Monthly Archives: October, 2015

እነ ሀብታሙ አያሌው ለጥቅምት 22 ተቀጠሩ

᎐ማረሚያ ቤት እነ ሀብታሙን አላቀረባቸውም

Politicians
የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ እንዲሰናበቱ የተበየነላቸው የአንድነት፣ የሰማያዊ እና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ላይ አቃቤ ህግ ይግባኝ ጠይቆ ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙት አምስት ተከሳሾች ለጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ቢጠበቅም ማረሚያ ቤት ሳያቀርባቸው በሌሉበት ቀጠሮ የተሰጣቸው የፓርቲዎች አመራሮቹ ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሽ እና አብሯቸው ይግባኝ የተጠየቀበት አብርሃም ሰለሞን ናቸው፡፡
የቂሊንጦ እና የቃሊቲ ማረሚያ ቤቶች እነ ሀብታሙን ፍርድ ቤት ያላቀረቡበትን ምክንያት ፍርድ ቤቱ ሲጠይቅ፣ “ቃሊቲ በፕላዝማ ይታያል ስለተባለ አላመጣናቸውም፤ ከአይ.ሲ.ቲ ጋር ተነጋግረው ነው ያስቀሯቸው” የሚል መልስ ተሰጥቷል፡፡ ማረሚያ ቤቱ እነ ሀብታሙን ብቻ ሳይሆን በሌላ መዝገብ በተለያዩ ወንጀሎች ስር የተጠቀሱ ተከሳሾችንም አለማቅረቡ ታውቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በበኩሉ የቃሊቲ ማረሚያ ቤትን መልስ ካደመጠ በኋላ፣ “ይሄ ቪዲዮ ኮንፈረንስ የሚባል ነገር የሚሆን አይደለም፤ አቅርቧቸው ብለን አዝዘን ነበር፤ እኛ ነን የምናዝዛችሁ ወይስ ማን ነው? አሁንም ቀጣይ ቀጠሮ ላይ አቅርቧቸው” ሲል በእነ ሀብታሙ መዝገብም በሌሎች መዝገቦችም ላይ ዛሬ ላልቀረቡ ተከሳሾች ተመሳሳይ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ በመሆኑም እነ ሀብታሙ አያሌው ሰኞ ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም የተጠየቀባቸው ይግባኝ ያስቀርባል ወይስ አያስቀርብም የሚለውን ብይን ቀርበው ለመስማት ቀጠሮ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ

ሰበር ዜና ፡- ፈቃድ የሌላቸው የኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራሞች በቤተ ክርስቲያን ስም እንዳይጠቀሙ ተወሰነ፤ የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት ይጀመራል

• የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ እና ዕውቅና የሌላቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል
• በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ መሠረት፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
የብዙኃን መገናኛ ቦርድ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው
• በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ላይ የቀረቡ ማስረጃዎች የበለጠ ተጠናክረው አጀንዳው በልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ተወስኗል
EOTC Synod 2008
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ከማእከል የተሰጠ ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም፣ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ(EBS) የቴሌቭዥን ጣቢያ፣ “ሃይማኖታዊ ትምህርት” የሚያስተላልፉ ፕሮግራሞች፣ የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ ወሰነ፡፡

ምልአተ ጉባኤው በዛሬ፣ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ስድስተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው ያሳለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲኾን፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቭዥን በደብዳቤ እንዲያውቁት ይደረግ ዘንድ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
በውሳኔው÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና “ቃለ ዐዋዲ” በስም የተጠቀሱ ሲኾን በፕሮግራሞቹ አዘጋጅነት የሚታወቁት በተለይ የ“ታዖሎጎስ” ግንባር ቀደም ምንደኞች፣ ፕሮግራማቸው“ራሱን የቻለ የሚዲያ ተቋም” እንጂ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ይኹን ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በይፋ በሰጡት መግለጫ ማረጋገጣቸው ይታወሳል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ከዚኹ ጋር በማያያዝ፤ በሊቃውንት ጉባኤ ሳይመረመሩ እና በማእከል ሳይፈቀዱ በግለሰቦች እየተዘጋጁ የቤተ ክርስቲያንን ስም ይዘው ስለሚወጡ የስብከት፣ የመዝሙር እና የመጻሕፍት ኅትመቶች እንዲኹም የአዳራሽ ጉባኤያት እና ስብሰባዎች ከተወያየ በኋላ ቀደም ሲል ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች በማጽናት ተመሳሳይ ትእዛዝ መስጠቱ ታውቋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ስብከተ ወንጌል እና ሚዲያን በተመለከተ” በተራ ቁጥር ሦስት በያዘው አጀንዳ፤ ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊነቱን ጠብቆ የራስዋን ድምፅ ለዓለም የምታሰማበት እና ስብከተ ወንጌልን የምታስፋፋበት የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት እንዲጀመርም ወስኗል፡፡

ለቤተ ክርስቲያንየቴሌቭዥን አገልግሎት ስርጭት የሚያስፈልገውና በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አስተባባሪነት የተጠናው በጀት ባለፈው ዓመት ግንቦት በምልአተ ጉባኤው የጸደቀ ሲኾን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር እንደተመለከተው፤ በዚኽ ዓመት በጀቱ በአፋጣኝ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበውን ጥያቄ በመቀበል የፋይናንስ ምንጮቹን ወስኖ ለነገ የሚያቀርብ ሦስት አባላት ያሉት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት(ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ) ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤ ተሠይሟል፡፡

ምልአተ ጉባኤው ባለፈው ዓመት ግንቦት ባጸደቀው የሚዲያዎች (የሬዲዮ እና የቴሌቭዥን አገልግሎት) ሥርጭት ደንብ መሠረት፤ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራ ዘጠኝ አባላት ያሉት የብዙኃን መገናኛ የሥራ አመራር ቦርድ የተቋቋመ ሲኾን ተግባሩን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ለ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ የቀረበው የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ሪፖርት ያስረዳል፡፡

በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልን ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በአጽናፈ ዓለም ለማስፋፋት እና ለማጠናከር ስለሚያስፈልጓት ሚዲያዎች፣ በመምሪያው አስተባባሪነት በብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎች የተካሔደውን ጥናት መሠረት አድርጎ መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ/ማኑዋል ተዘጋጅቷል፡፡

በተያያዘ ዜና፣“የቤተ ክርስቲያኗን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ማየት” በሚል ዐቢይ አጀንዳ ሥር በፊደል ተራ ቁጥር 4/መ፣ “የተሐድሶ እንቅስቃሴን በተመለከተ”፤ የተዘጋጀው ሰነድ በተጨማሪ ማስረጃዎች ተስፋፍቶ እና ተጠናክሮ ራሱን በቻለ ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል፡፡

የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፤ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ግንባር ቀደም መሪዎች በሚሰጣቸው ተልእኮ እና ድጋፍ በቤተ ክርስቲያናችን የአስተዳደር እና የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በመስረግ የኑፋቄውን አስተሳሰብ እና ድርጊት የሚያራምዱ የ66 አካላት እና ግለሰቦች የሰነድ፣ የምስል እና የድምፅ ማስረጃዎች ከኃምሳ ገጾች ማብራሪያ ጋር ተደግፎ ተዘጋጅቷል፡፡

ከቤተ ክርስቲያናችን ዐውደ ምሕረት እና የአስተዳደር መዋቅር ባሻገር፣ የኑፋቄው ግንባር ቀደም መሪዎች እና ምንደኞቻቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን(መንፈሳዊ ኮሌጆች እና የካህናት ማሠልጠኛዎች) ውስጥ በተለያየ ሽፋን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ከፍተኛ ትኩረት እንዲደረግበት ምልአተ ጉባኤው ኮሚቴውን አሳስቧል፡፡

በመካከለኛው ምሥራቅ አህጉረ ስብከት፣ ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ሳያውቁት ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በተቋቋመው የኑፋቄው መናኸርያ “ዱባይ ሚካኤል” እና “ቤርያ ቲኦሎጂካል ኢንስቲትዩት” በሚል መሪዎቹ የመሠረቱት ሕገ ወጥ ተቋም በከፍተኛ ደረጃ ያነጋገረ ሲኾን በምልአተ ጉባኤው ጥናት ተካቶ እንዲቀርብ መወሰኑ ተጠቁሟል፡፡

በተመሳሳይ ኹኔታ ጉባኤውን ያነጋገረው፣ በመንበረ ፓትርያርኩ የውጭ ጉዳይ መምሪያ በሓላፊነት የተቀመጡት መልአከ ሰላም አባ ቃለ ጽድቅ የተባሉ ግለሰብ፣ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቁ አንጻር ያላቸው ሃይማኖታዊ አቋም እና ሥነ ምግባራዊ ኹኔታ ነበር፡፡ የግለሰቡ አመጣጥ እና አመዳደብም ከፓትርያርኩ ልዩ ጸሐፊ ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ጋር ባላቸው የጥቅም ግንኙነት እንደኾነ መጠቆሙ ደግሞ ችግሩ ከግለሰቡም በላይ ልዩ ጽ/ቤቱ እንደ መዋቅር ያለበትን አስከፊ ደረጃ እና አሳሳቢነቱን ለምልአተ ጉባኤው አለብቧል፡፡
ከዚኽ ውስብስብነቱና ከሚያስፈልገው ጠንካራ ቅንጅት አኳያ፤ አጀንዳው ራሱን በቻለ አስቸኳይ እና ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሲወስን ጊዜው በመጪው ወርኃ ጥር ላይ ሊኾን እንደሚችል ከወዲኹ የተጠቆመ ቢኾንም በኮሚቴው ውጤታማ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚመሠረት ነው፣ በብዙኃን የምልአተ ጉባኤው አባላት ዘንድ መግባባት የተደረሰበት፡፡

በሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት መሠረት፤ አስቸኳይ እና ድንገተኛ ጉዳይ ሲያጋጥም ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም ቋሚ ሲኖዶሱ ወይም የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ በሚያደርጉት ጥሪ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሊካሔድ ይችላል፤ ከዐራቱ እጅ ሦስቱ እጅ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት ስብሰባም ምልዓተ ጉባኤ ይኾናል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ በማናቸውም ስብሰባ ላይ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍም፣ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ከኾነ በሙሉ ድምፅ ያልፋል፤ በሃይማኖት እና በቀኖና ጉዳይም ድምፀ ተዓቅቦ ማድረግ አይቻልም፡፡

ምንጭ፡- ሐራ ዘተዋሕዶ

በእስር ላይ የሚገኙት መምህር ግርማ ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄም ወድቅ ተደረገ

ጥላሁን ካሳ
ትናንት በቁጥጥር ስር የዋሉት መምህር ግርማ ወንድሙ ዛሬ ጥቅምት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበዋል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የፖሊስ መርማሪ ቡድን ዛሬ ግለሰቡን በፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት አቅርቧቸዋል።

መምህር ግርማ ወንድሙ

መምህር ግርማ ወንድሙ

ፖሊስ ግለሰቡ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ቀሪ የምርመራ ስራ ስላሉብኝ ተጨማሪ 14 ቀን ይፈቀድልኝ ብሏል።
ተጠርጣሪው በራሳቸውና በጠበቃቸው በኩል ፖሊስ የጠየቀውን ተጨማሪ ጊዜ በመቃወም የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል።
የፖሊስ የምርመራ ቡድን በበኩሉ እሳቸው ቢለቀቁ ሌሎች ተፈላጊዎችን እና የተለያዩ ሰነዶችን ስለሚያሸሹብን ጥያቄያቸው ውድቅ ይሁን ብሏል።
ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ አብዛኛውን የምርመራ ስራ ያካሄደ በመሆኑ ለቀሪ የምርመራ ስራዎቹ ይረዳል በማለት ከጠየቀው የ14 ቀን ጊዜ ውስጥ 7 ቀን ብቻ ፈቅዷል።
ውጤቱን ለመጠባበቅም ለጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
የወንጀሉ ዝርዝር
ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ.ም ነው ብሏል።
በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው።
እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።
እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል።
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ800 ሺህ ብር ይሸጡታል።
ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው የሚለው የምርመራ መዝገቡ።
ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው።
ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።
የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው።
ተጠርጣሪው እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።
ጠበቃቸውም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል አይደለም፤ ፖሊስም የሚጠበቁ ምርመራዎቹን አጠናቋል፤ ደንበኛዬ የዋስትና መብታቸው ይከበርልኝ በማለት ጠይውቋል።
ይሁን እንጂ ፍርድ ቤቱ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ አድርጓል።
ምንጭ፡- ሬዲዮ ፋና (ኤፍቢሲ)

“ክርስትና ዘውድ ሰጣቸው፥ ክርስትና ነጠቃቸው” ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

ያሬድ ሹመቴ

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ

በምስጋናው ታደሰ የተደረሰውን “ሚካኤል ንጉሰ ወሎ ወትግሬ” የተሰኘውን አዲስ መጽሐፍ ለመመረቅ ጥቅምት 14 ቀን 2008 ዓ.ም. በደሴ አይጠየፍ አዳራሽ የተገኙ ምሁራን ማራኪ ሀሳቦቻቸውን በመድረኩ አቅርበዋል። ከአቅራቢዎቹ መሀል ለዛሬ የዶክተር ዳኛቸውን ውብ ገለፃ ለንባብ እንዲመች አድርጌ በማቀናበር እነሆ በዝርዝር አቅርቤላችኋለሁ።(ያሬድ ሹመቴ)

ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ “እንግዲህ ንግግሬን የምጀምረው እንደ ጥሩ “ወሎዬ” በግጥም ነው። ገጣሚ ስላልሆኩ የኔን ሀሳብ የሚገልጸውን የቀኝ አዝማች ምስጋናው አዱኛን የተወሰነ ስንኝ ተውሼ ልጀምር።
‘በጣሙን ጨነቀኝ ልቤ ተበትኖ፥
እንጀራዬ ሸዋ ቤቴ ጎንደር ሁኖ።’
የዚህ ስንኝ መንፈስ የኔን አመለካከት ይገልጽልኛል ብዬ ስለማምን የሳቸውን ትከሻ ተንተርሼ እጀምራለሁ።
‘በጣሙን ጨነቀኝ ልቤ ተበትኖ፥
ውሎዬ ሸዋ ላይ ልቤ ወሎ ሁኖ።’
ብዬ እጀምራለሁ።

አልፎ አልፎ ከምስጋናው ጋር ስለዚህ መጽሐፍ በስልክ ስናወራ እኔ “ራስ ማይክ” ብዬ ስጠራው እሱ ደግሞ “የሰገሌው” ብሎ ይጠራኛል። ሁለቱም ምክንያት አላቸው። እሱ ስለ ራስ (የኃላው) ንጉስ ሚካኤል ስለጻፈ፥ ራስ ገብረየስ የተባሉ የኔ ቅድመ አያት ከዚች ቦታ [አይጠየፍ] ተነስተው ከራስ ሚካኤል ጋር አብረው ሰገሌ ዘምተው [በኃላ በራስ ካሳ ስር እስረኛ ሁነው ቢመለሱም] ወሎየነቴ ሰገሌን ያልፋል ለማለት ነው እንጂ እንዲያው በዚህ ሳልፍ እግረ መንገዴን ወሎዬ ነኝ አላልኩም ለማለት ነው።
ወሎዬ ነኝ ስል፥ አደራችሁን፥ ሰሜን ወሎ ነኝ አላልኩም። ደቡብ ወሎ አላልኩም። አርጎባም አላልኩም። ከሚሴ ነኝም አላልኩም። ሚሌም ነኝ አላልኩም። በደፈናው ወሎዬ ነኝ ነው ያልኩት።

እንግዲህ እንጀምር፡-
ትልቁ የጀርመን ፈላስፋ ሄግል አንድ ቦታ ላይ ስለ ታሪክ እንዲህ ይላል። ‘አፍሪካ በደፈናው ታሪክ የላትም። ይህንንም ስል ምክንያቴ ስለማትጽፍ ነው’ ይላል። በሱ አነጋገር ‘እንዲያውም ትንሽ ታሪክ ላይ የደረሱት አረቦቹ ናቸው። እነሱ ይጽፋሉና’ ይላል። እኛ ኢትዮጵያዊያን እንደምንጽፍ ሄግል አያውቅም። የምስጋናው መጽሐፍ ለዚህ መልሱ ነው። የንጉስ ሚካኤልና የወሎ ታሪክ ባይፃፍ ኖሮ ተረት ተረት ሆኖ ነበር የሚቀረው።

ሁላችንም ቤት ውስጥ [ይህ ታሪክ] የአፍ ብቻ ታሪክ ሆኖ ተቀምጦ ኖሯል። “ካልተጻፈ ታሪክ የለም።” መጻፍ መዘገብ ካልቻለ በአፍ ያለው ጠፍቶ ተረት ተረት ሆኖ ይቀራል። ታሪክ ከጽሁፍ ጋር የተቆራኘ በመሆኑ መፃፍ አለበት። ለዚህ ደግሞ ምስጋናው ተገቢ መልስ በመስጠቱ ባለውለታችን ነው የሚል እምነት አለኝ።
ሌላው ከክርስቶስ ልደት 600 ዓመት በፊት የነበረው ታላቁ ግሪካዊው የታሪክ ቀመር መስራች ሱሲዲየስ ምን ይላል? ‘ታሪክን ለመፃፍ የሚነሳ ሰው ቢያንስ ቢያንስ አርባ አመት ቢሞላው ይመረጣል’ ይላል። ‘ፀሀፊው እድሜው የጠና ካልሆነ እንዲሁ የሆነውን ያልሆነውን እየጻፈ ህዝብ ያበጣብጣል።’ ሲል ያክላል።

በአንድ በኩል እውነቱን ነው። ባለፉት ከ25 እስከ 30 ዓመታት ውስጥ የወጡትን “የታሪክ ድርሳናት” ስንመለከት መርዶ አቅራቢዎች ናቸው። ‘በእንዲህ ያለ ጊዜ እንዲህ እና እንዲያ ተደርገሀል፥ በእንዲህ ያለ ቦታ እንዲህ ተደርጎብሀል’ እየተባለ ይፃፋል። ታሪክ የተወሳሰበ ዲሲፕሊን ነው። ከመርዶ ነገራ በእጥፉ ይለያል።

በተጨማሪም ታሪክ ከመርዶ ነገራ አልፎ የርዕዮተ ዓለም እና የፖለቲካ አሽከር በሚሆንበት ጊዜ ብዙ ጣጣ ይመጣል። ርዕዮተ አለሙ ይቀድምና ታሪክ የበታችነትን ቦታ ትይዛለች። ይሄን ልጅ (ምስጋናው) ከዚህ አንፃር ስናየው 40 ዓመት ገና አልሞላውም። እንዲያውም አንድ ሰው ለአንድ ጓደኛዬ ’40 አመት ያልሞላው ሰው ታሪክ መፃፍ የለበትም ብሏል ዳኛቸው። እድሜው ያልደረሰውን ምስጋናው የፃፈውን መጽሀፍ ለመመረቅ ለምን ሄደ?’ ብሎ ጠይቋል። ስለ ታሪክ አረዳድ፥ ስለታሪክ ምርምር እና ስለ ታሪክ ትንተና እስከ ከፍተኛ ትምህርት ደርሶ የተማረው ምስጋናው፥ ትምህርቱ ባበረከተለት እውቀት የእድሜውን ማነስ ተሻግሮታል ብዬ አምናለው። እውቀት የእድሜን ክፍተት ይሞላልና።

የዚህ መጽሀፍ ንባብ ሲጀመር ገና ከጠዋቱ ጥያቄዎች ተጀምረዋል። አንዱ ‘የኔን አያት በደንብ አልፃፋቸውም’ ሲል ሌላው ደግሞ ‘የኔ ቅድም አያት ሊቀ መኳስ እከሌን አሳንሶ ጽፏቸዋል’ [እንዲህ እንዲያ] ወዘተርፈ ይላል። ለዚህ ደግሞ አጭሩ መልስ፥ የታሪክ ጸሀፊ ሊዘግበው በተነሳው ርዕስ ዙሪያ ሁሉንም ምንም ሳይተው አጠቃላይ ዘገባ ማቅረብ በፍፁም አይቻለውም። በመሆኑም የታሪክ ዘገባ የሚከናወነው ወሳኝ የሚላቸውን ጉዳዮች በመምረጥ እንጂ ሁሉንም በማካተት ሊፃፍ አይችልም።

[ሌላው ጉዳይ] ታሪክን ከአንድ ከማይላወስ እና ከማይነቃነቅ መድረክ ላይ ሆነን የምንረዳው እውነታ አይደለም። ታሪክ ምን ግዜም ተለዋዋጭ እና ፈሳሽ መሆኑን ማጤን ተገቢ ነው። ለምሳሌ የመንግስቱ ነዋይን ግርግር ደርግ ከመምጣቱ በፊት ያጠና ሰው የወታደር መፈንቅለ መንግስትን የሚያይበት አተያይ አለው። ከነመንግስቱ ነዋይ በኋላ የወታደር መንግስት 17 ዓመት በስልጣንከቆየ በኋል የመንግስቱ ነዋይን ታሪክ የሚያጠና ሰው አተያዩ በጭራሽ እንደ መጀመሪያው አይሆንም። ስለዚህ ታሪክን ከተለዋዋጭነቱ ሁኔታ አንጻር ማየት የግድ ይላል።

በሌላ መልኩ ደግሞ ዋናው የቀደመ ታሪክን ለመረዳት፥ የጀርመን ፈላስፋዎች እንደሚሉት አሁን ባለንበት በኛ ዘመን እና ባለፈው ዘመን መካከል የአተያይ አድማሳት ዑደትን ማግኘት ተገቢ ነው። (fusion of horizon)በመሆኑም 21ኛው ክፍለ ዘመን ላይ ሆነን 19ኛውን ክፍለ ዘመን ለመረዳት ሀሳባችንን መንፈስና ቀልባችንን ወደ ዘመኑ መላክ ተገቢ ነው። ያለፈውን እሴት ወግ እና መቼት በሚገባ ካላጠናን፥ የኛን ዘመን የአመለካከት ዘይቤ ብቻ ይዘን ያንኛውን ዘመን ልንረዳው አንችልም። በመንፈስ ልናጠናው ወደ ፈለግነው ዘመን እስካልተጠጋን ድረስ ያ ዘመን ለኛ ምን ግዜም ባይተዋር ሆኖ ይቀጥላል።

ከዚህ አኳያ ስንመለከት የምስጋናው ታደሰ መጽሐፍ ከመቶ አመታት በፊት የተካሄደውን የታሪክ ሂደት ከውጭ ሆኖ ሳይሆን በጊዜው እንዴት ያስቡ እንደ ነበርና የአመለካከት አድማሳቸውን በተገቢ አውድ በማስቀመጥ አቅርቦታል።
ወደ ሌላ ነጥብ ስናልፍ፥ ስለ መሪዎቻችን በምናወሳበት ጊዜ በአንድ ወጥ ትረካ መሪዎቹን አናገኛቸውም። እንደ ምሳሌም መምህር አለማየሁ ሞገስ ‘መልክዓ ኢትዮጵያ’ ላይ ከሰበሰቧቸው ስነ ቃሎች መሀል አፄ ቴውድሮስ ሲሞቱ የተገጠመላቸውን ሙሾ ላንሳላችሁ።

“ከመላክ ከሰይጣን እግዜር የሰራው…
….ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ
የመጨረሻው ቀን ግስላ ሆኑና ታነቁና ሞቱ’
‘ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ’ የሚለውን ያዙልኝ።

ሁሉም መሪዎቻችን ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ ናቸውና። በአንድ ቁንጠራ አንፍረዳቸው። ሚካኤል ስንል የዓድዋውን ሚካኤል ማስታወስ ሊኖርብን ይገባል። ሚካኤል ስንል ይህንን ወሎ የተባለውን ሀገር ያቆሙልንን ልናወሳ ይገባል። ሚካኤል ስንል ደግሞም ከአፄ ዮሀንስ ጋር ሆነው በኃይማኖት ጉዳይ ችግር የፈጠሩትን ልናነሳ እንችላለን። ይሄንን መቀበል ይኖርብናል። አንዷን ብቻ ይዘን ሚካኤል ይሄ ነው ለማለት በጣም አስቸጋሪ ይሆንብናል።

አፄ ቴውድሮስ ቆንጥረው ቆንጥረው ሁሉን ያካበቱ እንደተባሉት ማለት ነው። እዚህ መሀል ጎንደሬዎች ካላችሁ እንዳትቀየሙ። ስለሳቸው ከጀግንነት ውጪ ያወራ ሰው ሊሰዋ ይችላል ተብሏል አሉ። (ከፍተኛ ሳቅ)
ወደ ሌላ ወሳኝ ጉዳይ ስናመራ፥ ከወሎ ባህል ያፈነገጠውን ሙስሊሞችን ክርስቲያን የማድረግ ዘመቻ – የአፄ ዮሐንስ ፖሊሲን እናገኛለን። ምስጋናው በመጽሀፉ ምንም የደበቀው ነገር የለም። እንዲያውም ‘አራት እና አምስት አመታት ለወሎ ሙስሊሞች የጭንቅ አመታት ነበሩ’ ይላል። ትልልቅ ሸሆች ተጋድለው መስዋዕትነት መክፈላቸውንም ይተነትናል።

እኔ ንጉስ ሚካኤል ከአፄ ዮሐንስ ጋር አብረው ስህተት ሰርተዋል ነው የምለው። በወሎ ሙስሊሞች ላይ ትልቅ ጫና እና ሰቆቃ ደርሶባቸዋል። ከፊሉ ለስደት ሲዳረግ ከፊሉ ተቃውሞ ጀሀድ አውጆ ለሀይማኖቱ ተጋድሎ ተሰውቷል። ቀሪው ደግሞ ክርስትናን የተቀበለ መስሎ ህይወቱን አትርፏል። ምንም የሚያስደብቅ ነገር የለም። መሪዎች በሁሉ ነገር ልክ ናቸው ማለት አንችልም።
በምስጋናው መጽሐፍ ውስጥ ሙስሊሞቹ በጉልበት እንዲጠመቁና የክርስቲያን ስጋ እንዲመገቡ ሲገደዱ ቅሬታቸውን በሚያንፀባርቅ ስነ ቃል ስሜታቸውን ገልፀዋል እንዲህ ሲሉ ገልፀዋል።

“ታላቅ ታናሽ በላን ከርካ አደባባይ
አለ ልብ ስጋ ይጣፍጣል ወይ”
እንደዚሁም ሸህ ሁሴን ጅብሪል፡-
“ለጥቂት ቀን ብዬ አልበላም ነጃሳ
ወንዝ ለወንዝ ሄጄ እበላለሁ አሳ″

በሌላ በኩል ደግሞ ‘ሰው ያላመነበትን እንዲቀበል ማስገደል ልክ አይደልም’ ሲሉ ሊቁ ክርስቲያን መምህር አካለ ወልድ ይህን ዘመቻ አለመውደዳቸውን ገልፀዋል።

ይህ ሁሉ መዓት ከወሎ ህዝብ ከራሱ የመጣ አለመሆኑንም ማረጋገጥ ከፈለግን፥ አፄ ዮሐንስ አልፈው አፄ ምኒልክ ሲነግሱ፥ የክርስትና ሀይማኖትን በኃይል የመጫን ፖሊሲ ሲያበቃ፥ በወሎ ሙስሊም እና ክርስቲያን መሀል የነበረው የቀደመ ፍቅር መልሶ ቀጥሏል።
ንጉስ ሚካኤልን በኃይማኖት ጉዳይ የነበራቸውን ክፉ ጥላ ትንሽ ይቅር ለማለት የምንችለው የአፄ ዮሐንስ ስርዓት ሲያከትም ይኸው ተግባርም በዚያው በማክተሙ ነው። እንዲያውም ልጃቸው አቤቶ እያሱ ኢትዮጵያን የማስተዳደር ስልጣን ሲያገኙ፥ “ሙስሊምና ክርስቲያኑ እኩል ሊታይ ይገባል” ባሉ ጊዜ ንጉስ ሚካኤል አልተቃወሟቸውም ። ይሄ እሳቸውን ትንሽ ይቅር ለማለት ያስችለናል።
ከማመዶቹ ስርዐት ጋር ተፋልመው ከአፄ ዮሐንስ እና አፄ ምኒልክ ዘመን ጋር ተፋልመው ወሎ የፖለቲካ ወሳኝ ማዕከልነትን ቦታ እንድትይዝ ሲያደርጓት ደግሞ ታያላችሁ። አፄ ምኒልክ እንዳረፉ የአቤቶ እያሱን አልጋ ወራሽነት ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ሲያውጁ ‘ሸዋ ተስማምቷል፥ ወሎ ተስማምቷል’ ብለው ነው የሚጀምሩት። ይህ አዋጅ ከአጀማመሩ የወሎን የፖለቲካ ማዕከላዊነት ያሳያል። በነገራችን ላይ አሁን በያዝነው ዘመን ሸዋ ተስማማ ወሎ ተስማማ ምንም ለውጥ ያለው አይመስለኝም። (ከፍተኛ ሳቅ) ነገሮች ተለዋውጠዋል።

ሌላው የኔ ልብ የሚመታው ሰገሌ ላይ ነው። ሰገሌን የሚመለከት ያለኝ ምክረ ሐሳብ (thesis) ፥ ንጉስ ሚካኤልን “ክርስትና ዘውድ ጫነላቸው በአንፃሩ ደግሞ የክርስትና እምነታቸው ዘውዳቸውን ነጠቃቸው” ነው እኔ የምለው። ክርስቲያን ባይሆኑ ኖሮ አይነግሱም ነበር። ደግሞ ደንበኛ አማኝ ክርስቲያን ባይሆኑ ኖሮ ሰገሌ ላይ አይሸነፉም ነበር። “የፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ደብዳቤ አታለላቸው” የሚለው የልጆች ተረት ተረት ነው ለኔ። መስቀል ተልኮ ትልልቅ ቀሳውስት አባቶች ካህናት ተልከው እንዴት እምቢ ይበሉ? አማኝ ናቸዋ።
እዚህ ላይ የኒኮሎ ማኪያቬሊን አስተምህሮት ማስታወስ ጠቃሚ ይሆናል። ለማኪያቬሊ ሁለት አይነት የሞራል አድማስ አለ። አንደኛው “የክርስቲያን ሀይማኖታዊ ‘ሞራሊቲ′ (ግብረ ገብ)” ይለዋል። ሁለተኛውን “ማህበረሰባዊ የፖለቲካ ሞራሊቲ″ ይለዋል። በመሆኑም ፖለቲካል አለም ውስጥ መጠቀም ያለብን የማህበረሰባዊ የፖለቲካ ሞራሊቲን እንጂ የክርስቲያን ሀይማኖታዊ ሞራሊቲ አይደለም” ይላል።

ለመሆኑ በሁለቱ የሞራሊቲ መርሆች መካከል ልዩነቱ ምንድን ነው?

ለማኪያቬሊ የክርስቲያን ስነ ምግባራት እንደ ርህራሄ፥ ለቃል መታመን፥ መሀላ፥ መማለድ እና ወዘተርፈ ሲሆኑ። በአንፃሩ የፖለቲካ ሞራሊቲ ማለት የወጠንከው ግቡ ላይ ለመድረስ ማናቸውንም አማራጮች የሞራል መስፈርት ጥሶ ያለ ገደብ መጠቀም ማለት ነው። ለምሳሌ፡- ሀይማኖትን እንደ መሸምገኛ መጠቀም፥ የማያከብሩትን ቃል መግባት፥ በውሸት መማል፥ ወዳጅነትን እንደ ማዘናጊያ ማቅረብ እና ወዘተርፈ።

ወደ ሰገሌ ስንመጣ ሸዋ የፖለቲካ ሞራሊቲ ይዞ መጣ። ወሎ የክርስቲያን ሞራሊቲ ይዞ ቀረበ። የምስጋናው መጽሐፍ እንደሚያስተምረን፥ ንጉስ ሚካኤል፥ ከሸዋ ቀድሞ የመጣውን የራስ ልዑል ሰገድን ጦር ቶራ መስክ ላይ ከደመሰሱ በኋላ ገስግሰው ወደ አዲስ አበባ ሳይገቡ ለምን እንደ ቀሩ እና የሸዋው ኃይል ከየጠቅላይ ግዛቱ ጦሩን እስኪያሰባስብ ድረስ ለምን ሰገሌ ላይ እንደቆዩ ብዙ ጊዜ የሚሰጠው መልስ የሚከተለው ነው።

“ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ በተለመደው ብልሀታቸው ከንጉስ ሚካኤል ጋራ እንደሆኑ እና አቤቶ እያሱን እንዳልከዱ በመግለጽ ለጊዜው አሉበት ቦታ ሆነው እንዲቆዩላቸው መልዕክት ልከው ስላታለሏቸው ነው።” ይባላል። ይሔ ለኔ ተረት ተረት ነው።
የአሸናፊዎቹ ተረት ተረት የሆነው ደብዳቤ ተጽፏል ወይ? አዎ ተጽፏል። ግን ከልባቸው አምነው የተታለሉት ለመስቀሉ ነበር። የክርስትናን እውነታ ፀንተው ስለያዙ ተታለሉ። ‘ክርስቲያ አይዋሽም። ክርስቲያን ቃሉን ይጠብቃል’ ከሚል እምነታቸው ተነስተው ዘውድ የሰጣቸው ክርስትና በእምነታቸው ምክንያት ዘውዱን መልሶ ነጠቃቸው።

ንጉስ ሚካኤል በእመነታቸው ፀኑ። ሀብቴ አባ መላ ግን “መስቀልም አውጥተን ታቦትም አውጥተን ይሄን ሰው ማሸነፍ አለብን” አሉ። ይሄ ማለት ከላይ ለማሳየት እንደሞከርነው ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ የማኪያቬሊን የፖለቲካ ሞራሊቲ ይዘው ሲመጡ፥ እኚህ ደግሞ የክርስቲያን ሞራሊቲ ይዘው ስለቀረቡ ለኃብተ ጊዮርጊስ “ክርስቲያናዊ” ጥሪ ታምነው የፖለቲካዊ ሞራሊቲ ሰለባ ሆኑ።
ዕምነቱን እንደ መሰሪያ የተጠቀሙት ፊታውራሪ ኃብተ ጊዮርጊስ ብልህ ብልጥ ሲባሉ፥ በሀይማኖታቸው መርህ የፀኑት ንጉስ ሚካኤል ግን ገራገር ተባሉ። ይኸው እስካሁን ወሎ ገራገሩ እየተባለ ይዘፈናል። (ሳቅ) ወይ ሀብቴ አባ መላ… ይሄ መቼስ የሚገርም ነው። (ሳቅ)
በመጨረሻም፡-
አደራ እምለው፥ ከወሎ ባህል ያፈነገጠና አስከፊ የሆነው የእምነት ጫና እና ግፊት ህዝቡ ተሻግሮ እንዳለፈው ሁሉ፥ የወሎን ህብረ ብሔራዊነት ተፃፈ ከተባለው ህገ መንግስት እና ፌዴሬሽን በፊት በወሎ የኖረውን የሀይማኖት መደጋገፍ እና ተቻችሎ በፍቅር የመኖርን ባህል አንግሶ መቀጠል ይገባናል ስል ንግግሬን እጨርሳለሁ። አመሰግናለሁ።” (ታላቅ ጭብጨባ)
ዶክተር ዳኛቸው ጋር የቀረቡ ሌሎች ጥናቶችን በሌላ ጽሁፍ እመለስባቸዋለሁ። በእለቱ ከተሳታፊዎች ጥያቄዋች እና አስተያየቶች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

አንድ መንፈሳዊ አባት በንግግራቸው ንጉስ ሚካኤል በእምነታቸው ጥልቀት አማካኝነት መሸነፋቸው የሀይማኖት ሰማዕት እንዳደረጋቸው በመግለጽ ዘውትር ስመ ክርስትናቸውን በቤተ ክርስቲያን እየተነሳ ፀሎተ ፍትሀት ይደረግላቸዋል” ሲሉ የምሁሩን ሀሳብ አጠናክረዋል።
በተሳታፊዎች “ታሪክን ወደ ኋላ ሂዶ መዘገብ ስለምን በመንግስት በኩል አስፈሪ ሊሆን ቻለ?” የሚል እና የንጉስ ሚካኤልን ሀውልት ማቆም የተመለከቱ ጥያቄዋች ቀርቦ፥ ዶክተር ዳኛቸው ሲመልሱ “የንጉስ ሚካኤልን ሀውልት በሚመለከት፥ ሲታሰብ የሳቸውን ብቻ ሳይሆን ሌሎችንም ለሀይማኖታቸው ሲሉ የወደቁ ኢማሞች አሉና ለነሱም ሀውልት ሊቆም ይገባል። ምን አልባት በእስልምና ሀይማኖት ሀውልት የማይፈቀድ ከሆነ በስማቸው የጥናት ማዕከላት ሊገነቡ ይችላል። የራሳችን ታሪክ አካል ስለሆነ ተቻችለን ተሳስበን መዘከር ይገባናል።

ታሪኩ ለምን አልወረደም ላልሽው፥ እኔ እምልሽ ታሪክ በጣም ከባድ ነገር ነው። አንድ አንድ ጊዜ ታሪክ የፖለቲካ አሽከር የምትሆንበት ጊዜ አለ። የፖለቲካ ሀይሉ ጠምዝዞ ይመራዋል። በአፄ ኃይለ ስላሴ ጊዜ ስለ ልጅ እያሱ መፃፍ በጣም አስቸጋሪ ነበር። በደርግ ጊዜ ስለ አፄ ኃይለ ስላሴ መፃፍ አስቸጋሪ ነበር። አሁን ደግሞ አንድ አንድ ሁኔታዎች መፃፍ አስቸጋሪ ነው። ከዚህ አልተላቀቅንም።
እንዲያውም “ሀቅ ሀቁን ለህፃናት” የሚል የፕሮፖጋንዳ መጽሀፍ ተለቋል አሁን። እሚገርም ነው መቼም። አስቸጋሪ ነው። አረ ተመስገን ነው። አይጠየፍ ሁነን እንዲህ ያለ ውይይት ማድረጋችንም ተመስገን ነው። (በከፍተኛ ሳቅ እና ጭንጨባ ተቋጨ)

ምንጭ፡- ቋጠሮ ድረ-ገፅ

የኢትዮጵያ ድርቅና ርሃብ ትናንት እና ዛሬ

ብስራት ወልደሚካኤል

በርግጥ ድርቅ በተፈጥሮ ሊከሰት የሚችል የአየር መዛባት አደጋ ውጤት ነው፡፡ ድርቅ ባለፀጋም ሆነ እንደኛ ባሉ ደሃ ሀገራት ሊከሰት ይችላል፡፡ የድርቁ መንስኤም ተፈጥሯዊ አሊያም ሰው ሰራሽ ሊሆን ይችላል፡፡

Ethiopia_drought_cows

ርሃብ በምግብ እጥረት የሚከሰት ሲሆን፤ መንስዔውም የምርት አቅርቦት ማነስ አሊያም የምግብ ፍላጎት ከምርት አቅርቦት ጋር አለመጣጣም ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ዋነኛ ምክንያት ደግሞ ፍላጎት እና አቅርቦትን አሊያም የሀገር ምርት ለማሳደግ ሀገሪቱ የምትከተለው ፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡ በኢትዮጵያም በተለያዩ መንግሥታትም ሆነ ዘመን ድርግቅን ተከትሎም ይሁን ያለድርቅ ለተከሰቱት እና እየተከሰቱ ላሉ ችግሮች ዋነኛ መንስዔው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ትግበራ ውጤት ነው፡፡

ርሃብ በተፈጥሮ የሚከሰት ሳይሆን የሀገሪቱ መንግሥት ስርዓት በሚከተለው የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡ ደካማ ወይም ተፈጥሮንና የሀገሪቱን ህዝብ አቅምና ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ፖሊሲ ትግበራ ባለበት ሀገር ድርቅ ከተከሰተ ምንጊዜም ርሃብ አለ፡፡ ርሃቡ ምንም እንኳ ድርቅን ተከትሎ የመጣ ቢሆንም ዋነኛ ምክንያቱ ግን የፖሊሲ ንድፍና ትግበራ ውጤት ነው፡፡

በሀገራችን በተከታታይ የተከሰተውም ርሃብ ዋነኛ ምክንያት ድርቁ ሳይሆን የደካማ ፖሊሲ ውጤት ነው፡፡ ምክንያቱም ድርቅ የተከሰተባቸው ሀገሮች ሁሉ ርሃብ አይከሰትም፡፡ ደካማ ፖሊሲ ያለባቸው ሀገሮች ግን ድርቅ ካለ ምንም ጊዜም ርሃብ አለና፡፡

በዘመናዊ ኢትዮጵያ የመንግሥት ታሪክ ጎልቶ መታወቅ የጀመረው በዳግማዊ አጼ ምኒልክ ዘመን ቢሆንም እስከዛሬም ይህን ችግር የሚቀርፍ የመንግሥት ፖሊሲና ተግባር አልታየም፡፡ አሳዛኙ ነገር በዘመነ ዳግማዊ ምኒልክ የነበረውን ርሃብ ለዓለም ማኀበረሰብ አሳውቆ ተገቢውን ርዳታ ይቆ ለተጎጂዎች በማድረስ ህይወት ለማትረፍ ቴክኖሎጂው ችግር ነበረብን፡፡ ቢሆንም ግን ይህን ክፍተት ንጉሱን ጨምሮ ባለሟሎቹ (አመራሮቹ) የተፈጠረውን ርሃብ በድርቅ ላይ ሳያመሃኙ ወዲያው ለህዝቡ በማሳወቅ ወገን ለወገን በሚችለው አቅም እንዲረዳዳ እና የመንግሥት ካዝና (ለችግር ጊዜ የተቀመጠ የእህል ጎተራ) ሳይቀር በይፋ ተከፍቶ ለተጎጂዎች ወዲያው እንዲደርስ ለማድረግ ተሞክሯል፡፡ ይህ በጎ አስተሳሰብ ቢሆንም ከነበረው የእህል ክምችት አናሳነት እና የትራንስፖርት ችግር አኳያ ለሁሉም ተጎጂ እኩል ማድረስ ባይቻልም መንግሥት ችግሩን አምኖ የህዝቡን ድጋፍ ጤቆ ተገቢውን ምላሽ አግኝቶ ነበር፡፡ ቢሆንም ግን ብዙ ወገኖቻችንን በርሃቡ አጥተናል፡፡

Ethiopian famine 2015

በዘመነ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ የነበረው በ1965/66 ዓ.ም. ርሃብ ግን ንጉሱም ህዝቡም እንዳያውቁ መኳንንቱ ለመሸፋፈን ሞክረዋል፡፡ በዚህም መኳንንቱ ጠግበው እየበሉ በርካታ ወገኖቻችን በወቅቱ በተከሰተው ርሃብ ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ይሄ በተለይ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍለክ እጅግ የከፋ የታሪክ ጠባስም ጥሎልን አልፏል፡፡

በዘመነ ደርግ በተለይ በ1977 ዓ.ም. የተከሰተውን ልብ ይሏል፡ የተከሰተውን ርሃብ የሀገሪቱ መራሄ መንግሥት መንግሥቱ ኃይለማርያምና ሁሉም ሹማምንት ቢያውቁም ከሀገሪቱ ህዝብ (ርሃብ ካልነካቸውን) እና ከዓለሙ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ተሞክሯል፡፡ በዚህም ብዙ ወገኖቻችን በጊዜ ማዳን ሲቻል በሞት ተነጥቀናል፤የበለጠ ክብራችንም እንዲዋረድ በር ከፍቷል፡፡

በዘመነ ኢህአዴግ ከአንዴም ሶሰት ጊዜ፤በተለይ በ1985ዓ.ም.፣ 1986/87 ዓ.ም. እና የአሁኑን የ 2007/08 ዓ.ም. ርሃብ መንግሥት ከሀገሬው ህዝብና ከዓለም አቀፉ ማኀበረሰብ ለመደበቅ ሞክሯል፤ባይችልም፡፡ በቅርቡ በተለይም ባለፈው ክረምት በምስራቁ የሀገራችን ክፍል የተጀመረው ርሃብ ወደ ሰሜኑ እና መካከለኛው የሀገራችን ክፍል በፍጥነት ቢዛመትም መንግሥት በምግብ ራሳችንን ችለናል፣ ርሃብ አልተከሰተብ፣ …ወዘተ የሚለው ፈሊጥ አንድ ወር እንኳ አልሞላውም፡፡ ርሃቡ ልክ እንደሰደድ እሳት እና አውሎ ነፋስ ማዕበል ምስራቁን፣ ሰሜኑን እና ከፊል መሐከለኛ የሀገራችን አካባቢ በፍጥነት ተዛመተ፡፡ ርሃብ የለም፣ በምግብ ራሳችንን ችለኛል፣…የክፉዎች ወሬ ነው ሲባል የነበረው ርሃብ፤ አሁን መንግሥት በህዝብ ላይ እና በእንሰሳቶቻቸው ላይ ከፍተኛ እልቂ ከደረሰ በኋላ “ኢሊኖ በሚባለው ድርቅን ተከትሎ በነሳው ርሃብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር 5 ሚሊዮን አካባቢ ደርሷል፣ ከዓለም አቀፉ ለጋሽ ድርጅቶች እና ሀገራት አፋጣኝ እና በቂ ድጋፍ አላገኘንም,…” የሚል ይፋ ልመናዊ መግለጫ ተሰጠ፡፡ የተራቡ ወገኖቻንን ቁጥር መገመትና መናገር ቢከብድም አስቸኳይ የምግብ ርዳታ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ግን ከ 10 ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ይገመታል፡፡

በጣም የሚያሳዝነው ሁሉም ስርዓቶች በተፈጥሮ ሃብትና በግብርና ላይ ያላቸው ፖሊሲ የአንዳቸው ከአንዳቸው የማይሻል፣ ያልተለየ ቢሆንም በዳግማዊ ምኒልክ ጊዜ ግን ርሃብ ለመደበቅ አልተሞከረም፤ ይልቁንም ከመንግሥት ካዝና በተጨማሪ ህዝቡ እንዲረዳዳ የጠማፅኞ ጥሪ ተደረገ እንጂ፡፡ በኃይለስላሴ ዘመንም ቢሆን ሹማምንቱ ከንጉሱ እና ርሃብ ካልደረሰበት ህዝብ ለመደበቅ ቢሞከርም መደበቁ አልቻሉም፡፡ የደርግና ኢህአዴግ ስርዓት ክፋት ግን ከበታች ሹም እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ድረስ ርሃቡን እያወቁ ለመደበቅ መሞከራቸው የፖሊሲ ችግራቸውን ለመደበቅ ከመሞከራቸው ይልቅ በሰብዓዊ ፍጡር ህይወት ላይ ያላቸውን ጭካኔ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም ርሃብ ቀን አይሰጥምና፡፡ ርሃብ የሰውንም ሆነ የእንሰሳትን ህይወት ሲቀጥፍ ዳግም አናገኛቸውምና፡፡

አሁን ርሃቡ በዋነኛነት የተከሰተው ውሃ ቅዳ ውሃ መለስ የሆነው የመንግሥት ስርዓትና በመሪዎች ቸልተኝነት፤ የተፈጥሮ ሃብት፣ የመሬት፣ ስነ ህዝብ፣የምግብ እና የመረጃ ጥንቅር ፖሊሲ ችግር ነው፡፡ ባለፈው ከነበረው ችግር ለነገው አለመማራችን እና ለመማር አለመዘጋጀታችን ውጤትም ነው፡፡ ስለዚህ ርሃብን እና የተራበውን ህዝብ ቁጥር በመደበቅና በማዛበት ርሃብን ማቆም እንደማይቻል ልናውቅ ይገባል፡፡ ስለዚህ በርሃብ የተጎዱ ወገኖቻችንን በተመለከተ የውጭ መንዛሪ እጠረት ለመሸፈን ባለመ የውጭ ለጋሽ ሀገሮችን ተማፅኞ ብቻ ሳይሆን ዜጎች ወገኖቻችንን እንዲረዳዳ ዕድሉ ሊሰጥና በይፋ የምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ ማሰባሰብ ስራ በማድረግ የወገኖቻችንን ህይወት መታደግ ይቻላል፡፡ ለዚህም ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፤ ርሃብ ጊዜ አይሰጥምና፡፡

ከፖሊሲ ችግር አንዱ ከዝናብ ጥገኝነት ለመውጣት የሚያስችል መስኖ አለማስፋፋት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሜትሪዮሎጂ ተቋም ብቃት ባላቸው የአየር ትንበያ ባለሙያዎች አለመዋቀር እና አለመጠናከር፣ መስኖ በሌለባቸውና ዓመታዊ የዝናብ መጠናቸው ዝቅተኛ የሆኑ ቆላማ አካባቢዎች የተለየ ትኩረትና ጥንቃቄ እንዲሁም በቂ የእንሰሳትና የሰው ህክምና እና የምግብ ቅድመ ዝግጅት ክምችት አለማድረግን መጥቀስ ይቻላል፡፡

ከአስቸኳይ ርስበርስ የመረዳዳት እና ዓለም አቀፍ ድጋፍ ጥየቃ እንቅስቃሴው እንዳለ ሆኖ፤ ለ24 ዓመታት ተሰርቶበት ለውጥ ያላመጣውን ፖሊሲም ማሻሻል አሊያም መቀየር ዋነኛው ቁልፍ ተግባር መሆን አለበት፡፡ አለበሊያ በኢህአዴግ ዘመን ለ4ኛ እና 5ኛ ጊዜ መከሰቱ እንደማይቀር የአሁኑን ጨምሮ ያለፉት ጊዜያት ከበቂ በላይ አስተማሪዎች ናቸውና ከፖለቲካ ጋጋታ ትርፍ ይልቅ ሕይወት የማዳኑ ተግባር ሊፈጥን ይገባዋል፡፡

%d bloggers like this: