለየቅል የሚለዉ ብሂል እንዳለ ሆኖ ብርቱኳን መደቅሳ፤ዳኛ ፍረህይወት እና ሌሎች (ለህሊናቸዉ የተገዙ ዳኞች አልፎ አልፎም ቢሆን) የተገኙት በዚህ አፋኝ ስርኣት በዘረጋዉ መዋቅርና በህዝባችን ዘንድ እምነት በታጣባቸዉት የፍትህ ተቀዋማት ውስጥ ነዉ፡፡ታድያ እየተፈተኑ የሚወድቁትን ተቋማት ሳይሆን ግለሰብ ዳኞችንም ለመፈተን ይህን ታሪካዊ ክስ ስናቀርብ የግለሰቦችን የህሊና ዳኝነትንም ተስፋ ባለመቁረጥ ጭምር ይሆናል፡፡ ሁሌም እንደምንለዉ ፓርላማ ተቀምጦ የተከበሩ እየተባሉ ለመጠራት ሳይሆን ትግላችን ለለዉጥ ነዉና ድንክየዉን አንድነት ቢመለሱልንም ባይመሉሱልንም፤ የህዝብ ከሆነዉ ትግል መሃል ሆነን ፖለቲካዉን ከመስራት አንታቀብም፡፡ዉሳኔዉም በሁሉም የለዉጥ ሃይሎች ቀጣይ እንቅስቃሴ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡የአንድነት ልጆች ህወሓት ለመደዉ የጥባጥቤ ጨዋታዉ ቦታ ይኖረናል ተብሎ አይታሰብም፡፡አንድነታቸንን እንደ ጠበቅን የሚቀብሩት ከሆነ የአንድነት ፓርቲ “ቀብር” ላይ እንገናኝ፤ መቃብሩ ላይም እርም እናዉጣና የአንድነት ሃይሎች ዳብረን እንወጣ ዘንድ ትግሉ ግድ ይለናል!
ላለፉት አምስት አመታት ብዙዎቹ በእስር የሚማቅቁበት የተሰደዱለትና የቆሰሉ፤ የደሙለት ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የብዙ ወገኖችን እና ተቋማትን የፍትህ ጥያቄ በማዉሳት ባደባባይ የጮኸዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡በኢትዮጵያዊነት ማእቀፍ ዉስጥ የብሄረሰቦችን እና የቡድኖችን መሰረታዊ የፖለቲካ ጥያቄ ለመመለስ ቁርጠኝነት የነበረዉ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ የህዝብን ጥያቄዎች በጠራ መልኩ በማዉሳት ድምጻቸዉን ከሚያሰሙ ፓርቲዎች ዉስጥ ተጠቃሹ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡የቅርርብ፤የመደማመጥና የመከባበር ፖለቲካ እንዲኖር ባሳለፋቸዉ አጭር አመታት ጥረት ያደረገ ፓርቲ አንድነት ነዉ፡፡ በዚህም ከህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሃገራቸዉ በጎዉን ለዉጥ የሚሹ በርካታ የኢህኣዴግ ተራ አባላትና አንድንድ ባለስልጣናትም ጭምር በበጎ አይን ይመለከቱት እንደነበር ገምግመናል፡፡ በዚህ ወቅት አወንታዊ ተፅእኖ ያመጣል ተብሎ በመፈራቱ ግን ከ40 አመት በኃላም ትቂቱ የህወሓት ቡድን በለመደዉ ስልቱ በልቶታል፡፡
ይህን ድርጊት ለዉጥ ፈላጊ ሃይሎች በጥሞና ይከታተሉታል ተብሎ ይገመታል፡፡የምትችሉ ሁሉ ፍርድ ቤት በመገኘት እስከ ታሪካዊዉ ዉሳኔ እለት ድረስ ሂደቱን ለመዘገብና ለታሪክ ምስክር ለመሆን፤ እንዲሁም አጋርነታችሁን ለመግለፅ ትገኙ ዘንድ የክብር ጥሪ ተላልፏል፡፡እዉነተኛ አንድነት ነባር አመራር፤አባለትና ደጋፊዎች ጉዳዩን በአንድነት እንቋጭኛ እንደስማቸን በአንድነት ቦይ እንፈስ ዘንድ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡
አቶ ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)
አንድነት ፓርቲ በአንድ ወር ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ አስቸኳይ ልዩ ጠቅላላ ጉባዔ ጠራ
የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠራ፡፡ ፓርቲው ነገ እሁድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባኤ በድጋሚ እንዲጠራ የተገደደው ገለልተኛ እንዳልሆነ ተደጋጋሚ ቅሬታዎች የቀረቡበትና እየቀረቡበት ያለው ምርጫ ቦርድ ባደረገበት ጫና መሆኑን በመግለጫው አስታውቋል፡፡
በተለይ በአሁን ወቅት በርካታ አመራሮቹና አባሎች የታሰሩበት አንድነት ፓርቲ፤ የፊታችን ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በሚደረገው ምርጫ ላይ ለመሳተፍ መወሰኑን እና በመላ ሀገሪቱም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩ 450 ዕጩዎቹን ማዘጋጀቱንና ምርጫውንም በአሸናፊነት ለመወጣት ህዝቡን “2007 ለለውጥ ተደራጅ” በሚል መርህ ሰፊ ሀገራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡ ይህንንም ተከትሎ አንድነት ፓርቲ፣ ከኢህአዴግና ከምርጫ ቦርድ ጋር ባለው የፖለቲካ እንቅስቃሴ ከቀድሞ በበለጠ እየተካረረ መሄዱን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ አውጥቷል፡፡ የፓርቲውን ሙሉ መግለጫ ከታች ይመልከቱ፡-
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካዊ ደባ አንድነት ከመስመር አይወጣም!
*******************************************************************************
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
በየትኛውም የአለም ክፍል በተለያየ አጣራርና ስያሜ ቢሰጣቸውም ምርጫን ለማስፈፀም በሕግ የሚቋቋሙ ተቋማት ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ተቋማት በአንድ ሀገር ዘላቂ ለሆነ ሠላምና መረጋጋት ብሎም ለዴሞክራሲዊ ስርዓት ግንባታ ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ በአንባገነን ስርዓት ውስጥ ላሉ ሀገሮች ደግሞ ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ያላቸው ሚና ከምንም በላይ ከፍተኛ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራው ምርጫ ቦርድ ይህን የመሰለ ግዙፍ ተግባር እንዲያከናውን፣ የሕዝብ እና የሀገር አደራ እንዲወጣ ኃላፊነት የተሰጠው ተቋም ነው፡፡ የዚህ ተቋም አሰራር በተቋቋመለት ዓላማ፣ ሕግ እና አለም አቀፍ መስፈርት መሠረት ነፃ፣ ገለልተኛ፣ ዴሞክራሲያዊ እና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀደሙት አሠራሮችና ውሳኔ አሰጣጦች በበርካታ ኢትዮጵያውያን እና አለም አቀፍ ታዛቢዎች በአሉታዊ ጎኑ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) የ2ዐዐ7 ሀገር አቀፍ ምርጫን ‹‹የኢህአዴግ መጨረሻ›› እናደርገዋልን ብሎ ፖለቲካዊ አቋም ወስዶ እንቅስቃሴ ሲጀምር የምርጫ ቦርድን ቀደምት አሉታዊ ተግባሩን ዘንግቶ አይደለም፡፡ ይህ ተቋም መልካም ስም እንዲገነባ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር በመሆን እድል ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህ ስትራቴጂ መሠረት ቦርዱን በተግባር ፈተና ላይ ጥለነዋል፣ ማንነቱንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ለዓለም ማህበረሰብ በማጋለጥ ላይ እንገኛለን፣ ዛሬ ለሁለም የሚዲያ አካላት ያካሄድናቸውን የደብዳቤ ልውውጦች በይፋ አንሰጣለን፣ ሁሉም ዜጋ እንዲደርሰውም እናደርጋለን፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ከ2ዐዐ7 አጠቃላይ ምርጫ ገፍቶ ለማስወጣት ካልተሳካለትም በተዳከመ የአባላትና ደጋፊ ስሜት ውስጥ ገብተን እንድንጫወት የፈለገ ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ የአንድነት ፓርቲ በ2ዐዐ7 ዓም ሀገራዊ ምርጫ ከጅምሩ በሁሉም ሂደቶች በንቁ ለመሳተፍ የያዘው አቋም እንዳስደነገጠው፤ ከዚያም አልፎ ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠውን ስልጣን አጣለሁ በሚል መሸበሩን የሚያጋልጥ ነው፡፡ ይህን ፍርሃቱን በህዝብ ፊት በሚደረግ ትግል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ የመረጠው ሜዳ በብሔራዊ ምርጫ ቦርደ በኩል እንዲሆን ነው፡፡ የቦርዱ ኃላፊዎች ተቋማዊ በሆነ መልክ ደብዳቤ ሲሰጣቸው፣ በደብዳቤ መልስ ከመስጠት ይልቅ በመገናኛ ብዙሃን ምላሻቸውን ቀድመው መናገር ጀምረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያው ታህሣሥ 27 ቀን 2ዐዐ7 ዓም የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ የሆኑት ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዝአብሔር ከቦርዱ ስብሰባ በፊት በሚዲያ ወጥተው ውሳኔ በመገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ቦርዱ እንደተቋም ሳይሆን በግለሰብ ውሳኔ የሚመራ መሆኑን ነው፡፡ ለዚህም መገለጫው በታህሳስ 30/2007 የደረሰን ደብዳቤ የቦርዱን ምክትል ስብሳቢ ከሚዲያ መግለጫ ጋር ተመሳሳይ መሆኑ ነው፡፡ ከምርጫ ቦርድ ባልተናነሰ ሁኔታ በኢትዮጵያ በህግ የተቋቋሙት እና በህዝብ ሀብት የሚንቀሳቀሱት የመገናኛ ብዙሃንም በፍጥነት ተቀብለው ማስተጋባታቸው በውዥንብር ፈጠራ ላይ ተሳታፊነታቸውን ያሳያል፡፡ ዓላማው በአባላት፣ በደጋፊና በህዝቡ ውስጥ ውዥንብር ለመፍጠር ታሰቦ የሚካሄድ ፖለቲካዊ ደባ ነው፡፡
በሀገራችን አስተማማኝ ሠላም እና ዘላቂነት ያለው ደህንነት የሚያረጋግጠው እንደ ምርጫ ቦርድ ያሉ ተቋሞች ነፃ፣ ገለልተኛ እና በህዝብ ዘንድ አመኔታ ሲጣልባቸው ነው፡፡ ይህ ተቋም አሁን በያዘው ሁኔታ ከቀጠለ ከታሪክ ተጠያቂነት አይድንም፡፡ ገዢው ፓርቲም ጧት ማታ የሚያባንነው ሕዝባዊ እምቢተኝነት መምጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ በመሆኑም አሁን ፓርቲያችንን ለመታደግ እና የቦርዱን የመጨረሻ ካርድ ለማስጣል አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ለ2ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ጠርተናል፡፡ ይህ ማለት የትግሉ መጨረሻ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያደረሰብንን የሕግ ጥሰት ይዘን በፍርድ ቤት ክስ እንመሰርታለን፡፡ እስከ አሁን ያለውን ሂደት ስናየው የቦርዱ ፖለቲካዊ ደባ ቀጣይ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ስለሆነም መላው አባሎቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ለምንወስዳቸው ተከታታይ ፖለቲካው ውሳኔዎች እና እርምጃዎች ከጎናችን እንዲቆም ጥሪያችንን በአክብሮት እናስተላልፋለን፡፡
ድል የሕዝብ ነው
ጥር 1 ቀን 2ዐዐ7 ዓም
አዲስ አበባ
የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ለአዳሩ ሰልፍ የእውቅና ደብዳቤ አስገባ
- ቦታው መስቀል አደባባይ እንዲሆን ወስኗል
የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ከህዳር 27/2007 ዓ.ም እስከ ህዳር 28/2007 ዓ.ም ለሚደረገው የአዳር ሰላማዊ ሰልፍ ዛሬ ህዳር 18/2007 ዓ.ም ለአዲስ አበባ አስተዳደር የሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ክፍል የእውቅና ደብዳቤ አስገባ፡፡
ለሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ክፍል የገባው ደብዳቤ በሰማያዊ፣ መኢዴፓ እና ኢብአፓ ተፈርሞ የገባ ሲሆን የእውቅና ደብዳቤውንም ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የሰማያዊ ፓርቲና የትብብሩ ሊቀመንበር፣ የከንባታ ህዝቦች ሊቀመንበርና የትብብብሩ ም/ሊቀመንበር አቶ ኤርጫፎ ኤርጌሎ፣ አቶ ግርማ በቀለ ከኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅትና የትብብሩ ፀኃፊ እና የመኢዴፓ ሊቀመንበርና የትብብሩ ገንዘብ ያዥ አቶ ኑሪ ሙደሲር አስገብተዋል፡፡የትብብሩ አመራሮች ወደ ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ ማሳወቂያ ክፍሉ በሄዱበት ወቅት የአቶ ማርቆስ ተወካይ ለሆኑት አቶ ፈለቀ አበበ ደብዳቤውን ለመስጠት ጥረት ቢያደርጉም ተወካዩ ‹‹የከንቲባ ጉዳዮች ጽ/ቤ ኃላፊ አቶ አሰግድ ጌታቸው የለም፡፡ እሱ ካልመራበት መቀበል አንችልም›› በሚል ደብዳቤውን አልቀበልም እንዳሏቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ አመራሮቹ ወደ አቶ አሰግድ ቢሮ ቢያቀኑም እንዳላገኙዋቸው ጨምረው ገልጸዋል፡፡
ሆኖም የትብብሩ አመራሮች ደብዳቤ መስጠት እንጂ ደብዳቤ ማስመራት የሰራተኞቹ እንጂ የእነሱ ስራ እንዳልሆነ በመግለጽ ደብዳቤውን ዛሬ ህዳር 18/2007 ዓ.ም ታመዋል የተባሉት የአቶ ማርቆስ ተወካይ የሆኑት አቶ ፈለቀ ቢሮ በአራት ምስክሮች ፊት አስቀምጠው መምጣታቸውን አስረድተዋል፡፡ አመራሮቹ የእውቅና ደብዳቤውን አቶ ፈለቀ ቢሮ አስቀምጠው ከመውጣታቸውም ባሻገር በኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት በፈጣን መልዕክት (ኢ ኤም ኤስ) በሪኮመንዴ ቁጥር eg157416502et መላካቸውን ገልጸዋል፡፡
የአዳር ሰላማዊ ሰልፉ ህዳር 27 ከጠዋቱ 3 ሰዓት ተጀምሮ ህዳር 28 ከቀኑ 6 ሰዓት ላይ እንደሚጠናቀቅ የሚጠበቅ ሲሆን ቦታውም መስቀል አደባባይ ላይ እንደሚሆን መወሰኑ ታውቋል፡፡
የትብብሩ አመራሮች የእውቅና ደብዳቤውን ለማስገባት በሄዱበት ወቅት በቦታው የትብብሩ አመራሮች የሚያውቋቸው ደህንነቶች ባለ ጉዳይ በመምሰል ይመላለሱ እንደነበርና ፖሊሶችም ይከታተሉ እንደነበር መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የአዲስ አበባ አስተዳደር ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል በሰማያዊ ፓርቲ ላይ እርምጃ እወስዳለሁ ማለቱ ተገለፀ
- “ማስጠንቀቂያውን እንደ ቁም ነገር አንቆጥረውም” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
• “ስርዓቱ ምን ያህል ዝቅጠት ውስጥ እንደገባ ያሳያል” አቶ ግርማ በቀለ
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ ያስተባበረው የ9ኙ ፓርቲዎች የአደባባይ ህዝባዊ ስብሰባ ፀረ ህገ መንግስት በመሆኑና ነዋሪዎችን ሰላምና ፀጥታ በማወኩ በቀጣይ ተመሳሳይ እንቅስቃሴ ካደረገ ለህዝብ ሰላምና ደህንነት ሲባል እርምጃ እወስዳለሁ ሲል አስጠነቀቀ፡፡
አስተዳደሩ ትናንት ህዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም በጻፈው ደብዳቤ፤ ህዳር 6 ቀን “ነጻነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚል በሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት ለህዝብ የተሰራጨው በራሪ ወረቀት ህገ ወጥ መሆኑን፣ ህዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም በኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መሪነት ሊደረግ የነበረው አደባባይ ስብሰባ ህገ ወጥ እንደነበርና በወቅቱ የስብሰባው ተሳታፊዎች ከፖሊስ ጋር ግብ ግብ ከመግጠማቸውም በተጨማሪ የአካባቢውን ህዝብ ሰላምና ፀጥታ አውከዋል ሲል ከሷል፡፡ አስተዳደሩ አክሎም ፓርቲው የአደባባይ ብጥብጥና ሁከት በመፍጠሩ እርምጃ እወስዳሉ ሲል ማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ልኳል፡፡
በሌላ በኩል ሰማያዊ ፓርቲ በቀን ህዳር 5 ቀን 2007 ዓ.ም ለአስተዳደሩ የእውቅና ደብዳቤ ያስገባ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን የሰማያዊ ፓርቲና የትብብሩ አመራሮች አስተዳደሩ የላከው ደብዳቤ ከገዥው ፓርቲ ፍርሃት የመነጨ በመሆኑ ከእንቅስቃሴያቸው እንደማይገታቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብርና የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ደብዳቤው ስርዓቱ የደረሰበትን መጠነ ሰፊ የፍርሃት ደረጃና ትግሉን ይበልጥ አጠናክረን መቀጠል እንዳለብን የሚያሳይ ነው ሲሉ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
ማስጠንቀቂው የደረሰው ሰማያዊ ፓርቲና የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ‹‹የረዥም ጊዜ የመንግስት ታሪክ ባላት አገር የከተማ አስተዳደር ነኝ ያለ አካል እንዲህ አይነት ደብዳቤ መጻፉ ኢትዮጵያ ምን ያህል ውድቀት እንደገጠማትና እኛም እንደ ህዝብ የውርደት ካባ መከናነባችንን በግልጽ የሚያሳይ ነው፡፡ እንደ ሰማያዊ አሊያም የትብብሩ ሊቀመንበርነት ሳይሆን እንደ አንድ ይህን ያህል ውርደት እንደገጠማት አገር ዜጋ ሀፍረት ይሰማኛል፡፡›› ሲሉ አስተዳደሩ የላከው ደብዳቤ ላይ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ማስጠንቀቂያው በቀጣይ የፓርቲውም ሆነ የትብብሩ እንቅስቃሴ ላይ የሚያመጣው ችግር ካለ በሚል ለኢንጅነር ይልቃል ላነሳነላቸው ጥያቄም ‹‹ደብዳቤው የኢህአዴግ ፍርሃት ገደብ መልቀቁንና ትግሉም ይበልጥ መጠናከር እንዳለበት የሚያሳይ ነው፡፡ ኢህአዴግ ሰላማዊ ህዝባዊ እንቅስቃሴን ብቻ ሳይሆን የራሱን ጥላም አለማመን ደረጃ ላይ መድረሱን ያሳያል፡፡ እኛ ይህን የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ እንደቁም ነገር አንቆጥረውም፡፡ ይበልጡንም ለትግሉ በተጠናከረ መንገድ እንድንነሳሳ ይገፋፋናል›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ የትብብሩ ፀሐፊና የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ግርማ በቀለ ‹‹ማስጠንቀቂያው ትብብሩ በየሳምንቱ ያቀዳቸውን መርሃ ግብሮች ለማደናቀፍ ያለመ ነው፡፡ ከአንድ የመንግስት መስሪያ ቤት እንዲህ አይነት አሳፋሪ ደብዳቤ መጻፉ ስርዓቱ ምን ያህል ዝግጠት ውስጥ እንደገባ ያሳያል፡፡ ሆኖም ማስጠንቀቂያው ከእንቅስቃሴያችን አይገታንም፡፡ እንዲያውም ለዚህ የስርዓቱ ዝቅጠት የሚመጥን ስልት ነድፈን በጋራ እንድንሰራ ያደርገናል፡፡›› ማለታቸውን የነገረ ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡



