የጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮቹ አቤቱታዎች ውድቅ ተደረጉ
በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው የሚገኙት የዞን ዘጠኝ ጦማርያንና ሦስቱ ወዳጅ ጋዜጠኞች መጋቢት 15 ቀን 2007 ዓ.ም ከሰዓት 8፡00 የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡
መዝገቡ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሾች ባቀረቧቸው ሁለት አቤቱታዎች ላይ ፍርድ ቤቱ መርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር፡፡ በዚህም አንደኛ አቃቤ ህግ በተከሳሾች ላይ አለኝ ካለው ማስረጃ ዝርዝር ውስጥ 12 የኦዲዮ-ቪዲዮ ሲዲዎች አያይዞ ያቀረበ ቢሆንም፣ ሲዲዎቹ ለተከሳሾች እስካሁን ባለመድረሳቸው ተከሳሾች የቀረበባቸውን ማስረጃ ተመልክተው መልስ ለማዘጋጀት ሲዲዎቹ እንዲሰጧቸው ያቀረቡት አቤቱታ ሲሆን፣ ሁለተኛው ጉዳይ ደግሞ 4ኛ ተከሳሽ ማህሌት ፋንታሁን እና 9ኛ ተከሳሽ ኤዶም ካሳዬ በቃሊቲ እስር ቤት አስተዳደር ላይ ከጎብኝዎቻቸው መከልከል ጋር በተያያዘ አቅርበውት በነበረው አቤቱታ ላይ ብይን መስጠት ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱም ሁለቱንም አቤቱታዎች ውድቅ አድርጓል፡፡
የሲዲ ማስረጃውን በተመለከተ አቃቤ ህግ ማስረጃዎችን ኢግዚቪት ብሎ ስላስመዘገበ አሁን በዚህ ደረጃ ሲዲዎቹ ለተከሳሾች የሚደርሱበት አግባብ የለም በሚል ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን አቤቱታ እንዳልተቀበለው ገልፀዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሾች ማስረጃ በመስማት ሂደት ወቅት ማስረጃዎችን እየተመለከቱ መልስ እንዲሰጡ እንጂ ቀድሞ እጃቸው የሚደርስበት አሰራር የለም ብሏል ፍርድ ቤቱ፡፡
ፍርድ ቤቱ የቃሊቲ እስር ቤት አስተዳደር ላይ በሁለቱ ሴት ተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታም ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ እና የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰጠውን መልስ መመልከቱን የገለጸው ፍርድ ቤቱ፣ “ለቀረበው አቤቱታ ማስረጃ ተያይዞ ያልቀረበ በመሆኑ…” በሚል አቤቱታውን ቅድቅ አድርጓል፡፡ ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች ከሰኞ መጋቢት 21 ቀን 2007 ጀምሮ ለሦሰት ቀናት ይሰማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
“ተወይኖብኛል… በዶ/ር አድማሱ ፀጋዬ ተልዕኮ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተባርሬአለሁ”
ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ከሦስት አሥርት ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ በሚሌኒየሙ መባቻ ወደ አገራቸው ተመልሰው ላለፉት ሰባት ዓመታት በማስተማር ሥራ ላይ ቆይተዋል፡፡ ምሁሩ በዋናነት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና መምህር ቢኾኑም በሕግ ፋክልቲ፣ በሴንተር ፎር ሂዩማን ራይትስ፣ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም፣ በአምስት ኪሎ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፋክልቲ፣ በቴአትሪካል አርትስና በያሬድ የሙዚቃ ት/ቤትም አስተምረዋል፡፡ ለሰባት ተከታታይ ዓመታት በተጠቀሱት የትምህርት መስኮች በተለያየ ጊዜ ሲያስተምሩ ቢቆዩም ከጠየቁት የዓመት ዕረፍት (sabbatical leave) ጋር ተያይዞ ከዩኒቨርስቲው መሰናበታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲስ አድማስ ጋዜጣ በጉዳዩ ዙሪያ ከዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጋር ተከታዩን አጭር ቃለምልልስ አድርጓል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እና በእርስዎ መካከል ምንድን ነው የተፈጠረው?
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደር ጋር በኹለት ጥያቄዎች ዙሪያ የማይታረቅ ልዩነት ተፈጥሯል፡፡ በመጀመሪያ የዩኒቨርስቲው የሴኔት ሕግና የቅጥር ውሌ ላይ በግልጽ እንደሰፈረው÷ አንድ መምህር ለስድስት ዓመት በተከታታይ ከአስተማረ፣ ለአገለገለበት ዘመን የአንድ ዓመት የጥናትና ምርምር ዕረፍት (sabbatical leave) እንደሚሰጠው ተደንግጓል፡፡ ኾኖም ግን ዩኒቨርስቲው ‹‹የጡረታ ሥርዓተ – ሒደቱን አላሟላኽም›› በሚል በሕጉ ፊት የማይጸና ሰበብ ፈጥረው ይገባኻል ብለው ከፈቀዱልኝ በኋላ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ለማንኛውም መምህር ሥርዓተ ሒደቱን የማስፈጸም ሓላፊነት የሰው ሀብት አስተዳደሩ ድርሻ ኾኖ ሳለ፣ እኔን ተጠያቂ ማድረጋቸው ብዙዎችን አስገርሟል::
በነገራችን ላይ የጥናት ዕረፍት ፈቃዴን የጠየቅኹት ከሦስት ዓመት በፊት፣ ስድሳ ዓመት ሳይሞላኝ ነበር፡፡ በየሰበቡ ሲጓተት ስለቆየ ወደ ስድሳ ዓመቱ ገደብ ደረስኹ፡፡ ጉዳዩ ወደ ማኅበራዊ ፍርድ ቤት ከመሔዱ አስቀድሞ ውስጣዊ ተቋማዊ መፍትሔ ለማበጀት ወደ ዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ ቀርቦ ምላሽ ስጠባበቅ ከሦስት ወራት በላይ ተቆጥረዋል፡፡
የሥራ ውሌን በተመለከተ፣ የፍልስፍና ትምህርት ክፍል የእኔን የአገልግሎት ቆይታ እንደሚፈልግና በተለይም በቅርቡ ለሚጀምረው የሦስተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ተሳትፎዬ እንደሚጠቅም በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ በመወሰኑ ውሌ እንዲራዘም ለማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ አካዳሚክ ኮሚሽን ጽፎልኝ ነበር፡፡ የማኅበራዊ ሳይንስ ትምህርት ክፍል ሓላፊዎች በተሰበሰቡበት፣ ኮሚሽኑ ጉዳዩን በአጀንዳ ይዞ ከተወያየበት በኋላ የፍልስፍና ትምህርት ክፍሉን ጥያቄ ዳግመኛ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶበት፣ ውሳኔው በማኅበራዊ ሳይንስ ኮሌጅ ዲኑ በፕ/ር ወልደ አምላክ በዕውቀት በኩል የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት ይኹንታቸውን እንዲሰጡበት(እንዲያጸድቁት) ተጠይቆ ነበር፡፡ ፕሬዝዳንቱ ግን ከአራት ወራት ያኽል ቸልተኝነት በኋላ ‹‹ወረቀቱ ይመጣለታል›› በሚል ለተከታዩ ሴሚስተር እንዳልደለደል በአዲሱ ዲን በኩል ለትምህርት ክፍሉ ሊቀ መንበር መመሪያ አስተላለፉ፡፡ መመሪያው የእኔን መሰል ጥያቄ ባቀረቡ ሌሎች መምህራን ላይም የተላለፈ ነበር፡፡ ከሦስት ወራት በላይ ደመወዜን ይዘው መክፈል ከአቆሙ በኋላ ‹‹ለሚመጣው ሴሚስተር አትመድቡት›› ማለት በአካዳሚያ ቋንቋ ግለሰቡ ተሰናብቷል ማለት ነው፡፡
በመሠረቱ፣ የትምህርት ክፍሌና አካዳሚክ ኮሚሽኑ የሥራ ውሌን መራዘም ተስማምተው ላቀረቡት ጥያቄ ሲኾን እንደወጉ ማጽደቅ አልያም በአስቸኳይ ውሳኔን ማሳወቅ ሲገባ፣ ፕሬዝዳንቱ ከሦስት ወራት በላይ ማቆየታቸው ኢ-ሕጋዊ ነው፤ ሕጉን ጠብቆ በወጉ ለቀረበ ጥያቄ ከሦስት ወራት በላይ ምላሽ አለመስጠት እብሪት፣ ትዕቢትና ማናለብኝነት እንጂ ሌላ ሊኾን አይችልም፤ በተመሳሳይ ወቅት አንድ ዐይነት ጥያቄ በደብዳቤ ከአቀረብነው መምህራን መካከል፣ ለምሳሌ ከኛው ትምህርት ክፍል ዶ/ር በቀለ ጉተማ በሥራው እንዲቀጥል በቃል ትእዛዝ ፈቅደው፣ ለእኔ በአግባቡ ውሳኔ ሳይሰጡ ‹በሚቀጥለው ሴሚስተር እንዳትመድቡት’ ማለት የአድልዎ አቀራረብ ብቻ ሳይኾን በዘፈቀደና በግፊት የሚካሔድ አመራር መኾኑን ያረጋግጣል፡፡ በሌላ በኩል፣ ፕሬዝዳንቱ ዶ/ር አድማሱ ዩኒቨርስቲውን ለመምራት ያላቸውን ብቃት ከዚህ ቀደም በአደባባይ ስለጠየቅኹ በቂም በቀልና ኹን ብለው እኔን ለመጉዳት የደረሱበት ውሳኔ ነው፡፡
የጥናትና ምርምር ዕረፍት(sabbatical leave) በተመለከተ በጊዜው የኮሌጁ ዲን የነበሩት ዶ/ር ገብሬ ይንቴሶ፤ የፕሬዝዳንቱን ፍላጎት ተከትለው ከላይ እንደጠቀስኹት የሰጡኝን ፈቃድ መልሰው ነጥቀውኛል፡፡ ጉዳዩን ለማየት ሥልጣን ወዳለው ፍርድ ቤት ከማምራቴ በፊት፣ የፕሬዝዳንቱን ምላሽ ከወዲኹ ባውቀውም አቤቱታዬን የግድ ለእርሳቸው ማቅረብ ነበረብኝ፡፡
በኮሌጁ የቀድሞ ዲን ውሳኔ ላይ ከዐሥር ገጽ ያላነሰ አባሪ ሰነዶች አያይዤ ጠዋት ላቀረብኹት አቤቱታ፣ ከቀትር በኋላ ‹‹በጥልቅ መርምረን›› በሚል በአንድ መሥመር የኮሌጁ ውሳኔ እንደማይሻር የሚገልጽ ፌዝና የቀልድ ምላሽ ነው የተሰጠኝ፡፡ ይህ የሚያሳየው ፕሬዝዳንቱ ለዩኒቨርስቲው መምህራን ከበሬታ የሌላቸውና አመራራቸውም ከሞራላዊነት የተራቆተ መኾኑን ነው፡፡ እኔ ግን ታዋቂው አርበኛ አበበ አረጋይ በአንድ ወቅት በፋሽስት ጣልያንና በባንዳ ለተከቡበት የተራቡ ጭፍሮቻቸው ‹‹ሞተን አንጠብቃቸውም፤ ተረጋግታችኹ ብሉ›› እንዳሉት፣ ከማባረር ያልተናነሰ የዘገየ አንድ ብጣሽ ወረቀት ገና ለገና ይመጣል ብዬ ሞቼ አልጠብቃቸውም፡፡
ከዚህ ቀደም የጡረታ ጊዜያቸው ደርሶ ለማራዘም የተፈቀደላቸው መምህራን አሉ ? ማለትም በዩኒቨርስቲው አሠራር የጡረታ ጊዜያቸው የደረሰ መምህራን ውላቸውን ማራዘም ይችላሉ?
በተለምዶ ስድሳ ዓመት የሞላቸው መምህራን የውል ማራዘሚያ ጊዜ ይጠይቃሉ፡፡ እኔ የማውቃቸውና በተደጋጋሚ የተጨመረላቸው መምህራንም አሉ፡፡ በጣም አስገራሚና በግቢው አነጋጋሪ የኾነው የእኔና የዶ/ር መረራ ጉዲና የውል ማራዘሚያ ጊዜ መከልከሉ ነው፡፡
ግን የዚህ ኹሉ መነሻ ምንድን ነው ብለው ይገምታሉ?
ከኹሉ በፊት የእኔ መከልከልና መሰናበት ከፖሊቲካ እይታ አኳያ የመነጨ መኾኑ የታወቀ ነው፡፡
ማለት…
በዩኒቨርስቲው በማስተማር ሥራ በቆየኹባቸው ባለፉት ሰባት ዓመታት፣ በጽሑፍና በተለያዩ መድረኮች የማደርጋቸው የዐደባባይ አእምሯዊ እንቅስቃሴዎች አልተወደዱም፡፡ እንዲያውም ለሹመኞች ቅርበት ያላቸው አንዳንድ ወዳጆቼ እንዳጫወቱኝ፣ ‹‹ዳኛቸው፣ ዩኒቨርስቲውን እንደ ደጀንና ገዥ መሬት ተጠቅሞ መድፍ ሲተኩስብን ቆይቷል›› ተብዬአለኹ፡፡ በርግጥ ይህ ዓይነቱ አቋም ከተወሰደ በኋላ በሥራ ገበታዬ እንድቀጥል አለመደረጉ አይገርመኝም፡፡
ከዩኒቨርስቲው በዚኽ መልኩ ሲሰናበቱ ምን ተሰማዎ?
እንደ እውነቱ ከኾነ የተደበላለቀ ስሜት ነው በውስጤ የተፈጠረው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ፣ ይህ ነገር ከሰባት ዓመት በኋላ መኾኑ አስደስቶኛል። ይኸውም የመጣኹበትን የማስተማር ዓላማ ከሌሎች ባልደረቦቼ ጋር በመኾን ለመስኩ ተተኪና ምሉዕ የኾኑ ተማሪዎች ለማፍራት በመብቃታችን አስደስቶኛል፡፡ ይህ ክልከላና ስንብት በቂ ምሩቃን ባላፈራንበት ከሦስትና ከአራት ዓመት በፊት ቢከሠት ኖሮ አዝን ነበር፡፡ በኹለተኛ ደረጃ፣ ‹የዓመት ዕረፍት(ሳባቲካል) አይሰጥኽም፤ ከእንግዲኽ ማስተማርም አትችልም› ስባል ለራሴ በጥልቀት ተሰምቶኝ ያልኹት፣ ‹‹አኹን ገና ኢትዮጵያዊ ኾንኩ፤ ኢትዮጵያዊ ማለት መብቱ የሚረገጥ ማለት ነው›› የሚል ነበር፡፡ በዚኽ ሰባት ዓመት ቆይታዬ ከአሜሪካ ሳልፈታ ይዠው የመጣኹት የነፃነትና የመብት አቅዋም፣ ከአገራችን ፖሊቲካዊ ነባራዊ ዕቀባ በተፃራሪው እንደ ልቤ እንድተችና ያለገደብ እንድናገር አስችሎኝ ነበር፡፡ አኹን ግን ሥርዓቱ ‹ይኼ አሜሪካ አይደለም፤ እንደ ጎረቤትኽ ሳይኾን እንደቤትኽ እደር› ብሎኛል፡፡ ይህን ስል ግን፣ እኔ በዕድሜዬ የምወልዳቸው ልጆች በኾነ ባልኾነ ክሥ ወኅኒ ቤት ተወርውረው ባሉበት ኹኔታ ከሥራ አባረሩኝ ብዬ የማለቅስ ሰው አይደለኹም፡፡ በእኒኽ ብሩህ ተስፋ ባላቸው ወጣቶች ላይ ከደረሰው አንጻር ሲታይ መብቴ መረገጡ እውነት ቢኾንም፣ የአገራችን ተረት ‹‹እናቱ ውኃ ልትቀዳ የወረደች ልጅና እናቱ የሞተችበት ልጅ አንድ ጋር ቆመው ያለቅሳሉ›› እንደሚባለው ይመስልብኛል፡፡
በመጨረሻም በአንድ በኩል፣ በውጭ ለብዙ ዓመት ቆይቼ ስመጣ የኢትዮጵያ ሕዝብ የት ከረምክ ሳይለኝ፣ ችሎታዬ በሚፈቅድልኝ ቦታ ሥራ ሰጠኝ፡፡ ለዚኽ ትልቅ ምስጋና ነው የማቀርበው፡፡ ኾኖም በሌላ በኩል የውስጥ አስተዳደሩና የውጭ የፖሊቲካ ኃይሎች በመተባበር መክረው ከሕዝብ ባገኘኹት ቸርነት ላይ ወይነውብኛል!
ከዚኽ በኋላስ ምን ዓይነት ሥራ ላይ ለማተኮር ያስባሉ?
ይህን ጥያቄ ዴሞክራሲና የሕግ የበላይነት ባለበት አገር ብትጠይቀኝ ኖሮ፣ ጉዳዩ በራሴ የሚወሰን በመኾኑ አኹኑኑ እመልስልኽ ነበር፤ ነገር ግን እንደ ቤትኽ እደር ተብዬአለኹና የጥያቄው ምላሽ በእኔ ብቻ የሚወሰን አይደለም፡፡ እንዲያውም ጥያቄው በአንድ ወቅት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ አሉ የተባለውን ያስታውሰኛል፡፡ አንድ ሹም ጃንሆይ ፊት ቀርበው የንጉሡ ትችትና ተግሣጽ ሲገጥማቸው፣ ‹‹እንዲያውም ግርማዊ ሆይ፣ የሰጡኝ ሹመት ይቅርብኝ፤ የአባቴን ርስት እያረስኩ እኖራለኹ›› አሏቸው፡፡ ጃንሆይም ወዲያው ‹‹እርሱንም እኛ ስንፈቅድ ነው…›› አሉ ይባላል፡፡
እኔም እንደ አቅሜ ለመሥራት ፍላጎት ቢኖረኝም፣ በቀጣይ ምን መሥራት እንደምችልና እንደማልችል ብያኔው በመሠረቱ ከእኔ ውጭ ነው፡፡ በተቻለኝ መጠን ግን በአለችኝ ቀሪ ዕድሜ አገሬን ለማገልገል ዝግጁ ነኝ፡ በዚኹ አጋጣሚ በቅርቡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሚገኝበትን ተቋማዊ ኹኔታ በተመለከተ አንድ ጽሑፍ እንደማቀርብ ከወዲኹ ለማሳወቅ እወዳለኹ፡፡
ምንጭ፡-አዲስ አድማስ ጋዜጣ
“ብሔር”ን ማን ፈጠረው?
የ”ብሔር”ን አፈጣጠር አስመልክቶ ሶስት ዋና ዋና አስተሳሰቦች የየራሳቸውን መልስ ይሰጣሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል ተፈጥሯዊ (Primordial)፣ በማህበራዊ ሂደቶች የተፈጠረ (constructed) እና ልሂቃን ለስልጣን መሳሪያነት የፈጠሩት (instrumental) የሚባሉ ናቸው፡፡ የመጨረሻዎቹ ሁለቱ ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር የተሳታፊ ሀይሎችንና ወቅት ላይ ልዩነት ያላቸው ቢሆንም ከመጀመሪያው በተቃራኒ ‹‹ብሄር›› የሠው ልጆች የፈጠሩት እንጂ ተፈጥሯዊ አይደለም ብለው ያምናሉ፡፡ በመሆኑም ክርክሩ ተፈጥሯዊ እና ሰዎች የፈጠሩት በሚል ሁለት ጎራ ጠበብ ብሎ መቅረብ ይቻላል፡፡
የመጀመሪያው አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› ድሮ ሰው ከተፈጠረበት ወቅት ጀምሮ የኖረና ሰዎች እርስ በእርሳቸው ጠንካራ ግንኙነት በመፍጠር ጥቅማቸውን ያስጠብቁበት የነበረ ተፈጥሯዊ (ሲወረድ ሲዋረድ የመጣ) ቡድናዊ መገለጫ ነው የሚል ነው፡፡ ሆኖም ይህ አስተሳሰብ ከጊዜ ወደጊዜ ከአንድ ‹‹ብሄር›› እየተሰነጠቁ ወይንም በሌላ ምክንያት የሚወጡ ‹‹ብሄሮች››ን ጥያቄ ሊመልስ አልቻለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአንዳንድ አገራት ጠንካራ የአገር ግንባታ ምክንያት የተለያዩ የነበሩ ህዝቦች አንድነት ስለማድረጋቸውም መለስ የለውም፡፡ ከምንም በላይ የዘመኑ ኢኮኖሚና አገራዊ ብሄርተኝነት ‹‹ብሄር›› የሚባልንም ሆነ ሌላ ማህበራዊ ስብስብን እያፈረሰ መገኘቱ ለዚህ አስተሳሰብ ድክመት ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡
‹‹ብሄር›› በሂደት የተፈጠረ ነው የሚለው አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› የተፈጠረው በተለያዩ ምክንያቶች በጊዜ ሂደት በተለይም በማህበራዊ ግንኙነት የተፈጠረ እና ትርጉሙ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀየረ የመጣ ነው የሚል ነው፡፡ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው ከሚሉት በተቃራኒ ‹‹ብሄር›› ማህበራዊ ፈጠራ ነው የሚለው የባህል ለውጥ፣ ድንበር፣ ታሪካዊ ወቅት፣ የግለሰቦች ሚና፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ምክንያቶች ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር እንደ ምክንያትነት ይጠቅሳል፡፡
ሶስተኛው አስተሳሰብ ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ተጠያቂ የሚያደርጋቸው ልሂቃንን ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ ‹‹ብሄር›› የተፈጠረው ለልሂቃን መሳሪያነት (instrument) ነው ይላል፡፡ በዚህ አስተሳሰብ ስር የሚገኙ ምሁራን ‹‹ብሄር››ን የፈጠሩት በ‹‹ብሄር›› ስም የሚነግዱ ልሂቃን ወይንም ‹‹የብሄር ኢንተርፕርነሮች›› (ethnic entrepreneurs) ይሏቸዋል፡፡ ይህንም የሚያደርጉት በአንድ አገር መንግስት ውስጥ ይገባናል የሚሉትን ጥቅም ለማሳደግ፣ ለዚህምና ለሌሎቹ ለሚደረጉ ትግሎች በዚህ በፈጠሩት ማንነት ስም በርከት ያሉ ምልምሎችን ለማግኘትና ይህንንም ተጠቅመው የራሳቸውን ግለሰባዊ ስልጣን ለማጠናከር ነው፡፡
ሁለተኛውና ሶስተኛም አስተሳሰቦች ከልዩነታቸው ይልቅ ተመሳሳይነታቸው የጎላ ነው፡፡ ልዩነታቸው ‹‹ብሄር›› በሂደት የመጣ ነው የሚሉት ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር የፖለቲከኞቹን ሚና አጉልተው አለማሳየታቸው ሲሆን በአንጻሩ ‹‹ብሄር›› የልሂቃን ፈጠራ ነው የሚሉት ትልቅ ትኩረት የሚሰጡት ለልሂቃን ብቻ መሆኑ ነው፡፡ በእርግጥ ‹‹ብሄር›› ቀስ በቀስ የተፈጠረ ነው የሚሉትም ስለልሂቃን በስፋት ባያነሱም ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ጠባብ ብሄርተኝነትን እንደምሳሌ ሲጠቅሱ የሚነሳው ‹‹ብሄር›› ለልሂቃን መሳሪያ መሆኑ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአንድ ወቅት በልሂቃን የበላይነት የተፈጠረው ብሄርተኝነት ቀስ በቀስ በህዝብ ዘንድ ሲዘወተር ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ድርሻቸው ከፍተኛ ስለሚሆን ሁለቱ አስተሳሰቦችን የሚመሳሰሉባቸው ነጥቦች ይበዛሉ፡፡ ሁሉቱ አስተሳሰቦች በየራሳቸው ያለባቸው መጠነኛ ክፍተትም ሁለቱን አስተሳሰቦች በጥምረት በመጠቀም ለ‹‹ብሄር›› መፈጠር ሙሉ እይታ መፍጠር እንደሚቻል ብዙዎቹ ምሁራን ያምኑበታል፡፡ ሁለቱን የጋራ የሚያደርጋቸው ደግሞ የልሂቃን ሚና ነው፡፡
ኢትዮጵያና ‹‹ብሄር››
ኢትዮጵያ የተለያየ ባህል፣ ወግ፣ ታሪክና ቋንቋ ያላቸው ህዝቦች መኖሪያ ብትሆንም ‹‹ብሄር›› በፖለቲካ ቃናው ትኩረት እየተሰጠው የመጣው ከጣሊያን ወረራ በኋላ ነው፡፡ በእርግጥ ከዚያ በፊትም ቢሆን የኢትዮጵያ የተለያዩ ገዥዎች ህዝብን በቋንቋ፣ ከባቢና በመሳሰሉት አንቀሳቅሰው ከሌሎች ጋር ያላቸው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልዩነት ለማጠናከር አልጣሩም ለማለት አይቻልም፡፡ በተለይ ህዝቦች በመንገድና በመሳሰሉት መሰረተ ልማት ባለመገናኘታቸው ባህል፣ቋንቋና ሌሎችም ባህላዊ እሴቶቻቸው በመለያየታቸው በሂደት ከሌሎች ለሚለዩባቸው አጋጣሚዎች ክፍተት ይፈጠራሉ፡፡ ይህን ልሂቃን በመሳሪያነት ሲጠቀሙበት ደግሞ ‹‹ብሄር›› መፈጠሩ የግድ ነው፡፡
አንድ ተመሳሳይ ቋንቋ፣ ባህልና ሌሎች ማህበራዊ እሴቶችን ይከተላል የምንለው ህዝብ በውስጡ መጠነኛ ልዩነቶች ይኖሩታል፡፡ ህዝቦች በተለያዩ ምክንያች ግንኙነታቸው ከተዳከመ እያደር እነዚህ ልዩነቶች እየተጠናከሩም በእነዚህ ህዝቦች መካከል ሰፋ ያለ ልዩነት ይፈጠራል፡፡ በተለይ እነዚህን ልዩነቶች የሚያስታርቅና የበላይ የተባለ ገዥ ማህበራዊ እሴት ከሌለ ህዝቦቹ ቀስ በቀስ ልዩነታቸው ሊሰፋ ይችላል፡፡ በየትኛውም አንድ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝብ መካከል ዘየና ሌሎች ልዩነቶች በሂደት የቋንቋ መሰረታዊ ልዩነቶችን ይፈጥራሉ፡፡ ለአብነት ያህል አማርኛ እና ትግርኛ ከግዕዝ የመጡ መሆናቸው የሚነገርላቸው ቢሆንም የህዝቦች አሰፋፈር ልዩነት፣ መንገድና ሌሎችን የመሳሰሉ መሰረተ ልማት አውታሮች አለመኖር እንዲለያዩ አድርጓቸዋል፡፡ የልሂቃን ሚና ሲጨመርበት ደግሞ የአሁኑን ፖለቲካ ፈጥሯል፡፡
በአሁኑ ወቅት በትምህርት ደረጃ የሚሰጠው አማርኛ ሸዋ፣ ጎንደር፣ ጎጃምና ወሎ አካባቢ የሚነገሩ ዘየና ሌሎች የቋንቋው ልዩነቶችን ማስታረቅ ባይችል፣ በመሰረተ ልማት መገናኘት ባይችሉ እነዚህ ከጅኦግራፊያዊ አቀማመጥ ውጭ የማይለያዩ አማርኛ ተናጋሪ ህዝቦች ትግርኛ እና አማርኛ እንደተለያዩት የተለያዩ ቋንቋዎች መሆን ይችሉ እንደነበር አያጠራጥርም፡፡
ኢትዮጵያ አገውኛ ተናጋሪ ህዝቦች ይኖሩባት እንደነበር ታሪክ ያስረዳል፡፡ በሰሜን ኢትዮጵያ ይኖሩ የነበሩት ህዝቦች አገዎች እንደነበሩ በኢዛናና ካሌብ ዘመን የነበሩ ቅሬቶች ፍንጭ ሰጥተውል፡፡ እነዚህ ህዝቦች በአማርኛና ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ ተውጠው በአሁኑ ወቅት በተወሰኑ አካባቢዎች ብቻ ይገኛሉ፡፡ ለአብነት ያህል በወሎና ጎጃም አገው በሚል፣ በጎንደር ቅማንት፣ በባህር ዳር አካባቢ ወይጦ እና የመሳሰሉ ስሞች ተሰጥቷቸው ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ህዝቦች ትግራይና ኤርትራ ውስጥም ተበታትነው ይኖራሉ፡፡ ከከረን ጀምሮ በቋራ፣ ዳንግላ፣ ሰቆጣ፣ ጣና ዳር….ተበታትነው ከሚገኙት ውጭ ሌሎቹ በትግርኛ እና አማርኛ ተናጋሪ ሆነዋል፡፡ ይህኛው ክስተት የሚያሳየው ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ማንነት ሳይሆን የሚዋጥ፣ የሚቀየር መሆኑን ነው፡፡ እነዚህ በአንድ ወቅት ‹‹አገው›› ተብለው የነበሩ ህዝቦች በሂደት በመጣ ማግበራዊ፣ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ‹‹ኤርትራዊ››፣ ‹‹ትግሬ››ና ‹‹አማራ›› ተብለዋል፡፡ ልሂቃንም በተለያዩት እነዚህ ማንነቶች በአንድ ወቅት አንድ የነበሩትን ህዝቦች አንቀሳቅሰዋቸዋል፡፡ ሌላው ይቅርና ግዕዝ ከቤተክርስቲያን አልፎ በተወሰነ ህዝብ የሚነገር ቢሆኑ ኖሮ ኢህአዴግ አንድ ተጨማሪ ‹‹ብሄር›› ሊያቋቁም ነበር ማለት ነው፡፡
የአክሱም ስርወ መንግስት በተለያዩ ምክንያቶች ተዳክሞ የዛጉየ ስርወ መንግስት ሲተካ ከድልነአድ እስከ ይኩኑ አምላክ ያሉት 8 የአክሱም ስርወ መንግስት ነገስታት በሸዋ እየሸሹና ተደብቅው ኖረዋል፡፡ የአሁኑ ወቅት ልሂቅ መር የ‹‹ብሄር›› ፖለቲካ አክሱም ውስጥ የነበሩትን ነገስታት ‹‹የትግሬ ቅድመ አያቶች›› አድርገው ይወስዷቸዋል፡፡ ከአክሱም መጥተው ሸዋ ነገስትነትን የመሩትን ደግሞ ‹‹አማራ›› ይሏቸዋል፡፡ ታሪክ ደግሞ የአክሱም ስርወ መንግስት ወቅት በሰሜን ኢትዮጵያ ይነገር የነበረው ቋንቋ አገውኛ እንደነበር ያስረዳናል፡፡
‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ቢሆን ኖሮ አገውኛ የሚናገሩት አብዛኛዎቹ ኢትዮጰያ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ህዝቦች ሌሎች ቋንቋዎችን በሚናገሩ ህዝቦች ሳይዋጡ ‹‹አገው›› ሆነው በቆዩ ነበር፡፡ ትግሬ ከአክሱማውያን የመጣ ‹‹ብሄር›› ቢሆን ኖሮ መነሻቸው ከአክሱማውያን የሆኑት የሸዋ ነገስታትም እስከ አሁን ‹‹ትግሬ›› ሆነው በቀጠሉ ነበር፡፡ ይሁንና ‹‹ብሄር›› በሂደት በተለይም የልሂቃን ሚና ተጨምሮበት የሚፈጠር አዲስና የፈጠራ ማንነት በመሆኑ እነዚህ ህዝቦች የተለያዩ ማንነቶች እንዳላቸው እየተቆጠረ ነው፡፡
በአንድ ወቅት ኢህአዴግ አራት ያህል የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችን ‹‹ወጋጎዳ›› በሚል አዲስ የ‹‹ብሄር›› ማንነት ለመመስረጥ ጥረት አድርጎ ነበር፡፡ ይህ አዲስ ማንነት ቢሳካ ኖሮ ሀይለማሪያም ደሳለኝ የወላይታ ሳይሆን በልሂቃን መሳሪያነት ከሌሎች ሶስት (ጋሞ፣ ጎፋና ዳዋሮ) ጋር የተለነቀጠው ‹‹ወጋጎዳ ብሄር›› ተደርገው ሊወሰዱ ነበር፡፡ ምንም እንኳ በተለያዩ ምክንያቶች ባይሳካም ‹‹የወጋጎዳ›› ፕሮጀክት ብሄርን የሚፈጥሩት ልሂቃን መሆናቸውን ቁልጭ አድርጎ አሳይቷል፡፡
ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ በኋላ ‹‹ብሄር›› በግልጽ ተፈጥሯዊ እንደሆነ ተደርጎ ተግባራ ሊሆን ችሏል፡፡ ብሄር ተፈጥሯዊ ነው የሚለውን አስተሳሰብ የሚከተሉ አካላት አንድ ግለሰብ በ‹‹ብሄሩ›› እንጂ በግለሰባዊነቱ መቆም አይችልም የሚል አስተሳሰብ ያራምዳሉ፡፡ ይህም በእኛው ህገመንግስት ‹‹እኛ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች›› በሚል ተቀምጧል፡፡ በመሳሪያነት የሚጠቀሙ ፖለቲከኞች ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው የሚሉ አካላት አስተሳሰብ የሚጠቀሙ ናቸው፡፡ በመሆኑም በአስተሳሰብ ደረጃ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ነው የሚለውን በመጠቀም ኢህአዴግ የ‹‹ብሄር ኢንተርፕርነር›› ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ከሆነ የትኛውም ፖለቲከኛ ወይንም ፓርቲ ሊመሰርተው የሚችለው መንግስትም ሆነ ስርዓት ‹‹ብሄር›› ተመሳሳይ የ‹‹ብሄር›› ማንነት ላይ ያተኮረ መሆን አለበት፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ህዝቦች በአጼ ሀይለስላሴ፣ ደርግ፣ ኢህአዴግ ስር የያዙት የ‹‹ብሄር›› ማንነት በየ ስርዓቱ የተለያየና በየ ጊዜው እንደ ልሂቃኑ ጥበትና ኢትዮጵያዊ አላማ የሚወናበድ ነው፡፡
ወደ ኢህአዴግ ወረድ ብልን እንኳ በአቶ መለስና በሌሎቹ ገዥዎች ኢትዮጵያንም ሆነ በየ የኢትዮጵያን ‹‹ብሄሮች›› የሚያንቀሳቀሱበት አጋጣሚ የተለየ ነው፡፡ አንድ ህዝብ ሊከተለው የሚችለው በጊዜው በኢኮኖሚ፣ ሚዲያም ሆነ ወታደራዊ ሁኔታ ጊዜው ስልጣን የሰጠውን አካል ነው፡፡ ህወሓትና አረና የትግራይን ህዝብ የ‹‹ብሄር›› ማንነት የሚቀርጹበት ሁኔታ ተመሳሳይ አይሆንም፡፡ ብአዴንና የድሮው መአአድ፣ ኦነግና ኦህዴድ፣ የደቡብ ህብረትና ደኢህአዴን፣ ሶዴፓና ኦብነግ፣ ሻቢያና ጀብሃ እንወክለዋነን የሚሉትን ህዝብ ብሄራዊ ማንነት የሚመሩበትና የሚፈጥሩት በተለያየ መልኩ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከ20 አመት በፊት የነበሩትና አሁን ያሉት እነዚህ ፓርቲዎች ህዝብን የሚቀሰቅሱበት አጋጣሚ የተለያየ ነው፡፡ በቅርቡ ኦነግ የመገንጠል ጥያቄውን አንስቻለሁ ሲል ከ20 አመት በፊት ከነበረው የኦነግ የ‹‹ብሄር›› ማንነት መለየቱን ለመገንዘብ ይቻላል፡፡
‹‹ብሄር››ና ደም
‹‹ብሄር›› ተፈጥሯዊ ካልሆነ ከደም ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም ማለት ነው፡፡ ሳይንስ በራሱ ዘር፣ ብሄርና ሌሎችን የሰው ልጅ ማህበራዊ ትስስሮች ለማመሳሰል ቢሞክርም ሊሳካለት አልቻለም፡፡ በተለይ ምዕራባዊያን ከሌሎች የተለዩ መሆናቸውን ለማረጋገጥ ሙከራ ያደረጉ ‹‹ሳይንቲስቶች› ዘንድ የሰዎች ዘረመል የሰውን ዘርቁልጭ አድርጎ ያሳያል የሚል መላ ምት የነበራቸው ቢሆንም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ እስካሁን አንድ ሰው ከየትኛው አገር እንደመጣ የሚያሳይ አስተማማኝ መረጃ እንኳን ማግኘት አልተቻለም፡፡
በእነዚህ ጥናቶችን ተንተርስ ለአብነት ያህል ኢትዮጵያን እንደምሳሌ ብንወስድ የሚያሳየው የአንድ አገር ሰው በዘረመልም ሆነ በደም ከሌሎች አገራት ጋርም የሚመሳሰል ነው፡፡ እንደ ጥናቶቹ ኢትዮጵያዊያን ከቻይና፣ አብዛኛው የአረብና የኤሲያ አገራት፣ አንዳንድ የደቡብ አሜሪካና ሜክሲኮ ህዝቦች መካከል ከ10-15 የሚሆኑት በተመሳሳይ የኤ የደም ዘር ባለቤቶች ናቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን፣ አብዛኛዎቹ የአፍሪካዊያን፣ የደቡብ አሜሪካ ኤሲያ ከ5-10 እና ከ10-15 የሚሆነው ህዝባቸው ቢ የደም አይነት ያለው ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያን ጨምሮ አፍሪካ፣ የመንና ሳውዲ የመሳሰሉ የአረብ አገራት፣ የተወሰነ የቻይና ከፍል፣ ጥቂት የምስራቅ አውሮፓ አገራት፣ ከደቡብ አሜሪካ አገራት መካከል አንዳንድ አካባቢዎች፣ የአውስትራሊያ ጠረፋማ ክፍሎች ከሚኖሩት ህዝቦች መካከል ከ40-70 ኦ የደም አይነት ባለቤቶች ናቸው፡፡ በ‹‹ብሄሮች›› መካከል ይህን ያህል የሚመሳሰል የዘረመልና የደም አይነት ለማግኘት አልተቻለም፡፡ በዓለም ህዝቦች ሁሉ ኤ፣ ቤ፣ ኤቤና ኦ የተባሉት የደም አይነቶች የትም የሚገኙ ሲሆን ከአንድ ቤተሰብ ይልቅ በተለያዩ አገራት ያሉ ህዝቦች ለሌላኛው ደም መስጠት ይችላሉ፡፡ በመሆኑም አንድ ኦሮሞ ከብሄሩ ያላገኘውን ተመሳሳይ የደም አይነት ወይንም ልብ፣ ኩላሊትና ሌሎች ተመሳሳይ የአካል ክፍሎች ከትግሬ፣ ከአማራ፣ ከጉራጌና ከሌሎች ብሄሮች አልፎ ደቡብ አሜሪካ፣ ኤሲያ፣ አውሮፓና አውስትራሊያ ከሚገኝ ነጭ ማግኘት ይችላል፡፡
አንድ ቋንቋ የሚናገሩና በተለያየ የአየር ንብረት ከሚኖሩ ህዝቦች በተሻለ የተለያየ ቋንቋ የሚናገሩና በተመሳሳይ የአየር ንብረት የሚኖሩ ህዝቦች ተመሳሳይ የሰውነት ገጽታ ይኖራቸዋል፡፡ ለአብነት ያህል በመተማና ሁመራ አካባቢ የሚኖሩ ትግርኛ እና አማርኛ ተናጋሪዎች በቆላማው ሶማሊና አፋር ክልሎች ከሚኖሩት የሶማልኛና አፋርኛ ተናጋሪ ህዝቦች ተመሳሳይ የሰውነት ገጽታ፣ አለባበስና አመጋገብ ባህል አላቸው፡፡ ከምንም በላይ በአገራችን ብሄር የፈጠራ ማንነት መሆኑን የሚያሳየው ሁለት የተለያየ ማንነት አላቸው ከተባሉ ቤተሰቦች የተገኘ ልጅ የእናቱን ማንነት ትቶ የአባቱን ማንነት በግድ እንዲቀበል የመመደቡ ጉዳይ ነው፡፡ አንድ ግለሰብ በተለያዩ ምክንያቶች የእናቱን አሊያም ግለሰባዊ ማንነቱን መቀበል ቢፈልግ የወቅቱ የአገራችን ስርዓት በግድ የአባቱን ብሄር አባል ያደርገዋል፡፡ ሰው የፖለቲካ እንሰሳ እንደመሆኑ ‹‹ብሄር››ን ሲፈጥር እንሰሳት ከሰው የተሻለ ቁርጥ ያለ ዘር ያላቸው ማንነታውን በሂደት በሚፈጠር ማህበራዊ ማንነት አሊያም የልሂቃን ፈጠራ የሚያወናብደው ፖለቲካዊና ማህበራዊ ምክንያት ባለመጠቀማቸው ብቻ ነው፡፡
ሶቭየት ወዲያ ኢትዮጵያ…
በአገራችን የ‹‹ብሄር›› ማንነት የሚጣረሰው ገና ከትርጉሙ ነው፡፡ ‹‹ብሄር›› በግዕዝ አገር ማለት ቢሆንም ከ1960ው ጥራዝ ነጠቅ ትውልድ ትርጉም በኋላ አገሪቱ የተሰራችባቸው ማንነቶች ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በእነ ስታሊኑ ትርጉም እንኳ ብንሄድ ብሄር የሚለውን ‹‹ተመሳሳይ ወይንም ተቀራራቢ ቋንቋ፣ ባህል፣ ታሪክ፣…..›› ለሚጋሩ ህዝቦች የሚሰጥ ነው፡፡ እንግዲህ እነዚህ ህዝቦች ከሌሎች የተለዩ፣ ማንነቱ ተፈጥራዊና ከሌሎች በፍጹም የተለየ በመሆኑ መቼም ቢሆን ይህን ባህላቸውን፣ ማንነታቸውን አይቀይሩም እንደማለት ነው፡፡ ‹‹የጋራ ታሪክ ያላቸው›› ብሎ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ወላይታ፣ (ቢሳካ ኖሮ ደግሞ ‹‹ወጋጎዳ)፣ ሲዳማ…ሲልም የአድዋና ማይጨውን ጨምሮ የሚጋሩት ታሪክ የላቸውም እያሉን ነው፡፡
በቭየት ህብረትና በኢትዮጵያ መካከል ከፍተኛ ልዩነት ነው ያለው፡፡ ሌኒን 15 አገራት አንድ ከማድረጉ በፊት ኢትዮጵያውያን በጋራ አገር ለመመስረት ለረዥም አመት ሰርተዋል፡፡ በአንጻሩ የሶቭየት ክፍሎች አንድ እስኪሆኑ ድረስ ያላቸው ታሪክ የተለየ ነው፡፡ የሶቭዬት ህብረት አባላት ህብረቱን ከመራችው ሩሲያም ሆነ ከሶቭየት ህብረት የተለየ የአገር ምስረታ ታሪክ አከናውነው የተቀላቀሉ ናቸው፡፡ አብዛኛዎቹ የሩሲያ መንግስት ከመስፋፋቱ በፊት በኦቶማን ቱርክና በሌሎች ቀኝ ገዥዎች ስርም የነበሩ ናቸው፡፡
የሶቬት ህብረት ፌደራል አወቃቀር በአገራት እንጅ አገር ውስጥ ባሉ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች የተመራ አልነበረም፡፡ ኢህአዴግም የነ ስታሊንን ስርዓት ሲገለብጥ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይ፣ አፋር፣ ሀረሪ…..እያንዳንዳቸው ‹‹አገር›› ሆነው ፌደራሊዝሙን እንደተቀላቀሉ እየነገረን ነው፡፡ በተቃራኒው ኢትዮጵያ ውስጥ በየ አካባቢው የነበሩ ነገስታት ኢትዮጵያን በራሳቸው መልክ ለመገንባት እንጅ የያዙትን አካባቢ ገንጥለው አገር ለመመስረት አልነበረም፡፡ የየራሳቸውን ግዛት ለመመስረት ነበር የሚል የፈጠራ መረጃ እንኳን ቢቀርብ ‹‹አገር›› ለመሆን የሚያስችል ቅርጽ ሳይዙ ማዕከላዊ መንግስት ውስጥ መጠቃለላቸው ከሶቬት አባላት በእጅጉ የተለዩ ያደርጋቸዋል፡፡
እንዲያው የስታሊኑን ትርጉም ብንወስድ እንኳን የእኛው የ‹‹ብሄር›› ትርጉም የተሳሳተ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ ኢትዮጵያውያን ቋንቋ ሳይገድባቸው እንጀራና ጥሬ ስጋ ይመገባሉ፡፡ ጠላና ጠጅ ይጠጣሉ፡፡ ተዋልደውና በጉድፍቻ አብረው ይኖራሉ፡፡ አተራረሳቸው፣ አመራረታቸውና ምርቶቻቸው በአየር ንብረት ካልሆነ በስተቀር ልዩነቱ ጎልቶ የሚተይ አይደለም፡፡ በጋራ አላማ ቅኝ ገዥዎችን ተዋግተዋል፡፡ አገር ገንብተዋል፡፡ በመሆኑም በስታሊኑ ቋንቋ ‹‹ተመሳሳይ ወይንም ተቀራራቢ ባህል፣ ታሪክ፣ አላማ….›› መሰረት አንድ ብሄር (አገር›› ውስጥ የሚካተቱበት እንጅ የሚነጣጠሉበት አልነበረም፡፡
በነገራችን ላይ ህዝቦች የተለያዩ ናቸው ተብሎ ‹‹ብሄር›› የተለያዩ ቋንቋ ተናገሪ ህዝቦች መጠሪያ በዋለበት እንደገና ‹‹ብሄር›› ማለት አገር ማለት መሆኑን ይነገረናል፡፡ ለአብነት ያህል ብሄራዊ ቡድን ሲባል የኦሮሞ፣ የአማራ፣ ትግሬ፣ ወላይታ ተጫዋቾች ብቻ የተሰባሰቡበት ሳይሆን የአገሪቱ ቡድን መሆኑ ነው፡፡ ብሄራዊ ባንክ ሲባልም ቢሆን የአገሪቱ ማዕከላዊ ባንክ እንጅ በሂደት ሲቀየር፣ ሲዋጥ፣ ሲያንሰራራ በኖሩት ቋንቋን መሰረት ያደረጉ ማንነቶች ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ከማርክሲስቱ ትርጉም ይልቅ የምዕራባዊያን ትርጓሜ ‹‹ብሄር›› የተወናበደ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ ያሳየናል፡፡ ብሄር (አገር) በእንግሊዘኛው (በምዕራባዊያኑ አስተሳሰብም) ‹‹Nation›› በሚለው ቃል ይገለጻል፡፡ ‹‹Nationality›› የሚለው ደግሞ አንድ ግለሰብ ከአገሩ ጋር ያለው ግንኙነት የሚገለጽበት ነው፡፡ ነዋሪ፣ ተወላጅ፣ ዜጋ በሚለው ልንወክለው እንችላለን፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥም ቢሆን በፓስፖርትና በመሳሰሉት ‹‹Nationality›› ቋንቋ ሳይገድበው የሚገልጸው ዜግነትን ነው፡፡ ለፖለቲካው ዘርፍ ደግሞ ‹‹ከትልልቆቹ ብሄሮች ያነሱ›› የሚሏቸውን ማንነቶች ለመግለጽ ይውላል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብሄር የሚባለው ‹‹Nation›› (አገርን) ሳይሆን ‹‹ethnicity›› የሚለውን ‹‹ማንነት›› እንዲወክል ተደርጓል፡፡ ‹‹ethnicity›› ደግሞ በወጉ ይተርጎም ከተባለ ከጎሳ ያለፈ ቃል ሊገኝለት አይችልም፡፡
ይህ የሚያሳየው መሰረታቸውን ካደረጉበት የስታሊኑ ትርጉም ጋር እንኳ አብረው መሄድ አለመቻላቸውን ነው፡፡ ይህ ተቃርኖ የሚመነጨው ብሄር ከሂደቱም ይልቅ ፖለቲካ ፈጠራው ማመዘኑ ነው፡፡ በአገራችን ደግሞ ከሁለቱም ትርጉሞች ሳይሆን ጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅም ላይ ማተኮሩ ተቃርኖውን ውስብስብ አድርጎታል፡፡
ኣሸጎዳ የንፋስ መብራት ማመንጫ ሃይል ዲናሞ በመቃጠሉ ምክንያት ከጥቅም ውጭ ሆነ
በመቀሌ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኝ የኣሸጎዳ በንፋስ የሚሰራ ኤለክትሪክ ማመንጫ ሃይል በዲናሞ መቃጠል ምክንያት ከስራ ውጭ መሆኑ ታውቋል። የተቃጠለው ዲናሞ 150 ሜጋዋት የማመንጨት ኣቅም የነበረው ሲሆን ምክንያቱ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠሉ ሃይል የማመንጨት ኣቅሙ ሙሉ በሙሉ ማቆሙ ታውቋል።
የተቃጠለው ዲናሞ ቅያሪ በሃገር ውስጥ እንደሌለና ከፈረንሳይ ሃገር እንደሚመጣ ታውቋል። የህወሓት የ40 ዓመት የልደት በዓል እንደ ታላቅ ውጤትና ማጣፈጫ ተደርጎ ሊወሰደ ታስቦ የነበረ ሲሆን ባልታወቀ ምክንያት መቃጠሉ በክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከፍተኛ ቁጣና ድንጋጤ መፍጠሩ ታውቋል።
የትግራይ ባለስልጣናት እንደ ግዝያዊ መፍትሄ ኣድርገው የወሰዱት የየካቲት በዓል እስኪያልፍ ከፈርንሳይ በክራይ እንዲመጣና ብልሸት እንዳልደረሰው ኣስመስሎ በማሳለፍ በዓሉ ከተጠናቀቀ በሗላ ዲናሞው ወደ ፈረንስይ እንዲመለስ የሚል ትእዛዝ ኣስተላልፈዋል።
የህወሓት ባለስልጣናት የየካቲት በዓል ታዳሚዎች ኣሳፋሪ በሆነ ድራማ ኣጭበርብረው ለመመልስ ከፈረንሳይ ዲናሞ ተከራይተው ካሳዩሗቹ በሗላ ተመልሰው ወደ መጣበት ይመልሱታል። ህወሓት የዲናሞው መቃጠል ለየካቲት በዓል ማክበርያ ካወጣችው 1 ቢልዮን ብር ወጪ የምታወጣው ተጨማሪ ግዙፍ ብር ይሆናል።














