አንድነት ፓርቲ የጠራው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ሲጠናቀቅ፤በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል
-“የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!”- አንድነት
-በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞችም ተከታታይ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎች እንዲቀጥሉ ተወስኗል
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዛሬ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ አራት የክልል ከተሞች የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ ተጠናቀቀ፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የነበረው የተቃውሞ ሰልፍ መነሻውን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ጽህፈት ቤት በማድረግ መዳረሻውን ጥቁር አንበሳ አካባቢ በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሰልፍ በፅህፈት ቤቱ አካባቢ በተፈፀመ የፖሊስ ድብደባና እገታ ሊቋረጥ ችሏል፡፡
የተቃውሞ ሰልፉ ዋነኛ ዓላማም ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ አንድነት ወደ ምርጫው መግባቱን በመወሰን በመላ ሀገሪቱ ከ450 በላይ ዕጩዎቹን ማቅረቡን ይፋ ማድረጉን ተክትሎ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ፓርቲው ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በሚል ፓርቲውን ከምርጫ ውድድር ለማስወጣት የሚደረገውን ተግባር ለመቃወም መሆኑን ቀደም ሲል ይፋ ማድረጉ ይታወቃል፡፡ ከተጠቀሰው ዓላመ በተጨማሪ በዜጎች ላይ የሚደርስ ህገወጥ እና የግፍ እስር እንዲቆም፣ የታሰሩ የህሊና እስረኞች እንዲፈጡ፣ ነፃና ገለልተኛ ምርጫ ቦርድ እንዲኖር፣…የሚሉ ጥያቄዎች ይገኙበታል፡፡
መረጃዎች ከስፍራው እንደጠቆሙት ከሆነ፤ የተቃውሞ ሰልፉ ቀበና ከሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት የተነሳው ከ 150 በላይ የሚሆን ሰልፈኛ ከጽህፈት ቤቱ 100 ሜትር ርቀት ላይ ከሚጠብቁ ከ500 በላይ ሰልፈኞች ጋር ከመቀላቀላቀላቸው አስቀድሞ ፖሊሶች ቆርጠው በመግባት ከባድ ድብደባ አድርሰዋል፡፡ አራት ኪሎ፣ በፒያሳና የሰልፉ ማጠናቀቂያ በሆነው ኢቲዮ -ኩባ አደባባይ ይጠባበቅ የነበረው ሰልፈኛ ሊበተን መቻሉንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡
በተፈፀመው የፖሊስ ድብደባም ከ26 በላይ የፓርቲው አባላትና አመራሮች ጉዳት የደረሰባቸው ሲሆን፤ ከሰልፉ ጋር ምንም ንክኪ ያልነበራቸውና ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን የነበሩ የ70 ዓመት አዛውንትም ከፍተና ጉዳት ደርሶባቸው በአቅራቢያው በሚገኝ የጤና ተቋም የህክምና ዕርዳታ ሲደረግላቸው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት በክልል ከተደረጉት የተቃውሞ ሰልፎች መካከል ፓርቲው በደብረማርቆስ፣ በሸዋሮቢት እና በጋሞጎፋ ከምባ የተሳካ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መደረጉ ተጠቁሟል፡፡
በአዲስ አበባው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጉዳት ከደረሰባቸው የአንድነት አባላት መካከል የሚሊዮኖች ድምፅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ስለሺ ሐጎስና የፓርቲው ኦዲትና ኢንስፔክሽን ኃላፊ ዳግማዊ ተሰማ ከፍተኛ ጉዳት ስለደረሰባቸው ራሳቸውን ስተው እንደነበርና ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የህክምና ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደነበር የዓይን እማኞች ከስፍራው አስታውቀዋል፡፡ በተመሳሳይም ……የተባሉ ነፍሰጡር በፖሊስ ድብደባ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተጠቆመ ሲሆን፤በፖሊስ ድብደባ ከተፈፀመባቸውና ጉዳት ከደረሰባቸው የፓርቲው ስራ አስፈፃሚና አባላት መካከል፡-
- አቶ አስራት አብርሃም (የህዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሃላፊ)
2. አቶ ዳንኤል ተፈራ (የውጭ ጉዳይ ሃላፊ)
3. አቶ ብሩ ብርመጅ (የፖለቲካ ጉዳይ ሃላፊ)
4. አቶ ፀጋየ አላምረው (ምክትል አፈ-ጉባኤ)
5. አቶ አሻግሬ መሸሻ (የሰሜን ቀጠና ሃላፊ)
6. አቶ ሰለሞን ስዩም (የኤዲቶሪያል ቦርድ ሰብሳቢ)
7. ወ/ት ልዕልና ጉግሳ (የም/ቤት አባል)
8. አቶ ዳግማዊ ተሰማ (የም/ቤት አባል)
9. ጋዜጠኛ ስለሺ ሀጎስ (የም/ቤት አባል)
10. አቶ ስንታየሁ ቸኮል (የአዲስ አበባ የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ)
11. አቶ አሸናፊ አሳምረው (የወረዳ አመራር)
12. አቶ ኢሳያስ ቱሉ (አባል)
13. ወ/ት መስከረም ያረጋል (አባል)
14. አቶ ሃይሉ ግዛው (የወረዳ ሰብሳቢ)
15. አቶ አዲሱ መኮንን (የወረዳ ሰብሳቢ)
16. አቶ ሲሳይ ካሴ (አባል)
17. አቶ ወጋየሁ አድማሴ (አባል)
18. አቶ ክብረት ሃይሉ (የም/ቤት አባል)
19. አቶ ስለሺ ደቻሳ (አባል)
20. አቶ ማሩ አካሉ (አባል)
21. አቶ ክፍሉ በዳኔ (አባል)
22. አቶ ፋሲካ አዱኛ (የወረዳ አመራር)
23. ወ/ሮ ገነት ሞገስ (የወረዳ አመራር)
24. ተስፋየ ብዙነህ (አባል)
25. ሙሉጌታ ተፈራ
26.ኤፍሬም ሰለሞን(የአዲስ አበባ ስራ አስፈፃሚ)
በተቃውሞ ሰልፉ ፖሊሶች ያደረሱትን ጉዳት በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩት የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች የአንድነት አመራሮችን እና ጉዳት ደርሶባቸው በየሆስፒታሉ የሚገኙ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎችን አነጋግረዋል፡፡ የፓርቲው አመራሮች ከአባላትና ከደጋፊዎች ጋር ውይይት ያደረጉ ሲሆን አንድነት በአዲስ አበባ ተከታታይ የተቃውሞ ሰልፎችን እንደሚያደርግ ይፋ ተደርጓል፡፡ ይህንንም በተመለከተ ፓርቲው መግለጫ ያወጣ ሲሆን፤ ሙሉ መግለጫውን ከዚህ በታች ይመልከቱ፡-
የፍትህና የነፃነት ጥያቄያችን ደም በማፍሰስ አይቀለበስም!!!
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
ፓርቲያችን አንድነት ገዥው ፓርቲ፣ ምርጫ ቦርድና የገዥው ፓርቲ ልሳን በመሆን እያገለገሉ ያሉ ሚዲያዎች በመተባበር ከምርጫ ለማስወጣትና ተለጣፊ አንድነት ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት በመቃወም የተቃውሞ ሰልፍ መጥራቱ የሚታወቅ ነው፡፡
የተቃውሞ ሰልፉን ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም እንደምናከናውን ለአዲስ አበባ መስተዳድር ብናሳውቅም መስተዳድሩ በ12 ሰዓት ውስጥ በፅሁፍ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ ሰልፉ እውቅና አለው፡፡ መስተዳድሩ ግን የተጣለበትን ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ወደ ጎን በመግፋት የተወሰኑና የማይታወቁ ግለሰቦች ፔቲሽን ተፈራርመው አምጥተዋል በማለት ብዥታ ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ፓርቲያችን ህጉን ጠብቆ ህጋዊ የሆነ ሰልፍ ለማካሄድ ቢሞክርም አሁንም ሃላፊነት በጎደለው ሁኔታ የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ጭካኔ በተመላበት ሁኔታ ከፍተኛ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በተደጋጋሚ እንዳየነው ፖሊስ ደንብ ማስከበር ሲገባው አድሎ ለፈፀመው አካል በመወገን ድብደባ መፈፀሙ ከወገንተኝነት ያልፀዳ መሆኑን እንድናረጋግጥ አድርጎናል፡፡
ጥያቄያችን አሁንም የፍትህ፣ የእኩልነትና ህግ እንዲጠበቅ የማድረግ ነው፡፡ ገዥው ፓርቲ የመንግስትነት ስልጣኑን በመጠቀም የስልጣን ዘመኑን ለማስረዘም እየከወነ ያለውን ሴራ ማስቆም ነው፡፡ ጥያቄያችን የነፃነትና ያልተሸራረፈ ዴሞክራሲ ይረጋገጥ የሚል ነው፡፡ ጥቄያችን ምርጫ ቦርድ የገዥው ፓርቲ አጋር መሆኑ ቀርቶ ገለልተኛ ሚናውን ይወጣ የሚል ነው፡፡ እነዚህ ጥያቄዎቻችን ደግሞ ደም በማሰስ፤ በድብደባም ሆነ በእስር ፈፅሞ አይቆሙም፡፡
በሚቀጥለው ሳምንትም በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የሰላማዊ ተቃውሞ ድምፃችንን ከፍ አድርገን እናሰማለን፡፡ ትግሉ ይቀጥላል፡፡
ድል የህዝብ ነው!!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.
አዲስ አበባ
የመኢአድ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ዘመነ ምህረት ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው ፓርቲው ገለፀ
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የፓርቲያቸው ምክትል ፕሬዝደንት እና የሰሜን ቀጠና ኃላፊ የሆኑት አቶ ዘመነ ምህረት እጅግ ዘግናኝ ድብደባ ደርሶባቸው ሲል ፓርቲው ጥር 15 ቀን 2007 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ አስታወቀ፡፡ አቶ ዘመነ የመኢአድን ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ወደ መኖሪያቸው ጎንደር ከተማ ከተመለሱ በኋላ ከፍተኛ የደህንነት ክትትልና ጫና ይደረግባቸው እንደነበር ለፓርቲያቸው አሳውቀው ነበር ያለው ፓርቲው ጥር 10 ቀን 2007 ዓ.ም ጎንደር ከሚገኘው መኖሪያው ቤታቸው ከባቤታቸውና ከህፃን ልጃቸው ፊት የፖሊስ ልብስ በለበሱ አካላት ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸው ወዳልታወቀ ቦታ መወሰዳቸውን ግልጾአል፡፡ በአሁኑ ወቅት የፓርቲው አባላት ባደረጉት ክትትል አቶ ዘመነ አዘዞ የሚገኘው የመከላከያ ካምፕ ውስጥ እንደሚኙ አረጋግጠናል ያለው መግለጫው የሰው ልጅ ላይ ይፈጸማል ተብሎ የማይገመት ከፍተኛ ስቃይና ሰቆቃ ደርሶባቸዋል ብሏል፡፡
ከአቶ ዘመነ በተጨማሪ ጠቅላላ ጉባኤውን ተሳትፈው የተመለሱት የፓርቲው የማህበራዊ ጉዳይ ኃላፊ አቶ እያሱ ሁሴን 3 አመት ተፈርዶባቸው እስር ቤት እንደሚገኙ፣ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ፣ መ/አ ጌታቸው መኮንን፣ አቶ ጥላሁን አድማሴ የተባሉትን ጨምሮ ሌሎችም የፓርቲው አመራሮች ለእስር መዳረጋቸውን ያወሳው መግለጫው በአመራርና አባላቶቻቸው ላይ የሚደረገው እስር መኢአድ ምርጫውን ተጠቅሞ በገዥው ፓርቲ ላይ ጫና ማሳደር ስለሚችል እንደሆነ ተገልጾአል፡፡
በሌላ በኩል በአባላቶቻቸው ላይ በሚደርሰው በደልና ጫና ባሻገር ምርጫ ቦርድ ፓርቲውን ከምርጫ 2007 እንዳይሳተፍ የኢህአዴግ ቀኝ እጅ ሆኖ በመስራት ላይ እንዳለ ያወሳው መግለጫው ፓርቲው በምርጫው እንዳይሳተፍ ከተደረገ ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብሏል፡፡ ምርጫ ቦርድና ኢህአዴግ በፓርቲው ላይ የሚፈጽመውን በደል ተከትሎ ፓርቲው በሚደርገው ትግልም ህዝቡ ከጎኑ እንዲቆም ጥሪ ማቅረቡን የነገረ-ኢትዮጵያ ዘገባ አመልክቷል፡፡
በኤርትራ የታሰሩ 6 ጋዜጠኞች ተፈቱ
የኤርትራ መንግስት ባለፈው የካቲት 2001 ዓ.ም. በርካታ ጋዜጠኞች በጅምላ ካሰረቻቸው መካከል በረከት ምስግና፣ ይርጋዓለም ፍስሃ፣ ባሲሎስ ዘሞ፣ ንጉሴ ክፍሉ፣ግርማይ አብርሃም እና ጴጥሮስ ተፈሪ ከ6 ዓመታት እስር በኋላ መፈታታቸውን ድንበርየለሹ የጋዜጠኞች ቡድን (Reporters without Border) ይፋ አድርጓል፡፡
ጋዜጠኞች በሬዲዮ ባና፣ በሬዲዮ ዛራ እና በሬዲዮ ድምጺ ሃፋሽ ይሰሩ የነበረ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ወቅት ከታሰሩት ጋዜጠኞች መካከል ባለፈው መጋቤት 2005 ዓ.ም. 7 ጋዜጠኞችን እንዲሁ የኤርትራ መንግስት በዋስ መፍታቱ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ አሁንም ጋዜጠኛ ዳዊት ይስሃቅ እና ስዩም ፀሐዬን ጨምሮ 16 ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙ ድንበር የለሹ የጋዜጠኞች ቡድን አስታውሷል፡፡
ሰሞኑን ከእስር ስለተፈቱት ጋዜጠኞች ያሉበት ሁኔታና የቴንነት ጉዳይን በተመለከተ እስካሁን ለማወቅ እንዳልተቻለና ይህንንም ለማወቅ ክትትል እንደሚያደርጉ የተቋሙ የአፍሪካ ጉዳይ ዳይሬክተር ተናግረዋል፡፡
በተለይ በአፍሪካ ጋዜጠኞችን በማሰር ከጎረቤቷ ኢትዮጵያ ጋር ኤርትራ ቀዳሚ ሀገር እንደሆነች እና ለጋዜተኞች ከማይመቹ የዓለማችን ሀገራት እጅግ አደገኛ በሚል ዝርዝር ውስጥ መግባቷ ይታወሳል፡፡ በዚህም ሀገሪቱ ከኢትዮጵያ ጋር ተመሳሳይ ባህሪ ያላት ሲሆን፤ በኢትዮጵያም ሆነ በኤርትራ መንግስት ስልጣን ላይ ያሉት አካላት በትጥቅ ትግል ወደ ስልጣን እንደመጡ አይዘነጋም፡፡
አንድነት ፓርቲ እሁድ “የነፃነት ቀን ቀርባለችና ወደ አደባባይ ውጡ” በሚል ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ጠርቷል
-የሰልፉን ቅስቀሳ ተከትሎ የፓርቲው ወጣት አመራሮች ታስረዋል
.አንድነት ፓርቲ የጠራው የነገው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ተጠናክሮ ቀጥሏል
አንድነት ፓርቲ ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በኢህአዴግና በምርጫ ቦርድ በኩል ፓርቲው ወደ ምርጫ ውድድር እንዳይገባ የሚደረገውን እንቅስቃሴና ድርጊት በመቃወም የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ በፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን ተከትሎ ዛሬ ጥር 16 ቀን 2007 ዓ.ም. የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም፣ ምክትል ኃላፊው አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ኃላፊው አቶ ሰለሞን ስዩም እና የፓርቲው የአዲስ አበባ ወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ቸኮል እና ሌሎች አመራሮች አቶ ያሬድ አለማየሁ፣ አቶ ሲሳይ ጌትነት፣ አቶ ማቲያስ ሐረጉ በፀጥታ ይሎች መታሰራቸውና ወዳልታወቀ ስፍራ የተወሰዱ ሲሆን፤ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት አቶ አስራት አብርሃም፣ አቶ ንዋይ ገበየሁ፣ አቶ ሰለሞን ስዩም እና አቶ ስንታየሁ ቸኮል መፈታታቸውን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
ፓርቲው ሰልፉን እንዲጠራ ያስገደደው ምርጫ ቦርድ ከሀገሪቱ የምርጫ አዋጅ ህግ አግባብ ውጭ በአንድ ወር ውስጥ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ በመወሰኑ ሲሆን፤ ቅሬታ ነበረን በሚል ጥያቄ ካቀረቡት ዋነኞቹ አቶ አየለ ስሜነህ እና አቶ ኢሳይያስ ቱሉ ምርጫ ቦርድ እና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲውን ለሁለት ለመክፈል በመሞከሩ፣እኛ ደግሞ አንድነት አንድ ነው እንዲከፈልም ስለማንፈልግ ተመልሰን ወደ ዋናው ፓርቲያችን ቢሮ ተመልሰናል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ከዚህ ቀደም አንድነት ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በጠራው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ እንዲታዘብ ጥሪ ሲደረግለት እነ አቶ አየለ ስሜነህ ሌላ ጠቅላላ ጉባኤ ለማድረግ ደብዳቤ ስላስገቡ ቦርዱ ሁለት ቦታ ለመታዘብ ወኪል መላክ እንደማይችል በጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ደብዳቤ መፃፉ ታውቋል፡፡
አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣ የነበርነው የአንድነት ፓርቲ አባላት ከ15 አንበልጥም፤ ነገር ግን የፓርቲው አባላት ያልሆኑ ከ60 በላይ ሰዎች በስብሰባችን ላይ ተገኝተዋል፣የሆቴል አዳራሽ ኪራይ ማን እንደከፈለ አናውቅም፣ ተከፍሎላችኋል እዛ ሆቴል ሂዱ እንባላለን፣ይሄ ሁሉ ስላላማረን እና ፓርቲያችን አንድነት አንድ ስለሆነ ወደ ፓርቲያችን ተመልሰናል ሲሉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ለፓርቲው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲታዘብ ለቀረበለት ጥሪ እነ አቶ አየለ ስሜነህም ጠርተውናል ሲል በፃፈው ደብዳቤ ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ በበኩላቸው እኛ ምንም ዓይነት ጠቅላላ ጉባኤ አልጠራንም፣በመካከላችን የነበረው ጥቂት አለመግባባት እንዲፈታ ስንል እንጂ ከፓርቲው ህልውናም ሆነ አሰራር ጋር ቅሬታም ሆነ ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ የሚል ጥያቄ አላቀረብንም ሲሉ አስታውቀዋል፡፡
በአሁን ወቅት ጥያቄ ነበረን ያሉት አቶ አየለ፣ ያለንን ጥያቄ በፓርቲያችን ውስጥ ሆነን እንፈተዋለን፣ ወደ ውጪ ይዘን መውጣታችን ትክክል እንዳልነበረና እኛ ባላሰብናውና ባልፈለግነው መንገድ ፓርቲው ላይ በእኛ ስም አደጋ ለመፍጠር እየተሰራ እንዳለ ስንገዘነብ ተመልሰናል፣ መጀመሪያም ቢሆን ፓርቲው አልተከፈለም፣ እኛም ጥያቄ አቀረብን እንጂ ከፓርቲው አልወጣንም ሲሉ አክለዋል፡፡ አቶ አየለ ስሜነህ ለጋዜጠኞች የሰጡትን መግለጫ ለራሱ ለምርጫ ቦርድ ግልባጭ ማድረጋቸውንም አስታውቀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ ጥያቄ አቅርበው የነበሩት አቶ አየለ ስሜነህ ወደ ፓርቲው መመለሳቸውን ቢያሳውቁም፤ ምርጫ ቦርድ ግን በነ አቶ አየለ ስሜነህ ስም ሌላ አካል እያደራጀ መሆኑን በመጥቀስ ፓርቲው ድርጊቱን ለማውገዝ የሰልፍ መጥራቱን ይፋ አድርጓል፡፡ ፓርቲው ድርጊቱን የኢትዮጵያ ህዝብም እንዲረዳውና እንዲያወግዘው ለነገ እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ኣ.ም. የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉን መጥራቱን ፓርቲው አስታውቋል፡፡ ከዚህ በኋላ ፓርቲው ህዝባዊ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ በመላ ሀገሪቱ ማካሄድና ነውጥ አልባ የነፃነት ትግሉን አጠናክሮ ከመቀጠል ውጭ ለ3ኛ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ እንደማይጠራ ማሳወቁ አይዘነጋም፡፡ ወደ ፓርቲያቸው ስለተመለሱት አቶ አየለ ስሜነህ እስካሁን ባይዘግብም ፓርቲው እንደተከፈለ አድርገው ከሬዲዮ ፋና እና ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን በተደጋጋሚ ከሚያቀርቡት በስተቀር ምርጫ ቦርድ እስካሁን የሰጠው ምላሽ የለም፡፡
የነገው የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ መነሻ አዲስ አበባ ቀበና መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ፊትለፊት ከሚገኘው የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት ሲሆን፤ የሰላማዊ ሰልፉ መነሻ ሰዓት ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት መሆኑንም ታውቋል፡፡
የሰልፉ መዳረሻ ቦታ አዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ጀርባ እና ዋናው ፖስታ ቤት ፊትለፊት በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ መሆኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ቀንና ሰዓት (እሁድ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም.) የተቃውሞ ሰልፉ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በደብረ ማርቆስ፣ በአርባምንጭ አካባቢ ከምባ ወረዳ፣በጂንካ እና በሸዋ ሮቢት እንደሚደረግ በፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በመወሰኑ በክልሎችም የሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ ቀጥሏል፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ቀኑ እንዲራዘም የመንግስት አካላትና ዲፕሎማቶች ጥረት ቢያደርጉም፤የአንድነት ፓርቲ ምክር ቤት ዛሬ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ መብታችንን ከእንግዲህ ለምነን አናገኝም፣ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉም በታቀደለት መሰረት ይቀጥል ሲል መወሰኑን ፓርቲው አስታውቋል፡፡
ፓርቲው ከላይ ከተጠቀሱት 5 ከተሞች በተጨማሪ በተከታታይ በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞችም የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ እንደሚቀጥል ይፋ አድርጓል፡፡
የእንግሊዝ የፓርላማ ልዑክ አባላት በአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ለመደራደር ወደ ኢትዮጵያ ሊገቡ ነው
አቶ አንዳርጋቸው ባለፈው ወር ከባለቤታቸው ጋር በስልክ ተነጋግረዋል
የእንግሊዝ የፓርላማ አባላትን የያዘ የልኡካን ቡድን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከእስር ማስፈታት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ለመደራደር በቀጣዩ ወር ወደ ኢትዮጵያ እንደሚመጣ የዘ ኢንዲፔንደንት ዘገባ አመልክቷል፡፡
ሁሉንም የእንግሊዝ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአባልነት የያዘው የፓርላማ አባላት የሰብዓዊ መብቶች ቡድን ምክትል ሊቀመንበር ጀርሚ ኮርባይን የሚመሩት የልኡካን ቡድኑ፣ ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ጋር በመምከር የሞት ፍርዱ ተፈጻሚ እንዳይሆንና ግለሰቡ ከእስር እንዲፈቱ ለማስቻል እንደሚሰሩ ዘገባው አመልክቷል፡፡አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እንግሊዛዊ ዜግነት ያላቸው እንደመሆኑ የእንግሊዝ መንግስት ጉዳዩን አጽንዖት ሰጥቶ መከታተልና ግለሰቡን ከሞት ማዳን ይጠበቅበታል ያሉት ኮርባይን፤ ቡድኑ አቶ አንዳርጋቸው ግልጽ ባልሆነና ተቀባይነት በሌለው የህግ አካሄድ ለእስር ተዳርገዋል ብሎ እንደሚያምን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ አቶ እንዳርጋቸው የአሸባሪ ቡድን አባል ቢሆኑም በእስር ላይ ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው ሲል በተደጋጋሚ መግለፁ ይታወሳል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ባለፈው ነሐሴና ታህሳስ ወር ላይ ከተደረጉት ሁለት የመንግስት ተወካዮች ጉብኝቶች ውጭ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ለመጎብኘት እንዳንችል አግዶናል ብለዋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት የአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳስበው ገልጸው፣ በግለሰቡ ላይ የተጣለው የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እንዳይሆን በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና ማድረጉን እንደቀጠለበትም አስረድተዋል፡፡በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የኢትዮጵያን መንግስት ለማፍረስ የሚሰራ አሸባሪ ቡድን አባል ናቸው፣ በእስር ላይ ሆነውም ተገቢው እንክብካቤ እየተደረገላቸው ነው፤ እስረኞችን ማሰቃየት ኢሰብአዊ ድርጊት እንደመሆኑ በዛሬዋ ኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ የሚደረግ አይደለም ሲሉ መናገራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አምነስቲ ኢንተርናሽናል በቅርቡ ይፋ ያደረገው ሪፖርት ግን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት ከቅርብ አመታት ወዲህ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች የሚፈጸምባቸው ስቃይ እያየለ መምጣቱን የሚያመላክት መሆኑን አክሎ ገልጿል፡፡
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፤ ባለፈው ወር እንግሊዝ አገር ወደምትገኘው ባለቤታቸው ስልክ ደውለው መገናኘታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በአብዛኛው ስለልጆቻቸው ጉዳይ እንዳወሩ፣ ደህንነታቸውን እንደገለጹላቸው፣ እንዲሁም ለልጆቼ የማይሆን ተስፋ መስጠት አልፈልግም ማለታቸውን ባለቤታቸው እንደተናገሩ አመልክቷል ሲል አዲስ አድማስ ዘግቧል፡፡ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ “ግንቦት 7” የተባለ የተቀናቃኝ የፖለቲካ ድርጅት ዋና ፀሐፊ መሆናቸውና በኢትዮጵያና በየመን የደህንነት ኃይሎች ከየመን ታግተው መታሰራቸው ይታወቃል፡፡












