Category Archives: Human Rights

የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አቶ ዮናታን ተስፋዬን ፍር ቤት እንዳልቀረበ ተገለፀ

በኦሮምያ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማስቀጠል ፌስቡክ ላይ በመጻፍ ተንቀሳቅሰሃል በሚል በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የቀረበበት የሰማያዊ ፓርቲ የቀድሞው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ  ሐምሌ 20 ቀን 2008 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀጠሮ የነበረው ቢሆንም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ተከሳሹን አላቀረበውም፡፡

Yonatan Tesfaye

የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ለዛሬ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ይዞ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ተከሳሽ በእስር የሚገኝበት የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሳያቀርበው ቀርቷል፡፡ ተከሳሹን ለምን እንዳላቀረበ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ተወካይ እንዲያስረዳ ተጠይቆ፣ የዕለቱ ጉዳይ አስፈጻሚ ሳሙኤል ደሚ ‹‹ተከሳሹ ታሞ አላቀረብነውም›› የሚል መልስ በቃል ሰጥቷል፡፡

ከሳሽ የፌደራል አቃቤ ህግ ሁለት ምስክሮቹን ለማሰማት አቅርቦ ነበር፡፡ ሆኖም ተከሳሹ ባለመቅረቡ ሁለቱ ምስክሮች አቶ አብርሃም ወልዴ እና አቶ መኮንን በላይ በቀጣይ ቀጠሮ ተጨማሪ መጥሪያ ሳያስፈልጋቸው ቀርበው እንዲመሰክሩ በዳኞች ተነግሯቸው ተመልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ሁለቱን ምስክሮች ለመስማት ለሐምሌ 22 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በሌላ በኩል አቶ ዮናታን ተስፋዬ በጨለማ ቤት ታስሮ እንደሚገኝና በእስር ቤት ሰብዓዊ መብት ጥሰት እየተፈጸመበት እንዳለ ጠቅሶ አያያዙ እንዲሻሻልለት ሰኔ 14 ቀን 2008 ዓ.ም አቤቱታ ማስገባቱ ይታወሳል፡፡

ማረሚያ ቤት ለዚህ አቤቱታ ሐምሌ 14 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ መልስ ሰጥቷል፡፡ ችሎት ሳይሰየም ጉዳዩን በቢሮ የተመለከቱት ዳኞች የተሰጠውን የጽሁፍ መልስ ለተከሳሽ ጠበቃ በንባብ አሰምተዋል፡፡ በዚህም ማረሚያ ቤቱ ጨለማ ክፍል እንደሌለው፣ አቶ ዮናታን ከሌሎች እስረኞች በተለየ እንዳልተያዘ በመግለጽ ተከሳሹ ያቀረበው አቤቱታ ከእውነት የራቀና ስም ማጥፋት ስለሆነ ፍርድ ቤቱ ማስጠንቀቂያ ይስጥልኝ የሚል መልስ እንደሰጠ የጽሁፍ መልሱ በንባብ ሲሰማ ለመረዳት ተችሏል፡፡

የተከሳሽ ጠበቃ በበኩላቸው የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር የሰጠው መልስ ክህደት መሆኑን በመግለጽ፣ ደንበኛቸው ችሎት ያልቀረበው በማመልከቻው ላይ እንደገለጸው የመብት ጥሰት እየተፈጸመበት መሆኑን በመቃወም የርሃብ አድማ ላይ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ደንበኛዬ በማመልከቻው የገለጸው የመብት ጥሰት እንደተፈጸመበትና እየተፈጸመበት ስለመሆኑ ማስረጃ አለን›› ብለዋል የተከሳሽ ጠበቃ፡፡ ፍርድ ቤቱ በበኩሉ ጉዳዩን ተከሳሹ በአካል ሲቀርብ እንደሚያየው በመግለጽ ለሐምሌ 22 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ ዛሬ ችሎት ያልቀረበው ለሳምንት የዘለቀ የርሃብ አድማ ላይ በመሰንበቱ ሰውነቱ ተዳክሞ ሊሆን እንደሚችል ከቤተሰቦቹ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ተከሳሹ ባለፈው ቀጠሮ የእምነት ክህደት ቃሉን በሰጠበት ወቅት፣ ‹‹ክሱ በቀረበበት መንገድ የተገለጸውን የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም፡፡ ሀሳቤን በነጻነት የመግለጽ መብቴን ተጠቅሜ ግን ጽፌያለሁ፡፡ በመሆኑም የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም፤ ጥፋተኛ አይደለሁም›› ማለቱ ይታወሳል፡፡
ምንጭ፡- ኢሰመፕ

ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ

ሁለት ኢትዮጵያውያን ካይሮ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን በራፍ ራሳቸውን አቃጠሉ። በቅርቡ ኦሮሚያ ከተካሄደው መጠነ ሰፊ ግድያና እስራት ሸሽተው ግብጽ መድረሳቸው የተገለጸው እነዚህ ሁለት የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ ኢትዮጵያውያን፣ ራሳቸውን ያቃጠሉት በተቃውሞ መሆኑን ተመልክቷል።

UNHCR

ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን በማቃጠል ተቃውሟቸውን የገለጹት የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን የካይሮ ቢሮ የስደተኝነት ጥያቄያቸው ውድቅ በማድረጉ እንደሆነም መረዳት ተችሏል። በግብፅ ካይሮ የሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) በርካታ ኢትዮጵያውያን የጥገኝነት ጥያቄ ውድቅ በማድረጉ ብዙዎች በባህር ወደ አውሮፓ ለመሻገር በሚያደርጉት ጉዞ ህይወታቸው ማለፉ ይታወቃል።

ለጊዜው ስማቸው ያልታወቀው ኢትዮጵያውያን መቃጠላቸውን ተከትሎ ፖሊስ በስፍራው መድረሱን እና ራሳቸውን ካቃጠሉት ኢትዮጵያውያን አንዱ ቆዳው ጉዳት መታየቱን ተጠቁሟል፡፡ የሁለቱም ጤንነት አሁን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም።

የእነ ኦሞት አግዋ ላይ ዛሬም የአቃቤ ህግ ምስክር ሳይሰማ ተቀጠረ

ከመጋቢት 2007 ዓ.ም ጀምሮ የዋስ መብት በፍርድቤት ተከልክለው በእስር የሚገኙት እነ ኦሞት አግዋ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. የህግ አማካሪና ጠበቃቸው አመሃ መኮንን በህመም ምክንያት ችሎት ባለመገኘታቸው መዘገቡ የአቃቤ ህግ ምስክር ለመስማት ብቻ ለዘጠነኛ ጊዜ ተቀጥሯል፡፡

Omot Agua

አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት አግዋ ጠበቃችን አመሃ መኮንን ታመው ሆስፒታል የተኙ ስለሆነ ያለእርሳቸው ውክልና ምስክር እንዳይሰማብን ፍርድቤቱ አጭር ቀጠሮ ይስጠን ሲሉ ሶስቱንም ተከሳሾች ወክለው ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡

በዕለቱ ችሎት አቃቤ ህግ አሉኝ ካላቸው ሰባት ምስክሮች መካከል ሶስቱ በችሎቱ ምስክርነታቸውን ለመስጠት ቀርበው ነበር፡፡

ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለአቃቤ ህግ ምስክር ለመሆን የመጡት ቄስ ሽብሩ ኦጅራ በተደጋጋሚ መጥተው ሳይመሰክሩ ተመልሰውብኛል ስለዚህ እንዲመሰክሩ ይደረግልኝ ብሎ ለተከራከረው አቃቤህግ፣ ዳኛ ታረቀኝ አማረ የስነስርዓት ህጉ ተከሳሾች ያለጠበቃቸው ውክልና እንዲከራከሩ አይፈቅድም በሚል ጥያቄውን ውድቅ አድርገውታል፡፡

የአቃቤ ህግ ምስክር ቄስ ሽብሩ ከምዕራብ ሸዋ ባኮ ከተማ ለምስክርነት ለመጡበት የሁለት ቀን ትራንስፖርት እና አበል እንዲከፈላቸው እንዲሁም ዛሬ የቀረቡ ምስክሮች ያለምንም የፍርድቤት መጥሪያ ሌሎች ተጨማሪ የአቃቤህግ ምስክሮች በጠቅላላ በቀጣይ ቀጠሮ ነሐሴ 9 ቀን 2008 ዓ.ም እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ወንጀል ክስ ቀርቦባቸው ክሳቸው ከነሐሴ 29 ቀን 2007 ዓ. ም ጀምሮ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት አየታየ የሚገኛው የእነ ኦሞት አግዋ ሶስት ተከሳሾች ያሉበት(ኦሞት አጉዋ፣ አሽኔ አስቲን እና ጀማል ኡመር ) የክስ መዘገብ ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮችን ማሰማት የጀመረው መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም ነው፡፡
ምንጭ፡- EHRP

በእነ በቀለ ገርባ የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላለፈ

*ወህኒ ቤት ለአቶ በቀለ ገርባ የታዘዘውን መድሃኒት ፈልጌ ማግኘት አልቻልኩም ብሏል

Bekele Gerba

በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሰው በቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኙት እነ በቀለ ገርባ (22 ሰዎች) የእስር ቤቱ አስተዳደር የሰብዓዊ መብት ጥሰት እያደረሰባቸው መሆኑን ሰኔ 15 ቀን 2008 ዓ.ም ለፍርድ ቤት ባቀረቡት አቤቱታ ላይ ችሎቱ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት (ጉዳያቸውን ያይ የነበረው 19ኛ ወንጀል ችሎት እንደነበር ይታወሳል 19ኛ ችሎት ለሁለት ተከፍሎ አዲስ 4ተኛ ችሎት የሽብር ጉዳዮችን ማየት ጀምሯል) በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ሰኔ ቀን 2008 ዓ.ም የሰጠውን መልስ ተመልክቶ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾች ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም ወደ ፍርድ ቤት ሲወሰዱ ድብደባ እንደደረሰባቸው፣ ልብሶቻቸው እንደተወሰዱባቸው፣ በጨለማ ቤት ስለመታሰራቸው፣ በህክምና የታዘዘን መድሃኒት እንዳያገኙ ስለመደረጋቸው፣ ቤተ መጽሐፍት እንዳልተሟላላቸው፣ በቤተሰቦቻቸው እንዳይጎበኙ ገደብ እንደተጣለባቸው፣ ገንዘብ እንደተወሰደባቸው እና ሌሎች የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንደደረሱባቸው አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር በበኩሉ አቤቱታቸውን ‹‹የተቋሙን ስም ለማጥፋት›› የቀረበ ነው ሲል አጣጥሎ መልስ መስጠቱ ይታወቃል፡፡

በዚህ ላይ ፍርድ ቤቱ ዛሬ ውሳኔውን አሳውቋል፡፡ በዚህ መሰረት በሀኪም የታዘዘን መድሃኒት ማግኘት አልቻልንም በሚል ተከሳሾች ላቀረቡት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ የእስር ቤቱ አስተዳደር ተጠርጣሪዎቹ መድሃኒቱን እንዲያገኙ እንዲፈቅድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾች ድብደባ ደርሶብናል፣ ገንዘብም ተወስዶብናል በሚል ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ድርጊቱ ተፈጽሞ ከሆነ ወንጀል ስለሆነ አስፈላጊውን ማጣራት አድርገው ተከሳሾች በህግ ሊጠይቁ የሚገባቸው ስለሚሆን በዚህ የክስ መዝገብ ውሳኔ ሊሰጥበት አይችልም ብሏል፡፡
ተከሳሾች በጨለማ ክፍል መታሰራቸው ህግን ያልተከተለና የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በተመለከተ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ፍርድ ቤቱ ‹‹በማረሚያ ቤቱ በኩል ጨለማ ቤት የለም ተብሏል፤ ተከሳሾች ደግሞ ጨለማ ክፍል ታስረናል ብለዋል፡፡ ይህ ጉዳይ ማጣራትን የሚጠይቅ ስለሆነ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ጉዳዩን አጣርቶ ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም አስተያየቱን ይስጥበት›› የሚል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

የቤተ መጽሐፍትና የቴሌቪዥን አለመሟላትን እና የቤተሰብ ጥየቃ ሰዓትን በተመለከተ በተከሳሾች የቀረበውን አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ‹የማረሚያ ቤቱን አስተዳደራዊ አሰራር የሚመለከት ስለሆነ ውሳኔ አንሰጥበትም› በሚል አልፎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አቶ ደጀኔ ጣፋ በቤተሰብ መጎብኘት ህገ መንግስታዊ መብታችን እንጂ የአስተዳደር ጉዳይ ነው ተብሎ የሚታለፍ እንዳልነበር በመጥቀስ በውሳኔው ላይ ቅሬታቸውን ለችሎቱ አሰምተዋል፡፡

ሌላ የተሰሙ አቤቱታዎች

ፍርድ ቤቱ ቀደም ብሎ በተከሳሾች ለቀረቡት አቤቱታዎች ውሳኔ ቢያሳልፍም ዛሬም ሌሎች አቤቱታዎች ቀርበውለታል፡፡ በዋናነት አቶ በቀለ ገርባ የታዘዘላቸውን መድሃኒት አለማግኘታቸውን በተመለከተ የቀረበ አቤቱታ ሲሆን፣ አቶ በቀለ መድሃኒት ከታዘዘላቸው ሁለት ወራት ቢቆጠርም መድሃኒቱን ማግኘት አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡

የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር ዋና ኦፊሰር የሆኑት ተሾመ ስዩም በጽሁፍና በቃል በሰጡት መልስ እንደተመለከተው ለአቶ በቀለ ገርባ በሀኪም የታዘዘላቸው መድሃኒት በአስተዳደሩ ባለሙያዎች በመንግስትና በከነማ መድሃኒት ቤቶች ተፈልጎ ሊገኝ አልቻለም፡፡ ‹‹መድሃኒቱ ተፈልጎ አለመገኘቱንና የሚችሉ ከሆነ በቤተሰብ በኩል እንዲሞክሩ ለአቶ በቀለ ነግሬያቸዋለሁ›› ብለዋል ዋና ኦፊሰሩ፡፡

አቶ በቀለ ገርባ በበኩላቸው በኦፊሰሩ የተሰጠው መልስ ስህተት ነው ብለዋል፡፡ ‹‹ዛሬ ፍርድ ቤት እንደምቀርብ አውቀው የተዘጋጁበት መልስ ነው፡፡ ለእኔ የነገሩኝ ነገር የለም›› ብለዋል አቶ በቀለ፡፡ ፍርድ ቤቱ ይህን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ በቤተሰብ በኩል መድሃኒቱ ተገዝቶ እንዲገባ እንዲፈቅድ ማሳሰቢያ በመስጠት አልፎታል፡፡

ሌላው አቶ በቀለን ከሚኖሩበት አዳማ ከተማ ተመላልሰው ከሚጠይቋቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ልጃቸው ቦንቱ በቀለ ባለተገለጸ ምክንያት አባቷን በእስር ቤት እንዳትጠይቅና ምግብ እንዳታደርስላቸው መከልከሏን የአቶ በቀለ ጠበቃ ለችሎት በመግለጽ፣ ልጃቸው አባቷን እንድትጠይቅና ስንቅ እንድታቀብላቸው እንዲፈቀድላት ችሎቱን ጠይቀዋል፡፡ ችሎቱ ዋና ኦፊሰር ተሾምን ስለጉዳዩ ቢጠይቅም፣ ኦፊሰሩ ‹የማውቀው ነገር የለም፣ ግን ለሚመለከታቸው አካላት አሳውቃለሁ› የሚል መልስ ሰጥተዋል፡፡

በሌላ በኩል 22ኛ ተከሳሽ የስዋህሊኛ ቋንቋ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በተደጋጋሚ አቤቱታ ማቅረባቸው የሚታወስ ሲሆን፣ ስዋህሊኛ አስተርጓሚ ኬንያ ኤምባሲ ጭምር ተፈልጎ ማግኘት እንዳልተቻለ ተገልጹዋል፡፡ በመሆኑም ተከሳሹ በመጠኑ እግሊዝኛ ቋንቋ ስለሚረዱ የእንግሊዝኛ አስተርጓሚ እንዲመደብላቸው በጠበቃቸው በኩል አሳስበዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ የመቃወሚያ ብይን ለማሰማት ለሐምሌ 25 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

ምንጭ፡- EHRP

እነ በቀለ ገርባ ላቀረቡት የሰብዓዊ መብት ጥሰት አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ምላሽ ለመስጠት ዳግም ቀጠሮ ሰጠ

– አቶ ደጀኔ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መገናኘት እንዲችሉ ፍርድቤቱ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
– አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አቤት ብለዋል፡፡
– አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ሰለታመሙ ህክምና እንዲያገኙ ፍርድቤቱን ጠይቀዋል፡፡
– ተከሳሾች ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀው፡ ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሏል፡፡

Bekele-June-27-court-150x150

ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ጉርሜሳ አያኖ መዝገብ ክስ የተመሰረተባቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ በቀለ ገርባና ሌሎች አመራሮች(22 ተከሳሾች) ዛሬ ሐምሌ 8 ቀን 2008 ዓ.ም ችሎቱን ከሚመሩት ሶስት ዳኞች መካከል ዳኛ ታደለ ተገኝ ስልጠና ላይ በመሆናቸው የተከሳሾችን አቤቱታ እና የማረሚያ ቤቱን ምላሽ መርምረው ብይን መስራት እንዳልቻሉ ዳኛ ሳሙኤል ታደሰ ለተከሳሾች አስረደተዋል፡፡

ፍርድቤቱ ብይኑን ለመሰጠት ማክሰኞ ሐምሌ 12 ቀን 2008 ዓ.ም ከሰዓት በኃላ ቀጥሯል፡፡
የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት አዲስ አበባ ድረስ መጥተው በጡረታ መታወቂያ ልጃቸውን ለማየት እንደተከለከሉ ያሰረዱት የተከሳሽ ጠበቃ ፍርድቤቱ መፍትሄ እንዲሰጣቸው ጠይቀው ፍርድቤቱ በተለየ ሁናቴ የአቶ ደጀኔ ጣፋ እናት ስም ከነአባት በዝርዘር ጠይቆ ለማረሚያ ቤቱ ጉብኝት እንደፈቀድላቸው ትዕዛዝ እንደሚሰጥ ገልጿል፡፡

አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ደጀኔ ጣፋ በሀኪም የታዘዘላቸውን መድሃኒት እንዳያገኙ መደረጋቸውን ለችሎት በድጋሚ አመልክተዋል ፤በሌላ በኩል አቶ ጉርሜሳ አያኖ ጆሮቸውን ታመው ህክምና ቢጠይቁ ከህመም ማስታገሻ ውጪ ምንም እርዳታ እንዳልተሰጣቸው እና ለከፍተኛ ህመም መጋለጣቸውን አስርድተዋል፡፡ ፍርድቤቱ ህክምናን በተመለከተ ተከሳሾቹ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ ትዕዛዝ ለማረሚያ ቤቱ ስጥቷል፡፡

በተያያዘ የተከሳሾችን አቤቱታ ሲሰማ የዋለው ችሎት ተከሳሾች ክስ ተመስርቶባቸው ከማዕከላዊ ፖሊስ ምርመራ ወደ ቅሊንጦ ማረሚያቤት ሲገቡ ማረሚያቤቱ የወሰደባቸው 825 ብር እንዲመለሰላቸው ጠይቀዋል፡፡ ተከሳሾች ብራቸውን ቆጥረው ለማረሚያ ቤቱ እንዳስረከቡ ምስክሮች አሉን ቢሉም ማረሚያ ቤቱ ምንም ብር አልተረከብኩም ብሎ ለፍርድቤቱ ደብዳቤ ልኮ አስታውቋል፡፡

ምንጭ፡-የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት