መንግሥት ራሱ በጠራው ሰልፍ በርካታ ሰዎችን ሲደበድብ፤ ከመቶ በላይ ሰዎች ታስረዋል
ሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መንግሥት በሊቢያ፣በደቡብ አፍሪካና በየመን ኢትዮጵያውያን በግፍ መገደላቸውን በተመለከተ በአዲስ አበባ ድርጊቱን ለማውገዝና ለመቃም ሰልፍ ጠርቶ የነበረ ቢሆንም፤ በሰልፍ የተገኙ በርካታ ሰዎች በፖሊስ ተደብድበው ወደ አካባቢው ሆስፒታሎች የተወሰዱ ሲሆን፤ ከ100 በላይ ሰዎች መታሰራቸውንም አልጀዚራን ጨምሮ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ከስፍራው በቀጥታ ዘግበዋል፡፡ በተለይ በአሸባሪው በ አይ ኤስ አይ ኤል (ISIL) ቢያንስ 28 ኢትዮጵያውያን በጭካኔ መገደላቸውና መንግሥትም ለዚህ ያሳየው ቸልተንነት ህዝቡን የበለጠ በማስቆጣቱ ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ያለማንም ቀስቃሽ የአዲስ አበባ ነዋሪ ለተቃውሞ ሰልፍ ቢወጣም መንግሥት ፈቃድ አልሰጠሁም በሚል በርካቶች ከደበደበ በኋላ ለሚያዝያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. ራሱ ድርጊቱን በመቃወም ሰልፍ ቢጠራም መጨረሻው በፖሊስ ከፍተኛ ድብደባና እስር ተጠናቋል፡፡ ሰልፉ ከመጀመሩ በፊት የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶችን ጨምሮ በርካታ ወጣቶች ወደሰልፉ ሲሄዱ የታሰሩ ሲሆን፤ ከሰልፉ በኋላ የመንግሥት ባለሰልጣናት መስቀል አደባባይ ንግግር ሲያደርጊ ህዝቡ በልቅሶ ተቃውሞ ካሰማ በኋላ የአዲስ አበባ እና የፌደራል ፖሊስ እዛው ሰልፉ ቦታ ሲደበድብ ታይቷል፡፡ ይሄንንም የተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን በቀጥታ አሰራጭተዋል፡፡
ዓለም አቀፍ አሸባሪው ቡድን ISIL በሊቢያ የገደልኩት ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን ቢልም፤ በአዲስ አበባው ተቃውሞ የእስልምና እና የክርስትና ኃይማኖት ተከታዮች በጋራ ድርጊቱን ሲያወግዙ ተስተውሏል፡፡ በዕለቱም በርካታ መፈክሮች የተሰሙ ሲሆን፤
ታርዷል ወገኔ፣ ታርዷል ወገኔ…(በኡኡታና ልቅሶ)
ሽብርን እንቃወማለን፣እናወግዛለን
መንግሥት ኃላፊነቱን አልተወጣም
ሞት ለወያኔ፤ ያረደንም ያሳረደንም ወያኔ ነው
ይለያል ዘንድሮ የዌኔ ኑሮ
ውሸት ሰለቸን፤ የወንድሞቻችን ደም ይመለስ
የሀገር ውስጥ ISIL ወያኔ ነው፤…በቃን
ISIL እስልምናን አይወክልም፤ እኛ የኢትዮጵያውያ ሙስሊሞች ወንድሞቻችን ክርስቲያኖች በአሸባሪ ቡድኑ መገደላቸውን አጥብቀን እናወግዛለን፤ ድርግቱም ሽብር እንጂ እስልምናን አይወክልም (በተለይ በሰልፉ የተገኙ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች)
መንግሠት የሌለው እዚህ ብቻ ነው
የኢትዮጵ አምላክ ይፍረድ (በተለይ የሟቾቹ ቤተሰቦች)
ና ና መንጌ ና ና (የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዘዳንት መንግሥቱ ኃይለማርያምን)
የቤት አንበሳ የውጭ እሬሳ (መንግሥትን) የሚሉ መፈክሮች ይገኙበታል፡፡
በመጨረሻም በመንግሥት ላይ የህዝቡ ተቃውሞ ተጠናክሮ ሲቀጥል የመንግሥት ባለስልጣናት ንግግር በቅጡ ሳይሰማ የተቋረጠ ሲሆን፤ ፖሊስም ወዲያውኑ ያገኘውን ሁሉ እያሳደደ ሲደበድብ ለማየት ተችሏል፡፡ በቂርቆስ ሰፈር ልቅሶ ቤት አካባቢ በነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻ በስፍራው እጅግ በርካታ ፖሊሶች በስፍራው የነመበሩ ሲሆን፤ በኋላም ከፍተኛ የመሳሪያ ተኩስ ተሰምቷል፡፡ እስካሁን ባለው መረጃ በተተኮሰው ጥይት በሰው ህይወትና አካል ላይ ጉዳት ስለማደረሱ የተረጋገጠ መረጃ ባይኖርም መስቀል አደባባይ በነበረው የፖሊስ ድብደባ ራሳቸውን ስተው የወደቁ ሴቶች፣እናቶችና ወጣቶች የታዩ ሲሆን፤ ብዙ ወጣቶች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸው በአምቡላንስ እና በሰው እግዛ ወደ ህክምና ጣቢያ ሲሄዱና የህክምና እርዳታ ሲደረግላቸው ታይቷል፡፡
መንግሥትም በተመሳሳይ በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የሽብር ድርጊቱን በመቃወም በመዋቅሩ ሰልፍ ማዘጋጀቱና ለዚህም የኢህአዴግ ሊግና ፎረነም አባላት ከየቀበሌው በነበረው መዋቅር ወደሰልፍ እንዲወጡ፣ ሌላ ወደተቃውሞው ሰልፍ የሚመጣ ካለ በደንብ ከበው እንዲከታተሉት፣ መፈክሮችም በኢህአዴግ ብቻ እንዲዘጋጅ ከዛ ውጭ ያለ መፈክር ይዞ የሚመጣ ማንኛውም አካል ካለ ወደሰልፉ መሐል ከመቀላቀሉ በፊት ጥብቅ ምርመራ መደረግ እንዳለበት ትዕዛዝ መሰጠቱንም ምንጮች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡
በተለይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ቀደም ሲል የሽብር ድርጊቱን በማውገዝ መንግሥት እርምጃ እንደሚወስድ በፌስ ቡክ ግድግዳቸው ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቢናገሩም፤ በመጨረሻም አሸባሪው ድርጅት ላይ በመንግሥት እርምጃ ይወሰዳል ተብሎ ሲጠበቅ፤ በአዲስ አበባ ሰልፈኛ ላይ እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡ መንግሥት በበኩሉ እርምጃ የተወሰደው ፖሊሶች ላይ ድንጋይ ስለተወረወረ ነው የሚል ምክንያት ሰጥቷል፡፡
በተለይ በሊቢያ የሟቾች ማንነት እየተለየ ሲሆን፤ ስማቸውም ኢያሱ ይኮኖአምላክ፣ ባልቻ በለጠ፣ ብሩክ ካሳ፣ በቀለ ታጠቅ እና ኤልያስ ተጫኔ ከአዲስ አበባ ቂርቆስ ሰፈር፤ መንግሥቱ ጋሼ እና አወቀ ገመቹ ከወለጋ ነቀምት፣ በቀለ አርሰማ ከጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ ካራቻ አካባቢ፣ የጅማ ዩኒቨርስቲ ምሩቅ የነበረው ዳንኤል ሓዱሽ፣ አለም ተስፋይ እና ዳዊት ሀድጉ ከትግራይ መቀሌ አካባቢ፣ ክርስቲያን ወንድሞቼን ለይታችሁ አትገድሉም፤ በእስልምና የሰውን ህይወት ማጥፋት ኃጥትም ወንጀልም ነው፣ እኔ ከእነሱ አልለይም በማለት ሲከራከር የነበረው ኢትዮጵዊው ሙስሊም ጀማል ረህማንም አብሮ መገደሉ ታውቋል፡፡ በአሸባሪው ቡድን ከተገደሉ ኢትዮጵያውያን ጋር ተስፋይ ኪዳኔን ጨምሮ ሶስት ኤርትራውያንም እንደሚገኙበት የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ ተስፋይ ከዚህ በፊት በእስራኤል ጥገኝነት ጠይቆ በመከልከሉ በሊቢያ ወደ አውሮፓ ለመሄድ ሲሞክር በአሸባሪ ቡድኑ እጅ መግባቱ ተጠቁሟል፡፡
በአዲስ አበባ የተቃውሞና የሀዘን ሰልፍ በመንግሥት ተበተነ፤በሊቢያ አሁንም በርካታ ኢትዮጵያውን የአድኑን ጥሪ እያሰሙ ነው
ዛሬ ሚያዚያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም. ባለፈው እሁድ በበኣለም አቀፉ አሸባሪው አይ ኤስ አይ ኤል በተባለው ቡድን በሊቢያ በጥቂቱ 28 ኢትዮጵያውያን በመገደላቸው በመላው ኢትዮጵያውያን ሀዘኑ የበረታ ቢሆንም፤ በአዲስ አበባ ግን ህዝቡ በራሱ አነሳሽነት የተቃውሞና የቁጣ ሰልፍ ወጥቶ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ህዝቡ ከተገደሉት መካከል የአዲስ አበባ ቂርቆስ ሰፈር ቀበሌ 25 ነዋሪ የነበሩት ጓደኛሞች ኢያሱ ይኮኖአምላክ እና ባልቻ በለጠ ቤተሰብ ልቅሶ ከደረሱ በኋላ በርካታ ሰዎች “አንመካም በጉልበታችን …” መዝሙር፣”ወያኔ ሌባ…ኢቴቪ ሌባ…መንግሥት የሌለው እዚህ ብቻ ነው፣ ታርዷል ወገኔ…” የሚሉ መፈክሮች፣ ልቅሶና ተቃውሞ እያሰሙ ወደ ቤተመንግሥት ለማቅናት ሲሞክሩ በተደጋጋሚ በአዲስ አበባና በፌደራል ፖሊስ ሲከለከሉ ታይቷል፡፡
ህዝቡ የመጀመሪያ መነሻውን ከልቅሶ ቤት ያደረገ ሲሆን በሌላ በኩል ከቄራ ቡልጋሪያ ሰፈርና ከሳሪስ ጎተራ ሪቼ መሷለኪያ ባለው መንገድ እንዲሁም ከሜክሲኮ መስመር ወደመስቀል አደባባይ ሲመጡ አብዛኞቹ በፖሊስ ድብደባና ክልከላ እንዲበተኑ መደረጉን ታውቋል፡፡ በመጨረሻም በተደጋጋሚ በፖሊስ አገታና የተደረገበት የሪቼው፤የሟቾቹ ቤተሰቦች ያሉበት ከቂርቆስ ሪቼ መስቀል አደባባይ የነበረው ሰልፍ እስጢፋኖስን አልፎ ወደ ውጭበ ጉዳይ ሚኒስቴር አካባቢ ሲደር ሙሉ ለሙሉ በፖሊስ ከታገተ ቧላ መንግሥት ለነገ ሐሙስ ሚያዚያ 14 ቀን 2007 ዓ.ም. ሰልፍ መጥራቱን አስታውቋል፡፡
ዛሬ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ድርጊቱን በማውገዝ ከነገ ጀምሮ የ3 ቀናት ብሔራዊ ሀዘን ያወጀ ሲሆን፤ የሀገሪቱ ሰንደቅዓላማም በመላ ሀገሪቱ እና የኢትዮጵያ ኤምባሲና ቆንስላ ጽህፈት ቤት በሚገኙበት ሁሉ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ተወስኗል፡፡ በተለይ በፓርላማ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የተሰማቸውን ሀዘን ከገለፁ በኋላ መንግሥት እርምጃ እንደሚወስድ ቢናገሩም ምን ዓይነት እርምጃ በመንግሥት እንደሚወሰድ ግን እስካሁን በዝርዝር አልገለፁም፡፡
በኢትዮጵያውን ላይ በአሸባሪ ቡድኑ የተፈፀመውን ጥቃት ኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ፣ የአሜሪካ መንግሥት፣ በእንግሊዝ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ፣ የሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን እና በውጭ የሚገኘው የኢትዮጵያው ፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን በትናንትናው ዕለት ድርጊቱን ወዲያው አውግዘዋል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት፣ መድረክ፣ ሰማያዊ ፓርቲ፣ ኢዴፓ፣ ድምፃችን ይሰማ ድርጊቱን በመቃወም አውግዘው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በተለይ ከህዝቡ ቁጣን የቀሰቀሰው የኢትዮጵ መንግሥት አሸባሪ ቡድኑ ኢትዮጵያውን ክርስቲያኖችን መግደሉን ቢያሳውቅም፤ የኢትዮጵያ መንግሥት እና በአዲስ አበባ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶስ ድርጊቱ ቢያወግዙም ዜግነታቸው ኢትዮጵያውያን ስለመሆናቸው አላጣራንም ካሉ በሁለተኛው ቀን አምነው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ መንግሥትም ሆነ ቤተክርስቲያኗ ከማመናቸው በፊት ከተገደሉት ኢትዮጵያውን መካከል የኢያሱ እና ባልቻ ቤተሰቦች ቀድመው በማወቅ ልቅሶ መቀመጣቸው ታውቋል፡፡ ይህም በህዝቡ ዘንድ ቅሬታን ፈጥሯል፡፡ ዛሬ ዘግይቶ በተገኘው መረጃ መሰረት ከተገደሉት መካከል ቀደም ሲል ኢያሱና ባልቻ የታወቁ ሲሆን፤አሁን ደግሞ ከመቀሌ አካባቢ የጅማ ዩኒቨረስቲ ምሩቅ የነበረው ዳንኤል ሓድሽ እና አለም ተስፋይ እንዲሁም አንድ ኤርትራዊ እንደነበሩበት መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በአሁን ሰዓትም በርካታ ኢትዮጵውያን ከሊቢያ ትሪፖሊ ባልታወቁ ሰዎች ታፍሰው መወሰዳቸውን እና በስከተማው እና በሊቢያ ባህር ዳርቻ አካባቢ ከአሸባሪ ቡድኑ ጥቃት የተደበቁ በርካታ ኢትዮጵያውያን የአድኑን ጥሪ በማሰማት ላይ ይገኛሉ፡፡
በሊቢያ ዓለም አቀፉ አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው አሸባሪ ድርጅት 28 ኢትዮጵያውያንን በሊቢያ መግደሉን አስታወቀ
በኢራቅና በሶሪያ በሚፈፅማቸው አሰቃቂ ድርጊቶች የሚታወቀው አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው አሸባሪ ድርጅት አካል ዛሬ ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. 28 ኢትዮጵያውያንን በለመደው አሰቃቂ ግድያ መፈፀሙን የሚገልፅ ቪዲዮና ምስል ለቋል፡፡ 29 ደቂቃ የፈጀው ቪዲዮ መረጃ መሰረት 12ቱ በምስራቃዊ ሊቢያ ባህር ዳርቻ አንገታቸውን ሲቀላ፤ከ16 ያላነሱትን ደግሞ በደቡባዊ ሊቢያ በረሃ ላይ በጥይት ደብድቦ መግደላቸውን ይፋ መደረጉን ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል፡፡ ቡድኑም አሰቃቂ ግድያውን ሲፈፅም የጠላታችን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የመስቀሉ ተከታዮች የሚል ግልፅ ፅሑፍና ንግግር አድርጓል፡፡
ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ስለጉዳዩ ከሮይተርስ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ለቀረበላቸው ጥያቄ በቡድኑ የተገደሉት ኢትዮጵውን ስለመሆናቸው በግብፅ ከሚገኘው የኢትዮጵ ኤምባሲ ማረጋገጫ አላገኘንም የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡ አሸባሪ ቡድኑ ግድያውን የፈፀመው ሊቢያ ውስጥ እንጂ ግብፅ እንዳልሆነ ይታወቃል፡፡ የሟቾችም የቪዲዮ ምስል ቡድኑ ከገለፀው በተጨማሪ የተለመደው ኢትዮጵያዊ ገፅታ በግልፅ ይታያል፡፡ ቡድኑም ግድያውን የፈፀመበትን ሲናገር ሟቾቹ የነበሩትን የክርስትና ኃይማኖት ክደው እስልምናን እንዲቀበሉና በሊቢያ ለሚገኘው የአሸባሪው ቡድን አካል ልዩ ግብር ቢከፍሉ እንደሚለቀቁ የቀረበባቸው አስገዳጅ ጥያቄ ባለመቀበላቸው እርምጃውን መውሰዱን አስታውቋል፡፡
ቡድኑ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ መልኩ ከ30 ያላነሱ የግብፅ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችን መግደሉን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ፤ ግብፅ ብሔራዊ የሀዘን ቀን በማወጅ በሊቢያ የቡድኑ ይዞታ ነው በተባለ ቦታ በአየር ኃይሏ ተደጋጋሚ ድብደባ በማድረግ ፈጣን የአፀፋ መልስ መስጠቷ ይታወቃል፡፡ አይ ኤስ አይ ኤል የተባለው ይህ አሸባሪ ቡድን በኢራቅና በሶሪያ በተመሳሳይ መልክ የበርካታ ክርስቲያኖችን እና ከሱ ወገን አይደሉም ያላቸው ሙስሊሞች ላይ ተመሳሳይ አሰቃቂ ግድያ መፈፀሙና አሁንም በዚህ ተግባሩ ላይ መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተያያዘ ዜና አሁንም አሸባሪ ቡድኑ በቅርብ ከሚገኝበት ሊቢያ ከ90 በላይ ኢትዮጵያውያን ተሸሽገው የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ መሆኑን እና፤ ተደብቀው ምግብ ሳይበሉ ከተቆለፈባቸው 3 ቀናት እንደሞላቸው የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከ40 የማያንሱ ኢትዮጵውያን በዛው ሊቢያ የወደብ ከተማ በሆነችው ትሪፖሊ ወደ አውሮፓ ለመሻገር መርከብ በመጠባበቅ ላይ ሲሆኑ፤ በስፍራው በርካታ ኢትዮጵውን ሴቶችና ህፃናትም እንደሚገኙበትና በአቅራቢያቢያው የአሸባሪው ቡድን አካላት ስለሚንቀሳቁ ስጋት ላይ በመውደቃቸው እነሱም የአስቸኳይ የድረሱልን ጥሪ ማሰማታቸው ታውቋል፡፡በትናንትናው ዕለትም ከዚህ ከትሪፖሊ ወደ አውሮፓ 700 አፍሪካውያንን ስደተኞች የያዘች መርከብ መስጠሟን እና እስካሁን በአውሮፓ የነፍስ አድን ሰራተኞች የ28 ሰዎች ህይወት ብቻ ማትረፍ መቻሉ የተዘገበ ሲሆን፤ ተጓዦች ውስጥ ኢትዮጵያውያንም እንደሚኖሩበት ይገመታል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በየመን ባለው ጦርነት ምክንያት ባለፈው መጋቢት 2007 ዓ.ም. በስደተኛ መጠለያ ያሉ 46 ኢትዮጵያውን በሳውዲ ዓረቢያ የቶር አውሮፕላን መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን፤ በርካታ ኢትዮጵያውያን የሚታደጋቸው አጥተው አሁንም በየመን ስቃይ ላይ በመሆናቸው የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ ይገኛሉ፡፡
በደቡብ አፍሪካ የ7 ሰዎችን ህይወት ያጠፋው የጥላቻ አመፅ ወደሌሎች ከተሞችም መዛመቱ እየተነገረ ነው
በደቡብ አፍሪካ በያዝነው ሚያዝያ ወር 2007 ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ በወደብ ከተማዋ ደርባን ጥቁር የውጭ አፍሪካውያን ነጋዴዎች ላይ የተቀሰቀሰው ጥላቻ የ6 ሰዎች ህይወትን እንዳጠፋ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያ ዘገባ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በሌሎች የአፍሪካ ጥቁር ዜጎች ላይ የተጀመረው ጥላቻ ከደርባን ከተማ ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የተዛመተ ሲሆን፤ ትናንት ቅዳሜ ጆሃንስበርግ ከተማ ላይ አንድ ሞዛምቢካዊ መግደላቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
በጥቃቱ በብዛት ሰለባ የሆኑት የኢትዮጵያ፣ የሶማሌ፣የናይጄሪያ፣የሞዛምቢክ፣የዙምባቤና የማላዊ ዜጎች የገለፀ ሲሆን፤ ከተገደሉት መካከልም 3ቱ ኢትዮጵውን መሆናቸውን የተለያዩ ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በጥቃቱ ምክንያት ኬንያ፣ ማላዊ እና ዙምባቤ ወዲያውኑ ዜጎቻቸውን ከደቡብ አፍሪካ ለማስወጣት የሞከሩ ሲሆን፤ በተለይ ዙምባቤ እና ቦትስዋና ዜጎቻቸው በሰላም እስኪወጡ ድረስ ከጥቃቱ ለመከላከል ልዩ የጦር ኃይል ወደስፍራው መላካቸው ተሰምቷል፡፡ ሞዛምቢክ በበኩሏ ዜጎቿና የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ሌሎች ጥቁር አፍሪካውያንን ለመታደግ ድንበሯን የከፈተች ስትሆን፤ ጥቃቱ ወዳለበት ስፍራ ድረስ በመሄድ ዜጎቻቿን ለመታደግ ትራስፖርትና አስፈላጊውን ነገር ሁሉ ስታቀርብ ተስተውሏል፡፡
በተለይ ናይጄሪያና የሶማሊያ መንግሥት ድርጊቱን ከማውገዝ አልፎ፤ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት የተፈጠረውን ቀውስ በአስቸኳይ እንዲቆጣጠርና እንዲያቆም ማስጠንቀቂያ ጠይቀዋል፡፡ በናይጄሪያ በዓለም አቀፍ አሸባሪነት የተፈረጀው ቦኮ ሃራም በበኩሉ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት በናይጄሪያውያን ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በ24 ሰዓታት ውስጥ ማስቆም ካልቻለ በምዕራብ አፍሪካ ባሉ የደቡብ አፍሪካ ኤምባሲና ዜጎቿ ላይ እርምጃ እንደሚወስድ ከመዛት በተጨማሪ የደቡብ አፍሪካዋን ጆሃንስ በርግን ባግዳድ አደርጋታለሁ ሲል ማስጠንቀቁ አነጋግሯል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ በደቡብ አፍሪካ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አገኘሁት ባለው መረጃ መሰረት በጥቃቱ የሞተው አንድ ኢትዮጵዊ መሆኑን በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮረፖሬሽን አስታውቋል፡፡
በደርባን የተቀሰቀሰው በተለምዶ የውጭ ሀገር ዜጋን የመጥላት “ዜኖፎቢያ” ዘመቻ በአሁን ሰዓት ጋብ ያለ ቢመስልም፤ወደተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች መዛመቱንና ችግሩ ከከተማ ውጭ የሚሰሩ ሌሎች ጥቁር የአፍሪካ ዜጎች አደጋ ላይ መሆናቸውንና እስካሁንም የደረሰባቸውን ችግር ለማወቅ እንዳልተቻለም ተጠቁሟል፡፡ ድርጊቱንም የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ፕሬዘዳንት ጃኮብ ዙማና የተለያዩ የሀገሪቱ ዜጎች በይፋ ቢቃወሙም፤የአመፁ ዋና ቀስቃሽ ተደርገው የተወሰዱት በደርባን ያሉት የዙሉ ጎሳ ንጉስ ጉድዊል በወቅቱ በአንድ መድረክ ባደረጉት የጥላቻ ንግግር መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የፕሬዘዳንቱ ጃኮብ ዙማ ልጅም ድርጊቱን የሚያበረታታ ነገር ከዚህ በፊት በሌላ መድረክ መናገራቸው እየተጠቆመ ይገኛል፡፡ በጥቃቱም ሁለት ጥቁር አፍሪካውያን ከነ ህይወታቸው በደቡብ አፍሪካውያን የተቃጠሉ ሲሆን ሌሎቹ ስለት ባላቸው መሳሪያዎችና በድንጋይ ተደደብድበው መገደላቸው ታውቋል፡፡
በተቀሰቀሰው የጥላቻ አመፅም የኢትዮጵያውንን ጨምሮ የበርካታ የጥቁር አፍሪካውያን ሱቆች ተዘርፈዋል፣ ከዝርፊው የተረፉትም ተቃጥለዋል፡፡ ድርጊቱን ዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ቢያወግዘውም ወደሌሎች ከተሞች መዛሙቱ አሁንም ስጋትን ጭሯል፡፡ በርካቶችም የንግድ ሱቆቻቸውን ጥለው በተለይ በደርባን ከተማ ጊዘየያዊ የስደተኛ መተጠለያ ጣቢያና በፖሊስ ጣቢያዎች እንደተጠለሉም ለማወቅ ተችሏል፡፡ በደቡብ አፍሪካ ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ በጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን በተፈፀመ ተመሳሳይ ጥቁር አፍሪካውያን ስደተኞች በተሰማሩበት የንግድ ስራ ጥላቻ ከ60 ያላነሱ ሰዎች መገደላቸውንና የበርካቶች ሱቆችና ሌሎች የንግድ ተቋማት መዘረፋቸውን መረጃዎች አመለክተዋል፡፡
ጥቁር ደቡብ አፍሪካውያን አነስተኛ የንግድ ሱቅ በሚሰሩ አፍሪካውያን ላይ በጥላቻ ቢዘምቱም፤ለዛሬው ነፃነታቸው ያበቋቸው በዋናነት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች አፍሪካውያን ትልቅ ሚና እንደነበራቸው አይዘነጋም፡፡
የት ሂዱ ነው?
ዓለም ሁሉ ጠላን፤ በየትም አገር እየሄድን ‹‹የሙጢኝ!›› ከራሳችን መሬት በጉልበት እየተነቀልን፣ ከራሳችን ቤት እየተባረርን፤ ከተወለድንበትና ከአደግንበት አካባቢ እየተፈናቀልን፣ ጭራውን ቆልምሞ እንደሚሮጥ ባለቤቱ እንዳባረረው ውሻ በአገኘነው አቅጣጫ እየሮጥን፣ እጃችንን እያርገበገብን ‹‹የሙጢኝ!›› እንላላን፤ የፈራነውን ሞት በየመንገዱ እናገኘዋለን፤ ሞትን ሸሽተን ሞትን ያጋጥመናል፤ የሞቱ ልዩነት አይታየንም፤ በየመንገዱ የሚያጋጥመው ሞት የውርደት ሞት ነው፤ የብቸኛነት ሞት ነው፤ ዘመድ-ወዳጅ ለቀብር የማይገኝበት ሞት ነው፤ ሠለስት፣ አርባ፣ ሙታመት የማይወጣበት ሞት ነው፤ ባዕድ ምስጥ ያላሳደገውን አካል የሚበላበት ነው፤ የሞት ሞት ነው፡፡
ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ከአገር አስወጥቶ ባዶ መሬት ብቻ ይፈልግ ይመስል የወያኔ ሎሌዎች በማስፈራራት ሁሉም አገሩን እየተወላቸው እንዲሄድ ያቀዱ ይመስላል፤ ጥንት ኢሰመጉ በምሠራበት ጊዜ በየጊዜው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሰዎችን በማስፈራራት ሰላማቸውን ለመረበሽ ወደስደት ወይም ወደወንጀል ተግባር የሚመሩ የወያኔ አባለች ነበሩ፤ አሁን እንደገና ብቅ ማለት ጀምረዋል፤ ሕጋዊ ሥርዓት እየላላ ጉልበተኞች በግላቸው ለዘረፋና ለቅሚያ እየተሰማሩ ይመስላል፡፡
ስለራሴ ላውራ፤ ከእኔ የሚፈልጉት ምን እንደሆነ እርግጠኛ አይደለሁም፤ የሚፈልጉት የምኖርበትን አፓርትመንት እንደሆነም አላውቅም፤ በእኔ ቤት ያለ ሀብት የሚባል ለወያኔ አገልጋዮች የሚጠቅም ሁለት የገብረ ክርስቶስ ስዕሎች ብቻ ናቸው፤ (በዚህ አጋጣሚ እነዚህን ስዕሎች ለመግዛት የሚፈልግ ያነጋግረኝ)፤ ከዚህ ሌላ ለወያኔ ዋጋ የሌላቸው መጻሕፍት ናቸው፤ ስለዚህም አሁን በእኔ ላይ የተሰነዘረው ጥቃት እኔን ወደስደት ለመግፋት የሚደረግ ሙከራ ይሆናል፤ በ1992 ግድም ተሞክሮ ነበር፤ አልሠራም፤ ዛሬ ይበልጥ አይሠራም፤ ለማናቸውም ምክንያቱን በትክክል ለማወቅ ባልችልም በእኔ ላይ ዘመቻ መጀመሩን አንድ በቅርብ ከማውቀው ወያኔ በትክክል ተረድቻለሁ፤ ይህንን ዘመቻ በመምራት ላይ ያለውንም ሰው ማንነት ተነግሮኛል፡፡
ይህ አገር የአንድ ጉልበተኛ ቡድን ነው ብዬ አልቀበልም፤ የአባቶቼና የእናቶቼ፣ የኤቶቼና የቅድማያቶቼ አጥንትና ደም የገነባው አገር ነው፤ ማንም ለስደት አይዳርገኝም፤ ማንም አስፈራርቶ ኢትዮጵያዊነት መብቴን መግፈፍ አይችልም፤ አልፈቅድለትም፤ በግልጽ በማያጠራጥር ቋንቋ ኑሮዬም፣ ሕይወቴም፣ ሞቴም እዚሁ ነው፤ ከኢትዮጵያ አፈር የሚለየኝ የለም፡፡
እኔን ለማጥቃት ላሰፈሰፉት ወያኔዎችና ሎሌዎቻቸው አንድ እውነት ልንገራቸው፤– በፈለጉትና በተመቻቸው መንገድ በእኔ ላይ በጉልበታቸው ግፍ ቢፈጽሙ ነገ በነሱ ላይ የባሰ ግፍ እንደሚደርስባቸው ይወቁት፤ ሁልጊዜም ከሕግ የወጣ ጉልበተኛነት ጉልበተኛነትን ያነግሣል፤ በመግደል ድል ይገኛል ብለው የሚያምኑ ወያኔዎች ትንሽ ቆም ብለው ያስቡ፤ በመሞትም ድል ይገኛል፤ በመሞትም ማሸነፍ ይቻላል፡፡
በእኔ ላይ የዘመተው ወያኔ ወይም ሎሌ ማናቸውም ሥራ ውጤት እንዳለው ማወቅ አለበት፤ አንድ ነገር አድርጎ ምንም ዓይነት ውጤት አያስከትልም ብሎ ማሰብ ድንቁርና ነው፤ ይህ የሳይንስ ሕግ ነው፤ For every action there is a reaction ይላል!