Tag Archives: National Electoral Board of Ethiopia

በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ በከፍተኛ ደረጃ ለተቃዋሚዎች ድጋፍ እየሰጠ መሆኑን ተከትሎ ገዥው ፓርቲ ኦህዴድ/ኢህአዴግ ምርጫውን ከወዲሁ ማስጀመሩ ተገለፀ

ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ገዥው ፓርቲ ምርጫውን ከአሁኑ እንደጀመረው ምንጮች ገለፁ፡፡ በተለያዩ የኦሮሚያ ክፍሎች የገዥው ኢህአዴግ ካድሬዎች መራጮችን በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ እያደራጁ “ኦህዴድ/ኢህአዴግን መርጫለሁ” በሚል እያስፈረሙና ፎርም እያስሞሉ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ ተደራጅተው ‹‹ኦህዴድን መርጠናል›› ብለው እንዲፈርሙ የተደረጉ ዜጎች ፎርሙን ከሞሉበት ቀን ጀምሮ የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ መሪዎቻቸው እንደሚሰጡ ታውቋል፡፡ የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ መሪዎችም ኢህአዴግን ከአሁኑ መርጠዋል ተብለው የተደራጁ ዜጎችን ስምና የምርጫ ካርድም ለኦህዴድ/ኢህአዴግ ከፍተኛ ካድሬዎች እንደሚሰጡ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

OFC_MEDREK

የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ግንቦት 16 ቀን በፊት የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ለሴልና ለኔትወርክ መሪዎች የሚሰጡትን ዜጎች ቤት ለቤት እየዞሩ እያስፈረሙ እንደሚገኙ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ በጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ ተደራጅተው ኦህዴድ/ኢህአዴግን ከአሁኑ እንደመረጡ በፊርማቸው አረጋግጠዋል የተባሉት ዜጎች ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም በሚደረገው ምርጫ እንደማይሳተፉ የታወቀ ሲሆን አብዛኛዎቹ በግዳጅና በማስፈራሪያ እየሞሉ እንደሚገኙ ተገልጾአል፡፡

የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ እንዲሁም የመራጮች ስምና ፊርማቸው እየሰፈረበት ከግንቦት 16 በፊት እንደመረጡ ተደርጎ ዜጎች እንዲሞሉት የሚደረገውና ከስር የሚታየው ቅጽ ካድሬዎች በአርሲ ዞን በቆጅ ወረዳ ቤት ለቤት ሲያስሞሉ መገኘቱ ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይም በምዕራብ ኢትዮጵያ እዚሁ ኦሮሚያ ክልል ተመሳሳይ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዶ/ር መረራ ጉዲና የሚመራው ቡድን በአካባቢው የተጠናከረ የምርጫ ቅስቀሳ በማድረጋቸውና ኦፌኮ/መድረክ በአካባቢው ህዝብ ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘቱን ተከትሎ የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ከአካባቢው የፀጥታ ኃይል ጋር በመሆን የተቃዋሚ ደጋፊዎችና የአካባቢው እጮዎች ጭምር ድብደባና እስራት እየፈፀመባቸው መሆኑን ምንጮችን ጠቅሶ ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል ፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ መንግስት የከፈተበትን የጥላቻ ዘመቻ በአስቸኳይ እንዲያቆም አሳሰበ

መንግስት ሊቢያ ውስጥ ኢትዮጵያውያን ላይ አሰቃቂ እርምጃ የወሰደውን አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም ራሱ በጠራው ሰልፍ ላይ ከህዝብ የገጠመውን ተቃውሞ ተከትሎ ሰማያዊ ላይ የጥላቻ ዘመቻ እንደከፈተበትና ይህንን የጥላቻ ዘመቻውን እንዲያቆም ሰማያዊ ፓርቲ በሰጠው መግለጫ አሳስቧል፡፡
መንግስት የጠራውን ሰልፍ ከማንም ተቃዋሚ ፓርቲ ቀድሞ የደገፈው ሰማያዊ እንደሆነ የገለጸው መግለጫው “የዜጎችን ስቃይ ለፖለቲካ ፍጆታ ማዋል የፈለገው ህወሓት/ኢህአዴግ ሰማያዊ ፓርቲ በወገኖቻችን ላይ ለሚደርሰው በደል መፍትሄ እንዲሰጥ መወትወቱ፣ የፖለቲካ ልዩነታችንን ወደ ጎን አድርገን በሰልፉ ላይ መገኘታችን እንዳላስደሰተው ከሰልፉ ቀን ጀምሮ በፓርቲያችን ላይ የተከፈተው ዘመቻ ትልቅ ማሳያ ነው፡፡” ብሏል፡፡
ከሰልፉ ማብቃት ጀምሮም ጉዳዩን ገና ፖሊስ ሳይመረምረው የመንግስት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ሚኒስትር ሬድዋን ሁሴን ሰማያዊ ፓርቲ ሁከትና ብጥብጥ ለማስነሳት እየጣረ ነው በሚል መወንጀላቸውን፣ የመንግስት ሚዲያዎች ሰማያዊ ፓርቲ ሁከትና ብጥብጥ ሊያስነሳ ነው ብለው ሚዛናዊ ያልሆነ መረጃ ማሰራጨታቸውንና አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም ተብለው በተጠሩ ሰልፎችም ሁሉ መንግስት ሰማያዊ ፓርቲ ለመቃወም እየተጠቀመባቸው መሆኑን መግለጫው አትቷል፡፡
በተጨማሪም በሰልፉ ዕለት የሰማያዊ አባላት ገና ሰልፉ ሳይጀመርና መስቀል አደባባይ ሳይደርሱ እንዲሁም ሰልፉ ካበቃ በኋላ እየታደኑ ሲታሰሩ መስቀል አደባባይ ላይ የተያዙት የኢህአዴግ አባላት ከቀበሌ ደብዳቤ እያመጡ መፈታታቸው መንግስት ሰማያዊን በሀሰት ለመወንጀል መነሳቱን ያሳያል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል 6 ያህል የሰማያዊ አባላት በታሰሩበት ሁኔታ መንግስት 7 አመራሮችና 20 ያህል አባላት ታስረዋል ማለቱ ትክክል አለመሆኑንና ከመጀመሪያውም 6 አባላቱ የታሰሩበት መንገድና አሁንም በሰማያዊ ላይ የሚቀርበው ክስ መሰረተ ቢስ ነው ብሎታል፡፡

Semayawi party

“ይህ በህወሓት/ኢህአዴግ መንግስት አማካኝነት እየቀረበ ያለው ክስ እና የሀሰት ፕሮፓጋንዳ ህወሓት/ኢህአዴግ ለዜጎች ህይወት የማይጨነቅ እና በዜጎች ሞት የራሱን የፖለቲካ ትርፍ ለማጋበስ እና ጠንካራ ተቃዋሚ የሆነውን ሰማያዊ ፓርቲን ለማጥቃት እየተጠቀመበት መሆኑን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው፡፡” ሲልም የመንግስትን ተግባር ተቃውሟል፡፡ በፍርድ ቤት ውሳኔ ያልተሰጠበትን ጉዳይ ተጠርጣሪ ከማለት ይልቅ ወንጀለኞች ናቸው በማለት በህገወጥ ስራ እንደተሰማራ ያሳያል ሲልም ወቅሷል፡፡

“መንግስት እና የመንግስት መገናኛ ብዙኃን ከዚህ አኩይ ተግባራቸው የማይታቀቡ ከሆነ፣ የሰማያዊን ስም በሀሰት በማጠልሸት ስራ ላይ የተሰማሩ የመንግስት ተቋማትን እና ግለሰቦችን በህግ ፊት ለማቆም ይገደዳል” ያለው መግለጫው ሌሎች ተከታታይነት ያላቸውን እርምጃዎችም እንደሚወስድና መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሰማያዊ ፓርቲ ለሚያደርጋቸው ህዝባዊ ጥሪዎች በንቃት ተዘጋጅቶ እንዲጠብቅ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

በሀዲያ ዞን በምርጫ 2007 ዓ.ም. ቅስቀሳ ምክንያት የሁለት ሰዎች ህይወት አለፈ

በደቡብ ክልል በሀድያ ዞን ሶሮ ወረዳ ጊምቢቹ ከተማ በህዝብና በራሱ ላይ በሚፈፀመው አስተዳደራዊ በደል የተማረረውና በተደጋጋሚ በሚፈፀሙት አስተዳደራዊ በደሎች ላይ ቅሬታ አቅርቦ መፍትሄ ያላገኘው የአካባቢው የ2007 ዓ.ም. ምርጫ የመድረክ ዕጩ የነበረው መምህር ጌታቸው አብርሃም ሚያዝያ 17 ቀን 2007ዓ.ም በጊምቢቹ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ግቢ ውስጥ ራሱን ያቃጠለ ሲሆን በሆሳዕና ሆስፒታል ህክምና ሲደረግለት ቢቆይም ህይወቱ እንዳለፈች ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

ቡሬ ለንጌ ትምህርትር ቤት የሲቪክስ መምህር የነበረው መምህር ጌታቸው በአካባቢው ባለው የከፋፍለህ ግዛና የጎሳ ፖለቲካ ተጠቂ ከመሆኑም ባሻገር በህዝብና በእሱ ላይ የሚደርሰውን በደል በመቃወም መፍትሄ እንዲሰጥ ለባለስልጣናት ሲያሳውቅ መቆየቱን፣ ሆኖም ህዝቡ እና በራሱ ላይ የሚፈፀምበት በደል በመባባሱና መፍትሄ ማግኘት ባለመቻሉ አስተዳደሩ ግቢ ውስጥ ራሱን ማቃጠሉ ታውቋል፡፡
መምህር ጌታቸው ራሱና ህዝብ ላይ የሚደርሰውን በደል በመቃወም በከተማው አስተዳደር ምክር ቤት ግቢ ውስጥ ራሱ ላይ ጋዝ በማርከፍከፍ ራሱን ባቃጠለበት ወቅት ግቢው ውስጥ የነበሩት ሰዎች ደርሰው እሳቱን በማጥፋታቸው ህይወቱን ለማዳን ጥረት አድርገው የነበር ቢሆንም የደረሰበት ጉዳት ከፍተኛ ስለነበር ህይወቱ አልፏል፡፡

Hossana hospital

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛው በሀድያ ዞን አምቡላንሶች ለምርጫ ቅስቀሳ እየዋሉ በመሆኑ ህመምተኞች በተለይም ነፍሰ ጡር እናቶች ህክምና ሳያገኙ ለሞት እንደሚዳረጉ ነዋሪዎቹ ገለፁ፡፡ ሚያዝያ 20 ቀን 2007 ዓ.ም አንዲት ምጥ የተያዙ እናት በአቅራቢያቸው በሚገኝ የጎምበራ የጤና ጣቢያ በሄዱበት ወቅት ‹‹ከአቅማችን በላይ ነው!›› ተብለው ወደ ሆሳዕና ሪፈራል ሆስፒታል ሄደው እንዲታከሙ ሪፈር ቢፃፍላቸውም በትራንስፖርት ችግር ነፍሳቸው አልፋለች፡፡

ለጤና ጣቢያው የተመደበችው አምቡላንስ በጎምበራ ወረዳ ኦሌ ቀበሌ ለገዥው ደኢህዴን/ኢህአዴግ ፓርቲ የምርጫ ቅስቀሳ በመውጣቷ ቤተሰብ ነፍሰጡሯን ከጎምበራ ክሊኒክ ወደ ሆሳዕና ሪፈራል ሆስፒታል በቃሬዛ ለመውሰድ መገደዳቸውን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአካባቢው ነዋሪዎች ወደ ሆሳዕና ሆስፒታል በቶሎ መድረስ ባለመቻላቸው የነፍሰ ጡሯ ህይወት መንገድ ላይ ሊያልፍ ችሏል፡፡
ነዋሪዎቹ እንደገለጹት ከሆነ አምቡላንሶች ለምርጫ ቅስቀሳ በመዋላቸው ምክንያት በርካታ ህመምተኞች በተለይም እናቶችና ህፃናት በቶሎ ወደ ሆስፒታል መድረስ ባለመቻላቸው ተመሳሳይ ችግር እየገጠማቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ በምርጫ 2002 ዓ.ም ወቅትም በተመሳሳይ መልኩ በዚሁ በሀዲያ ዞን አምቡላንሶች ለኢህአዴግ ምርጫ ቅስቀሳ ወጥተው ነፍሰ ጡር እናቶች ህይወታቸው ማለፉ አይዘነጋም፡፡

መንግሥት ራሱ በጠራው ሰልፍ በርካታ ሰዎችን ሲደበድብ፤ ከመቶ በላይ ሰዎች ታስረዋል

ሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መንግሥት በሊቢያ፣በደቡብ አፍሪካና በየመን ኢትዮጵያውያን በግፍ መገደላቸውን በተመለከተ በአዲስ አበባ ድርጊቱን ለማውገዝና ለመቃም ሰልፍ ጠርቶ የነበረ ቢሆንም፤ በሰልፍ የተገኙ በርካታ ሰዎች በፖሊስ ተደብድበው ወደ አካባቢው ሆስፒታሎች የተወሰዱ ሲሆን፤ ከ100 በላይ ሰዎች መታሰራቸውንም አልጀዚራን ጨምሮ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ከስፍራው በቀጥታ ዘግበዋል፡፡ በተለይ በአሸባሪው በ አይ ኤስ አይ ኤል (ISIL) ቢያንስ 28 ኢትዮጵያውያን በጭካኔ መገደላቸውና መንግሥትም ለዚህ ያሳየው ቸልተንነት ህዝቡን የበለጠ በማስቆጣቱ ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ያለማንም ቀስቃሽ የአዲስ አበባ ነዋሪ ለተቃውሞ ሰልፍ ቢወጣም መንግሥት ፈቃድ አልሰጠሁም በሚል በርካቶች ከደበደበ በኋላ ለሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. ራሱ ድርጊቱን በመቃወም ሰልፍ ቢጠራም መጨረሻው በፖሊስ ከፍተኛ ድብደባና እስር ተጠናቋል፡፡ ሰልፉ ከመጀመሩ በፊት የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶችን ጨምሮ በርካታ ወጣቶች ወደሰልፉ ሲሄዱ የታሰሩ ሲሆን፤ ከሰልፉ በኋላ የመንግሥት ባለሰልጣናት መስቀል አደባባይ ንግግር ሲያደርጊ ህዝቡ በልቅሶ ተቃውሞ ካሰማ በኋላ የአዲስ አበባ እና የፌደራል ፖሊስ እዛው ሰልፉ ቦታ ሲደበድብ ታይቷል፡፡ ይሄንንም የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን በቀጥታ አሰራጭተዋል፡፡

ዓለም አቀፍ አሸባሪው ቡድን ISIL በሊቢያ የገደልኩት ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን ቢልም፤ በአዲስ አበባው ተቃውሞ የእስልምና እና የክርስትና ኃይማኖት ተከታዮች በጋራ ድርጊቱን ሲያወግዙ ተስተውሏል፡፡ በዕለቱም በርካታ መፈክሮች የተሰሙ ሲሆን፤

ታርዷል ወገኔ፣ ታርዷል ወገኔ…(በኡኡታና ልቅሶ)

ሽብርን እንቃወማለን፣እናወግዛለን

መንግሥት ኃላፊነቱን አልተወጣም

ሞት ለወያኔ፤ ያረደንም ያሳረደንም ወያኔ ነው

ይለያል ዘንድሮ የዌኔ ኑሮ

ውሸት ሰለቸን፤ የወንድሞቻችን ደም ይመለስ

የሀገር ውስጥ ISIL ወያኔ ነው፤…በቃን

ISIL እስልምናን አይወክልም፤ እኛ የኢትዮጵያውያ ሙስሊሞች ወንድሞቻችን ክርስቲያኖች በአሸባሪ ቡድኑ መገደላቸውን አጥብቀን እናወግዛለን፤ ድርግቱም ሽብር እንጂ እስልምናን አይወክልም (በተለይ በሰልፉ የተገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች)

መንግሠት የሌለው እዚህ ብቻ ነው

የኢትዮጵ አምላክ ይፍረድ (በተለይ የሟቾቹ ቤተሰቦች)

ና ና መንጌ ና ና (የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት መንግሥቱ ኃይለማርያምን)

የቤት አንበሳ የውጭ እሬሳ (መንግሥትን) የሚሉ መፈክሮች ይገኙበታል፡፡

pretest victims2

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል

በመጨረሻም በመንግሥት ላይ የህዝቡ ተቃውሞ ተጠናክሮ ሲቀጥል የመንግሥት ባለስልጣናት ንግግር በቅጡ ሳይሰማ የተቋረጠ ሲሆን፤ ፖሊስም ወዲያውኑ ያገኘውን ሁሉ እያሳደደ ሲደበድብ ለማየት ተችሏል፡፡ በቂርቆስ ሰፈር ልቅሶ ቤት አካባቢ በነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻ በስፍራው እጅግ በርካታ ፖሊሶች በስፍራው የነመበሩ ሲሆን፤ በኋላም ከፍተኛ የመሳሪያ ተኩስ ተሰምቷል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በተተኮሰው ጥይት በሰው ህይወትና አካል ላይ ጉዳት ስለማደረሱ የተረጋገጠ መረጃ ባይኖርም መስቀል አደባባይ በነበረው የፖሊስ ድብደባ ራሳቸውን ስተው የወደቁ ሴቶች፣እናቶችና ወጣቶች የታዩ ሲሆን፤ ብዙ ወጣቶች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በአምቡላንስ እና በሰው እግዛ ወደ ህክምና ጣቢያ ሲሄዱና የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ታይቷል፡፡

protest 2

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል የተወሰኑት የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው

በሰልፉ ላይ በፖሊስ ከተጎዱት መካከል የተወሰኑት የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው

መንግሥትም በተመሳሳይ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የሽብር ድርጊቱን በመቃወም በመዋቅሩ ሰልፍ ማዘጋጀቱና ለዚህም የኢህአዴግ ሊግና ፎረነም አባላት ከየቀበሌው በነበረው መዋቅር ወደሰልፍ እንዲወጡ፣ ሌላ ወደተቃውሞው ሰልፍ የሚመጣ ካለ በደንብ ከበው እንዲከታተሉት፣ መፈክሮችም በኢህአዴግ ብቻ እንዲዘጋጅ ከዛ ውጭ ያለ መፈክር ይዞ የሚመጣ ማንኛውም አካል ካለ ወደሰልፉ መሐል ከመቀላቀሉ በፊት ጥብቅ ምርመራ መደረግ እንዳለበት ትዕዛዝ መሰጠቱንም ምንጮች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡

በተለይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ቀደም ሲል የሽብር ድርጊቱን በማውገዝ መንግሥት እርምጃ እንደሚወስድ በፌስ ቡክ ግድግዳቸው ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቢናገሩም፤ በመጨረሻም አሸባሪው ድርጅት ላይ በመንግሥት እርምጃ ይወሰዳል ተብሎ ሲጠበቅ፤ በአዲስ አበባ ሰልፈኛ ላይ እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡ መንግሥት በበኩሉ እርምጃ የተወሰደው ፖሊሶች ላይ ድንጋይ ስለተወረወረ ነው የሚል ምክንያት ሰጥቷል፡፡

በተለይ በሊቢያ የሟቾች ማንነት እየተለየ ሲሆን፤ ስማቸውም ኢያሱ ይኮኖአምላክ፣ ባልቻ በለጠ፣ ብሩክ ካሳ፣ በቀለ ታጠቅ እና ኤልያስ ተጫኔ ከአዲስ አበባ ቂርቆስ ሰፈር፤ መንግሥቱ ጋሼ እና አወቀ ገመቹ ከወለጋ ነቀምት፣ በቀለ አርሰማ ከጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ ካራቻ አካባቢ፣ የጅማ ዩኒቨርስቲ ምሩቅ የነበረው ዳንኤል ሓዱሽ፣ አለም ተስፋይ እና ዳዊት ሀድጉ ከትግራይ መቀሌ አካባቢ፣  ክርስቲያን ወንድሞቼን ለይታችሁ አትገድሉም፤ በእስልምና የሰውን ህይወት ማጥፋት ኃጥትም ወንጀልም ነው፣ እኔ ከእነሱ አልለይም በማለት ሲከራከር የነበረው ኢትዮጵዊው ሙስሊም ጀማል ረህማንም አብሮ መገደሉ ታውቋል፡፡ በአሸባሪው ቡድን ከተገደሉ ኢትዮጵያውያን ጋር  ተስፋይ ኪዳኔን ጨምሮ ሶስት ኤርትራውያንም እንደሚገኙበት የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ ተስፋይ ከዚህ በፊት በእስራኤል ጥገኝነት ጠይቆ በመከልከሉ በሊቢያ ወደ አውሮፓ ለመሄድ ሲሞክር በአሸባሪ ቡድኑ እጅ መግባቱ ተጠቁሟል፡፡

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ 28 ቀን ቀጠሮ ተጠየቀባቸው

ከግራ ወደቀኝ  ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

ከግራ ወደቀኝ ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድና ኢየሩሳሌም ተስፋው

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችና አባላት የሆኑት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረማሪያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ትናንት መጋቢት 21 አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው 28 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ፖሊስ እነ ብርሃኑ ተክለያሬድን ‹‹ለግንቦት 7 አባላትን መልምለው ወደ ኤርትራ በመላክና ቡድኑን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ተይዘዋል›› ብሏል፡፡

ጠበቃው እነ ብርሃኑ ተ/ክለያሬድ ለግንቦት ሰባት ሲመለምሉም ሆነ አባል ሲሆኑ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ እንደሌለ በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ፖሊስ ‹‹ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምመረምራቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ ሌሎች የምንይዛቸው ግብረ አበሮችም አሉ፡፡ መረጃ ያጠፉብናል፡፡›› በሚል ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቆ 28 ቀን ተፈቅዶለታል፡፡ ሚያዚያ 19 ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡

ፖሊስ ሌሎች ሰዎች ይዘውት የተነሱትን መሳሪያ በማሳየትም እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት ሰባትን ሊቀላቀሉ እንደነበር ለማሳየት በመረጃነት አቅርቧል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹የማህበራዊ ሚዲያ ላይ ምርመራ ለማድረግና መረጃዎችን ለማሰባሰብ ተጠርጣዎቹን ማሰር ተገቢ አልነበረም፡፡ ሌሎች ሰዎች የያዙትን መረጃ እነሱን ለመክሰስ መጠቀም ተገቢ አይደለም፡፡›› ሲሉ ተቃውመዋል፡፡

በሌላ በኩል ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ የታሰረበት ቤት መብራት ስለማይጠፋ አይኑ ላይ ለከፍተኛ ችግር እንዳደረሰበት ቅሬታ አቅርቧል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ለ15 ደቂቃ ፀኃይ እንዲሞቁ ከሚፈቀድላቸው ውጭ ወደ ከታሰሩበት ቤት ውጭ መውጣት እንደማይፈቀድላቸውና ቤተሰቦቻቸውም እንዲጠይቋቸው እየተደረገ አለመሆኑን በቅሬታ አቅርበዋል፡፡