በጉጂ ዞን ያለው ውጥረት እስካሁንም አለመብረዱ ተገለፀ
በደቡብ ኢትዮጵያ ኦሮሚያ ክልል በሚገኘው ጉጂ ዞን ባለፈው መጋቢት 4 ቀን 2006 ዓ.ም. በኦዶ ሻኪሶ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች እና ከዞኑ ከተማ መስተዳደር ጋር በተፈጠረው አለመግባባት ሁለት ወጣቶች በፌደራል ፖሊስ መገደላቸውን ተከትሎ የፈጠረው ውጥረት እስካሁንም አለመብረዱ ተገለፀ፡፡ እንደምንጮች ገለፃ ከሆነ የ9ኛ ክፍል ተማሪ የሆነችው ብስራት ኃይሌ እና በግብርና ሙያ የሚተዳደረው ወጣት ሀለቄ ሮባ በከተማው የዕለት ስራውን ለማከናወን እየተንቀሳቀሰ ሳለ በፌደራል ፖሊስ በተወሰደ የጥይት ተኩስ እርምጃ ወዲያው ህይወታቸው አልፏል፡፡
በፌደራል ፖሊስ ተገደሉ ከተባሉት ተማሪዎች በተጨማሪ በከተማው ማንነቱ ባልታወቀ አካል በተተኮሰ ጥይት አንድ የፌደራል ፖሊስ ላይ ከፍተኛ አደጋ በመድረሱ ወዲያው ወደ አዲስ አበባ ለህክምና መላኩን እና በከተማውም ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሌሎች ነዋሪዎች ላይ በፖሊስ በተወሰደ የኃይል እርምጃ ቆስለው በከተማው ሆስፒታል ህክምና እርዳታ ያገኙም እንዳሉበት የአዲስሚያ ምንጮች ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በጉጂ ዞን ባሉ 15 ወረዳዎች እና በሶስቱ ከተማ መስተዳደሮች ነጌሌ ቦረና፣ ክብረ መንግስትና ኦዶሻኪሶ በነዋሪውና በመንግስት ኃላፊዎች መካከልበተፈጠረ አለመግባባት እስካሁን ውጥረቱ አለመርገቡ እና ችግሩ በዞኑ ባሉ ገጠሮች ድረስ መዛመቱም ተጠቁሟል፡፡ የግጭቱ መንስኤም ተማሪዎቹ ለአስተዳዳሪዎቹ ባነሱት የመጠጥ ውሃ፣ የመብራትና ተያያዥ የመብት ጥያቄዎች መሆኑንም መዘገባችን ይታወሳል፡፡
በዚህ ዙሪያ የመንግስት ኃላፊዎች እስካሁን ምንም የሰጡት ማስተባበያም ሆነ መልስ ባይኖርም፤ በወጣቶቹ መገደል በተፈጠረው ውጥረት የአካባቢው የመንግስት ሹማምንት ዛሬ እሁድ መጋቢት 7 ቀን 2006 ኣ.ም. ከጠዋቱ 3 ሰዓት በጉጂ ዞን አንድነት ፓርቲ የገንዘብና ንብረት ክፍል ኃላፊ የሆኑትን አቶ ዮሐንስ ኢብሶን ተማሪዎቹ ላነሱት ጥያቄ ምክንያት ናቸው በማለት መንግስት ማሰሩ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡