በኢትዮጵያ ስኳር ፕሮጀክት ላይ የተጋረጠው አደጋ

ብስራት ወ/ሚካኤል

awash

ጨዋማው የኢትዮጵያ ሐይቅ 15 እጥፍ ይዘቱና ስፋቱ እየጨመረ በሀገሪቱ ታላላቅ ወንዞች መካከል አንዱ በሆነው ወንዝ ላይ ስጋትን ጭሯል፡፡ ይህ ስጋት በቡና አምራችነቷ ከአፍሪካ ታላቅ በሆነችው ሀገር ላይ አደጋ እያንዣበበ ነው፡፡

ጨዋማው ውሃ ታማኙንና ታላቁን አዋሽ ወንዝን በመበከል በኢትዮጵያ መንግስት ባለቤትነት በሚተዳደረው ስኳር ፋብሪካ እና ከህንድ ድጋፍ በማግኘት ስኳር ወደ ውጭ ላኪ ሀገሮች ተርታ  ለመሰለፍ ያለው ዕቅድ ላይ አደጋ ተጋርጧል፡፡ ስጋትን የጫረው ይህ ጨዋማው ሐይቅ የበሰቃ ሐይቅ ነው፡፡

የበሰቃ ሐይቅ በስምጥ ሸለቆ ውስጥ የሚገኝና ባለፉት ዓመታትም እጅግ እተስፋፋ ወደ መስኖው ውሃ እየተቃረበ ነው፡፡ ይህ ሐይቅ ወደ አዋሽ ወንዝ የሚገባ ከሆነ በኢትዮጵያ ግዙፍ የስኳር አምራችነት ዕቅድ ላይ የአደጋ ጥላ ያጠላል፡፡

እዚህ ላይ የውሃና ማዕድን ሚኒስቴር የከርሰ ምድር ውሃ ኃላፊ የሆኑት አቶ ተስፋዬ ታደሰ ‹‹ለወንዙ ነው የምንሰጋው፤ ከቁጥጥራችን ውጭ ሆኖ በራሱ ጊዜ ወደ ወንዙ የሚደባለቅ ከሆነ እስከወዲያኛው ወንዙን እየበከለው ይሄዳልና” ሲሉ መስጋታቸውን ገልፀዋል፡፡

አባይ ተፋሰስን ጨምሮ ከሀገሪቱ ከፍታ ቦታዎች የሚመነጩ ወንዞች ኢትዮጵያን ከአህጉራቱ አፍሪካ በሁለተኛ ደረጃ የውሃ ኃይል ባለቤት አድርጓታል፡፡ መንግስት ይህን ታሳቢ በማድረግ ከህንድ የገንዘብ፣ የሳውዲው ቢሊየነር እና ከቻይናው አበዳሪ ስኳር፣ ሩዝ፣ ሙዝና ብርቱካን ምርትን ለማስፋፋትና ወደ ውጭ ለመላክ ያለነዳጅ ዘይት በአፍሪካ ፈጣን ኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ አስባለች፡፡

የላይኛው አዋሽ ተፋሰስ ባለስልጣን የቴክኒክ ኃላፊ የሆኑት እንደሻው ታደሰ እንዳሉት ከሆነ የሰኔው ወቅታዊ ዝናብ ከመጀመሩ በፊት ሐይቁ ወደወንዙ እንዳይፈስ የሚቻለውን ጥረት ሁሉ እንዳደረጉ ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ፍሰቱ ከሀገሪቱ ዋና መናገሻ አዲስ አበባ በስተምስራቅ የጎርፍ መጥለቅለቅን በማስከተል በአካባቢው የነበሩትን አርብቶ አደሮች እንደሚያርቅ ይጠበቃል፡፡

በሰቃ ከ954 ሜትር የሚመነጭ ፍልውሃ በ1960ዎቹ ዓ.ም.(እ.ኤ.አ) 3 ስኩዌር ኪሎ ሜትር ይሸፍን የነበረው በአሁን ሰዓት 5 እጥፍ በማድረግ ወደ 45 ኪሎ ሜትር ስፋት በመጨመር ከአዲስ አበባ ወደ ጅቡቲ ወደብ ዋና የንግድ መስመር የሆነውን መንገድ አቅጣጫ ማስቀየሩም ግድ ይላል፡፡

ያልተሳኩ ጥረቶች

መንግስት ላለፉት 14 ዓመታት በየጊዜው ስፋቱና ይዘቱ እየጨመረ የመጣውን የበሰቃ ሐይቅ የማስቀየሻ ቦይ ግንባታ በመስራት እንዲፈስ ቢያደርግም ሐይቁን እንደባህር ባለበት ማስቀረት አልቻለም፡፡

በዚህ ላይ በ2009 (እ.ኤ.አ) እና ባለፈው ዓመት ጥናታቸውን ያቀረቡት የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በሲቪል ምህንድስና ረዳት ፕሮፌሰር የሆኑት መገርሳ ኦኩማና ደንቃ እንዳሉት ከሆነ በአካባቢው የመስኖ ፕሮጀክቱ መጨመር ውሃ ወደ ሐይቁ በመግባት ተመጋጋቢነት ይኖረዋል፡፡ ይህም በሚደረጉ የመስኖ እንቅስቃሴዎች ላይ ተፅዕኖ ሊኖረው ይችላል፡፡

አሁን ባለው የበሰቃ ዕድገት ባህርይ መተሐራ አካባቢ ያለውን መስኖ ከጥቅም ውጭ ሊያደርግ ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ በያዝነው ዓመት የተገዛውና ንብረትነቱ የመሐመድ አል አሙዲ የሆነው ሆራይዘን ፕላንቴሽን ከመንግስት የገዛው የላይኛው አዋሽ የግብርና ኢንዱስትሪንም አደጋ ላይ ይጥለዋል፡፡ ይህን በተመለከተ የሆራይዘን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ጀማል አህመድ ከሐይቁ ምንጭ ዕድገት ጋር ተያይዞ የተደረገውን ጥናት አላረጋገጥንም፣ ምናልባት በአካባው ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ይኖር ይሆናል ሲሉ ተናግረዋል ፡፡

ኢንቨስትመንት

አል አሙዲ የግብርና ምርት ወደሆኑት ሩዝ፣ ሙዝና የተጠናቀቀ ቡና ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ ለመላክ እንቅስቃሴ መጀመራቸው ይታወቃል፡፡ ስለሆነም ሆራይዘን በላይኛው አዋሽ 432 ሚሊዮን ብር ኢንቨስት በማድረግ የብርቱካን ምርትን በእጥፍ በማሳደግ ወደ 50,000 ቶን ለማድረስ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡

ከአዲስ አበባ በሰሜን ምስራቅ 380 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከህንድ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ በተገኘ 640 ሚሊዮን ዶላር ብድር እየተገነባ ያለው የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካም  የበሰቃ ሐይቅ ወደ አዋሽ ወንዝ በመግባት ወንዙ ጨዋማ የሚሆን ከሆነ አደጋ ይገጥመዋል፡፡ እንደሚታወቀው ህንድ በዓለም ሁለተኛ የስኳር አምራችና ከፍተኛ ተጠቃሚ ነች፡፡

ሌላው ወደ 30,000 ነዋሪዎች የሚገኙበት መተሐራ እና አዲስ ከተማ፣ መተሐራ ስኳር ፋብሪካን ጨምሮ በአፋር ክልል እየተገነባ ያለው ግዙፍ የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ የሐይቁ መስፋት እየቀጠለ ከሄደ ለአካባቢው አደገኛ ነው፡፡

ስኳርና ጥጥ

ሀገሪቱን ለረጅም ጊዜ የመሰረት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ መለስ ዜናዊ 90 ሚሊዮን የሚደርሰው የሀገሪቱ ነዋሪ ወደመካከለኛ ገቢ እንዲያድግ የጥጥ እርሻን አቅርቦት ተንተርሶ የሚገነቡት የጨርቃጨርቅ እንዱስትሪዎች ማደግ እንዳለባቸው ዕቅድ ነድፈዋል፡፡ ይህ የጥጥ እርሻ ልማት ደግሞ ለመካከለኛው አዋሽ በአሚባራ ቢዝነስ ግሩፕ የሚመራው ኢንዱስትሪም የበሰቃ ሐይቅ ከአዋሽ ወንዝ ጋር በመቀየጥ ጨዋማ የሚሆን ከሆነ እሱም አደጋ ተጋርጦበታል፡፡ እንደዓለም አቀፍ የውሃ አስተዳደር ተቋም መሰረት ከ1984 ዓ.ም.(እ.ኤ.አ) ጀምሮ በፊት በመንግስት ቁጥጥር ስር የነበረ 2,000 ሄክታር በጨዋማ ውሃ ምክንያት ከጥቅም ውጭ ሆኗል፡፡

አሚባራ መካከለኛው አዋሽ የግብርና ልማት ድርጅት ምክትል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ውብሸት ይልማ እንዳሉት ከሆነ ‹‹ከዝናቡ በፊት የሐይቁ መስፋፋት ያሳስበናል፤ ምክንያቱም ሐይቁ ወደ አዋሽ የሚገባ  ከሆነ ለአማባራ ጥጥ እርሻ ችግሩ ከፍተኛ ነው የሚሆነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

የትምህርት ቤት መስጠም

በኢትዮጵያ መንግስት ንብረት የሆነውና በአፋር አካባቢ የተቋቋመው የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካን ጨምሮ በአዋሽ ወንዝ ግድብ ግንባታ ላይ መሰረት በማድረግ ከ600,000 ቶን በላይ የሸንኮራ እገዳ በዓመት ለማልማት የነበረው እቅድ ላይ ጨዋማ ውሃ የሚፈስ ከሆነ አሁንም እቅዱ ይጨናገፋል፡፡

በተለይ አቶ እንደሻው እንደተናገሩት ከሆነ “ዝናብ የሚዘንብ ከሆነ በቃ” ሲሉ ባለፈው ዓመት በሐይቁ ሙላት ምክንያት የሰጠሙ ሁለት ትምህርት ቤቶችን አስታውሰዋል ፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሐይቁን ስፋት ተከትሎ በተፈጠረ ድርቅ በተወሰደ እርምጃ በ2008 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) ክልላዊው መንግስት በ467 ሚሊዮን ብር የፈንታሌ መስኖ ቦይ ግንባታ መደረጉን የኢትዮጵያ ውሃ ስራዎች ዲዛይንና ቁጥጥር ድርጅት የውሃ ምህንድስና ኃላፊው እንግዳ ዘመዳገኘሁ ተናግረዋል፡፡

በተለይ እንደ አቶ ተስፋዬ ገለጻ ወንዙ 4 በመቶ የሐይቅ ውሃ የሚይዝ ቢሆን እንኳ በማንኛውም መልኩ አደገኛ ነው፡፡ ለዚህም በሚል በፓንፕ (ውሃ መሳቢያ መሳሪያ) ብዙ ውሃ ለመቀነስ ጥረት ብናደርግም መስፋፋቱን ግን ሊቀንስ አልቻለም ሲሉ አስታውሰዋል፡፡

በማኛውም አጋጣሚ ሐይቁ እየጨመረ ከሄደ “ሐይቁ ወደ አዋሽ ወንዝ የመፋሰስ አቅም ይኖረዋል፡፡ ይህ ደግሞ በሚቀጥሉት ቅርብ አመታት የመተሐራ ስኳር ፋብሪካን ያወድማል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ  ተንዳሆን ጨምሮ በአዋሽ ተፋሰስ በሚገነቡ በሁሉም ግዙፍ መስኖ ልማቶችም ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ይኖረዋል” ሲሉ ፕሮፌሰር መገርሳ ተናግረዋል፡፡

 የእሾሃማ ዛፎች እጣ ፈንታ

በመንግስት ባለቤት ከሚገነባው ተንዳሆ ስኳር ውጭ በኬንያ አቅራቢያ በደቡብ ኦሞ የሚገነቡትን 6 የኩራዝ ስኳር ፕሮጀክቶች ጨምሮ 10 ግንባታዎች ይካሄዳሉ፡፡ ከነዚህ መካከል በቻይና ዴቨሎፕመንት ባንክ የሚደረግ 150 ሚሊዮን ዶላር ብድር ድጋፍ በአዋሽ አካባቢ የሚገነባ የከስም ስኳር ፕሮጀክት ይገኛል፡፡ በዚህ ዙሪያ የስኳር ኮርፖሬሽን ስራ አስኪያጅ ቃል አቀባይ አቶ ይልማ ጥበቡ ከመጋቢት አጋማሸ ጀምሮ አስተያየት ቢጠየቁም ምላሽ እንዳልሰጡ የብሉምበርጉ ዘጋቢ ዳቪሰን አስታውሷል፡፡

ከኢትዮጵያ ከፍታ ቦታዎች በመመንጨት በሰሜን ምስራቅ ወደ አፋር በመፍሰስ ጅቡቲ አካባቢ ከመድረቁ በፊት አዋሽ ወንዝ 1,200 ኪ.ሜትር ይጓዛል፡፡ ከመተሐራ አካባቢ ጀምሮ ባሉ በአካባቢው ያሉ እሾሃማ ዛፎች(ግራርና ቆንጥር) በተጨማሪ በአካባቢው ሞቃታማ ስፍራ የሚበቅሉ የምግብ እህሎችን ተንተርሰው እየኖሩ ያሉ 1.5 ሚሊዮን ህዝብ አለ፡፡ ለነዚህ ህዝብ በተለይም የአፋር አርብቶ አደሮች ለረጅም ጊዜ ህይወታቸውን እዚህ ወንዝ ላይ መሰረት ያደረጉ ናቸው ፡፡ ስለዚህ የአዋሽ ወንዝ በበሰቃ ሐይቅ ብክለት የሚያጋጥመው ከሆነ ለእነኛ ነዋሪዎች አደገኛ ነው የሚሆነው ሲሉ ፕሮፌሰሩ ያላቸውን ስጋት ገልፀዋል፡፡

አቶ ተስፋዬ በበኩላቸው የከፍተኛ ባለሙያዎችና የመንግስት ባለስልጣናት ስብስብ ስለሐይቁ እንዴት እያደገ እንደመጣ ጥናትና ምክክር እየተደረገ ነው፡፡ በአሁን ሰዓት ግን ምን መደረግ እንዳለበት የተያዘ አቅጣጫም ሆነ የተወሰደ እርምጃ የለም ሲሉ ማከላቸውን ሚያዚያ 24 ቀን 2013 (እ.ኤ.አ) በብሉምበርግ ድህረ-ገፅ ዊሊያም ዳቪሰን አስነብቧል፡፡

አሁንም ቢሆን ከአዲስ አበባ ወደምስራቅ 195 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው የመተሐራ በሰቃ ሐይቅ ዘላቂ መፍትሄ ካልተገኘለት በአዋሽ ተፋሰስ ላይ በብዙ ቢሊየኖች ብር ግንባታቸው ተካሂደው በስራ ላይ ያሉ የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ፤ በቅርቡ ስራ ይጀምራል ተብሎ የሚጠበቀው የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ፣ በስራ ላይ ያሉት የላይኛውና መካከለኛው አዋሽ የግብርና እንዱስትሪዎች እንዲሁም በእቅድ ላይ ያለው የከሰም ስኳር ፕሮጀክት በተጨማሪ የመተሐራን ከተማ ነዋሪዎችና አዋሽ ወንዝን ተጠግተው የሚኖሩ የአፋር ክልል ነዋሪዎችን በነበሩት ዳግም ላናገኛቸው እንችላለን፡፡

ከላይ የተጠቀሰው የብሎምበርግ ዘገባ እንደሚያሳየው ከሆነ የኢትዮጵያ መንግስት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ነድፎ ተግባራዊ ሲያደርግ ከሚፈልገው ገንዘብ ውጭ አካባቢያዊ ጥናት የማድረግ ትኩረትም ሆነ ፍላጎት እንደሌለው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት መጨው ትውልድ ላይ ጭምር ዕዳ ተጥሎ የሚገነቡ ፕሮጀክቶች የሚጠበቅባቸውን ውጤት ሳያስገኙ በሚደርስባቸው የአካባቢ አደጋ በሀገር ላይ ከፍተኛ የሃብት ውድመት ማስከተላቸው የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት የግብር ውጣ ስራ የሚያደርገውን የዘመቻ የልማት ፕሮጀክቶች ስራ አካባቢውንና ተፈጥሯዊ ሁነቶችን ከከፍተኛ ባለሙያዎች ጋር ማጤንና ማገናዘብ አለበት፡፡

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Twitter picture

You are commenting using your Twitter account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

%d bloggers like this: