በጎንደር ህዝባዊ ተቃውሞ እና ውጥረቱ ቀጥሏል
(አዲስ ሚዲያ) በጎንደር ከተማ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን የሚመሩ የኮሜቴ አባላትን ለማሰር በተወስደ እርምጃ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከፍተኛ ግጭት አስከተለ። ግጭቱ የተከሰተው ትናንት ሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ሌሊት ጀምሮ እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የመንግሥት ደህነት እና የፀጥታ ኃይሎች የወልቃይት ማንነት ጥያቄ የሚመሩ ኮሜቴ አባላት መካከል አቶ አታላይ ዘርፌ፣ አቶ ጌታቸው አደመ፣ አቶ መብራቱ ጌታሁንና አቶ አለነ ሻማ በቁጥጥር ስር ያደረገ ሲሆን፣ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ በህግ የምትፈልጉኝ ከሆነ ሲነጋ መምጣት ትችላላችሁ በማለታቸው በተፈጠረው አለመግባባትና ግጭት በግድ እጅ እንዲሰጡ በኃይል በመንቀሳቀሳቸው ኮሎኔሉ እርምጃ መውሰዳቸው ተሰምቷል። ለምንግሥት የፀታ ኃይል እጃቸውን እንዲሰጡ በኃይል የተጠየቁት ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ ቤታቸው በፀጥታ ኃይል መከበቡን ተሰምቷል፡፡ በተፈጠረው አለመግባባት ሰላማዊ ሰዎች በመንግሥት በመገደላቸው በህዝቡ በተወሰደ የአፀፋ እርምጃ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችም መገደላቸውን የኢሳት ዘገባ አመልክቷል፡፡

መንግሥት ማክሰኞ ሐምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደርና ወልቃይት አካባቢን በተመለከተ ማምሻውን በሰጠው መግለጫ በተፈጠረው አለመግባባት 3 የልዩ ሃይል ፖሊሶች ሲገደሉ፣ 5 መቁሰላቸውን አስታውቋል። ይሁን እንጂ መንግሥት ለግጭቱ መንስኤ የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን በቁጥጥር ስር ለማዋል መሆኑን ከመግለፅ በመቆጠብ በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን እና ለማዋል የፈለጋቸውን የወለወቃይት ማንነት መብት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላትን ከኤርትራ መንግሥት ጋር በማያያዘ ሲወነጅል ተሰምቷል፡፡
በያዝነው 2008 ዓ.ም. ቀደም ሲል የወልቃይት ማንነት መብት ጥያቄ አቅራቢ ኮሚቴ አባላት መካከል አቶ ሲሳይ ሊላይ የሚባሉ የኮሚቴ አባል በትግራይ ክልል ልዩ ኃይል ታግተው ከተሰወሩ በኋላ በአካባቢው ውጥረት መንገሡን ተከትሎ ወህኒ ቤት በማሰር ለፍርድ ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡ የእስርና ፍርድ ጉዳያቸውም በሰቲት ሁመራ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ፤ በጎንደር የመንግሥት የኃይል ርምጃን በመቃወም ህዝቡ ንብረትነቱ የህወሓት/ኢህአዴግ የሆነውን ሰላም የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ፣ በተጨማሪ ሌላ መለስተኛ የፀጥታ ኃይሉ ተሽከርካሪ እና በጎንደር ከሚገኙ የህወሓት የንግድ ኩባንያ መደብሮች መካከል የተወሰኑት ላይ የማቃጠል ርምጃ መወሰዱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በተቃውሞው ከጎንደር አዲስ አበባ ያሉ መንገዶችም በድንጋይ ተዘግተው ታይተዋል፡፡
መንግሥት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 አካባቢ 6 ያህል ነዋሪዎች ገድሎ ከ3 ሺህ ያላነሱ ነዋሪዎችን ቤት አፈረሰ
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ሐና ማርያም፣ ፉሪ፣ ቀርሳ፣ ኮንቱማ እና ማንጎ ጨፌ አካባቢ ነዋሪዎች ላይ መንግሥት በወሰደው የኃይል ርምጃ አንዲት ነፍሰጡር እናት እና አንድ ቄስን ጨምሮ 6 ያህል ሰዎች ሲገደሉ፤ ከ 3 ሺህ ያላነሱ የመኖሪያ ቤቶች በዶዘር እየፈረሰ መሆኑ ተጠቆመ፡፡ መንግሥት የኃይል ርምጃውን የወሰደው ሐሙስ ሰኔ 23 እና ትናንት አርብ ሰኔ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲሆን፤ በአካባቢው ህፃናት፣ ሴቶች እና ነፍሰጡር የሆኑ እናቶችን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መፈናቀላቸው ታውቋል፡፡ በተለይ አንዲት ነፍሰጡር እናት በቤቷ ተኝታ እያለ፤ ቤቷ በዶዘር ሲፈርስ እዛው መገደሏም ተሰምቷል፡፡

የቤቶቻቸውን በክረምት መፍረስና የመንግሥትን የኃይል ርምጃ የተቃወሙና በጉዳዩ ዙሪያ የሌሉትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውም የተገለፀ ሲሆን፤ የአካባቢው ወንዶች እየፈረሱ ባሉ ቤቶች አካባቢ እንዳይገኙ አካባቢው በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር መውደቁ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት የአካባቢው ነዋሪዎች ከቤቶቻቸው መፍረስ በተጨማሪ የመንግሥትን ግድያ እና እስር በመፍራት ከአካባቢው መሰደዳቸው ተጠቁሟል፡፡
መንግሥት የነዋሪዎቹን ቤት በክረምቱ የዝናብ ወቅት ጠብቆ ለምን ማፍረስ እንደወሰና እንደጀመረ ባይታወቅም፤ እንዲፈርሱ የተወሰኑ ቤቶችን የማፍረስ ስራው እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡ በአካባቢውም ቤቶቻቸው በዶዘር እንዲረስ የተደረጉባቸው ሰዎች ንበርትም አብሮ ከጥቅም ውጭ እንዲሆን መደረጉን የአካባቢው ሴቶች ይናገራሉ፡፡
ቀደም ሲል ረቡዕ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. መንግሥት ወደ 30 ሺህ የሚጠጋ የነዋሪዎችን ቤት “ህገወጥ ነው፣ መፍረስ አለበት” በሚል መወሰኑን ተከትሎ ቅሬታ በመቅረቡ፣ የአካባቢው ወረዳ 1 አስተዳደር ነዋሪውን በቦታውና በቤቶቹ ጉዳይ እንነጋገር ብሎ ሰብስቦ እያወያየ ሳለ፤ በጎን አፍራሽ ግብረ ኃይልና የፀጥታ ኃይል ልኮ ማፍረስ በመጀመሩ በተፈጠረ አለመግባባት የወረዳው ስራ አስፈፃሚ እና ፖሊሶች መገደላቸውን፣ ከነዋሪዎችም ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች መገደላቸውን እና መቁሰላቸው ይታወሳል፡፡
ከቤቶቹ መፍረስ ጋር በተያያዘ የሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ሰመጉ)፤ መንግሥት ከ19 ሺህ ያላነሱ ቤቶችን ማፍረሱን በመጠቆም፤ እየተወሰደ ያለውን የኃይል እርምጃ እንዲያቆምና ቤቶቹን አፍርሶ ነዋሪዎቹን ለጎዳና ህይወት ከመዳረግ ይልቅ መፍትሄ ሊበጅለት እንደሚገባ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ጠይቋል፡፡
በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ በተቀሰቀሰ ግጭት 4 ሰዎች ተገደሉ
(አዲስ ሚዲያ)በምስራቅ ሐረርጌ ዞን አወዳይ ከተማ ትናንት ሐምሌ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጠዋት በመንግሥት ኃይሎች እና በህዝቡ መካከል በተፈጠረ ግጭት የ9 ዓመት ህፃንን ጨምሮ 4 ያህል ነዋሪዎች በከተማው አስተዳደርና በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኘው የሐሮማያ ሆስፒታል በበኩሉ የተገደሉት ሰዎች ቁጥር 4 መሆኑን እና የቆሰሉ 3 ሰዎች በሆስፒታሉ የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው ተጠቁሟል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 6 እንደሆነ እና በፅኑ የቆሰሉት ደግሞ 4 እንደነበሩ ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ የግጭቱ መነሻ እንደሆነ የተነገረው በአወዳይ ከተማ ውስጥ ያለ አንድ የሞባይል ስልክ መሸጫ ሱቅና አጠገቡ ያለው የፍራሽ መሸጫ ሱቅ ባልታወቀ ምክንያት በመቃጠላቸው የተነሣ የአከባቢው ህዝብ እሳቱን ለማጥፋት ጥረት ቢያደርግም ሊሳካ ባለመቻሉ በአከባቢው ያሉትን የባለሥልጣናት ለእርዳታ ቢማፀኑም ቆመው ከመሳቅ ባለፈ ምንም እርዳታ ባለማድረጋቸው የተበሳጩ ነዋሪዎች “ድሮም እናንተ የምታደርጉልን ነገር የለም” ስለዚህ ከዚህ ሂዱ ብለው በመናገራቸው የፀጥታ ኃይሎች በስልክ ወደ ቦታው መጠራታቸውንና ግጭቱ መከሰቱን የአካባቢውን ነዋሪ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የነጋዴዎቹን ሱቅ ቃጠሎ ተከትሎ በህዝቡና በመንግሥት በተለይም በአካባቢው አስተዳደር አካለትና የፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት የአወዳይ ቀበሌ 02 ሊቀመንበር አቶ አብዲ ኢድሪስ በቃጠሎው ስፍራ የነበሩ ነዋሪዎች ላይ በከፈቱት ተኩስ የ9 እና የ13 ዓመት ህፃናት ቆሰሉ፡፡ በሊቀመንበሩ የቆሰሉ ህፃናትም ወደ አካባቢው የጤና ተቋም ቢወሰዱም ወዲያው ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡ በዚህም ምክንያት በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች በቁጣና በጩኸት ወደቆሰሉ ህፃናት ሲመጡ የኦሮሚያ ልዩ ፖሊስ እና የፌደራል ፖሊስ በድንገት ወደስፍራው በመምጣት፣ አንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ተኩስ ከፍቶ 3 ወጣቶች ወዲያው ሲገደሉ፤ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎችም በፅኑ መቁሰላቸውን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኝ ተናግረዋል፡፡

በመንግሥትና በህዝቡ መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት በአወዳይ የሐረር መንገድ ዝግ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ይሁን እንጂ በግጭቱ ዙሪያ እስካሁን ከመንግሥት አካል የተሰጠ መግለጫም ሆነ ማብራሪያ ማግኘት አልተቻለም፡፡
የአቶ ሀብታሙ አያሌው ጤና አደጋ ላይ በመውደቁ ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለበት እግድ እንዲነሳ ተጠየቀ
(አዲስ ሚዲያ) የቀድሞው የአንደነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበረው አቶ ሀብታሙ አያሌው የጤናው ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ በመድረሱ ተገቢውን ህክምና ማግኘት አለመቻሉ ታውቋል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ህመሙ ይበልጥ ተባብሶ ራሱን በመሳቱ በአቅራቢያ ወደሚገኘው ዋሸንግተን ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ዕርዳታ ማግኘት ባለመቻሉ ወደ ቤተዛታ ሆስፒታል ቢወሰድም ተገቢውን የህክምና ርዳታ ባለማግኘቱ ወደ ካዲስኮ ሆስፒታል ተወስዶ በማስታገሻ ሆስፒታል ውስጥ አልጋ ይዞ እንዲቆይ ተደርጓል፡፡

አቶ ሀብታሙ የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ማዕከል “ማዕከላዊ”ን ጨምሮ ለ18 ወራት ያህል በታሰረበት ባጋጠመው ህመም ምክንያት የህክምና ዕርዳታ ቢጠይቅም ከመንግሥት በጎ ምላሽ ባለመገኘቱ ከእስር በነፃ ከተለቀቀ በኋላ ህመሙ እንደተባባሰ ተጠቁሟል፡፡
አቶ ሀብታሙ በሀገር ውስጥ ባሉ የተለያዩ የህክምና ተቋማት ተገቢውን የህክምና ክትትል ለማድረግ ቢንቀሳቀስም ህመሙ ካለበት ከፍተኛ ደረጃ አንፃር አቅም ካለው ከሀገር ውጭ ሄዶ ቢታከም የተሻለ እንደሆነ ከዶክተሮቹ በተነገረው መሰረት በውጭ ሀገር ህክምና ማድረግ ቢፈልግም፤ የፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከሀገር እንዳይወጣ በጣለው እግድ መሰረት ተገቢውን ህክምና ባለማግኘቱ ማክሰኞ ራሱን መቆጣጠር የማይችልበት ደረጃ ላይ መድረሱ ታውቋል፡፡ በአቃቤ ህግ ይግባኝ ምክንያት ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለው የፍርድ ቤት እግድ እንዲነሳ አቶ ሀብታሙ በጠበቃቸው አቶ አምሃ መኮንን አማካኝነት ፍርድ ቤቱን ቢጠይቅም እስካሁን ምላሽ እንዳልተገኘ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ኢትዮጵያውያን በማኀበራዊ ሚዲያ እና አምንስቲ ኢንተርናሽናል አቶ ሀብታሙ ከሀገር እንዳይወጣ የተጣለበት እግድ እንዲነሳ እና ተጊቢውን የህክምና ዕርዳታ እንዲያገኝ ሊፈቀድ ይገባል ሲሉ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን፤ የማኀበራዊ ሚዲያ ዘመቻው እስከነገ እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡ ይህ እስከ ተዘገበበት ድረስ አቶ ሀብታሙ ራሱን ስቶ በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ በካዲስኮ ሆስፒታል ተኝቶ እስኪነቃ በሚል ከሚሰጠው ማስታገሻ በስተቀር ምንም ዓይነት መደበኛ የህክምና ዕርዳታ እንዳልጀመረ ታውቋል፡፡
በአዲስ አበባ በመንግሥት እና በህዝብ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የአዲስ አበባ ፖሊሶች ተገደሉ!
(አዲስ ሚዲያ) በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፈለ ከተማ ወረዳ 1 በተለምዶ ፉሪ ሐና ማርያም ቀርሳ ኮንቱማ እና ማንጎ ሰፈር በሚባል ስፍራ ትናንት ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. እና ዛሬ ሰኔ 22 ቀን 2008 ዓ.ም. በነዋሪውና በከተማ አስተዳደሩ መካከል በተፈጠረ ግጭት ከ4 ያላነሱ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ 1 አፍራሽ ግብረ ኃይል እና 1 የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ እንደ አካባቢው የዓይን እማኞች ገለፃ ከሆነ፤ ከነዋሪዎችም በርካታ ሰዎች በፖሊስ በተተኮሰ ጥይት መቁሰላቸውን እና የህክምና እርዳታም እንዳያገኙ መደረጋቸውን ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በተፈጠረው ግጭት የሟቾች ቁጥር ከተጠቀሰው በላይ ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡ መንግሥት በበኩሉ ዛሬ በተፈጠረው ግጭት ሁለት ፖሊስ እና የአካባቢው የወረዳ ባለስልጣን መገደላቸውን አስታውቋል፡፡

የግጭቱ ዋነኛ ምክንያት መንግሥት በአካባቢው ያሉ 30 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ከመንግሥት እውቅና ውጭ በህገ ወጥ መንገድ ቤት ሰርተው እየኖሩ ያሉ ሰዎች ቤታቸውን አፍርሰው ከአካባቢው መነሳት አለባቸው የሚል ውሳኔን ተከትሎ፤መንግሥትም ቤቶቹን ለማፍረስ የቤት አፍራሽ ግብረ ኃይል፣ የአዲስ አበባ ፖሊሶች፣ አራት ሲቪለ የለበሱ ማንነታቸው ያልታወቁ ሰዎች፣ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ የመብራት ኃይል ሰራተኞች እና ሁለት የአካባው የወረዳ አመራር ወደስፍራው ልኮ እንደነበር ታውቋል፡፡
የቤታቸውን መፍረስ በመቃወም የአካባቢው ሴቶችና ህፃናት ወደ አዲስ አበባ ሴቶችና ህፃናት ቢሮ ቅሬታ ለማቅረብ ቢሄዱም ሰሚ ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ሐና ማርያም አካባቢ የሚገኘው የወረዳው አስተዳደር የአካባቢውን ነዋሪ በቤት መፍረሱ ጉዳይ ኑና እንነጋገር በሚል ከጠራ በኋላ፤ በጎን ወደነዋሪዎቹ አካባቢ አፍራሽ ግብረ ኃይል መላኩ ነዋሪውን ይበልጥ እንዳበሳጨውና ለህይወት መጥፋት ዋናው መንስኤ እንደሆነ የዓይን እማኞች ተናግረዋል፡፡
ቤቶቻቸው በኃይል እንዲፈርስ ከተደሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ምንም ዓይነት ካሳ እና ምትክ ቤትም ሆነ ቦታ በመንግሥት እንዳልተሰጣቸው የጠገለፀ ሲሆን፤ እንዲፈርሱ በተወሰነው የመንደሩ ነዋሪዎች በርካታ አዛውንት፣ ህፃናት፣ ነፍሰጡር እናቶች እንደሚገኙ የደረሰን መረጃ አመልክቷል፡፡ ወቅቱ ከፍተኛ ዝናብ የሚዘንብበት ክረምት በመሆኑ፤ ነዋሪዎች ቤቶቻቸው ያለምንም ምትክ ቤትና ካሳ ቤቶቻቸው የሚፈርሱ ከሆነ ህፃናትና ነፍሰጡር እናቶችን ጨምሮ ሁሉም ለጎዳና ህይወት እንደሚዳረጉ እየተናገሩ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ከመንግሥት በኩል ስለምትክ ቤትና ቦታም ሆነ ካሳን በሚመለከት እስካሁን የተባለ ነገር የለም፡፡ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ በአካባቢው አሁንም ውጥረት እንደነገሰ ነው፡፡
ባለፈው ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በተመሳሳይ መልኩ በቦሌ ልፍለከ ከተማ ወረዳ 12 ልዩ ስሙ ወረገኑ በሚባል ስፍራ 20 ሺህ ያህል ነዋሪዎች ያሉበትን ቤት፤ መንግሥት ህገወጥ ነው በሚል ለማፍረስ በመንቀሳቀሱ በተፈጠረ አለመግባባት የሰው ህይወት መጥፋት የአካል ጉዳት ማስከተሉ አይዘነጋም፡፡