ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ
ብስራት ወልደሚካኤል
በስደት ላይ የነበረው ታዋቂው ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ። ጋዜጠኛው ከነሐሴ 3 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በስደት ይኖርበት ከነበረው ጎረቤት ሀገር ኬንያ ናይሮቢ እያለ ባጋጠመው ህመም ምክንያት ረቡዕ ታህሣሥ 25 ቀን 2010 ዓ. ም. ከሰዓት በኋላ በተወለደ በ38 ዓመቱ ህይወቱ አልፏል። የቀብር ሥነ ሥርዓቱም በትውልድ ከተማው አዲስ አበባ በሚገኘው ኮልፌ የሙስሊሞች መካነ መቃብር ሥፍራ ቤተሰቦቹ፥ ወዳጆቹ፥ የሙያ አጋሮቹ እና አድናቂዎቹ በተገኙበት ዛሬ አርብ ታህሣሥ 27 ቀን 2010 ዓ. ም. ተፈፅሟል።

ፎቶ፡ ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ አህመድ (ከጋዜጠኛው ማኅበራዊ ገፅ የተወሰደ)
ጋዜጠኛው ቀደም ሲል በ1997 ዓ. ም. ተደርጎ የነበረውን ምርጫ ውጤት ተከትሎ በተፈጠረው አለመግባባት መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ ከታሰሩና ጉዳት ከደረሰባቸው በርካታ ዜጎች መካከል ኢብራሂም ሻፊ አንዱ የነበረ ሲሆን፤ በወቅቱ ሸዋ ሮቢት ወህኒ ቤት ተወስዶ በመንግሥት የፀጥታና የደህንነት ኃይሎች ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞበት አካሉ ላይ ጉዳት ደርሶ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፤ ያኔ የደረሰበት ድብደባ ህመሙ ፀንቶበት በመጨረሻም ለህይወቱ ማለፍ ምክንያት መሆኑ ተጠቁሟል።
የጋዜጠኝነት ሥራ ከጀመረበት ኢትዮ – ስፖርትና መዝናኛ ጋዜጣ በተጨማሪ ኤፍ ኤም አዲስ ሬዲዮ ቶክ ስፖርት፥በሸገር ኤፌ ኤም ሬዲዮ ኳስ ሜዳ እንዲሁም እንዳልክና ማኀደር ፕሮግራም ሰርቷል። በመጨረሻም በምክትል ዋና አዘጋጅነት ይሰራበት የነበረው አዲስ ጉዳይ መፅሔት በተለይም ምርጫ 2007 ዓ. ም. ዋዜማ ተከትሎ መንግሥት በስራ ላይ የነበሩ 5 ምፅሔቶችና 1 ጋዜጣ ላይ ክስ በመመስረት አዘጋጆቹ ላይ ርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀቱ ከታወቀ በኋላ ባልደረቦቹን ጨምሮ ከተሰደዱ ከ30 በላይ የሀገሪቱ ጋዜጠኞች አንዱ ነበር።
ጋዜጠኛ ኢብራሂም ሰኞ መስከረም 2 ቀን 1972 ዓ.ም. ከአባቱ አቶ ሻፊ አህመድ እና ከእናቱ ከወ/ሮ ኬሪያ ጀማል አዲስ አበባ ልዩ ቦታው ከለገሐር ጀርባ በሚገኘው በተለምዶ ቂርቆስ በሚባል አካባቢ ተወለደ። ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስም በመጀመሪያ ፈትህ የሙስሊም ትምህርት ቤት፤ በመቀጠልም ፈለገ ዮርዳኖስ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲሁም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አብዮት ቅርስ ትምህርት ቤት ካጠናቀቀ በኋላ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በመግባት፤ በ1993 ዓ. ም. በፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት የመጀመሪያ ድግሪውን አግኝቷል።
ጋዜጠኛ ኢብራሂም ከዩኒቭርስቲ ከተመረቀ በኋላ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግሥት ተመድቦ የወቅቱ የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር የፖለቲካ ጉዳዮች አማካሪ በመሆን ለአጭር ጊዜ ካገለገለ በኋላ ወደ አዲስ አበባ ተመልሷል ። አዲስ አበባ ከተመለ በኋላ በትምህርት ሚኒስቴር በመቀጠር ከፍተኛ 12 አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲሁም ዳሎል ኮሌጅ በመምህርነት በማገልገል ላይ ሳለ ነበር ወደ ጋዜጠኝነት ሙያ የተቀላቀልው ። ጋዜጠኛ ኢብራሂም ምንም እንኳ ስራውን የጀመረው ብስፖርት ጋዜጠኝነት ቢሆንም በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፥ ማኅበራዊና ሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ላይ ሐሳቦቹን በመሰንዘር የሚኢታወቅ ሲሆን፤ ለተወሰ ጊዜም የአዲስ አበባ ዩኒቭርስቲ እግር ኳስ አሰልጣኝ በመሆንም አገልግሏል።
ብዙዎች የሚያውቁት በስፖርት ትንታኔው እንዲሁም በኢትዮጵያ ፖለቲካና ማኀበራዊ ጉዳዮች ላይ በሚሰነዝራቸው ሐሳቦቹ ቢሆንም በተለያዩ ማኀበራዊ በጎ አድራጎት ተግባራት ላይም ንቁ ተሳታፊ ነበር። በተለይም ሀገር ቤት ተወልዶ ባደገበትና በኖረበት አዲስ አበባ ቂርቆስ ሰፈር አቅመ ደካማ ወላጆች ያላቸውና እገዛ የሚሹ ህፃናት በየ ዓመቱ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉና እንዲያጠናቅቁ ከሰፈር ጓደኞቹ ጋር በመሆን ድጋፍ በማስተባበርና በመለገስም የሚታወቅ ሲሆን፤ በተለይም አዲሱ የትምህርት ዓመት ከጀመሩ በፊት ነሐሴ ወር ላይ ገንዘብና ለትምህርት የሚያስፈልጉ ደብተር እስክሪብቶ፥ እርሳስና የመሳሰሉትን የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችን በመለገስ ተሳትፎ ላይም ዋና ተዋናይ እንደነበርም መረጃዎች አመልክተዋል።
ጋዜጠኛው ከቤተሰቦቹ በተጨማሪ በሙያ ባልደረቦቹ፥ ጓደኞቹና አድናቂዎቹ የሚወደድና ተግባቢ ጋዜጠኛ እንደነበር ይታወቃል። ለሀገሩ እና ለህዝቡ ያለው ፍቅርና ተቆርቋሪነትም በስፋት የሚታወቅበት መለያው ነበር። በተለይ ከመደበኛው የጋዜጠኝነት ስራው በተጨምሪ ከሀገሩ እስኪሰደድ ድረስ የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኀበር ስራ አስፈፃሚ አባል በመሆን ያገለገለ ሲሆን፤ ደቡብ አፍሪካና ብራዚል የተካሄዱ የዓለም ዋንጫ ጨዋታ የቀጥታ ዘገባዎች በተጨማሪ በተለያዩ ዓለም ዓለም አቀፍ ዘገባዎችን በአካል በመገኘት ለሀገር ውስጥ አድማጭና አንባብዎች መረጃዎችን ያቀርብም እንደነበር ይታወቃል።
ዳጉ ሚዲያም በጋዜጠኛ ኢብራሂም ሻፊ ሞት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን እየገለገፀ፤ ለጋዜጠኛው ነፍስ እረፍትን፥ ለወዳጅ ቤተሰቦቹና አድናቂዎቹ መፅናናትን ይመኛል።
ፍርድ ቤት በባለስልጣናቱ ምስክርነት ጉዳይ ብይን መስጠት አልቻለም
ጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት በጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እና የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ምስክርነት ጉዳይ ላይ ዛሬ ብይን እሰጣለሁ ባለው መሰረት ብይን መስጠት አልቻለም።
ታህሳስ 17 ቀን 2010 ዓ.ም. አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በጊዜ ጥበት ምክንያት ፍርድ ቤት ቀርበው መመስከር እንደማይችሉ በጠቅላይ ሚንስትሩ ፅህፈት ቤት በኩል ለፍርድ ቤቱ በደብዳቤ ተገልፆአል። በዚሁ ቀን አቶ ለማ መገርሳን ጨምሮ በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ተከሳሾች መከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱት የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት መቅረብ ባለመቻላቸው ፍርድ ቤቱ በቀጠሮው መጨረሻ፣ ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ብይን እሰጣለሁ ብሎ የነበር ቢሆንም ብይን ሳይሰጥ ቀርቷል። ታህሳስ 17 ቀን 2010 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ተከሳሾች አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ታስረው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ለችሎት ያመለከቱ ሲሆን ለኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ትዕዛዝ ስላልደረሳቸው በቀሪዎቹ ሁለት ቀናት ይቀርባሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር።
ትናንት ታህሳስ 18 ቀን 2010 ዓ.ም. በእነ ጉርሜሳ አያኖ የክስ መዝገብ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ተከሳሾች ጠበቃ አብዱልጀባር ሁሴን በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሱትን የኦሮምያ ባለስልጣናት በአካል አግኝተው ባነጋገሯቸው መሰረት ባለስልጣናቱ ለዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው ሊመሰክሩ እንደሚችሉ ለፍርድ ቤቱ አስረድተው ነበር። ይሁንና ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት በስብሰባ ምክንያት ቀርበው መመስከር እንዳልቻሉና ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ፍርድ ቤት ቀርበው እንዲመሰክሩ ከኦህዴድ ማህከላዊ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት በተፃፈ ደብዳቤ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል።
ሆኖም ፍርድ ቤቱ በቀጠሮው የመጨረሻ ታህሳስ 19 ቀን 2010 ዓ.ም. አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ታስረው እንዲቀርቡ የተነሳው አቤቱታ ላይ ብይን ይሰጣል ተብሎ ሲጠበቅ በዚህ ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል። ከአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በተጨማሪ በስብሰባ ምክንያት ለዛሬ ቀርበው መመስከር ባለመቻላቸው ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው በደብዳቤ የጠየቁት የእነ ለማ መገርሳ አቀራረብ ጉዳይ ላይም ታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ብይን እሰጣለሁ ብሏል።
የተከሳሾቹ ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን ባለስልጣናቱ ተለዋጭ ቀጠሮ በጠየቁበት ሁኔታ በእነሱ ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ መያዙ ግልፅ እንዳልሆነ ተናግረዋል። ታህሳስ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. በባለስልጣናቱ የመከላከያ ምስክርነት አቀራረብ ላይ ብይን ለመስጠት ብቻ የተያዘ ቀጠሮ ሲሆን ለተከሳሾቹ ከየካቲት 5 እስከ የካቲት 9 ተከታታይ ቀጠሮ ተይዟል።
በውዝግብ የተጠናቀቀው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የችሎት ውሎ
በጌታቸው ሺፈራው
~ተከሳሾቹ ጆሯቸውን በእጃቸው ደፍነው፣ ጀርባቸውን ለዳኞ ሰጥተው ችሎቱን “አንሰማም! አናይም!” ብለዋል
~ የዐቃቤ ሕግ ምስክር ነኝ ብሎ የቀረበውን ግለሰብ ዐቃቤ ሕጉ ክዶታል።ዐቃቤ ሕጉ በሀሰት እንድመሰክር ተገድጃለሁ ያለውን ግለሰብ የእኔ ሳይሆን የጠበቃ ምስክር ነው ብሎታል።
~ጨለማ ቤት የታሰሩት መነኩሴ በቀጠሯቸው አልቀረቡም
~ እነ ተሻገር ወ/ሚካኤል ለሁለተኛ ጊዜ በዳኛው ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል። ብይኑ በማረሚያ ቤት ይደርሳቸዋል ተብሏል። ታዳሚ ወደ ችሎት እንዳይገባ ተከልክሏል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ውሎ በውዝግብ ተጠናቅቋል። በጠዋቱ የፍርድ ቤቱ የስራ ሰዓት ተከሳሾች ችሎቱን አንሰማም፣ አናይም ብለው ተቃውሞ አሰምተዋል። ከሰዓት በነበረው የችሎቱ ሰዓት የቀረቡት እነ ተሻገር ወልደሚካኤል ባሰሙት ተቃውሞ ችሎቱ ብይን ማንበብ ባለመቻሉ ብይኑን ባሉበት ለማድረስ ተገዷል። ፍርድ ቤቱ ለእነ ተሻገር በችሎት ቀጠሮ እንዳልሰጠ ታውቋል።
ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት እነ ጎይቶም ርስቃይ ጆሯቸውን በእጃቸው በመድፈን እና ፊታቸውን በማዞር ችሎቱን አንሰማም አናይም ብለው ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።
እነ ጎይቶም ዛሬ ታህሳስ 11/2010 ዓም ቀጠሮ የተያዘላቸው በክሱ ላይ ያቀረቡትን መቃወሚያ ብይን ለመስማት ሲሆን ተከሳሾቹ ብይኑ ከመነበቡ በፊት ዳኛ ዘርዓይ ወ/ሰንበት ከችሎት እንዲነሱ አቤቱታ አቅርበው፣ ብይኑ ዳኛው ከተነሱ በኋላ እንዲሰራ ጠይቀዋል።
ይሁንና ፍርድ ቤቱ ብይኑን ማንበብ በመቀጠሉ ተከሳሾቹ ጆሯቸውን በእጃቸው በመድፈን አንሰማም ብለዋል። በተጨማሪም ፊታቸውን በማዞር ጀርባቸውን ለችሎቱ ሰጥተው ብይኑ ተነቧል። ብይኑን ያነበቡት ተከሳሾቹ ከችሎት እንዲነሱ አቤቱታ እናቀርብባቸዋለን ያሏቸው ዳኛ ዘርዓይ ወ/ሰንበት ናቸው።
~ከሰዓት በነበረው የፍርድ ቤቱ የስራ ሰዓት ፍርድ ቤት የቀረቡት በእነ ተሻገር ወ/ሚካኤል የክስ መዝገብ ስር የተከሰሱ 35 እስረኞች ለ2ኛ ጊዜ በዳኛ ዘርዓይ ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል። ተከሳሾቹ ባለፈው ቀጠሮ ዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት ሊዳኙን አይገባም የሚል ተቃውሞ በማሰማታቸው ችሎት ደፍራችኋል በሚል እንደተፈረደባቸው በመግለፅ በክሱ ላይ ያቀረቡት መቃወሚያ ብይን ከመነበቡ በፊት ዳኛው ሊነሱ እንደሚገባ መግለፃቸው ታውቋል።
ይሁንና ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹ የዳኛ ይነሳልን አቤቱታ በፅሁፍ ያልደረሰው መሆኑን ገልፆ ብይኑን ለማንበብ በመሞከሩ ተቃውሞ ገጥሞታል። የተከሳሾቹ መዝገብ የያዙትና ብይኑንም ለማንበብ የሞከሩት ከችሎት እንዲነሱ ተቃውሞ የቀረበባቸው ዳኛ ዘርዓይ መሆናቸው ተገልፆአል። ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን ስም ሲጠራ ተከሳሾቹ “አቤት” ባለማለታቸው እንዳልቀረቡ (እንደሌሉ) ተደርጎ ተመዝግቧል።
1ኛ ተከሳሽ ተሻገር ወ/ሚካኤል ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኘን አይገባም ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። አቶ ተሻገር ” እኔ ወልቃይቴ ነኝ። አማራ ነኝ። እኛን በፌስቡክ ሲዘልፍ የነበረ፣ ወልቃይት ጠገዴ የትግራይ ነው እያለ ሊዳኘን አይገባም። እኛ ትናንትም፣ ዛሬም ነገም አማራ ነን። ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኘን አይገባም። ዳኛ ዘርዓይ ሊዳኝ ከፈለገ ከፖለቲካው ገለልተኛ ሆኖ ሌላ ቦታ ሄዶ ይዳኝ” የሚል ይዘት ያለው አስተያየት ሰጥተዋል።
በሌላ በኩል ቂሊንጦ እስር ቤት ያለው ጨለማ ቤት ውስጥ የሚገኙት አባ ገብረስላሴ ወልደሐይማኖት በዛሬው ቀጠሮ አልቀረቡም። ወደ ችሎቱ መግባት የተከለከለ ሲሆን ፖሊሶችን እንድንገባ ስንጠይቅ ዳኞቹ ታዳሚ እንዳያስገቡ ትዕዛዝ እንደሰጧቸው ገልፀውልናል። ቀድመው ወደ ችሎት ገብተው የነበሩ የተከሳሾች ቤተሰቦች ከችሎት እንዲወጡ ተደርጓል። እነ ተሻገር ሲናገሩ ችሎቱ በር አካባቢ ሆነን ስናዳምጥ ፖሊሶች ከችሎት እንድንርቅ አድርገዋል። ከችሎት እንድንርቅ ያደረጉት በዳኞች ትዕዛዝ እንደሆነም ገልፀውልናል።
~ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ዐቃቤ ሕግ ራሱ የቆጠረውን ምስክር የእኔ አይደለም ብሏል። በእነ ክንዱ መሃመድ የክስ መዝገብ ላይ በዐቃቤ ሕግ 1ኛ ምስክር ሆኖ የተቆጠረውን አቶ ሸዋንግዛው የሽጥላ ዐቃቤ ሕግ “የእኔ ምስክር አይደለም” ሲል ክዷል። ምስክሩ በጠዋቱ የችሎት ሰዓት በችሎት ቀርቦ በተከሳሾች ላይ በሀሰት እንዲመሰክር መገደዱን ገልፆአል። በወቅቱ ዐቃቤ ሕጉ አቶ ሓፍታሙ ቸኮለ ምስክሩን እንደማያውቀው ገልፆ የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ 1ኛ የዐቃቤ ምስክር መሆኑን በማረጋገጡ ዐቃቤ ሕጉም እንደገና 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን አምኖ ነበር።
አቶ ሸዋንግዛው የሽጥላ ከሰዓት ምስክርነቱን እንዲሰጥ ቀጠሮ በተያዘው መሰረት ከሰዓት ሲቀርብ፣ ዐቃቤ ሕጉ “የተከሳሾች ጠበቃ ምስክር እንጅ የእኔ ምስክር አይደለም” ብሎ ክዷል።
የተከሳሾች ጠበቃ አዲሱ ጌታነህ በበኩሉ ምስክሩ ዐቃቤ ሕግ በማስረጃ ዝርዝር ላይ ያስቀመጠው፣ ጠዋትም ማንነቱን ለፍርድ ቤቱ የገለፀ፣ ዐቃቤ ሕግ በጠራው መሰረት በቀጠሮው የቀረበ እና በመታወቂያውም መለየት የሚቻል መሆኑን በመግለፅ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን አስረድቷል።
ዐቃቤ ሕግ ዛሬ የቀረበው ሳይሆን ሌላና በምስክርነት ቆጥሬዋለሁ የሚለው ሸዋንግዛው ቀርቦ እንዲመሰክር ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠኝ ብሏል። ፍርድ ቤቱ 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር መሆኑን ገልፆ በቀጠሮ መሰረት የቀረበውን አቶ ሸዋንግዛው በጠዋቱ ችሎት ከተናገረው፣ ከዐቃቤ ሕግና ከተከሳሾች ጠበቃ የራሱን ግምት እንደሚወስድ በመግለፅ 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር እንዲቀርብ ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
በቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ ክስ በቀረበባቸው እስረኞች ላይ የተፈፀመ በደል
ጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ያሬድ ሁሴን ኢብራሂም የክስ መዝገብ ክስ የቀረበባቸው 25 ተከሳሾች በአዲስ አበባ ቀጠሮ ማረፊያ ቤት( ቂሊንጦ) ቃጠሎ ሰበብ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው የደረሰባቸው የሰብአዊ መብት ጥሰትን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽ አጣርቶ እንዲያቀርብ በማዘዙ ኮምሽኑ ምርመራውን ለፍርድ ቤት ልኳል።
ተከሳሾቹ ያቀረቡት አቤቱታ:_
የቀጠሮ ማረፊያ ቤት ላይ በተፈጠረው ቃጠሎ ምክንያት በቃጠሎው እጃችሁ አለበት ተብለን ነሃሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለይተን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን ኢሰብአዊ ድርጊት ተፈፅሞብናል። በሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ያልፈፀምነውን ድርጊት እመኑ እየተባልን ለሰው ልጅ በማይመጥን፣ ኢሰብአዊ የሆነ ድርጊት ተፈፅሞብናል። ለአንድ ወር ያህል በካቴና ከአልጋ ጋር ታስረናል። ተገልብጠን ተገርፈናል። የውስጥ እግራችን ተገርፈናል። አንጠልጥለው በማሰር ውሃ እየደፉብን፣ በኤሌክትሪክ ሾክ እየተደረግን ተመርምረናል። በእምነትና ማንነታችን ጥቃት ደርሶብናል። በደረሰብን ድብደባና ስቃይ ብዛት ያልፈፀምነውን ድርጊት ፈፅመናል ብለን ለማመን ተገደናል።
ወደ ቀጠሮ ማረፊያ ቤት (ቂሊንጦ) ከተመለስን በኋላ ቢሆን በደረሰብን ድብደባ ብዛት ላጋጠመን ጉዳት ህክምና አላገኘንም። በቃጠሎው ወቅት አልባሳትን ጨምሮ ንብረቶቻችን በማረሚያ ቤቱ የተወረስን ሲሆን እንዲመለሱልን ስንጠይቅ ተቃጥለዋል የሚል ምላሽ ተሰጥቶናል።
በምርመራ ወቅት ጉዳት የደረሰባቸው ተከሳሾች:_
1) ፀጋዬ ዘውዱ:_ቀኝ እግር ከጉልበቱ በታች ጠባሳ፣ ግራ እግር ላይ የግርፋት የሚመስል ጠባሰ፣ ጀርባ ላይ ጠባሳ ፣ የአውራ ጣት ጥፍር መነቀል፣ የካቴና የታሰረበት ምልክት
2) ያሬድ ሁሴን:_ ግራ እግር ላይ ጠባሳ፣ቀኝ እጅ ላይ ጠባሳ፣ የካቴና እስር ምልክቶች፣
3) ኃይለ መስቀል ፀጋዬ:_ ሁለት እጆቹ ላይ ጠባሳ
4) ሁሴን አህመድ:_ የግራ እጅ ጠባሳ
5)ሰለሞን ጫኔ:_የቀኝ እጅ የመሃል ጣት ስብራት፣ የቀኝ እግር ደም ስር መዛባት
6)ስማቸው አርጋው:_ የግራ እጅ የመጀመርያ ጣት ስብራት፣ ሁለት እጆቹ ላይ ጠባሳ፣ ሁለት እግር ታፋዎች ላይ የግርፋት ጠባሳ ምልክቶች
7)ዋሲሁን አየለ:_ በካቴና የመታሰር ምልክቶች
8) ሀቢብ ከድር:_ሁለት እጅ ላይ የጠባሳ ምልክቶች፣ ቀኝና ግራ ክንድ ላይ የጠባሳ ምልክቶች፣
9) ግሩም አስቀናው:_ ሁለት እጆቹ ላይ በካቴና የታሰረበት ጠባሳ ምልክቶች፣ ከቀኝ ታፋ በላይ ትልቅ ጠባሳ
10) ሻሾ አድማሱ:_ ወገቡ ላይ ትልቅ ጠባሳ
11)ማናዬ መንገሻ:_ የአውራ ጣት ጥፍር መነቀል
12) ቢንያም አሰፋ:_ የቀኝና ግራ እጅ ላይ በካቴና መጥበቅ ምክንያት የጠባሳ ምልክቶች
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ከላይ የተጠቀሱት እስረኞች ወደ እስር ቤት ሲገቡ የተጠቀሱት ጉዳቶችና ምልክቶች እንዳልነበረባቸው አረጋግጧል። የኮምሽኑ ምርመራው የተካሄደው ድብደባው ከተፈፀመ 10 ወር በኋላ ቢሆንም የግርፋት ምልክቶች በግልፅ እንደሚታዩ በሪፖርቱ ላይ ተገልፆአል። በመሆኑም ተከሳሾች ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው በአቤቱታው ላይ የተጠቀሰው ለሰው ልጅ የማይመጥንና ኢ ሰብአዊ የሆነ ድርጊት እንደተፈፀመባቸው ተረጋግጧል።
ይሁንና አቤቱታ ያቀረቡት 25 ተከሳሾች ሆነው ኮምሽኑ የጠቀሰው የ12 ተከሳሾችን በደል ብቻ ነው። በሌሎች መዝገቦችም ተመሳሳይ አቤቱታ ቀርቦ ኮምሽኑ ሪፖርት ያቀረበ ሲሆን በእስረኞች ላይ የተፈፀመውን በደል በሚገባ በሪፖርቱ አላጠቃለለም ተብሏል።
በደል የተፈፀመባቸው እስረኞች ካለመጠቀሳቸውም በተጨማሪ በሪፖርቱ የተጠቃለሉ እስረኞች የደረሰባቸው በደል በሚገባ አልተጠቀሰም ተብሏል። በእነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ክስ መዝገብ የተከሰሱ 38 ተከሳሾች ሸዋሮቢት ተወስደው በደል በተፈፀመባቸው 175 እስረኞች ላይ ከተፈፀመው በደል መካከል ኮምሽኑ 6 በመቶውን ብቻ በሪፖርቱ ማጠቃለሉን ተከሳሾቹ በችሎት ተናግረዋል። ኮምሽኑ የተፈፀመውን በደል በሚገባ በሪፖርቱ ባለማጠቃለሉና ገለልተኛ አይደለም በሚል ሌላ ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ የተፈፀመባቸውን አስከፊ በደል እንዲያጣራ እስረኞቹ አቤቱታቸውን ለፍርድ ቤት እያቀረቡ ነው።
ኮምሽኑ በእስረኞች ላይ በደል ፈፀሙ የተባሉ አካላትን ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲያጣራ በምክረ ሀሳብ ያስቀመጠ ሲሆን እነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ኃላፊዎች ድብደባ እንደፈፀሙባቸውና እንዳስፈፀሙባቸው የኃላፊዎችን ስም ጭምር በመጥቀስ ገልፀዋል። በመሆኑም በደል የፈፀመው አካል ጉዳዩን እንዲያጣራ መታዘዙ የደረሰብን በደል ተሸፋፍኖ እንዲቀር ስለተፈለገ ነው የሚል ቅሬታ አቅርበዋል። ከተከሳሾቹ ባሻገር ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ ያቀረባቸውና ያዘጋጃቸው ምስክሮች በምርመራ ወቅት በደረሰባቸው ድብደባ ምክንያት ተገደው ለምስክርነት እንደቀረቡና ተገደው ምስክር በሆኑት ላይ የተፈፀመው በደልም እንዲጣራ ተከሳሾች ለፍርድ ቤት አመልክተዋል።
ፍርድ ቤቱ ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጣ
በጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእስር ላይ የምትገኘው ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጥቷል። በእነ ደቻሳ ሞሲሳ የክስ መዝገብ 4 ተከሳሽ ጫልቱ ታከለ “እናንተ ኢህአዴግ ናችሁ፣ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አልጠብቅም” ብላ ተናግራለች በሚል በችሎት መድፈር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።

ፎቶ፡- ጫልቱ ታከለ
ህዳር 28 ቀን 2010 ዓም እነ ደቻሳ ሞሲሳ ተከላከሉ የሚል ብይን በተሰጠባቸው ወቅት 3ኛ ተከሳሽ የሆነችው ጫልቱ በሰነድ ማስረጃነት የቀረበባት የደህንነት ሪፖርት ወደ ኤርትራ ስለመሄድ የጠቀሰው ነገር ሳይኖር ብይን ላይ ወደ ኤርትራ ልትሄድ እንደነበር ተጠቅሶ ተከላከይ መባሏ እንዳሳዘናት ገልፃለች።
ጫልቱ ታከለ በወቅቱ “ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አንጠብቅም። ወደፊትም ፍትህ እንደማናገኝ ነው የምናስበው።” ብላ በመናገሯ በችሎት መድፈር ጥፋተኛ ተብላ በአዳር ዛሬ ህዳር 29 ቀን 2010ዓ.ም. የ500 ብር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።
ጫልቱ ታከለ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ክስ ተፈርዶባት ፍርዷን ጨርሳ እንደወጣች ተገልጿል።