Daily Archives: December 2nd, 2016

እውቁ ፖለቲከኛ እና የኦፌኮ/መድረክ ከፍተኛ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ

(አዲስ ሚዲያ)የኦሮሞ ፌደራሊስት ሊቀመንበር እና የኢትዮጵ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንደነግ ግንባር (መድረክ) ምክትል ሊቀመንበር የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ታሰሩ፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት በቤልጂየም ብራሰልስ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ በተጋበዙት መሰረት ንግግር አድርገው ረቡዕ ህዳር 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሀገር ቤት ሲመለሱ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርሱ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸው ታውቋል፡፡ ዶ/ር መረራ የታሰሩት አብረዋቸው ከነበሩ ከሁለት የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ጋር እንደነበርም ታውቋል፡፡

dr-merera-gudina-aau

ገዥው የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት በበኩሉ ዶክተር መረራ የታሰሩት “በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመሪያ ቁጥር አንድ አንቀጽ 2 ላይ የተመለከተውን መመሪያ ተላልፈው በመገኘታቸው እና ከአርበኞች ግንቦት 7 መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር ተገናኝተው መግለጫ ሰጥተዋል“ በሚል መሆኑን በልሳኑ ፋና ብሮድካሲቲንግ ኮርፖሬት ዘገባ ይፋ አድርጓል፡፡

መንግሥት ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. የተቀሰቀሰውን የኦሮሚያ ክልል የፀረ አገዛዝ ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ፤ በተመሳሳይ መልኩ ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል እና በደቡብብ ክልል ኮንሶ የተዛመተውን ሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ ተከትሎ ከ1400 በላይ ዜጎች ሲገደሉ ከአንድ ሺህ ያላነሱ በፀጥታ ኃይሎች ወታደራዊ ርምጃ የቆሰሉ ሲሆን፤ ከ50 ሺህ ያላነሱ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ የፖሊስ መረጃዎችና የሰብዓዊ መብት አራማጆች መረጃ አመልክቷል፡፡የህወሓት/ኢህአዴግ ደጋፊዎችም ዶ/ር መረራ በአውሮፓ ፓርላማ ንግግር ማድረጋቸውን ተከትሎ እንደሚታሰሩ የሚያመለክት ቅስቀሳ ሲያደሩ እንደነበረም መረጃዎች አመልክተዋል፡፡

በተለይ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀውን የፀረ አገዛዝ ህዝባዊ ተቃውሞውን ተከትሎ ገዥው መንግሥት መስከረም 28 ቀን 2009 ኣ.ም ጀምሮ ለ6 ወራት ተግባረዊ የሚደረግ የአስቸኳይ ዚጌ አዋጅ አውጥቷል፡፡ አዋጁ ተግባራዊ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ጋዜጠኞች፣ የተለያዩ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ የመብት አራማጆችንና ሲቭል ማኀበረሰቡን ጨምሮ በአንድ ወር ብቻ ከ11,706 ማሰሩን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም፡፡

ዶ/ር መረራ ጉዲና በቅርቡ በጡረታ እንዲሰናበቱ ከመደረጋቸው በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህርነት ለ28 ዓመታት ያገለገሉና የፓርላማ አባል የነበሩ ሲሆን፤ ላለፉት 20 ዓመታትም በሀገሪቱ ፖለቲካ ባላቸው ተሳትፎ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሚታወቁና ከፍተኛ ተቀባይነት እንዳላቸው ይታወቃል፡፡ ቀደም ሲል የፓርቲያቸው ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባ፣ ዋና ፀሐፊያቸው አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ደስታ ዲንቃን ጨምሮ በርካታ አመራሮችና አባሎቻቸው ከአንድ ዓመት በፊት መታሰራቸው ይታወቃል፡፡

%d bloggers like this: