Daily Archives: October 22nd, 2015

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ተላለፈበት

የሎሚ መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ የ18 ዓመት እስራትና የ100 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲሁም በመፅሔት አሳታሚ ድርጅቱ ላይ የ200 ሺህ ብር ቅጣት ተወስኖበታል። ጋዜጠኛ ግዛው ታዬ ከዓመት በፊት የሶስት ዓመት ከ3 ወር እስራት እንደተፈረደበት ይታወሳል።

ግዛው ታዬ

ግዛው ታዬ

ከ800 ሺህ ብር በላይ ታክስ በማጭበርበርና በሌሎች 14 ክሶች ጥፋተኛ የተባለው የሎሚ መጽሄት ዋና ስራ አስኪያጅ በ18 ዓመት ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነ።
ውሳኔውን የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት ነው ያስተላለፈው።
ተከሳሾቹ ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ታዬ ግዛው ናቸው።
የፌደራል ገቢዎች እና ጉሙሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፥ ድርጅቱም ሆነ ስራ አስኪያጁ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ክሱ እስከተመሰረተበት ድረስ ለተከታታይ 5 ዓመታት ኦዲት አልተደረጉም።
በዚህ ሂደትም ድርጅቱም ሆነ ግለሰቡ የታክስ ማጭበርበሮችን ሲያከናውን ቆይቷል ሲል የአቃቤ ህግ ክስ ያስረዳል።
የተጨማሪ እሴት ታክስ እና የገቢ ግብር መሰወር የሚለውም በወንጀል ድርጊቱ ማስረጃዎች ጉዳይ ሲሆን፥ እንደ አቃቤ ህግ ገለጻ በዚህ ሂደት ውስጥ ድርጅቱ እና ስራ አስኪያጁ ለመንግስት መግባት የነበረበትን ከ800 ሺህ ብር በላይ አሳጥተዋል ይላል።
በዚህ የክስ መዝገብም ግለሰቡ በችሎቱ አልቀረበም።
ይህን ተከትሎም የክስ ሂደቱ በሌሉበት እንዲቀጥል በተሰጠው በይን መሰረት አቃቤ ህግ የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
ጉዳዩን ሲመለክት የቆየው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት 8ኛ የወንጀል ችሎት በተከሳሾች ላይ የቀረበው ማስረጃ ወንጀሉን ስለመፈጸማቸው የሚያረጋግጥ ነው ሲል ቅጣቱን አስተላልፏል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ስምንተኛ የወንጀል ችሎት ዛሬ በዋለው ችሎት ዳዲሞስ ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት በ200 ሺህ ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲሁም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛውታዬ ላይ ደግሞ የ18 ዓመት ጽኑ እስራት እና የ100 ሺህ የገንዘብ ቅጣት አስተላልፏል።
የድርጅቱ ሎሚ መፅሔት (ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንት) ባለቤትና ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ አቶ ግዛው ታዬ ከዚህ በፊት “አመጽ በማስነሳት እና መሰል የሽብርተኝነት ወንጀሎች” ክስ ተመስርቶበት በ50 ሺህ ብር ዋስ ከተለቀቀ በኋላ መሰደዱ ይታወቃል፡፡ የአሁኑ ክስና ፍርድም ተከሳሹ በሌለበት ተወስኗል፡፡
ፍርድ ቤቱ ያሳለፈውን ውሳኔ በተመለከተ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽንን/ሬዲዮ ፋናን/ ዋቢ በማድረግ ቃልኪዳን ትዩብ ዘግቧል፡፡

%d bloggers like this: