“ሙሰኞቹ” የተያዙት በሟቹ አቶ መለስ ጥቆማ ከሆነ፤ ነገስ?

አየነው በጊዜው

(ከአዲስ አበባ)

 

Melaku

 

የኢትጵያ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሚኒስትርነት ማዕረግ የትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን አቶ መላኩ ፈንታንና ምክትላቸው አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስን፣ የኢንተር ኮንትኔታል ሆቴል ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ እና የኬኬ ኩባንያ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደን ጨምሮ 12 ሰዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል፡፡ እነኚህ ሰዎች ደግሞ ሊያዙ የቻሉት ከዛሬ 3 ዓመት በፊት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ መለስ ዜናዊ ጥቆማና ትዕዛዝ መሰረት መሆኑን ኮሚሽነሩ እግረ መንገዳቸውን ጠቁመዋል፡፡

እነኚህ ተጠርጣሪዎችም ወዲያው ለፍርድ እንዲቀርቡ መደረጉ የሚታወስ ነው፡፡ ኮሚሽኑም እንደትልቅ ጀብዱ በከፍተኛ የደስታ ስሜት ግንቦት 6 ቀን 2005ዓ.ም. ለፓርላማ ሪፖርት ሲያቀርብ የተያዙትን ተጠርጣሪዎች እንደ ትልቅ ስኬታማ ናሙና ስራ ሲጠቅስ ነበር፡፡ በርግጥ የሃገር ሃብት የሚመዘብሩ መያዛቸው ባይከፋም እስከዛሬ ትላልቅ ባለስልጣናት ላይ ለምን ዝምታን መርጦ ዛሬ እንደ ድል ይቆጥረዋል? የሚል ጥያቄን ማጫሩ አይቀሬ ነው፡፡

እንደኮሚሽኑ ገለፃ ከሆነ በአሁን ወቅት በቁጥጥር ስር ያሉት የመንግስት ሹመኞችና ነጋዴዎች ከመታሰራቸው በፊት ለሶስት ዓመታት ክትተል እየተደረገባቸው እንደነበርና ተግባራዊ ክትትሉም ከዛሬ አንድ ዓመት በፊት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር አሳሳቢነት ዛሬ ላይ መድረሳቸውን ኮሚሽነሩ በይፋ ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ዛሬ አቶ መላኩን ጨምሮ የመንግስት ሹመኞችን ብልሹ አሰራር በማጋለጣቸው ጭለማ ቤት ውስጥ እንደታሰሩ ጋዜጠኞችና ተቃዋሚ ፖለቲከኞች አቶ መላኩና ምክትላቸው ከልማታዊ ባለሃብቶቹ ጋር የዚህ ሰለባ ሆነዋል፡፡

እነኚህ ተጠርጣሪ ሙሰኞች ትናንት ሲወደሱና ሲመሰገኑ ከርመው ዛሬ ለረጅም ጊዜ ክትትል ይደረግባቸው እንደነበር መግለፁ ከበስተጀርባ ሌላ ነገር እንዳለ የሚያሳይ ይመስላል፡፡ ምክንያቱም እንደ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ከሆነ እስከዛሬ ንብረትነቱ በውል የማን እንደሆነ የማይታወቀውን በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ የሚንቀሳቀሰው ኤፈርት ኦዲት ተደርጎ ባለማወቁ ሙስና ከተባለ የድርጅቱ ባለቤቶችና አንቀሳቃሾች መቅደም ነበረባቸው ሲሉ ግምታቸውን ይሰጣሉ፡፡

በተለይ የሃብታቸው ምንጭ ምን እንደሆነ ያልታወቁት አብዛኞቹ አዳዲሶቹ የአዲስ አበባ ህንፃዎች ከባለስልጣና ጋር በመሞዳሞድ በሙስና የተሰሩ ሊሆኑ ስለሚችሉ እስካሁን በፌደራሉ ስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምንም የተደረገ አመላካች እርምጃ ባለመታየቱ አሁን በባለሃብቶቹና በባለስልጣናቱ ላይ የተወሰደው እርምጃ ከሙስና ይልቅ የፖለቲካ ጉዳይ ሊሆን እንደሚችል አመላካች እንደሆነ በስፋት ይነገራል፡፡ ለዚህም ድምዳሜ መሰረቱ የሙስናው ክትትል ከቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሟቹ አቶ መለስ ዜናዊና በስፋት በዚሁ ተግባር ከሚታሙት ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን መጀመር እንደነበረበት በመጠቆም፡፡

በተለይ ሌላው አስገራሚው ነገር ኮሚሽኑ አሁን በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን ተጠርጣሪዎች ከዓመታት በፊት በሟቹ አቶ መለስ ጥቆማ መሆኑ እስከ ዛሬስ ለምን ቆየ; አሁንም ቢሆን ኮሚሽኑ ዛሬ መድፈሩን ያሳየን በራሱ ተነሳሽነትና ጥረት ሳይሆን በፖለቲካ ስልጣን የበላዩ በመጠቆሙ በመሆኑ ነው፡፡ ይህም የሚያመለክተው ኮሚሽኑ በነፃነት ስራውን የመስራት አቅምም ሆነ ፍላጎት እንደሌለው አመላካች ከመሆኑም በተጨማሪ ለዛሬው ድል መሳካት ትልቅ ሚና የተጫወተው እሱ ሳይሆን ሟቹ ግለሰብ መሆናቸውን በተደጋጋሚ መግለፁ ነው፡፡

ኮሚሽኑ ከተቋቋመ ምንም እንኳ 10 ዓመት ቢሆነውም ሀገሪቱ በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ 11.2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር(ከ207 ቢሊዮን ብር በላይ) የተዘረፈች መሆኗንና በተለይ ኮሚሽኑ ከተቋቋመበት ዓመት አንስቶ ደግሞ ወደ 8.2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር(ወደ 152 ሚሊዮን ብር ገደማ) መዘረፉን መረጃዎች ቢጠቁሙም ኮሚሽኑ የመንደር ሌቦችን ብቻ እያሰሰ የፖሊስን ስራ ይሰራ እንደነበር የሚያወሱ በርካቶች ናቸው፡፡ በዚህም ሀገሪቱ ማዳን የነበረባትን ዝርፊያና የአባሕ ግድን የሚያህሉ ከሁለት በላይ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ሊገነባ የሚችል የሀገሪቱ ሃብት ሲዘረፍ በተለያ የመረጃ አውታሮች ቢነገርም ኮሚሽኑ እስካሁን ያለው ነገር ባለመኖሩ እራሱ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከሙስና ፀድቶ ነው ወይ የሚሉ በርካቶች ናቸው፡፡

ከላይ የተጠቀሱትን እንኳ ብንተው በሀገር ውስጥ ምን ያህል ህገወጥ ስራ በመንግስት መስሪያ ቤቶች እንደሚፈፀምና ለሙስና የተጋለጡ በርካታ ተቋማትን ኦዲት በማድረግ ይፋ የሚያደርገው የፌደራሉ ኦዲተር መስሪያ ቤት ሪፖርት በራሱ በቂ ማስረጃ ነበር፡፡ ነገር ግን ፀረ-ሙስና ኮሚሽኑ በቅርቡ እንደገለፀው በጠቅላይ ሚኒስትሩ አሳሳቢነትና ጥቆማ ካልሆነ በይፋ ለሙስና የተጋለጡ ጸቋማት ላይ የሚያደርገው ክትትልና ምርመራ እንደማይሰራም በተዘዋዋሪ መንገድ መግለፁ ከነ አቶ መላኩ ፈንታ እስር ጀርባ የፖለቲካ ጉዳይ እንዳለበት ቢያመላክት ስህተት ነው ማለት አይቻልም፡፡ ይህ ሲባል ግን ተጠርጣሪዎቹ ንፁኃን ናቸው፣ ሙስና አይፈፅሙም ማለት ሳይሆን ኮኮሚሽኑ እስካሁን የሚጠበቅበትን ምን ያህል ሰራ ብንል እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡

ጉዳዩ የሙስና ከሆነ አንድም የኢትዮጵያ ባለስልጣን ከሊቅ እስከ ደቂቅ ከሙስና ተግባር ሊነፁ እንደማይችሉ፤ ይህም የስርዓቱ መለያ ባህርይ በመሆኑ የፖለቲካ ልዩነት ሲያንፀባርቁ ብቻ ካርታ ለመምዘዝና የፖለቲካ ባርያ ለማድረግ በማሰብ ሙስና እንዲፈፅሙ እንደሚመቻች አንዳንድ የቀድሞ ታጋዮች ዛሬም ድረስ ይናገራሉ፡፡ ለአብነትም በ1993 ዓ.ም. በህወሓት መካከል የነበረውን ክፍፍል መሰረት በማድረግ ከነ ወንድሞቻቸው እንዲታሰሩ የሙስና ካርታ የተመዘዘባቸው የቀድሞ የህወሓት ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩትን አቶ ስየ አብርሃን እስር የሚያስታውሱ አልታጡም፡፡

በርግጥ የሙስና ተግባር ለሀገርና ለህዝብ ጠንቅ መሆኑ ቢታወቅ ኖሮ ህዝቡ ዛሬ የስቃይ ኑሮ ገፈት ቀማሽ ባልሆነ ነበር፡፡ ምክንያቱም ገዥው ኢህአዴግ አባላቱን ሲመለምል ቀድሞውንም ቢሆን ርዕዮተ ዓለሙን ሸጦና አሳምኖ ሳይሆን በፍቅረ ንዋይ የነደዱትን በማማለል እንደሆነ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ለዚህም ነው ዛሬ በሀገራችን የተማሩ አብዛኞቹ ወጣቶች በሙያቸው ሰርተው ተዓምር ለመፍጠር ከመሞከር ይልቅ የኢህአዴግ አባል በመሆን ትልቅ ስልጣን ላይ መውጣትን የሚሹት፡፡ የዚህም ምስጢር ያሉት የመንግስት ተቋማት በስርዓቱ ቸልተኝነት ለሙስና በመጋለጣቸው ነው፡፡

በአጠቃላይ ዛሬ የፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሙሰኞች ሲል የያዛውን ሰዎች በአቶመለስ ጥቆማ መሆኑን ከነገረን ነገ አቶ ኃይለማርያም ካልጠቆሙ ስራውን ሊያቆም ነው ማለት ነው ወይስ እንደለመደው ትናንሽ ዓሳዎችን ጃስ በማለት ጊዜውን ሊያባክን ነው; ይህን ወደፊት አብረን የምናየው ነው የሚሆነው፡፡ ምክንያቱም ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በፊት ለፊታቸው ምንም ያህል ሙስና በባልስልጣኖቹ ቢፈፀም እርምጃ እንዲወሰድባቸው የመጠቆምና የማዘዝ ድፍረቱ ይኖራቸዋል የሚል እምነት የለኝም፤ አቶ ኃ/ማርያም በራሳቸው አዲስ የአመራር ዕቅድ ከመከተል ይልቅ የሟቹን ጠቅላይ ሚኒስትር ሌጋሲ ለማስጠበቅ እየተጉ ነውና፡፡

ምንጭ፡- ኢቦኒ መፅሔት(ግንቦት 2005ዓ.ም.)

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: