Category Archives: Politics

የመድረክ እጩ ተወዳዳሪ በትግራይ ተምቤን በፖሊስ ተደበደበ

አቶ ዜናዊ ኣስመላሽ

አቶ ዜናዊ ኣስመላሽ

የወርቃ ኣምባ ምርጫ ክልል መድረክን ወክሎ ለክልል ምክርቤት በእጩነት የቀረበው ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ በፖሊስ ተደብድቦ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶታል።
ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ ትናንት ቅዳሜ የካቲት 7 ቀን 2007ዓ.ም ከቀኑ 11 ሰዓት የወርቃ ኣምባ ከተማ ኣስተዳዳሪ ተስፋይ ሃይሉ “..ይዛቹ ኣምጡት ብሎናል..” በማለት ሃፍተ ኪሮስ የተባለ ፖሊስና ገብረተኽለ ወለቸኣልና ገብረጀወርግስ ሙሉ የተባሉ ሚሊሻዎች ወደ ፖሊስ ኮሚኒቲ እየደበደቡ ወስደውታል። በወቅቱ በርካታ ህዝብ እየተመለከተ የነበረ ሲሆን ድብደባው በህዝቡ እርዳታ እንዲቆምና ወደ ዋና ፖሊስ ጣብያ ወስደው እንዲያስሩትና ድብደባው እንዲያቋርጡት ተቃውሞው በማሰማቱ ድብደባው ተቋርጧል።

ተደባዳቢው ፖሊስና ሚልሻዎቹ ለምን እንደደበደቡት ሲጠየቁ “..ወደ ፖሊስ ጣብያ ስንወስደው ቀስ እያለ ሲሄድ ፈጠን በል ስንለው ቀስ እያለ በመሄዱ ነው..” ሲሉ መልሰዋል።
ፖሊስ ኣዛዡ ያለ ምንም ምክንያት እንደተደበደበ ካረጋገጠ በሗላ “..ፖሊሱ ሰካራም መሆኑና ቅር ሊለው እንደማይገባው..” ነግሮ ማታ ሰዎስት ሰዓት ከእስር ቤቱ ኣስፈትቶታል።
ወጣት ዜናዊ ኣስመላሽ ከእስር ከተለቀቀ በሗላ በጤና ኬላ የህግምና እርዳታ ተደርጎለታል።

ማታ 5 ሰዓት ኣከባቢ ፖሊስ ሃፍተ ኪሮስ ከ3 ሚልሻዎች በመሆን ወዳረፈበት ቤት በመሄድ ለባለ ቤቱ ማስፈራራት ኣድርሰዋል።
የህወሓት መንግስት በሑመራና ሽረ የሚገኙ ኣባሎቻችንም ተመሳሳይ ድብደባ ኣድርሰዋል ሲል በመቀሌ የመድረክ አመራር አባል ገልፀዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ጽህፈት ቤቱን እንዲለቅ ክስ ቀረበበት

• በወር 40 ሺህ ብር ኪራይና 250,000 ብር ለ‹‹ኪሳራ›› እንዲከፍል ተጠይቋል

Semayawi-Party

ሰማያዊ ፓርቲ የካ ክ/ከተማ በቀድሞው መጠሪያው ቀበሌ 15 እንዲሁም በአዲሱ መጠሪያው ወረዳ 6 የቤት ቁጥር 460 የሆነውን ጽ/ቤቱን 25000 ሺህ ብር ቅጣት ከፍሎ እንዲለቅ በአከራዮቹ በኩል ክስ ቀረበበት፡፡ በከሳሽ እነ አቶ ሚስጥረ ሽበሽ የተመሰረተው ክስ ‹‹ቤቱን ለቀው ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው …በወር ብር 40,000 (አርባ ሺህ ብር) ሒሳብ ከጥር 16 ቀን 2007 ጀምሮ ቤቱን ለቀው እስከሚያስረክቡ ድረስ ባልተነጣጠለ ኃላፊነት እንዲከፍሉን›› ያሉ ሲሆን ‹‹ከሳሽ ቤቱን ለማደስ ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር በገባነው ውል መሰረት የደረሰብንን 250 ሺህ ብር ኪሳራ እንዲተኩልን›› ሲሉ ከሰዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሚፈልግባቸው ጊዜያት የቀበሌ ካድሬዎች አከራዮቹና ደላሎቹ ለፓርቲው እንዳያከራዩ ሲያስጠነቅቁ የቆዩ ሲሆን በተለይ በጥር ወር 2007 ዓ.ም ይህ ጽ/ቤት እንዳይከራይ ግፊት የማድረጉ ተግባር ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

የኦሕዴህ አባላት በሰማያዊ ምልክት ሊወዳደሩ ነው

  • “ለአንድ አላማ እንታገላለን” አቶ ግርማ በቀለ
  • “መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል” ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

ከግራ ወደ ቀኝ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ከ(ሰማያዊ) እና አቶ ግርማ በቀለ ከ(ኦህዴህ)

የኦሞ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት (ኦሕዲኅ) አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ምልክት ለመወዳደር መወሰናቸውን የኦሕዲኅ ሊቀመንበር አቶ ግርማ በቀለ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጹ፡፡ ‹‹ጥቅምት 26/2006 ዓ.ም ፓርቲው ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ አባላቱና አመራሩ ከአገር አቀፍ ፓርቲዎች ጋር በውህደት መስራት እንዳለባቸውና በኦሕዲኅ ስም የሚደረገው የመጨረሻ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲሆን ወስነው ነበር›› ያሉት ሊቀመንበሩ የፓርቲው እጩዎች በሰማያዊ ፓርቲ ስምና ምልክት መመዝገባቸው አባላቱና አመራሩ ‹‹አገራዊ ፓርቲ ጋር በውህደት አሊያም በሌላ መንገድ አብረን መስራት አለብን፡፡›› በሚል በጠቅላላ ጉባኤው ያስተላለፉት ውሳኔ አካል ነው ብለዋል፡፡

አቶ ግርማ ፓርቲያቸው ከሰማያዊ ጋር ሆኖ ለመታገል የተነሳበትን ምክንያትም ‹‹አሉ ከሚባሉት 70 ያህል ፓርቲዎች አብዛኛዎቹ የክልል ፓርቲዎች ናቸው፡፡ የክልል ፓርቲዎች በአገራችን ፖለቲካ ፋይዳ ያለው ለውጥ እያመጡ አይደለም፡፡ የክልል ፓርቲዎች ሲጠናከሩም ቢሆን ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው እንደሚያመዝን ተረድተናል፡፡ በተቃራኒው አገር አቀፍ ፓርቲዎች ሲጠናከሩ የተሻለ ለውጥ ማምጣት ይችላሉ›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ አቶ ግርማ አክለውም ‹‹እስካሁን የክልልና አገራዊ ፓርቲ ተባብለን ተበታትነን ቆይተናል፡፡ አሁን ግን የተሻለ ለውጥ ለማምጣት አንድ አይነት ጥያቄ አንስተን፣ በአንድ አላማ ለመታገል ወስነናል፡፡ አንድነት ኃይል በመሆኑ በኢትዮጵያ ፖለቲካ የተሻለ ለውጥ እንደምናመጣ የሚል ትልቅ ተስፋ አለን›› ብለዋል፡፡

ፓርቲው ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ስምምነት በመፈረሙ አባላቱ በሰማያዊ ፓርቲ ስር ሆነው እንዲወዳደሩ ለምርጫ ቦርድ ባስገባው ደብዳቤም ‹‹የዚህ ስምምነት አላማ ፈራሚዎች ለ2007 ዓ.ም አጠቀላይ አገራዊ ምርጫ አባላትን በጋራ በአንድ የመወዳደሪያ ምልክት ማቅረብ፣ ማለትም የአንዱ ፓርቲ አባልና አመራር በሌላው ፓርቲ ሥምና ምልክት የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ ስምምነት ሲደረስም ተግባራዊ ማድረግ ነው›› ብለዋል፡፡

በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የቀድሞ የአንድነት አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ መምጣታቸውን አስታውሰው አሁንም የኦሕዲኅ አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ስር ለመወዳደር በፓርቲው ጥላ ስር መሰባሰባቸው ሰላማዊ ትግሉን እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል፡፡ ‹‹በአንድነት መቆማችንና መሰባሰባችን ትግሉን ያጠናክረዋል፡፡ ኢህአዴግ የአንድነት አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ በመምጣታቸው፣ ሰማያዊም እጁን ዘርግቶ በመቀበሉ ከፍተኛ ፍርሃት ተፈጥሮበታል፡፡›› ብለዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል አክለውም ‹‹አሁንም ሌሎች ፓርቲዎች መቀላቀላቸው ለኢህአዴግ ትልቅ ስጋት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በቴሎቪዥንና በራዲዮ እጩ ያቀረቡ ፓርቲዎችን ሲያስተዋውቅ የሰማያዊን ስም ሳይጠቅስ ቀርቷል፡፡ በተቃራኒው በሬዲዮና በቴሊቪዥን ሰማያዊ ተቋማትን አይቀበልም እያለ በሀሰት እየወነጀለ ያለው የተቃውሞ ጎራው በአንድነት በመቆም እየተጠናከረ በመምጣቱ ነው፡፡›› ሲሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በሰማያዊ ስር መሰባሰባቸው ያለውን ፋይዳ መግለፃቸውን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡

የመሐል ዳኛው ሸለመ በቀለ ራሳቸውን ከተሰየሙበት ችሎት አገለሉ፤ ፤የጋዜጠኞቹ እና ብሎገሮቹ ጉዳይ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀርቧል

z9

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ለተከታታይ ሶስት ቀናት ፍርድ ቤት ሲመላለሱ የነበሩት 9 ተጠርጣሪዎች ዛሬ ለ19ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንደትላንትናው ሁሉ ዘግይቶ ተጀመረው ቸሎት የመሃል ዳኛው አንዲነሱ የቀረበውን አቤቱታ ምርምሮ ብይን ለመስጠት ነበር ፡፡ በዚህም መሰረት ያለመሃል ዳኛ የመጡት ሁለት የግራ እና የቀኝ ዳኞች ተሰይመው አቤቱታውን ካነበቡ በኋላ ማለትም
1.ዳኛው ለአቃቤ ህግ ተደጋጋሚ የማሻሻል እድል በመስጠት አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብታችንን ነፍገውናል
2. ፍርድ ቤቱ ራሱ የሰጠውን ትእዛዝ ራሱ ሽሮ ያለምንም የፍሬ ሃሳብ ለውጥ ያለተሻሻለ ክስ ተቀብሏል
3. ሃሳባችንን ስንገልጽ ክልከላዎች ይደረጉብናል በመሆኑም ለዚህ የፍትህ መጓደል መሃል ዳኛው ሚና ዋሳኝ ነው ብለን ስለምናምን አንዲቀየሩልን እንጠይቃለን የሚል ሲሆን ዳኞቹ አቤቱታው አግባብነት የሌለው ነው ውሳኜው በመሃል ዳኞች ብቻ ሳይሆነ በጋራ የሚወሰን ስለሆነም ጭምር አቤቱታውን ውድቅ አድርገነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም እንዲህ አይነት አቤቱታ ውድቅ ሲሆን ለእያንዳንዳቸው ተከሳሾች 500 ብር የሚያስቀጣ ቢሆንም በስሜታውነት ነው ያቀረቡት በማለት ፍርድ ቤቱ አልፎታል ብለዋል ፡፡

በመቀጠል መሃል ዳኛውን ይዘው በመምጣት ችሎቱን አሟልተው አንደሚመለሱ ገልጸው መሃል ዳኛውን ይዘው መጥተው ደግመው ተሰይመዋል፡፡ መሃል ዳኛ አቶ ሸለመ በቀለ እነደተሰየሙ የምናገረው ነገር አለኝ በማለት ” ምንም አንኳን ሌሎቹ ዳኞች በዳኝነት አንድቀጥል ቢፈቅዱልኝም እኔ ግን በዚህ ክስ መቀጠል አልፈልግም ከዚህ በኋላ የምሰጠውም ዳኝነትም ቢሆን አመኔታ ስለማያገኝ አንድቀየር ማመልከቻ አስገብቻለሁ በማለት ራሳቸውን ከችሎቱ እንዲያገሉ መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህንን ተከትሎ አዲስ ዳኛ ተተክቶ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል አንደሚቀበል እና ሌላ ቀጠሮ እነደሚሰጥ ተገልጿል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው ይህ ጉዳይ ተጠናቆ መቅረብ ሲገባው እነደገና ሌላ ቀጠሮ መሰጠቱ አግባብ ስላልሆነ አጭር ቀጠሮ ይሰጥልን በማለታቸው የእምነት ክህደት ቃል ለመስጠት ለየካቲት 11 ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ጦማሪ አቤል ዋበላ ላይ እየደረሰ ያለ ማሰቃየት

ጦማሪ አቤክ ዋበላ በበኩሉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ለማቅረብ አንደሚፈልግ ተናግሮ ሲፈቀድለት ትላንትና ከፍርድ ቤት መልስ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ እንዳደረና ሲሰደብና ሲያዋርዱት አንደነበር ተናግሯል፡፡ ትላንትና ከፍርድ ቤት ወደ ማረሚያ ቤት በሚመለሱበት ወቅት ጠባቂዎቹ በካቴና ሳያስሩት አንደረሱት እና በራሳቸው ጥፋት የተነሳ ለምን አልታሰርክም ሲሉኝ ራሳችሁ ስላላሰራችሁኝ ብዬ በመመለሴ እናሳይሃለን በሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ወደ ቅሊንጦ መመለሱን አና እዚያ ከደረሰ ጀምሮ በውሻ ሰንሰለት ታስሮ ማደሩን ማእከላዊ በደረሰበት ድብደባ የተነሳ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያ ለማድረግ ተገዶ የነበረ በመሆኑ የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያውንም አንደተቀማ ገልጾ ከዚህ ስወጣ ምን አንደሚጠብቀኝም አላውቅም ህይወቴ አደጋ ላይ ነው ሲል በከፍተኛ ምሬት እንባ እየተናነቀው ተናግሯል ፡፡ አቤት የደረሰበትን ሰቆቃ ሲናገር ችሎቱን ሲታደሙ የነበሩት ወላጅ አባቱ እህቱና ሌሎች ጓደኞች ሲያለቅሱ ታይተዋል፡፡

በቦታው የነበሩት የማረሚያ ቤቱ ተጠሪ ምክትል ሳጅን ዘውዱ በፍርድ ቤቱ ተጠርተው የተጠየቁ ሲሆን የማውቀው ነገር የለኝም በማለት መልሰዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ የአቤልን አቤቱታ በጽሁፍ አንዲያስገባ የተናገረ ሲሆነ ማረሚያ ቤቱ በሚቀጥለው ቀጠሮ ምላሹን ይዞ እነዲመጣ በማዘዝ ችሎቱ ተጠናቋል፡፡

UN

በተያያ ዜና  በእስር ላይ በሚገኙት የዞን 9 ብሎገሮችና  ጋዜጠኞች  የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ጉዳይ ለተባበሩት መንግሰታት ድርጅት አለአግባብ እስር የተፈጸመባቸው ዜጎችን ጉዳይ lሚያይ ቡደን ቀርቧል ፡፡ በቡድኑ አሰራር መሰረት የኢትዬጲያ መንግሰት የቀረበበትን አቤቱታ አስመልክቶ መልስ ለመስጠት ጊዜ ይሰጠዋል፡፡ አቤቱታው

የታሰሩትን ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ያጋጠማቸውን የመብት ጥሰት ዝርዝር
2. የመታሰራቸው ምክንያት አግባብ አለመሆን የክሱን አለም አቀፍ መብቶችንም ሆነ የወንጀል ህግ መሰረቶች የጣሰ እና ሃሳባቸውን በመግለጻቸው ብቻ መሆኑን የሚያስረዳ ሲሆን መንግሰት ላይ የቀረበውን ክስ ያዘጋጁት Ethiopian Human Rights Project እና Freedom Now በተባሉ ድርጅቶች ናቸው፡፡

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ደብዳቤ

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው

ቀን 02/06/2007 ዓ.ም
ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን

አዲስ አበባ

ጉዳዩ፡- የልጄ ተመስገን ደሳለኝን ጉብኝት ይመለከታል

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከአብራኬ የወጣ ሁለተኛ ልጄ ነው፡፡ ገና ከህፃንነቱ ጀምሮ ለሰው አሣቢ፣ ሀገር ወዳድና ታታሪ ስለመሆኑ ከእኔ በላይ የሚያውቁት ይመሰክራሉ፡፡ ልጄ ተመስገን ለወገኔ አሰብኩ ባለ በእስር ቤት ያለጎብኚ እየተሰቃየብኝ ይገኛል፡፡ መቼም፣ የእናት ሆድ አያስችልምና እባካችሁ ልጄን ታደጉት፡፡ እባካችሁ ቢያንስ ካለበት እየሄድኩ የልጄን አይን እንዳይ እንዲፈቀድልኝ ተባበሩኝ፡፡ የልጄን ድምጽ ከሠማሁ ይኸዉ አንድ ወር ሞላኝ፡፡ ታናሽ ወንድሙ ታሪኩ ደሳለኝ ለወንድሙ ብሎ የቋጠረዉን ምሣ ይዞ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ቢሄድም በማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች ተደብድቦ የያዘውን ምግብ እንኳ ሣያደርስ ሜዳ ላይ ተደፍቶ ተመልሷል፡፡ መቼም እናንተም ልጆች ይኖራችኋል፤ ደግሞም የልጅን ነገር ታውቁታላችሁ፡፡ እኔ አሁን በእርጅና ዕድሜዬ ላይ እገኛለሁ፡፡ ከአሁን በኋላ ብቆይም ለትንሽ ጊዜያት ነው፡፡ በዚህች ጊዜ ውስጥ ልጄን እየተመላለስኩ እየጠየኩ፣ ድምፁን እያሰማሁ፣ አይዞህ እያልኩ ብኖር ለእኔ መታደል ነበር፡፡ እባካችሁ እርዱኝ የልጄ ድምጽ ናፈቀኝ፡፡ እሱን መጎብኘት የተከለከለበት ምክንያት ምን እንደሆነ እንኳን እስካሁን አላወቅሁም፡፡ ከወንድሙ ድብደባ በኋላም ጥር 10 ወደ ጠዋት አካባቢ የሄዱት ጓደኞቹ እና ወንድሞቹ ሳያዩት ተመልሰዋል፡፡

ተምዬ ስታመም የሚያስታምመኝ፣ “አይዞሽ እማዬ” የሚለኝ ረዳቴ ነው፡፡ ሌላ ዘመድ የለኝም፡፡ የምተዳደረውም ልጆቼ ለፍተውና ደክመው በሚያመጧት ትንሽ ብር ነው፡፡ ዛሬ ግን ይኸዉ ልጆቼም ወንድማቸውን ለማየት እየተንከራተቱ ነው፡፡

በእናታችሁ ይዣችኋለሁ፤ ከቻላችሁ ልጄ እንዲፈታልኝ እና እኔም ያለችኝን ቀሪ የእድሜ ዘመን አይን አይኑን እያየሁ እንድኖር እንድታደርጉልኝ፤ ይህን ማድረግ ከአቅም በላይ ከሆነ ደግሞ ካለበት ድረስ እየተመላለስኩ እኔና ሌሎች ልጆቼ እንዲሁም ወገኖቹ እንዲጠይቁት ቢደረግልኝ ስል በአክብሮት እጠይቃችኋለሁ፡፡ ልጄን አውቀዋለሁ፡፡ አንድ ነገር ሲገጥመዉ ሆድ ይብሰዋል፡፡ ቢያንስ እንኳን ቤተሰቦቹን ሲያይ ስለሚፅናና ይኸዉ እንዲፈቀድልኝ እማፀናለሁ፡፡ እኔ ምንም አቅም የሌለኝ አሮጊት ነኝ፡፡ ሁሉንም ለናንተ ሠጥቻችኋለሁ፡፡ ከእግዚአብሄር ጋር እንደምታስተካክሉልኝ እና እንደገና የልጄን ፊት እንዳይ እንደምታደርጉኝ ሙሉ ተስፋ አለኝ፡፡

እንግዲህ የየካዉ ቅዱስ ሚካኤል ይከተላችሁ፡፡ መቼም የእናትን ሆድ ታውቁታላችሁ፤ የልጅ ነገር አያስችልም፡፡ ሆድም ቶሎ ይሸበራል፡፡ ስለዚህ እባካችሁ እኔንም ልጆቼንም እርዱን እንላለን፡፡

ግልባጭ
_ ለጠ/ሚኒስተር ፅ/ቤት
_ የህግና፣ ፍትህና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ
_ ለአፈ-ጉባኤ ፅ/ቤት
_ የሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ)
_ ለእምባ ጠባቂ
_ ለአሜሪካ ኢምባሲ
_ ለእንግሊዝ ኢምባሲ

ከሰላምታ ጋር
ወ/ሮ ፋናዬ እርዳቸው