የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ አድማ፤ ታሪክ ራሱን ሊደግም ይሆን?
ብስራት ወልደሚካኤል
የዛሬ 42 ዓመት በየካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም. በቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴ ዘመን በሊትር የ10 ሳንቲም የነዳጅ ጭማሪን (50 በመቶ ጭማሪን)ተከትሎ የታክሲ ባለንብረቶች እና ሾፌሮች የታሪፍ ማሻሻያ ጭማሪ ቢጠይቁ ተቀባይነት በማጣታቸው የታክሲ አድማ ተደርጎ ነበር፡፡ በተመሳሳይ ዕለት የኢትዮጵያ መምህራን ማኀበር በጠራው አድማ የሀገሪቱ መምህራን በሙሉ ስራ አቁመው ነበር፡፡ ይህም እየተቀጣጠለ ከአዲስ አበባ ወደ ሌሎች ከተሞች ሳይዳረስ በሚል የወቅቱ መንግሥት የነዳጅ ጭማሪውን መሰረዙን ይፋ አደረገ፡፡

ይሁን እንጂ ተቃውሞው እንደሰደድ እሳት ተቀጣጠለ፤ከዛም መፍትሄ ይሆናል በሚል የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ፀሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ኃብተወለድ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የካቲት 21 ቀን 1966 ዓ.ም. ከስልጣናቸው እንዲሰናበቱ ተደረ፡፡ ይሄም መፍትሄ አልሆነም፤ይልቅ የመምህራን ማኀበርና የታክሲ የተቃውሞ አድማ ወደ ወታደሩ ዞረ፤ከዛም ንጉሱንም ዘውዳዊ ስርዓቱን ላይመለስ እስከነ አካቴው አሰናበተው፡፡ ልብ በሉ ይህ ሁሉ ልክ የዛሬ 42 ዓመት የነበረ የአዲስ አበባ ታክሲ አድማ ምን እንዳስከተለ፡፡ ይሄ ሁሉ 4ኛ ወሩን ያስቆጠረውና እስካሁንም የቀጠለውን የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ በተጨማሪ መሆኑ ነው፡፡ አሁን ደግሞ በጎንደርም ተቃውሞዎች እያገረሹ መንገድ እስከመዝጋት እንደደረሱ እየተሰማ ነው፡፡
ዛሬ ከ42 ዓመት በኋላ በዘመነ ኢህአዴግ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የመንግሥትን አዲስ መመሪያ በመቃወም የተደረገው የታክሲ አድማ በጠዋቱ ጀምሯል፡፡ ይህ እስከተፃፈበት ድረስም የአዲስ አበባው የታክሲ አድማ እንደቀጠለ ነው፡፡ አድማውም ለ ሁለት ተከታታይ ቀናት እንደሚደረገ የታቀደ ቢሆንም፤ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ ግን አድማው ሊቀጥል እንደሚችል ነው፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ የአዲስ መመሪያ ዋና ሰለባዎች የታክሲ ሾፌሮች በመሆናቸው ነው፡፡


እስካሁን ባለው አድማም በከተማው የመንግሥት የመስሪያ ቤት የትራንስፖርት አገልግሎት አውቶቡስ፣ የግለሰቦች የጭነት ተሸከርካሪዎች (በግድ ተሳፋሪ እንዲጭኑ እየጠደረጉ) ከሚሰጡት አገልግሎት በስተቀር የተለመዱት የሚኒባስ ታክሲዎች አድማ መትተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ህዝብ ብዛትና ከተጠቃሚው ብዛት እንዲሁም ቀድሞም ከነበረው የትራንስፖርት እጥረት አንፃር የታክሲዎች አድማ የሚያስከትለው ተፅዕኖ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡መንግሥት በስሩ ባሉ መገናኛ ብዙኃን በጠዋት ዜና እወጃው የአዲሱን የአዲስ አበባ ትራንሰፖርት ደንብ መመሪያ ትግበራ ለ3 ወራት ማራዘሙን ቢገልፅም፤የታክሲዎች አድማ ግን ቀኑን ሙሉ ቀጥሎ ውሏል፡፡
ምንም እንኳ ሀገር አቀፍ ምርጫ ከተደረገ 100 ቀናት ቢያልፉትም፤ የዛ “ምርጫ” ኢህአዴግ 100% የህዝብ ድምፅ “በምርጫ” አሸንፊያለው የሚለው መዝሙር ሳያባራ በየአቅጣጫው ጠንከር ያለ ተቃውሞ መምጣቱ ምናልባትም አማራጭ ሐሳብ ያለመኖርና እንዲኖር ያለመፈለጉ ያመጣው መዘዝም ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በርግጥ የዛ ተዓምረኛው “ የ100% ምርጫ” ውጤት መዘዝ ገና ብዙ ክስተቶችን በመላው ሀገሪቱ ሊያስተናግድ እንደሚችልም ይጠበቃል፡፡
የዛሬው የአዲስ አበባ የታክሲ ተቃውሞ አድማ ወደ ሌሎች የግልና መንግሥታዊ ተቋማት አድማሱን አስፍቶ የዛሬ 42 ዓመቱን ታሪክ ይደግመው ይሆን?

በተለይ ከዓለም ገበያና ሀገሪቱ ነዳጅ ከገዛችበት 365 % (ነዳጁ ከተገዛበት ወደ 4 እጥፍ) ክፍያ የተጫነበት ተጠቃሚው ህዝብ ትክክለኛ መረጃ ቢኖረው ከታክሲ አድማው ይልቅ የተሳፋሪው አለመቅደሙ አስገራሚ ቢሆንም፤የዛሬው የታክሲዎች አድማ ሌላም ቁጣ ይቀሰቅስ ይሆን ወይስ እንደተለመደው በማስፈራሪያ አሊያም ደንብ ቁጥር 208/2003 ተከትሎ ወጥቷል የተባለው አዲሱ መመሪያ ተሰርዟል በሚል ወደስራቸው ይመለሱ ይሆን?
ሁሉንም ጊዜ ያሳየናል፡፡
ገራፊዬን አየኹት

አቤል ዋበላ
ቀልድ ያለፈበት ጨዋታ ሆኗል፡፡ አሁን ዘውጉ ተቀይሯል፡፡ ፍጥጥ ግጥጥ ያለ ዕውናዊ ድርሰትን መመልከት ይዘናል፡፡አይን አያየው የለም፡፡ አሁን ደግሞ ገራፊዬን አሳየኝ፡፡ በኮምፒዩተር የኤሌክትሪክ ገመድ ጀርባዬ እስኪቀደድ የገረፈኝን፣ በመጥረጊያ እንጨት ውስጥ እግሬን ያነደደኝን፣ እጄ በካቴና ታስሮ ወለል ላይ ያንከባለለኝን፣ ጨለማ ቤት ውስጥ አስገብቶ ከየት እንደመጣ በማላውቀው ጅራፍ አሳሬን ያበላኝን፣ እናቴን ከመቃብር ጠርቼ “አንቺ እናቴ ለምን ጥሩ ሁን ብለሽ አሳደግሽኝ? ብዙ ክፉ ሰዎች እንዳሉ ለምን አልመከርሽኝም?” ብዬ እንድወቅሳት ያደረገኝን፣ ወንድ፣ የወንዶች ቁና በካቴና የታሰረን ሰው በዕኩለ ሌሊት ጠርቶ አፉ ውስጥ ጨርቅ ወትፎ የሚደበድብ በአይኔ በብረቱ አየኹት፡፡
ዮናታን ተስፋዬ ለጊዜያዊ ቀነ ቀጠሮ አራዳ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ሰምቼ ነው ወደዚያ የሄድኩት፡፡ ይህችን የተለመደች ሰርከስ ሁሉም የፖለቲካ እስረኛ ይወዛወዛታል፡፡በማዕከላዊ ይጀመራል ከዚያ አራዳ ፍርድ ቤት ይቀጥላል፡፡ የማዕከላዊ ደብዳቢዎች በጨለማ የሚያሰቃዩትን እስረኛ በቀን ሰው መስለው (ወገኞች ናቸው አንዳንዴማ ዩኒፎርምም ያጠልቃሉ) ፍርድ ቤት ያቀርቡታል፡፡ ውሸት ውሸቱን ይቀባጥራሉ፡፡ “ግበረ አበሮቹን በኢንተርፖል እያሳደድን ነው፣ ክቡር ዳኛ በዋስ ከተለለቀቁ ልማታችንን ያደናቅፋሉ፡፡ ወህኒ ሰብረው እስረኛ ያስፈታሉ” የመሳሰሉትን በጠራራ ጸሐይ ይቀባጥራሉ፡፡ እየቀለድኩኝ አይደልም የምሬን ነው እንዲህ አይነት በሬ ወለደ ምክንያት በጆሮዬ ሰምቻለው፡፡ ዳኛውም አብሮ ይተውናል፡፡ የፈለጉትን ቀን ያህል ያራዝማል፡፡
ገራፊዬንም ያየሁት እኔንና ጓደኞቼን እንደነዳው እንዲሁ ተረኛውን ገፈት ቀማሽ ሲያመጣ ነው፡፡ ላንዳፍታ አይኖቻችን ተጋጩ፡፡ አስተውሎኝ ይሁን አይሁን አላውቅም በፍርድ ቤቱ ቢሮዎች መሐል ገብቶ ተሰወረ፡፡ እኔ ግን በእርግጠኝነት ለይቸዋለው፡፡ ውስጤ ዳግም ተቆጣ፡፡ እስር ቤት ብቻዬን ደጋግሜ ባሰብኩት ቁጥር እንደአዲስ የልቤ ቁስል ያመረቅዝ ነበር፡፡ ቂም ስቋጥር እና ስፈታ ከአመት በላይ ቆይቻለው፡፡ ቂም ይዣለው በውድም ሆነ በግድ ኢትዮጵያዊ በሆነ ሁሉ ላይ ቂም ይዣለው፡፡ እንዴት ሰው በሀገሩ ይህንን ጉድ ተሸክሞ ይኖራል? እንዴት እንደዚህ አይነት ተቋም በመዲናይቱ እምብርት ላይ አስቀምጦ ዝም ይላል? ይህን ባርቤሪዝም ጌጡ ካደረገ ማኀበረሰብ ጋር በቀላሉ የማይበርድ ግጭት ውስጥ ነኝ፡፡ ስለዚህ በመንገድ ስታገኙኝ ፊቴ ጥቁር ብሎ ብታገኙኝ “ምን ሆነህ ነው?” አትበሉኝ፡፡ ቂም ይዤ ነው፡፡ ተራ ማኩረፍ አድርጋችኹ አትውሰዱት ስር የሰደደ ከነፍስ የሚቀዳ ጸብ ነው፡፡
በግርፋት የተሰነጠቀውን ጀርባዬ በቅባት ላሹኝ ዕድሜ ለእነ ኤባ ቁስሉ እዛው ማዕከላዊ ነው የዳነው፡፡ የልቤ ስንጥቅ ግን አልዳነም ፡፡ ያ ዘላለም ክብረት “ምድር ብዙ ክፋት የሚፈጸምባት ቦታ ናት በእኛ ላይ የደረሰውም አዲስ ነገር አይደለም” እያለ ብዙ እንዳላዝን ቢመክረኝም ያቄመው ልቤን ሊያሸንፈው አልቻለም ነበር፡፡ የተገኘሁበት፣ ያሳደገኝ ማኀበረሰብ ላይ እንዳቄምኩኝ ከእስር ወጣኹኝ፡፡ ባለፉት አራት ወራት በአንጻራዊ ነጻነት ማሳለፌ ግን ትንሽ እንዳዘናጋኝ የገባኝ ግን በቀደም ገራፊዬን ያየኹት ቀን ነው፡፡ወይ ጊዜ ስንቱን ያስረሳል አልኩኝ፡፡ አሁን ከእስር መፈታት ብርቅ የሆነበት ጊዜ አልፏል፡፡ ቁስሌ ዳግም አመርቅዟል፡፡ ገራፊዬን እና አለቆቹን የያዘው ህንጻ ካልፈረሰ አልያም ሙዚየም ካልሆነ ዕርቅ የማይታሰብ ነው፡፡ ድሮ እስር ቤት ሳለኹኝ በእስረኛ ማጓጓዣ መኪና ወደ ፍርድ ቤት ስንመላለስ በመስኮት ስመለከተው የዕለት ጉርሱን ለማብሰል የሚራኮተው አዳሜ አሁንም ውስጡ ሁኜ ስመለከተው ከሆዱ በቀር የኔ ቁስል ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ ስለዚህ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ ብዬ ይቅር እላለው? ውስጤ የበለጠ ስለሻከረ እምቢኝ ብያለው፡፡ ይህ የአንዲት ነጠላ ነፍስ መብት ነው፡፡ በገዛ ነፍሴ ጥላቻን ማርገዝ መብቴ ነው፡፡ ከፈለጋችኹ ለዐቃቤ ሕግ ንገሩትና በፊት ‘የማኀበረሰቡን ጤና እና ደህንነት ለአደጋ በማጋለጥ’ እንደ ከሰሰኝ አሁን ደግም ‘በማኀበረሰቡ ላይ ስር የሰደደ ጥላቻና ቂም በመቋጠር’ ይክሰሰኝ፡፡
እነ ኤቢሳ አካላዊ ቁስሌን እንደሳምራዊው ሰው በቅባት እንዳሹልኝ አሁን ደግሞ ዘመዶቻቸው የተሰበረ መንፈሴን የቆሰለ እኔነቴን ሊጥገኑ ተነስተዋል፡፡ የእነኤቢሳ፣ የእነቶፊቅ እና የእነ ቶላ ዘመዶች እኔን ከህመሜ ሊያድኑኝ ደማቸውን እየከፈሉ መሆናቸውን ድፍን ፌስቡክ እየተመለከተው ነው፡፡ አዲስ አበቤ “አገር ሊያፈርሱ ነው ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አትኖርም” ቅብርጥሴ ቅብርጥሴ ቢልም እኔ ግን ከሚፈርሰው አገር ከፒያሳ ከፍ ብሎ ያለው ማዕከላዊ ጎልቶ ይታየኛል፡፡ ስለዚህ በመሬት ላይ ዋጋ እየከፈሉ ያሉትን ወገኖቼን ይቅር ብያለው፡፡ ከነዚህ በቀር ሌላው ማኀበረሰብ “እርሱ” አይደለም “እኔ” ራሱ ይቅርታን አያገኛትም፡፡ አራዳ ፍርድ ቤት መሄዴ አይቀርም፡፡ በማዕከላዊ በርም አልፋለው፡፡ በየጊዜው እየሄደኩኝ ከገራፊዎቼ አንዱን እያየው ጥላቻዬን እያደስኩኝ እመጣለው፡፡ ቁስሉ ይበልጥ እንዲቆጠቁጠኝ ወደገራፊዬ ተጠግቼ አይኖቹን በአይኖቼ አድናለው፡፡ አይገርምም ግን ………….…ገራፊዬ እስካሁን እዚያው ነው፡፡
በጋምቤላ በተቀሰቀሰው ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰማ
ባለፈው ሳምንት ጥር 19 ቀን 2008 ዓ.ም. በምዕራብ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል በተከሰተው የብሔር ግጭት ከ40 በላይ ሰዎች መሞታቸው ተሰምቷል፡፡ የግጭቱ መንስኤ እስካሁን በገለልተኛ አካል ባይታወቅም ግጭቱ በክልሉ ነዋሪ በሆኑ አኝዋክና ኑዌር ማኀበረሰብ መካከል በተፈጠረ ግጭት እንደሆነ ይነገራል፡፡

የማዕከላዊ መንግሥት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩሉ የሟቾች ቁጥር 14 ነው ግጭቱም በቁጥጥር ስር ውሏል ቢሉም፤ የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ኢታንግ ወረዳ አስተዳደር አቶ ኦኬሎ ኦባንግ በበኩላቸው ብዙ ሰዎች እንደሞት እንደሚነገርና በአሁን ወቅት የሟቾችን ቁጥር በርግጠኝነት መግለፅ እንደማይቻል ለብሉንበርግ ተናግረዋል፡፡
ለግጭቱ ምክንያት ሊሆን ይችላል ተብሎ የተገመተው በአካባቢው የደደቡብ ሱዳን አማፂ መሪ ሬክ ማቻር ደጋፊ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ከ264 ሺህ በላይ የኑዌር ጎሳዎች በክልሉ ኢታንግ ወረዳ መስፈራቸውና በአካባቢው ማኀበራዊ መስተጋብር ላይ ተፅዕኖው እየበረታ ነው በሚል እንደሆነም ቢነገርም ከመንግሥትም ሆነ ከዓለም አቀፉ ስደተኞች ድርጅት ስደተኞቹ አሳድረዋል ስለተባለው ተፅዕኖ የተገለፀ ነገር የለም፡፡
የተፈጠረውን ግጭት ተከትሎ በአካባቢው የፀጥታ ኃይሎች እና በማኀበረሰቡ መካከልም አለመግባባቶች እንደተፈጠሩ በዚህም በርካታ ሰዎች መጎዳታቸውን እና የመኖሪያ ቤቶች መቃጠላቸውን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ከግጭቱ ጋ በተያያዘም በርካታ ሰዎች በክልሉ ዋና ከተማ ጋምቤላ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውንና ጉዳት የደረሰባቸው የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
የመሬት ቅርምት እና ውጤቱ
ብስራት ወልደሚካኤል
በኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ ባለ ሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ ዕድገት አስመዝግቢያለሁ ሲል ይሰማል፡፡ በተለይ 11 በመቶ በተደጋጋሚ ዓመታዊ የኢኮኖሚ ዕድገት አስመዝግቢያለሁ ፣የምግብ ዋስትናን አረጋግጫለሁ ካለ ሰነባብቷል፡፡ ነገር ግን ተጨባጭ እውነታዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ የተባለ ባለሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ ዕድገት በመን እና እንዴት እንደመጣ፣ የት ማን ተጠቃሚ ሆነ የሚሉ ጥያቄወች ግን መልስ አይሰጥባቸውም፡፡
በዚህ ሁኔታ ዛሬ ላይ አስቸኳይ የምግብ ዕርዳታ የሚፈልጉ ዜጎች ቁጥር ከ15 ሚሊዮን ወደ 18 ሚሊዮን ማሻቀቡን ዓለም አቀፍ መረጃዎች እያመለከቱ ነው፡፡ በተለይ የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት በኢትዮጵያ የተከሰተው ርሃብ ሀገሪቱ በታሪኳ አይታው በማታውቀው መልኩ ከፍተኛ ህዝብ መራቡን እና አፋጣኝ ምላሽ ከዓለም አቀፍ ለጋሽ ሀገሮችና ተቋማት ካልተሰጠ ችግሩ ከዚህም ሊከፋ እንደሚችል በተደጋጋሚ የተማፅኖ እና ማስጠንቀቂያ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ይህም በተከታታይ ዓመታት ባለ ሁለት አሀዝ የኢኮሚ ዕድገት አስመዝግባለች በተባለችው ሀገር ባለሁለት አሀዝ 15 ሚሊዮን ህዝብ አስቸኳይ የምግብ ርዳታ አስፈላጊ መሆኑ አለ6 የተባለውን የቁጥር ዕድገት ገቢራዊ ሳይሆን ምናባዊ ያደርገዋል፡፡
በተለይ ሟቹ አቶ መለስ በስልጣን ላይ በነበሩበት እስከ 2002 ዓ.ም. ድረስ ከፍተኛ የሆነ የሀገሪቱን ለም መሬት በሊዝ/በኪራይ ሒሳብ ለውጭ ባለሃብቶች እንዲተላለፍ አድርገዋል፡፡ ከተላለፈው መሬት በተጨማሪ ለግብር እና ኢንዱስትሪ አገልግሎት በሚል ሰፋፊ መሬቶች ከዜጎች ተነጥቀው በመንግሥት የመሬት ባንክ ስር እንዲሆኑ ተደርገው ነበር፡፡
ለሽያጭ የተዘጋጀውና የተሸጠው መሬት መጠን
የማኀበራዊና ተፈጥሮ ሃብት ተመራማሪ ደሳለኝ ራህመቶ 2003 ዓ.ም. (እ.አ.አ. 2011)ጥናት፤ ከ1996 ዓ.ም. እስከ 2002 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ አጠቃላይ ለባለሃብቶች የተዘጋጀው ሰፋፊ ለም መሬት 3, 870, 280 ሄክታር መሬት ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ለባለሃብቶች የተላለፈው/የተሰጠው መሬት በከፊል 1, 342, 370 ሄክታር መሬት ነው፡፡ ይህም በሄክታር በየዓመቱ ከ14 ብር እስከ 135 ብር ዋጋ ከ30-50 ዓመት በሚፈጅ ኪራይ ውል የተላለፈ መሬት ነው፡፡ በመንግሥት እጅ ለሽያጭ/ኪራይ የተዘጋጀው መሬትና ተላልፎ የተሰጠውን መሬት በክልሎች ምን ያህል እንደነበር ያለውን በከፊል እንመልከት፤
ትግራይ ክልል 51, 544 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ30-40 ብር ዋጋ በመንግሥት ቢተመንም፤ በሊዝ የመሬት ኪራይ ለባለሃብት የተላለፈ መሬት የለም፡፡
አፋር ክልል 409, 678 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ እስካሁን ዋጋው ባልታወቀ ሒሳብ ለባለሃብት በሊዝ የተላለፈው መሬት 54, 000 ሄክታር መሬት ነው፡፡
አማራ ክልል 420, 000 ሄክታር መሬት ለባለሃብት በሚል ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ14-79 ብር ዋጋ ተተምኖ ከተዘጋጀው መሬት ላይ ለባለሃብት የተላለፈው 121, 370 ሄክታር መሬት ነው፡፡
ኦሮሚያ ክልል 1, 057, 866 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ70-135 ብር ዋጋ ተተምኖ ከተዘጋጀው መሬት ላይ 380 000 ሄክታር መሬት በሊዝ ተላልፏል፡፡
ደቡብ ክልል 348, 009 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር በዓመት በሄክታር ከ30-117 ብር ዋጋ ተተምኖ 60, 500 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡
ጋምቤላ ክልል 829, 199 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ20-30 ብር ዋጋ ተመን 535, 000 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡
በቤኒሻንጉል ክልል 691, 984 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ15-25 ብር ዋጋ ተመን 191, 500 ሄክታር መሬት ለባለሃብት ተላልፏል፡፡
ኦጋዴን (ሶማሌ) ክልል 26, 000 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቶ በዓመት በሄክታር ከ16-65 ብር ቢተመንም በሊዝ ለባለሃብት የተላለፈ መሬት የለም፡፡
*ከላይ የተጠቀሰው መረጃ የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች (አብዛኞቹ የህወሓት ሰዎች ናቸው) ከ2,000 ሄክታር መሬት በታች በእያንዳንዱ ባለሃብት የተወሰደውን ፣ ለአበባ እርሻ ልማት በየከተሞች አቅራቢያና ገጠር ከገበሬዎች ተነጥቆ የተሰጠውን መሬት ፣ መንግሥት ለስኳር ፕሮጀክት በሚል የወሰደውን 335, 000 ሄክታር መሬት አያጠቃልልም፡፡ መሬቱን ከወሰዱ ባለሃብቶች/ኩባንያዎች መካከል በአፋር ክልል የተሰጠው የግብፅ ብሔራዊ ባንክ እና በኦሮሚያ ክልል ለጥራጥሬ ምርት ከተሰጠው የጅቡቲ መንግሥት በስተቀር እስካሁን ምርታማና ውጤታማ የሆኑ የሉም፡፡ የግብፅ መንግሥት በብሔራዊ ባንኩ አማካኝነት እና የጅቡቲ መንግሥት በቀጥታ የሀገሮቻቸውን የምግብ ፍጆታ ለመደጎም የሚጠቀሙበት እርሻ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ግን የዜጎቹን የምግብ ፍጆታ ለመሸፈን እና የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በመንግሥት ተቋማትም ሆነ በባለሃብቶች በኩል አንዳችም የግብርና መሬት ጥቅም ላይ አላዋለም፡፡ ሰፋፊ ለም መሬት ለሀገር ውስጥና ለውጭ ባለሃብቶች የተሰጡትም ቢሆኑ ዋጋቸው እጅግ እርካሽ ከመሆኑ የተነሳ ከውጭ ምግብ ነክ ምርቶችን ወደሀገር ውስጥ ለማስገባት እንኳ የሚበቁ አይደለም፡፡
የአካባቢና ማኀበራዊ ተፅዕኖው
ሁሉም ባለሃብቶች ማለት ይቻላል መሬቶቹን በወሰዱበት አካባቢ የነበሩ ነዋሪዎችን ያለ በቂ ካሳና ምክክር ከማፈናቀላቸው በተጨማሪ ለዘመናት ሲንከባከቡት የነበሩ የተፈጥሮ ደኖች ሙሉ ለሙሉ ተመንጥረው ከጥቅም ውጭ ሆነዋል፡፡ ይሄም ምናልባት በ10 እና 20 ዓመታት ውስጥ ከማኀበራዊ ተፅዕኖ በተጨማሪ ተፈጥሮን በማዛባት የሀገሪቱ የአየር ንብረትና አካባቢ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ እንደሚኖረው ይታመናል፡፡ የአካባቢና አየር ንብረት መዛባት ተፅዕኖ ደግሞ እንደ ድርቅ ያሉ ሌላ ተጨማሪ ችግር ይዘው ከመምጣታቸው በተጨማሪ፣ ድርቅን ተከትሎ ምናልባትም ከአሁኑ መላ ካልተዘየደ ሀገሪቱ በታሪኳ አይታ ማታውቀው ርሃብ ሊከሰት እንደሚችል ይጠበቃል፡፡

አስገራሚው ነገር የሀገር ውስጥ ባለሃብቶችም ሆኑ ከውጭ የመጡ ባለሃብቶች ፕሮጀክታቸውን ለማሳካት ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ እና ንግድ ባንክ ከፍተኛ ብድር ወስደው ያልመለሱና በዛው የጠፉ በርካቶች ሲሆኑ፤ ምንም ሳይሰሩበት/ላይሰሩበት የተፈጥሮ ደኖችን (በተለይ በሰሜን ምዕራብ፣ በምዕራብ እና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢ) መንጥረው ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ከጥቅም ውጭ አድርገው መሄዳቸው ነው፡፡ ከዚህ ጋ በተያያዘ ሻምፖርጂየተባለ የህንድ ኩባንያ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 50 ሺህ ሄክታር ለም መሬት ለግብርና ልማት በሚል ወስዶ የነበረውን ደን መንጥሮና አቃጥሎ እስከ አዲስ አበባ ድረስ ከሰል ይሸጥ እንደነበርና ከዛም ጥሎ ወደሀገሩ ጠቅልሎ እንደሄደ ይነገራል፡፡ በአካባቢውም ከሰል ነጋዴ ባለሃብቶች በሚል ይተቻሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ተጨማሪ ሌላ ጉዳት ነው፡፡ ይህ ምንግሥት እሰራዋለሁ ላለው ስኳር ፕሮጀክት (ከሰም፣ ደቡብ ኦሞ እና ወልቃይት ) እና ኢሉባቦር ለማዳበሪያ ፋብሪካ ለማቋቋም በሚል ሙሉ ለሙሉ ከጥቅም ውጭ ያደረጋቸውን ደኖች ሳይካትት ነው፡፡ የስኳር ፕሮጀክቶቹም ሆኑ የማዳበሪያ ፋብሪካዎቹ የተፈጥሮ ደኖችን ከማውደም እና የአካባቢውን ነዋሪዎቸ ከማፈናቀል ባለፈ እስካሁን የታየ ምንም አዎንታዊ ውጤት የለም፡፡
ከላይ የተጠቀሱ እና ለባለሃብቶች በሊዝ መልክ የተላለፉ መሬቶች ውጤታማ ሆነው ቢታዩ ኖሮ የመንግሥት ዓላማና ግብ የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ላይ ሳይሆን የውጭ ምንዛሪ ላይ ትኩረት ያደረገ ነበር፡፡ ይህ የሚያሳየው ሀገሪቱ ላይ እየተተገበረ ያለው የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም እና የኢኮኖሚ ፖሊሲው ምን ያህል የተሳሳተ እንደሆነ እና መንግሥት እስካሁንም የዜጎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በስሩ ካሉ የመገናኛ ብዙኃን ከሚነገረው ወሬ በስተቀር በተግባር ይሄ ነው የሚባል ጅማሮም ሆነ ውጤት የለም፡፡
በተለይ ከመሬት ቅርምቱ ጋ በተያያዘ ሶስት ተጨማሪ ጉዳዮችን እናንሳ፡፡
መንግሥት ሰፋፊና ለም የሆኑ የሀገሪቱን መሬት እጅግ ዝቅተኛ በሆኑ ዋጋ ለግማሽ ምዕተ ዓመት ድረስ ለመስጠቱ በዋናነት የሚሰጠው ምክንያት ፤
– ለዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር/የስራ አጥ ቁጥር ለመቀነስ
– በግብርናው ዘርፍ የቴክኖሎጂ ሽግግር ለማምጣት
– የግብርና ምርትን በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪን ማስገኘት የሚል ነበር፡፡
ነገር ግን ከተጠቀሱት ምክንያቶች ስኬታማ የሆኑ የሉም፡፡ በአንፃሩ በማኀበረሰቡ እና በአካባቢው ላያ ያደረሱት ጉዳት ግን አለ፡፡ በመሬት ቅርምቱ ከደረሱ ጉዳቶች መካከል ጥቂቶቹ፡
ነዋሪዎችን ያለበቂ ካሳና ምክር አገልግሎት ማፈናቀል ይገኝበታል፡፡ ከዚህ ጋ በተያያዘ በዋነኛነት በጋምቤላና ደቡብ ኦሞ ከፍተኛውን ቁጥር ይይዛሉ፡፡
በጋምቤላ ወደ 225, 000 የአካባቢው ነዋሪዎች ያለበቂ ካሳና፣ ምክክርና ስምምነት ተፈናቅለዋል፡፡ ይህንም ተከትሎ ከ 8 ሺህ እስከ 10 ሺህ ተፈናቃዮች ሀገር ለቀው ወደ ጎረቤት ሀገሮች በተለይም ወደ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ኬንያ ተሰደዋል፡፡ የመሬት መፈናቀሉን ከተቃወሙ ከክልሉ ነዋሪዎች መካከል ፤ ከመንግሥት በተለይም ከወቅቱ ጠቅላ ሚኒስትር በነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝ በተወሰደ ወታደራዊ የኃይል እርምጃ 424 የአኝዋክ ማኀበረሰብ አባላት በተመሳሳይ ቀን በጅምላ ተገድለዋል፡፡ በርካታ ሰዎችም በጋምቤላና አዲስ አበባ በሚገኙ ወህኒ ቤቶች ታስረዋል፡፡ ይህ ድርጊት የተፈፀመው በአብዛኛው በዛው በጋምቤላ ክልል አኝዋክ ዞን ነዋሪዎች ነበሩ፡፡
በትውልድ ኢትዮጵ በዜግነት ሳውዲ ዓረቢያዊ የሆኑት መሐመድ አሊ አላሙዲ ንብረት የሆነው ሳውዲ ስታር ኩባንያ ከዚሁ ከጋምቤላ ብቻ 139 ሺህ ሄክታር መሬት ሩዝ እና አኩሪ አተር አምርተው የሰውዲ ዓረቢዎችን የምግብ ፍጆታ ለመሸፈን ታቅዶ ቢከናወንም ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ የህንዱ ካራቱሪ ኩባንያ 10 ሺህ ሄክታር መሬት ጠይቆ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በነበሩት በሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዛና ፈቃድ ያለ ኩባንያው ፍላጎት 300 ሺህ ሄክታር መሬት ቢሰጣቸውም ውጤታማ አልሆኑም፡፡ ይህ ኩባንያ በቅርቡ 100 ሺህ ሄክታር መሬት መነጠቁን ተከትሎ በኩባንያው ባለቤት ካራቱሪና በመንግሥት በኩል አለመግባባት ተፈጥሯል፡፡ ሁለቱም ኩባንያዎች በርካታ ነዋሪዎችን አፈናቅለዋል፣ የተፈጥሮ ደኖችን ከጥቅም ውጭ አድርገዋል፡፡
በደቡብ ኦሞ ሸለቆ በተለይ በደቡብ ኦሞ ዞን ልክ እንደጋምቤላው ያለበቂ ካሳና ምክክር ከ200, 000 በላይ የአካባቢው ነዋሪዎች ተፈናቅለዋል፡፡ ማፈናቀሉን ከተቃወሙት መካከል በተለይ ኩራዝ የስኳር ፕሮጀክት ግንባታ አካባቢ የነበሩ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ነዋሪዎች በተመሳሳይ ወታደራዊ እርምጃ ተገድለዋል፡፡ የመሬት ቅርምቱን የተቃወሙ ተፈናቃዮች መካከል በደቡብ ኦሞ እና ሐዋሳ በሚገኙ ወህኒ ቤቶች በርካቶች ሲታሰሩ፣ ከእስርና ግድያ ያመለጡ ደግሞ ወደጎረቤት ኬንያ ተሰደዋል፡፡
ሰፋፊ ለም መሬቶቹ ለባለሃብቶች ተሰጥተው፣ በመሬቱ ስም ከሀገሪቱ ከፍተኛ የባንክ ብድር እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ እስካሁን ባሉ መረጃዎች ከጅቡቲ መንግሥት እና ከግብፁ ብሔራዊ ባንክ መሬቶች በስተቀር በሌሎቹ መሬቶች ከባንክ ብድር ተወስዶባቸው በርካቶቹ ብድሮች አልተመለሱም፡፡ የባንክ ብድርንም ሆነ የመሬት ኪራይ ክፍያን ባለመፈፀም መሬት የተሰጣቸው የተለያዩ የህንድ ኩባንያዎችና የህወሓት ሰዎች ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛሉ፡፡ ከዚሁ ሰፋፊ የመሬት ቅርምት ጋር በተያያዘ ዜጎች በግፍ ተፈናቅለዋል፣እየተፈናቀሉም ይገኛሉ፡፡ የባለሃብቶችን ድምፅ የሚሰማ አካል ቢኖርም የዜጎችን ድምፅና አቤቱታ እንዲሁም መብትና ጥቅም የሚያስጠብቅ አካል ግን አልተገኘም፡፡ የዚህ ሁሉ ችግር አብይ ምክንያት ከ”ህገ መንግሥት” እስከ ኢህአዴግ ፖሊሲ መሬት “የመንግሥትና የህዝብ ነው፣ መሬት አይሸጥም አይለወጥም” በሚል ፈሊጥ እያንዳንዱ ዜጋ የመሬቱ ባለቤትነቱ በአዋጅ እንዲነጠቅ መደረጉ ነው፡፡
በህወሓት/ኢህአዴግ ቋንቋ መሬት የመንግሥትና የህዝብ ነው፤ መንግሥትና ህዝብ ደግሞ ህወሓት ነው፡፡ ዜጋው እየኖረበት ያለበት መሬት ባለቤትነቱ በመነጠቁና በሱስ ስም “መንግሥት” እና “ህዝብ” የሚል ምናባዊ ተቋም አማካኝነት በላዩ ላይ ቤቱ ከነንብረቱ ያለማንም ከልካይ ይሸጣል፣ ይለወጣል፣ ይሄንን ተቃውሞ ጥያቄ የሚያቀርብ ደግሞ ይገደላል፣ አሊያም ይታሰራል፣ በለስ ቀንቶት ከነኚህ ርምጃዎች ካመለጠ ወደጎረቤት ሀገር ጥገኝነት ፍለጋ ይሰደዳል፡፡
ዜጎች ለምን የመሬታቸው ባለቤት አልሆኑም?
ዜጎች የመሬታቸው ባለቤቶች አለመሆናቸውና በመሬታቸው ላይ ማዘዝና መወሰን አለመቻላቸው ራሳቸውን እንደ ዜጋ የሚያዩበት አሊያም የሀገሪቱ ሉዓላዊ ግዛት ባለቤት ስለመሆናቸው የሚያስችል መብት ሙሉ ለሙሉ በህገ መንግሥቱ አዋጅ ተነጥቋል፡፡ በዚህም ከስነ ልቡና በተጨማሪ የገበሬዎች መሬት ምርታማነት ላይ ጥያቄን ያስነሳል፡፡ ምክንያቱም መሬቱን የራሱ አድርጎ መወሰንና ማዘዝ እንዲሁም ከባንክ ብድር ማግኘትም ሆነ መሸጥ የሚያስችል መብት በመነፈጉ ከእለት ጉርስ ባለፈ ስለ ምርታማነት የመጨነቅ ስሜት አይስተዋልበትም፡፡ ከባለፈው ህዳር ወር 2008 ዓ.ም. በኦሮሚያ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅ መነሻው የአዲስ አበባ እና የኦሮሚል ክልል ልዩ ዞን የተቀናጀ መስተር ፕላን ይደረግ እንጂ ዋናው ምክንያት ዜጎች የመሬት ባለቤትነታቸው ተነጥቆ በተደጋጋሚ በግፍ መፈናቀላቸው ነው፡፡ ይሄ ዛሬ በአንድ ክልል ተጀመረ እንጂ ብሶቱ ከልክ እያለፈ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ነገ መከሰቱ የማይቀር ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ መፍትሄ ማስት ፕላኑን ማቆም ወይም የስርዓቱን ሰዎች ሰብስቦ የፕሮፖጋንዳ ድጋፍ ዜና እወጃ ሳይሆን መሰረታዊ የህገ መንግሥትና የፖሊሲ መሻሻል ነው፡፡
በኢትዮጵያ መሬት የእያንዳንዱ ባለ ይዞታ/ባለቤት ንብረት መሆኑን፣መሬትን የሚሸጥም ሆነ የሚሰጥ ራሱ ባለቡቱ እንደሆነ፣ መንግሥት ለከተማ መኖሪያና ማኀበራዊ አገልግሎት ተቋማት መገንባት ቢፈልግ ከባለይዞታቸው ተደራድሮ በገበያ ዋጋ እንዲገዛ ቢደረግ፣ ተቋማቱን ለመገንባት ዜጎች ተገቢውን ግብር እየከፈሉ ስለሆነ፣ በመሬታቸው ላይ የመወሰንና የማዘዝ ሙሉ ስልጣን ለእያንዳንዱ ዜጋ መሰጠት አለበት፡፡ አሁን ባለወ ነባራዊ ሁኔታ የሀገሪቱ መሬት ከፊውዳላዊ ስርዓት እጅግ የከፋ እንጂ የተሻለ ነገር የለውም፡፡ ምክንያቱም በፊውዳሉ ስርኣት ዜጎች የመሬታቸው ባለቤቶች አልነበሩም፣ ዛሬም አይደሉም፡፡ ይሄ ተለወጦ በደርግ ዘመን የካቲት 25 ቀን 1967 ዓ.ም. የታወጀው የመሬት ላራሹ አዋጅ እንደገና ተግባራዊ መደረግ አለበት፡፡ በግለሰቦችና በማኀበረሰቦች(ለግብርና እና ማኀበራዊ አገልግሎት) ያልተያዙ ቦታዎችን መንግሥት ለማኀበራዊ አግልግሎት ለማዋል ቢወስን ግልፅነትና ተጠያቂነት ባለበት መልኩ እንዲከናወን ግልፅ የሆነ ህጋዊ ማዕቀፍ ሊኖረው ይገባል፡፡ አሁን ያለው የጠባብ ፖለቲካዊ ቤተሰብ ግንኙነት ውርስ አሰራር መቆምና በግፍ የተወሰደው መሬት ለተፈናቃዮችና ባለቤቶች መመለስ እና አሰራሩ መከለስ ይኖርበታል፡፡
በሌላ በኩል የተለያዩ የሀገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች በግብርና ሙያ በርካታ ተማሪዎችን እያስተማሩ ቢያስመርቁም፤ ባለሙያዎቹ የቀሰሙትን እውቀት አሟጠው እንዲጠቀሙ፣ ሀገሪቱንም እንዲጠቅሙ፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ የተሻለ ውጤት እንዲያመጡ የመሬት አቅርቦትም ሆነ የባንክ ብድር በመንግሥት አልተመቻቸም ሳይሆን አልተፈቀደላቸውም፡፡ በሌላ በኩል ከግብርናው ጋርም ሆነ ከንግድ ጋ ምንም እውቀት የሌላቸው የህወሃት ሰዎች በፈለጉት ሰዓት የፈለጉትን መሬት ለሚፈልጉት ዓላማ በፈለጉት ቦታ ሲያገኙ፣ የባንክ ብድርም በፈለጉት ሰዓት ያገኛሉ፤ በተመሳሳይ የውጭ ባለሃብቶችም እንዲሁ፡፡ ነገር ግን ጊዜያቸውን እና ገንዘባቸውን መስዋዕት አድርገው ከ16 ዓመታት ያላነሰ በእውቀት ማዕድ ላይ የነበሩና ያሉ ዜጎች አብዛኞቹ ስራ አጥ ሆነው ስራ ለማግኘት መንግሥት እንዲጠብቁ ሲፈረድባቸው፣ በለስ የቀናቸውም ቢሆኑ አውቀታቸው በአግባቡ ስራ ላይ ለማዋዕል የሚያስችል መንግሥታዊ አገልግሎት ባለመኖሩ ቢሮ ገብቶ ወርሃዊ ደመወዝ በመጠበቅ ሙሉ ለሙሉ መንግሥት ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ ይገደዳሉ፡፡
በሀገሪቱ የሀገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ፣ የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም፣ ኢኮኖሚውን በተመለከተ የዜጎችን መብትና ጥቅም ሊያስጠብቅ የሚያስችል ፖሊሲ ባለመኖሩ ከሌሎች ሀገረች ሲነፃፀር እንደ ኢትዮጵያ በእውቀትና በትምህርት ኪሳራ የደረሰባትም ሆነ የሚደርስባት ሀገር ስለመኖሯ አጠራጣሪ ነው፡፡ ቢያንስ በግብርና ሙያ የሚመረቁ ባለሙያዎች በየመስካቸው በቂ የመሬት አቅርቦት እና የባንክ ብድር ቢመቻችላቸው ከራሳቸው አልፈው ሀገሪቱን በብዙ መልኩ መጥቀም በቻሉ ነበር፡፡ ምናልባት የተሻለ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ሽግግር ቢያስፈልግ እንኳ እዛው በሚማሩበት የትምህርት ተቋም ማመቻቸት አሊያም ለተጨማሪ አጫጭር የሙያ ስልጠናዎቹን ሊሰጡ የሚችሉ በዘርፉ ውጤታማና ከእኛ ልቀው ካሉ ሀገሮች ባለሙያዎችን አምጥቶ አሰልጥኖ ወደስራ እንዲገቡ ቢደረግ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ የስራ አጥ ቁጥርን ለመቀነስ፣ የዜጎችን መብትና ጥቀምን ለማስጠበቅና ለመጠበቅ እጅግ የተሸሉ ቢሆኑ እንጂ የሚያንሱ አይደሉም፡፡ የአካባቢና የተፈጥሮ ሃብት አጠቃቀም ላይም ቢሆን በተገቢው መንገድ እንዲከናወን በማድረግም ሆነ ጥራት ያለው ምርት አምርቶ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ለማስገኘትም ቢሆኑ ከውጭ ባለሃብቶችም ሆነ በፖለቲካ ወገንተኝነት ከሚደረግ የጥቅም ትስስር በእጅግ የዘርፉ ተማሪዎች ውጤታማ ስለመሆናቸው ጥርጥር የለውም፡፡
በርግጥ ዜጎች ሁሉ በፖለቲካው፣ በኢኪኖሚውም ሆነ በማኀበራዊ አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ ስርዓቱ ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ ከሚሰራ እና ራሱን የአናሳ ብሔር ተወካይ አድርጎ በዘረኝነት ፖለቲካዊ ወገንተኝነት በተጠመደ ህወሓት/ኢህአዴግ ቡድን ከላይ የተጠቀሰውን ቀና አስተሰሰብ መጠበቅ የዋህነት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ነገር ግን ጥቅሙ ለባለሙያዎቹ፣ ለሀገሪቱም፣ ለህዝቡም ሆነ ለራሳቸው የተሻለ ጥቅም ያለውና አዋጭ መፍትሄ ነው፡፡ መፍትሄዎቹ ላለፉት 25 ዓመታት ባለመወሰዳቸው የመሬት ቅርምቱ በሀገሪቱ ሰላምና መረጋጋት፣ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማኀበራዊ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ ችግር አስከትሏል፣ የተለመደው የኪሳራ አካሄድ አሁንም በተጠናከረ መንገድ ቀጥሏል፡፡ የዚህ ሁሉ መዘዝ ግን አንዱን አካባቢ ብቻ ነጥሎ ጉዳት የሚያደርስ ሳይሆን አጠቃላይ በሀገሪቱ ኢኮኖሚና ፖለቲካ ማኀበራዊ ጉዳይ ላይ የራሱን አሉታዊ ጫና ማሳረፉ አልቀረም፡፡ የመሬት ባለቤትነት የህግ ማሻሻያ እና የፖሊሲ ለውጥ ካልተደረገ ዜጎች ከመሬታቸው በግፍ የመፈናቀል እና የመሬት ቅርምቱ ተጠናክሮ መቀጠሉ የሚያጠያይቅ አይደለም፡፡
ባለ መሰንቆውና ባለ ወለሎው
በእውቀቱ ሥዩም

“ ሮድ ደሴት” በተባለ አገር ውስጥ እንደ እንደምኖር የነገርኩት ጓደኛየ“ እና ባሣ አጥማጅነት ነው የምትተዳደረው?”ብሎኛል፡፡ ሮድ ደሴት አበሻ እጥረት ክፉኛ ከሚያጠቃቸው ክልሎች አንዱ ነው ፡፡ አሁን ምድሩም ሰማዩም ሰውም ነጭ ነው፡፡
ያገር ሰው በጣም ይናፍቀኛል፡፡ የሆነ ያበሻ ዓይነ ውሃ ያለው አልፎ ሒያጅ መንገድ ላይ ካየሁ ከሚበር አውቶብስ ላይ እንደ ጅምስ ቦንድ ተወርውሬ ወርጀ ስልኩን በቃሌ እቀበለዋለሁ፡፡ ከሁለት ሱዳናውያን ጋር የተዋወቅሁት በዚህ አጋጣሚ ነው፡፡

ያበሻ ናፍቆቴንአናቴ ላይ ሲወጣ ወደአበሻ- ጠገብ ክልሎች እቀላውጣለሁ ፡፡ ባቡሬን ጭኘ መጭ ወደ ውሻንግቶን ዲሲ! ዲሲ የውሃና የመብራት እጥረት የሌለበት አዲስአበባ ማለት ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት ሚኒሶታ ወረድሁ፡፡ ከተማይቱ በበረዶ ተዝረክርካ የሰነፍ ቡሃቃ መስላለች፡፡ የተፈጥሮን ጨካኝነት፤ የቶማስ አልቫ ኤዲሰንን ያለም ቤዛነት ለማረጋገጥ የሚፈልግ ሚኒሶታ ይሂድ፡፡ ወይ አዲስ አበባ! አዱ ገነት፡፡ እብድ የያዘሽ ውበት፡፡ ሰው እንዴት ጥሎሽ ይመጣል? ሰው እንዴት ከገነት ያመልጣ?
ከመኪና ማቆምያው ተሥቼ አዳራሹ ድረስ እስክገባ ድረስ የተቀበልኩት መከራ ራሱን የቻለ ሰማእትነት ሆኖ ለትውልድ ይዘከርልኝ ፡፡ ብዙ ብርድ አጋጥሞኛል እንዲህ አራት ጃኬትና ሁለት ሱሪ ገልቦ፤ አስገድዶ የሚሠር ብርድ ደርሶብኝ አያውቅም፡፡ እድል ፈንታየ ብሎ ብሎ ደም እንደ ብይ በሚጠጥርበት፤ ያፍንጫ ጸጉር እንደጃርት ወስፌ በሚቆምበት አገር ይጣለኝ?
ደሞ እቺም ኑሮ ሆና “በርገርህን እየገመጥክ ትደነፋለህ አይደል?” የሚል ብሽቅ መልክት ይልኩልኛል። ባለመልክቱ! እስቲ ያዲሳባን የጧት ጸሐይ፤ በበርገር ለውጠኝ!!
ሳይደግስ አይጣላም በህይወቴ ባካል ላገኛቸው ከምፈልጋቸው ሰዎችአንዱ የሆነውን ጋዜጠኛ ሰሎሞን ደሬሳን አገኘሁት፡፡ ሰሎሞን ፈላስፋ ነው፡፡የመጀመርያው የሥእል ሓያሲም ነው፡፡ በኦሮምኛ ፤አማርኛ እንግሊዝኛና ፈረንሳይኛ የሚራቀቅ ሊቅ ነው፡፡ ወዳጅ ባታደርገው እንኳ ለፍልምያ የምትመርጠው ሰው ነው፡፡ እንድታስብ የሚገፋፋህ ፤አርፈህ እንድትቀመጥ የማያደርግህ ሰው ማግኘት መታደል አይደል? መጣጥፎቹ ተሰብስበው በመጽሐፍ አለመውጣታቸው ያስቆጫል፡፡ ”ልጅነት ” የምትል በዘልማዳዊው የአማርኛ ስነግጥም ላይ የሸፈተች የግጥም መደብል ሲያሳትም እንደ መናፍቅ ተቆጥሯል፡፡ የትውፊት አስጠባቂው አቤ ጉበኛ በሰሎሞንን ግጥምና በዳኛቸው ወርቁ ልቦለድ ላይ ለማላገጥ “ጎብላንድ አጭበርባሪው ጦጣ”የሚል መጽሐፍ እስከማሳተም ሂዷል፡፡ የአቤ ጎብላንድ ዛሬ በታሪክ ቅርጫት ውስጥ ተጥላለች፡፡ የሰሎሞንና የዳኛቸው መጽሐፎች ግን ገቢያ ላይ በጣም ይፈለጋሉ፡፡ ለምሳሌ ስለባህል ግብዝነት በተነሣ ቁጥር ይችን የሰውየውን ግጥም ማን ይረሣታል?
በኢትዮጵያ ባልጎ መታየቱ
ሳይሆን ቂንጥር ማስቆረጡ
ህጻኗን ልጅ እንደ ቆዳ መስፋቱ
መባለጉ
ኣፉን ሞልቶ” ቂንጥር “ ብሎ መጥራቱ
የሆነ ጊዜ ላይ፤ ስብሐት ገብረእግዚኣብሄር ስለወዳጁ ስለሰሎሞን ”ከሸክስፒርና ከዳንቴ ቀጥሎ ትልቁ ባለቅኔ ሰሎሞን ነው” ብሎ ጻፈ፡፡ ላዲስ ነገር ጋዜጣ የሚሆን ቃለመጠይቅ ሳደርግለት“ሰሎሞንን በዓለም ሦስተኛ ገጣሚ አድርገህ ጽፈሐል፤ አግባብ ነው?”አልኩት፡፡
“እንደዛ ብያለሁ?”
“ኣዎ”
ስብሐት ትንሽ አሰበና መለሰ፤ “ እንዲህ ያልኩት በጣም በናፈቀኝ ሠአት መሆን አለበት“
ከሥነጽሁፉ ምሽት በበኋላ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር ”ሬድ ሲ” ሬስቶራንት ራት ጋበዙን፡፡ እንደምንም እየተንፏቀቅሁ ከሰሎሞን አጠገብ ያለውን ቦታ ያዝኩ፡፡ ይችን ብርቅ አጋጣሚ ተጠቅሜ ከልጅነት እስከ ሽበት ያሳለፈውን ገድሉን አናዝዘዋለሁ ብየ አሰብኩ፡፡አልቀናኝም፡፡ ከሰለሞን ጋር ጨዋታ እንደ ጀመርሁ ከኋላየ ባለጌ ወንበር ላይ የተቀመጠ ተስተናጋጅ፤ ባንገት ጥምጥሜ ጎትቶ ካዞረኝ በኋላ” ቢራውን ትተህ ለምን ጠንከር ያለ ነገር አትወስድም?”በሚል ጥያቄ ጠመደኝ፡፡ ቢራውን ትቸ ጠንከር ያለ ነገር የማልወስድበትን ሰባት ምክንያት ስዘረዝር ራቱ ተገባድዶ ከፍ አለ፡፡
ከእራት በኋላ አዝማሪው ወደ መድረክ ወጣና ማሲንቆውን ማስተከዝ ጀመረ ፡፡ በቤቱ ያለው ሰው በማሲንቆ ዜማ ታጅቦ ወደ ግል ወሬው ተጠመደ፡፡ “ኣንድ ኮርኔስ እዚህ ጋ ያዘዘ ማን ነው?” የሚለው ያስተናጋጇ ድምጽ ካዝማሪው እንጉርጉሮ በላይ ጠብድሎ ይሰማኛል፡፡ ሰሎሞን ከወንበሩ ተነሥቶ በዝግታ እየተራመደ ወደ መድረኩ ከወጣ በኋላ አዝማሪውን ሸልሞ አጠገቡ ቁጭ አለ፡፡ ዓይኑን ለበስ አድርጎ እልምም !! በማሲንቆው ተሳፍሮ የት ደርሶ ይሆን? ወለጋ-አዲስአበባ – ደጃች ውቤ ሠፈር- ፤ የከተማ መኮንን ክራር – ምኒልክና ጊዮርጊስ በፈረቃ ከሚጋልቡት የአራዳ ፈረስ፡፡
ልጅነት በተባለቸው መድብሉ ስለአንድ የውቤ በረሃ ጀግና በጻፈው መወድስ ውስጥ እኒህ መስመሮች ተካትተዋል፡፡
”ደኑ ርቆት፤
መንገዱ ጠፍቶት
ጓዱ ረስቶት
በጨለማ ቤቱን ስቶት“
ዛሬ እኒህ መስመሮች በግዞትና በስደት ሰጥመው የቀሩ ድንቅ ኢትዮጵያውያንን ሁኔታ የሚገልጹ አድርጌ ብተረጉማቸው ማን ይፈርድብኛል?
( ወዳጄ ገጣሚ ዮናስ አንገሶም ኪዳኔ የሰሎሞንን መጽሐፎች ስለሰደድክልኝ ምስጋናየ ይድረስህ፡፡)