በፍትህ ሚኒስቴር በፌደራሉ አቃቤ ህግ በ”ሽብርተኝነት” ወንጀል ክስ ከተመሰረተባቸው በርካታ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች፣ ፖለቲከኞች እና ተማሪዎች መካከል ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙን ጨምሮ ጥቂቶች ተለቀዋል፡፡
ከእስር ከተለቀቁት መካከል የእርስ ጊዜዋን የጨረሰችው ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ፣ በሚያዚያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በጅምላ ከታሰሩት ጋዜጠኞች እና የዞን 9 ብሎገሮች መካከል ጋዜጠኛ ተስፋዓለም ወልደየስ፣ አስማማው ኃይለጊዮጊስ፣ኤዶም ካሳዬ፤ እንዲሁም የዞን 9 ብሎገሮች ዘለዓለም ክብረት እና ማህሌት ፋንታሁን ይገኙበታል፡፡
ከእስር ከተለቀቁት ተማሪዎች መካከል ከአዲስ አበባ አዲስ ማስተርፕላን ማስፋፊያ ጋር በተያያዘ ከኦሮሚያ ክልል ከታሰሩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች መካከል የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የነበሩት አዱኛ ኬሶ፣ ቶፊቅ ራሺድ፣ሌንጂሳ አለማየሁ፣ አብዲ ከማል፣ መገርሳ ወርቁ፣ ቤሊሱማ ዳመነ እና ተሻለ በቀለ ክሳቸው ተቋርጦ ከእስር መለቀቃቸው ታውቋል፡፡
ይህን እንጂ አሁንም ሆን በስፋት ከታወቁት የህሊና እስረኞች መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ, ውብሸት ታዬ እና የዞን 9ኙ በፈቃዱ ኃይሉን ጨምሮ 13 ጋዜጠኞችና ብሎገሮች፣ እነ አንዱዓለም አራጌ፣ ኦልባና ሌሊሳ ፣አብርሃ ደስታን ጨምሮ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት እንዲሁም የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በእስር ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ ምንም ክስ ሳይመሰረትባቸው ከአንድ ዓመት በላይ በእስር ላይ ከነበሩት የኦሮሚያ ተማሪዎች መካከል ተማሪ አስላን ሐሰን በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዳለ በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ማለፉም ተጠቁሟል፡፡
መንግሥት ቀደም ሲል ጋዜጠኞችን፣ ብሎገሮችን ፣ ፖለቲከኞች እና የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተማሪዎችን በተመሳሳይ “የሽብር ክስ ወንጀል” ቢመሰርትባቸውም ከተከሳሾች ጀምሮ በሀገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፉ ማኀበረስ፤ የተመሰረቱት ክሶች የፖለቲካ ውሳኔ እንጂ ከወንጀል ጋር የተያያዘ እንዳልነበር በመጠቆም ከፍተኛ ተቃውሞ ያስከተለ ሲሆን፤ ተቃውሞው አሁንም እንደቀጠለ ይገኛል፡፡