ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ አቶ አንዱዓለም አራጌ፥ እና ሌሎችም …
ብስራት ወልደሚካኤል
ረቡዕ መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ. ም. በግምት ከቀኑ 10 ሰዓት አካባቢ ሰላማዊ ሰዎች ከመደበኛ ዕለታዊ እንቅስቃሴዎቻቸው እንደወንጀለኛ ታድነው የታሰሩበት ቀን ነው።

ፎቶ፡ ከማኅበራዊ ገፅ
ረቡዕ መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ. ም. በግምት ከቀኑ 10 ሰዓት አካባቢ ሰላማዊ ሰዎች ከመደበኛ ዕለታዊ እንቅስቃሴዎቻቸው እንደወንጀለኛ ታድነው የታሰሩበት ቀን ነው።
አንዱዓለም አራጌ በወቅቱ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና ምክትል ሊቀመንበር ነበር። ሀገር ሊያቀና ሲኳትን የነበረው አንዱዓለም ሰላማዊ የመብት ትግልን ስራው አድርጎ መንቀሳቀስ የጀመረው ገና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተማሪ ሳለ ነው።
መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ. ም. ሰቆቃ አላልቅ ወዳለበት ማዕከላዊ እና ቃሊቲ ወህኒ ቤት ከገፋቱ በፊት ጠዋቱ የመጀመሪያ ልጁን ሩህ አንዱዓለምን ለመጀመሪያ ጊዜ ትምህርት ቤት አድርሶት ወደ አንድነት ፓርቲ መደበኛ ስራው ገብቷል። በዕለቱም ከመቼው ጊዜ በላይ ደስ ብሎት ይታይ ነበር። ምክንያቱ ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ የአብራኩን ክፋይ ፥ልጁን እጁን በመያዝ ወደ ትምህርት ቤት የወሰደበት ቀን ነውና። ይሄንን ደስታውንም በወቅቱ እዛ ለነበርን ሰዎች ሁሉ ሲያጋራ አስታውሳለሁ። ደስ የሚል ደስታ፥ በፍቅር የተሞላ ፈገግታ፥ የምርም ደስስስስ ይል ነበር። ማታ ወደ ቤት ተመልሶ የልጁን የትምህርት ቤት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ምን እንደሚመስል እና የተሰማውን ስሜት ለማጣራትም ያቺ የአንዲት ቀን ጉማጅ እንደረዘመችበት አስታውሳለሁ።
ግን ምን ዋጋ አለው? የዛሬን አያድርገውና ፤በዕለቱ በግምት ከቀኑ 8 ሰዓት አካባቢ ከአውራምባ ታየምስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል (ከዳዊት ከበደ እንደተደወለለት እንደነገረኝ ትዝ ይለኛ) ስልክ ተደወለለት። ስልኩንም አነሳ። ከዛም በዛሚ ኤፍ ኤም ሬዲዮ አንዱዓለምን፥ ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣና ይዛ በወጣችው ሐሳቦች ዙሪያ በዛሚ ኤፌ ኤም ሬዲዮ “የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ” በሚለው የዕለቱ የቀትር መርሃ ግብር ነገር እየተቦካ እንደሆነ እና እንዲያደምጥ ተነገረው።
በወቅቱ ቢሮው ውስጥ መደበኛ ሬዲዮ አገልግሎት ስለሌለና በስልኩም አገልግሎቱን ማግኘት ስላልቻለ ቢሮው ከሚገኝበት ፎቅ በመውረድ የሰማውን ነገር ነገረኝ። ያቺ ደካማ ስልኬ ሬዲዮ እንደምትሰራ ጠየቀኝ። እኔም በስልኬ መሰል አገልግሎት አልባነት እየሳቅሁ የስራ ባልደረባዬ የነበረውን ጋዜጠኛ ብዙአየሁን ጠየቅኩት። የእሱም ስልክ እንደኔው የሬዲዮ አገልግሎት አልነበረውም። ከዛም የጋዜጣው ፀሐፊዎች የነበሩትን የሺን እና ብርቱካንን ጠየቅን እና ከአንዳቸው አገኘን። በመጨረሻም ከማን እንደሆነ ለጊዜው ባላስታውስም በተገኘው ስልክ በነ ሚሚ ስብሃቱ (ዛሚ ኤፍ ኤሜ ሬዲዮ) “የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ” በሚለው የዕለቱ መርሃ ግብር ላይ ስለ አንዱዓለም አራጌ፥ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ የማክሰኞው መስከረም 2 ቀን 2004 ዓ. ም. ዕትም ይዘት ላይ ጭምር በነ ሚሚ ስብሃቱ፥ መሰረት አታላይ ፥ ፀጋልዑል መኮንን? እና ሁለት ሌላ ባልደረቦቻቸው በአደባባይ ሲቦጭቁ፥ ሲዘረጥጡና ሲወነጅሉ ሰማናቸው።
ሁላችንም በተደረገው የስም ማጥፋት እጅግ አዘንን፥ ተናደድን። ምክንያቱም እነ ሚሚ ምንም ያህል ለህወሓት/ኢህአዴግ ወግነው ጥብቅና የሚቆሙ፤ ኽረ እንደውም ከጳጳሱ ቄሱ ቢሆኑ እንኳ እንደዚህ በአደባባይ የሌለና ያልተፈፀመ እንዲሁም ያልተባለን ነገር ሽብር እንደተነዛና እንደተፈጠረ ተደርጎ መቅረቡ በጣም ያም ነበር። በርግጥ አሁንም ያው ናቸው። ውንጀላቸው በ “ፍኖተ ነፃነት” ጋዜጣ ላይ የወጡ ይዘቶችን፤ በተለይም የአንዱዓለም ቃለ መጠይቅ እና የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የአረቡን አብዮት በተመለከተ በአንድነት ፓርቲ በተደረገለት ግብዣ ያቀረበውን ትንታኔና ውይይት በተመለከት ነበር።
በነገራችን ላይ በአገዛዙ እና በአገዛዙ ወዳጆች በግል ሚዲያ ስም ድጋፍ እንደ ተቋቋመና እስካሁንም ሙሉ በጀቱ እንደሚሸፈንለት የሚነገረው የነ “ሚሚ ስብሃቱና ባለቤቷ ዘሪሁን ተሾመ” ዛሚ ኤፍ ኤም ሬዲዮ፤ “የጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ” የሚለው የእሁድና ረቡዕ የሚዘጋጅ መርሃ ግብር አለ። ይህ ኤፍ ኤም ጣቢያ የህወሓትን ጥቅም ይጎዳሉ ተብለው የሚታሰቡ ጋዜጠኞች፥ ህዝባዊ ቅቡልነትና ከፍተኛ ድጋፍ አላቸው የሚባሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፥ አንዳንዴም የህወሓትን ክፉ ስራና ድርጊት ይገዳደራሉ ተብለው የሚታሰቡ በስሩ ያሉ አንዳንድ የኢህአዴግ መሪዎችም ጭምር ለህወሓት የበቀል እስርና እርድ የሚታጩበት ልዩ የቁጩ መርሃ ግብር ነው።
በዕለቱ ረቡዕ መስከረም 3 ቀን 2004 ዓ. ም. የነ ሚሚ ስብሃቱ ዛሚ ኤፍ ኤም ከህወሓት ደህንነት ጋር ቀጥታ ግንኙነት ብቻ ሳይሆን ተልዕኮም ተሰጥቷቸው እንደሚሰሩ ለመጀመሪያ ጊዜ ያረጋገጥኩትም ያኔ ነው። እውነት ለመናገር ልክ የነሱ ውንጀላ ከተጠናቀቀ በኋላ እጅግ በጣም ተሰማኝ፥ ተናደድኩ። ብቻ እንዴት እንደምገልፀው አላውቅም። ምክንያቱም የጋዜጠኝነት ሙያ ለእንዲህ ዓይነት ርካሽ ተግባር ሊውል እንደሚችል በፍፁም ገምቼ አላውቅም ነበርና።
የነ ሚሚ ውንጀላ ከተጠናቀቀ በኋላ በግምት ከ 30 ደቂቃ በኋላ የአንድነት ፓርቲ ኤዲቶሪያል ቦርድ ኃላፊ እና በፓርቲው የፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ የበላይ ተጠሪ የነበረው አቶ በላይ ፈቃዱ ይመጣል። አቶ በላይም ሁላችንንም ሰላም ብሎን ስለጋዜጣዋ ዕትም ግርድፍ አስተያየት ( ማበረታቻና እርምት) ሰጥቶ ከአንዱዓለም ጋር ወደ ቢሮ ይገባሉ። ከተወሰኑ ደቂቃዎች በኋላም አንዱዓለምና በላይ ተያይዘው በበላይ መኪና እዛው ቀበና ባለው የአንድነት ዋናው ቢሮ አካባቢ ወደሚገኝ ካፌ ሻይ ቡና ለማለት ይሄዳሉ።
በወቅቱ ሁላችንም በሁኔታው ስለተናደድን ጥሩ ስሜት ላይ ባለመሆናችን የዕለቱን የከሰዓት በኋላ የኤዲቶሪያል ቦርድ ውይይት በይደር ለበነጋታው ሐሙስ አስተላልፈን ነበር። ስለሆነም ስለ ሚሚ ስብሃቱና በወቅቱ ስለወነጀሉ “ጋዜጠኞች” እንዲሁም ስለ ዛሚ የኋላ መረጃ ለመቃረም (በግሌ) ልምድ ወዳላቸውና ወደ ማውቃቸው ሰዎች አመራሁ። ይሁን እንጂ እኔ በወፍ በረር ከማውቀው የተለየ መረጃ አላገኘሁም። ከዛም ስለ ዛሚ ኤፍ ኤም ከኢንተርኔትና ብሮድካስት ባለስልጣን ድረ ገፅ የተሻለ መረጃ ባገኝ ብሞክርም ከማውቀው የተለየና ሚነግረኝን አጣሁ። ከዛም ስልኩ ቀደም ሲል ቢኖረኝም ለመጀመሪያ ጊዜ ደውዬ ላስቸግረው ወደ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ጋር ደወልኩ። ስልኩ ይጠራል አያነሳም። ያው ስራ ላይ ሆኖ ይሆናል በሚል ትንሽ ቆይቼ ደወልኩ፤ ስልኩ ይጠራል አይነሳም። በመጨረሻም ነገ እደውልለታለሁ ብዬ ወደ መኖሪያ ቤቴ አመራሁ።
ከዛም ለቀጣዩ ማክሰኞ ህትመት የሚሆን አዳዲስ መረጃ ከተገኘ በሚል ወደ ተወሰኑ የክፍለ ሀገር የመረጃ ምንጮች ጋር በመደወል ትንሽ ካወጋን በኋላ ሁለቱ በኢንተርኔት የመረጃ ሳጥኔ ውስጥ አዲስ መልዕክት እንደተውልኝ በምንግባባበት ቋንቋ ነገሩኝ። እኔም አመሻሹ ላይ ከቤቴ ሰፈር ካለ የኢንተርኔት ካፌ ደንበኛዬ ጋ እያመራሁ ሳለ አንድ ስልክ ከወንድሜ ተደወለ። አነሳሁ። የት ነህ? አለኝ። እዚሁ ሰፈር ነኝ አልኩት። ከዛም፤ ሰማህ? አለኝ። ምኑን? አልኩት። እነ እስክንድርና አንዱዓለም ታሰሩ፥ ዜናው በኢቴቪ ተለቋል አለኝ። አትቀልድ! ከአንድ ሰዓት በፊት ከአንዱዓለም ጋር ነበርኩ፤ ምንድነው ምታወራው? አልኩት። በቃ አትራቅ ብሎ ስልኩን ዘጋው። ውሽቱን መሰለኝ። ርግጥ ነው ማንም ቢሆን ሊያምን የሚችል አይመስለኝም።
ጋዜጠኛ እስክንድርን በተለይ በ1997 ዓ. ም. ቀውጢ ወቅት የክፍለ ሀገር ኮሌጅ ተማሪና ተመራቂ ብሆንም ሐዋሳ ለግሉ ፕሬስ ንባብና ገበያ እንግዳ አልነበረችም። ያኔ እስክንድርን በስራው አውቀዋለሁ። በዕድሜ ከኛ ላቅ ያሉ የምንግባባቸው አንዳንድ ሰዎች ደግሞ በደንብ በአካል የሚያውቁት ያህል አድናቂዎቹ እንደነበሩ አስታውሳለሁ። የመታሰራቸውን ዜና ያረዳኝ ወንድሜ ደግሞ በተመሳሳይ ዓመት አዲስ አበባ ተማሪና ተመራቂ ብቻ ሳይሆን ያን የጦዘ የተስፋ ፖለቲካና ሚዲያ ከተወሰነ ኩርኩም ጋር ስለቀመሰ ከእኔ በተሻለ እስክንድርን ያውቀዋል። ሲያደንቀውም ሰምቻለሁ። ነገር ግን በአካል የሚተዋወቁ አይመስለኝም። አንዱዓለምን በፖለትካው ተሳትፎው በሚዲያ ያውቀዋል እንጂ በአካል አያውቀውም።
ጋዜጠኛ እስክንድር ምኒልክ፥ አስኳል እና ሳተናው የሚባሉ ጋዜጦችን ለንባብ በማብቃት፥ በጋዜጠኝነት ስራውም ብዙ ዋጋ የከፈለ ሰው ነው። በኢትዮጵያ ፕሬስ ታሪክ በአንድ አገዛዝ ብቻ ተደጋጋሚ በደሎች ከደረሰባችውና ብዙ ዋጋ ከከፈሉ የሀገራችን ጋዜጠኞች ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛል። በዛ ላይ ትሁት፥ ሰው አክባሪና ጠንቃቃ ነው። አሳዳጆቹንና አሳሪዎቹን እንኳ ጠንቅቆ ያውቃል፤ ግን ቦታ አይሰጣቸውም። ስለሀገራችን ኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታና ከእኛ ታሪክና የመንግሥት ምስረታ እጅግ የሚራራቅ የቅርብ ጊዜ ታሪክ ያላቸው ግን በተሻለ ሁኔታ ቀድመውን ከሄዱ የሌላው ዓለም ሀገሮች ጋር ያለንን ልዩነት ሲያወራ በቁጭት ነው። የጥሩ ስብዕና እና አርዓያ ባለቤት ነው፤እስክንድር።
አንዱዓለም አራጌ፤ ከጥላቻ፥ የበቀልክና ክፋት ፖለቲካ ማርከሻ እና ለእኛ ትውልድ መሪ ቢሆኑ ብዬ ከምመኛቸውና ከማውቃችው እጅግ ጥቂት ግለሰቦች አንዱዓለም አራጌ ዋነኛው ነው። መልካምነቱን፥ ቅንነቱን፥ ለሰዎች ያለውን አክብሮትና ፍቅር፥ ታታሪነቱን፥ብቃቱን፥ ለሀገርና ለወገን ያለውን ፍቅር እና መልካም ስብዕናውን በቅርብ አውቃለሁ። ህልሙን እና ፍላጎቱንም አይደብቅም። ሲብዛም ግልፅ ነው።
በጣም የሚገርመው አንዱዓለም በብዙ ነገር መልካም አርዓያ ነው። አንዱዓለም ከማንበብ በስተቀር ከማንኛውም ጎጂ ደባል ሱስ ነፃ ነው። በዚህ ሁሉ እደመማለሁ። ውሸትና ማስመሰል ደግሞ አይታይበትም። ሲበዛ የዋህ ነው። በየዋህነቱና በቅንነቱም በግፍ ከመታሰሩ በተጨማሪ በሌሎች ክፉዎች ወጥመድ ውስጥ ሁሉ ገብቶ እንደነበር አስታውሳለሁ (ይሄንን ከለውጥ በኋላ ጊዜ ሲደርስ እነግራችኋለው)። ይሄንንም ለምቀርባቸው ብቻ ሳይሆን እንደው በሀገራችን ፖለቲካ ዙሪያ ወሬ ከገረብን እና በመሪዎች ጉዳይ ሲወራ አንዱዓለምን በመልካም ምሳሌነት አነሳዋለሁ። ዛሬም ቢሆን እንዲሁ። ያንን ወንድሜ ያቃል። ስለዚህ ወንድሜ እንዴት ሰላማዊና መልካም አርዓያ የሆኑ ሰዎችን በተመለከተ መጥፎ የውሸት መርዶ ይነግረኛል? የሚል ጥርጣሬ አሳደረብኝ። እንዲህ ዓይነት ቀልድ ደግሞ ደስ አይልም፤ ያው ቀልድ ስለመሰለኝ።
ከዛ ወዲያው ወደ አንዱዓለም ጋር ስልክ ደወልኩ፤ ስልኩ ይጠራል ግን አይነሳም። በተደጋጋሚ ደወልኩ አይነሳም። እስክንድርም ጋር ደወልኩ አይነሳም። ዛሬ የምን ነጃሳ ቀን ነው እያልኩ ጥሩ ባልሆነ ስሜት ወደ ደንበኛዬ ኢንተርኔት ካፌ ደረስኩ። እሱም ዜናውን ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ተለቆ ሰምቶ ኖሯል ተናዷል፥ በጣም ተከፍቷል። እነኝህ ጅቦች አሰሯቸው አይደል? አለኝ፤ ገና ከመግባቴ። አሁንም ኢንተርኔት ከፍቼ እስካይ አላመንኩም። ብቻ የንዴት ስሜቴ እየናረ ሄደ። ወንበር ሳብኩና በተረበሸ ስሜት ጥግ ወዳለችው ኮምፒዩተር መነካካት ጀመርኩ። ስድስት ኪሎ ያለ አንድ የቅርብ ወዳጄ የእስሩን የመርዶ ዜና ከቁጭት ጋር አጋርቶ አየሁ። ደነገጥኩ። ማመን አልቻልኩም። ከዛ ገለልተኛ የሚዲያ ወግ ከሚናፍቀው ኢቴቪ የተጋራውን ዜና ሰማሁ። በጣም ስሜታዊ ነበርኩ፤ነኝም። የንዴትና ቁጭት ለቅሶ ፈንቅሎ ወጣ። ቀደም ሲል የክፍለ ሀገር መረጃዎችን ለማየትና ለመገረብ ከቤት ብወጣም በሰዓቱ እነኛን መረጃዎች ማየት አልፈለኩም። ጭራሽ ሌላ በርካታ መልዕክቶች እንደተላኩ የመረጃ ሳጥኔ ያሳየኛል። እኔ ግን በዛ ስሜት ውስጥ ሌላ መረጃ ማየትም ሆነ ማጋራት አልፈለኩም። በምን ስሜት? ከዛም በርካታ የስልክ ጥሪዎች መጡ ማንሳት አስጠላኝ።
የኢንተርኔት ካፌው ባለቤት ረዳት ሆና ምትሰራው ልጅ ስሜታችን ግራ ቢገባት በተሸማቀቀ የፍርሃት ስሜት ታየናለች። ባለቤቱም በሁኔታው ስለተናደደ ያለወትሮው ከአምስት ደቂቃ በኋላ ቤቱን ስለሚዘጋ ሌሎች መደበኛ ደንበኞቹ ቶሎ ጨርሰው እንዲወጡ ትብብር ይጠይቃቸዋል። ሰራተኛዋንም ነገ በስራ ሰዓቷ እንድትመጣና በወቅቱ ወደ ቤቷ መሄድ እንደምትችል ይነግራታል። እኔና እሱ ብቻ ቀረን፤ በንዴትና ቁጭት ስሜት ውስጥ …. ። ትንሽ ካወራን በኋላ ኢንተርኔት ካፌውን ዘግተን ሁለታችንም ወደየቤታችን ሄድን። ቤት ስገባም በምሽት ድጋሚ ዜናውንና ድራማውን አየሁ። ህልም ሁሉ መሰለኝ። ምክንያቱም ለእንዲህ ዓይነት የጭካኔ ድራማ ምልከታ ገና እንግዳ ነበርኩና።
ለካ የዛን ዕለት እነ ሚሚ ስብሃቱ “በጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛ” መርሃ ግብራቸው ሲነግሩን የነበረው በህወሓት ደህንነት የታቀደና ያለቀ የእስር መርዶ ነበር፤ ወይ አለማወቅ!?
በዕለቱ እስክንድር ልጁ ናፍቆትን በራሱ መኪና ሰላም ባይኖርም፤ እንደወትሮው ሀገር አማን ብሎ ልጁን ከትምህርት ቤት ወደ መኖሪያ ቤቱ ይዞት እየመጣ ሳለ በበርካታ ፖሊሶች፥ የደህንነት ባልደረቦችና የህወሓት ካሜራማኖች ተደርድረው መንገድ ላይ ያውም አደባባይ ላይ እንደወንጀለኛ አስቁመው የያዙት። ምን ይሄ ብቻ፤ በህፃን ልጁ ፊት እጆቹን በካቴና አስረው ነው ያንገላቱት። በወቅቱ በስፍራው የነበሩ እንደነገሩኝ ከሆነ በህወሓት የወንጀል ድራማ ልጁ ናፍቆት ተደናግጦ አምርሮ ሲያልቅስ እንደታዘቡ በሀዘን አጫውተውኛል። ተመልከቱ! በሚያድግ ህፃን ልጅ ፊት እንደዛ ያለ ነውር ነው የፈፀሙት።
ያኔ የህፃን ኖላዊ እና ሩህ አባት አንዱዓለም አራጌ እና የህፃን ናፍቆት አባት ጋዜጠኛ እስክንድር በግፍ ታሰሩ። ባልዋሉብት፥ በሚጠሉትና በሚታገሉት መንግሥታዊ ሽብር ጭራሽ ተወነጀሉበት። ከዚያም የግንቦት 7 አባል ናችሁ ተብለው ፤ ጋዜጠኛ እስክንድር ላይ 18 ዓመት፥ አቶ አንዱዓለም አራጌ ላይ ደግሞ ዕድሜ ልክ ፈረዱባቸው።
በነገራችን ላይ በተመሳሳይ ክስ በዛው ቀን እዛው አዲስ አበባ ከእስክንድርና አንዱዓለም በተጨማሪ ከአንድነት ፓርቲ መምህር ናትናኤል መኮንን እና አሳምነው ብርሃኑ፤ ከመኢዴፓ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ (አበበ ቀስቶ) እና አቶ ዘመኑ ሞላ ታስረው ነበር። ከክፍለ ሀገር ደግሞ የአንድነት ፓርቲ አመራር የነበሩት ሻምበል የሺዋስ ይሁንዓለም፥ አቶ ዮሐንስ ተረፈ፥ እና አቶ ሻማ ነበሩበት። ይሁን እንጂ አቶ አሳምነው ብርሃኑ፥ ዘመኑ ሞላ እና አቶ ሻማ (የቤተ እስራኤል ማኅበረሰብ አባል እንደሆነ እና ወደ እስራኤል ለመሄድ ጉዞ ዝግጅት ላይ እያለ የታሰረ) አብረዋቸው በታሰሩት ላይ በግድ እንዲመሰክሩ ተደርገው ተለቀዋል።
የአንድነቱ መምህር ናትናኤል መኮንን አቶ አንዱዓለም አራጌ ላይ በሐሰት ” የግንቦት 7 አመራር ነው፥ ተዕልኮ ሰጥቶች ሀገር ልናሸብርን ተነጋግረን ወስነናል በል” ተብሎ ልክ እንደ አቶ አሳምነው ብርሃኑ መስክሮ እንዲወጣ ተደጋጋሚ ማስፈራሪያ፥ ድብደባና ዛቻ ደርሶበታል። ይሄንንም በተደጋጋሚ ፍርድ ቤት ችሎት ላይ ቢያመለክትም ሲመለሰ ከበፊት በከፋ መልኩ ተደብድቧል፥ ለ21 ቀናትም ራቁቱን ውጭ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ እየተደፋበት ተገርፏል፥ ብዙ ስቃይ ደርሶበታል። ግን እንዳሉት በሐሰት ለመመስከር ፈቃደኛ ሳይሆን በመቅረቱ 25 ዓመት እስር ፈርደውበት እዛው ወህኒ ቤት ይገኛል። መምህር ናትናኤል ደግሞ ከስራ ወደቤቱ በአምበሳ የከተማ አውቶቡስ ውስጥ ከስራ ወደቤቱ ሲያመራ ነው በፖሊሶች መኪና ከበባ ተሳፋሪው በሙሉ ታግቶ ተይዞ የታሰረው።
አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ የአሁኑ እስርና ስቃይ ብቻ ሳይሆን ከዚህ በፊት ልክ እንደሌሎቹ ብዙ ስቃይ እንደደረሰበት ፍርድ ቤት ተናግሯል። ስለሱ ማውቅ የሚፈልጉ የበለጠ የኤርምያስ ለገሰ “የመለስ ትሩፋቶችና ባለቤት አልባ ከተማ” የሚለው መፅሐፍ ላይ የተወሰነ ነገር ያገኛሉ። ሌላው ክንፈሚካኤል ደበበ (አበበ ቀስቶ) በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚያስብል ድፍረት ንጉስን በመፈንቅለ መንግሥት ለመጣል ሙከራ አድርገው የከሸፈባችውና አርዓያ የነበሩት የወንድማማቾቹ የነ ጀነራል መንግሥቱ ነዋይ እና አቶ ግርማሜ ነዋይ የቅርብ የሥጋ ዘመድም ነው።
በሙያው የሶስት ዓለም አቀፍ የፕሬስ ሽልማቶች ባለቤት የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከዚህ በፊት 7 ጊዜ ታስሮና ቶርቸር ተደርጎ የተለቀቀ ሲሆን፤ አሁን 7ኛ ዓመቱን እስር ላይ እያሳለፈ ያለው ለ8ኛ ጊዜ ከታሰረ በኋላ ነው። አቶ አንዱዓለም አራጌ ደግሞ በ1997 ዓ ም በነበረው ምርጫ ግርግር ከወቅቱ የቅንጅት አመራሮች ጋር ታስሮ በተመሳሳይ ዕድሜ ልክ ፈርደውበት ነበር። ከሁለት ዓመት በኋላም ከሌሎች የቅንጅት አመራሮችና ጋዜጠኞች ጋር ከተለቀቀ በኋላ ነው ድጋሚ የታሰረው።
አሳዛኙ ነገር፤ ” መንግሥት” በቅርቡ በሀገሪቱ ህዝብና በዓለም አቀፍ ምኅበረሰብና ተቋማት በደረሰበት ጫና የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞችን እንደሚፈታ ቃል ገብቶ ነበር። ይህንንም ተከትሎ ባለፈው አንጋፍውን የኦፌኮ/መድረክ ፓርቲ አመራር ዶ/ር መረራ ጉዲናን ጨምሮ በርካታ ዜጎችን ከእስር መልቀቁ ይታወቃል።
ሰሞኑን ደግሞ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና አንዱዓለም አራጌን ጨምሮ የቀሩ በርካታ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞች በቅርቡ እንደሚፈቱ ይፋ አድርጓል። መንግሥት ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ አቶ አንዱዓለም አራጌ፥ አቶ ክንፈሚካኤል ደበበ ባልተቀበሉት፥ በተከሰሱአበትና በተፈረደባችው ክስ ” የግንቦት 7 አባልና አመራር ነበርኩ፥ በፈፀምኩት የሽብር ተግባር ተፀፅቻለሁ፥ መንግሥትንና ህዝቡን ይቅርታ እጠይቃለሁ” ብላችሁ ፈርሙና ውጡ ማለቱ ተሰምቷል። ይሁን እንጂ የመንግሥት የወንጀል ይቅርታ ጥያቄው በነ እስክንድር ተቀባይነትን ሊያገኝ አልቻለም።
በእስር ያሉ የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎችም በተመሳሳይ ጥያቄ ” በፈፀምነው የሽብር ተግባር ተፀፅተናል፥ መንግሥትና ህዝቡን ይቅርታ እንጠይቃለን” ብላችሁ ፈርሙና ውጡ የሚለው የመንግሥት ተማፅኖ ተቀባይነት አላገኘም። ይፈታሉ ከተባሉ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞች በተጨማሪ እነ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ኦልባና ሌሊሳን ጨምሮ በርካታ ሰዎች አሁንም እስር ላይ እንደሆኑ ይታወቃል።
በርግጥ አንድ እውነት አለ። መንግሥት በደረሰበት ጫና እንጂ ለእስረኞ አዝኖ ወይም እስረኞችን በግፍ ስላሰቃያቸው ተፀፅቶና ርህራሄ ተሰምቶት አይደለም የለቀቃቸውና ሊለቃቸው የፈለገው። አሁን ያለው የሀገር ውስጥ የፖለቲካ ድባብ፥ የህዝቡ ዛሬም ያልተቋጨ ትግልና የዓለም አቀፉ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ጫና በርትቶበት እንጂ። ስለዚህ መንግሥት ጊዜ ያለፈበትን የፖለቲካ መቆመሪያ ቅድመ ሁኔታ ትቶ ሁሉንም በሚባል ደረጃ የህሊና እና የፖለቲካ እስረኞች የመለቀቁ ጉዳይ ቀጥይ እንደሚሆን ይገመታል። ከለው ተለዋዋጭ የሀገሪቱ የፖለቲካ ትኩሳት አኳያ ከህሊና እስረኞች መለቀቅ በኋላስ የሚለውን የሀገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ በተመለከተ ያው ጊዜ ይፈተዋል ከማለት ውጭ መተንበይ አስችጋሪ ነው።
የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ: በወልድያ የበዓለ ጥምቀት ግጭትና ግድያ የጸጥታ ኃይሉን ወቀሱ፤“የእነርሱ መዘዝ ነው፤ወጣቱ አበላሸ የምንለው ነገር የለም”
“መከላከያዎቹ እንዳይመጡ ቀድመን አሳስበናል፤ከዞኑም ጋር ተናበን እየሠራን ነበር፤”
“በሰላም ሊጠናቀቅ ባለበት ሰዓት መጥተው ግጥም አሉ፤ ይኸው ወጣቱን አሳበዱት፤”
“ወጣቱን ሌላ የፖሊቲካ አካል ቀሰቀሰው አሉ፤ ወታደሮቹን ማን ነው የቀሰቀሳቸው?”
“የበቀል ነው የሚመስለው፤እንደው ከራሳቸው መካከልም የሚያጠፋ ያለ ይመስለኛል፤”
“ታቦቱን ያከበሩት ካህናት፣በጎናቸው ባሉት ካህናት ተገድፈው ነው እንጅ ወድቀዋል፤”
“ተዉ ብሎ ይህን ማስተካከል እና መሥመር ማስያዝ ያለበት መንፈሳዊ አባት ነው፤”
“ቤተ ክርስቲያኗን ወጣቱ ሰምቶልናል፤ታቦቱ ከገባ በኋላ ሁሉም እንሙት እያለ ነበረ፤”
†††
“ተረጋግቶ እያለ ድኻ የሚረዳ ልጅ ገድለው ዳግም በእነርሱ ስሕተት ግጭቱ ቀጠለ፤”
“ሕንፃ እግዚአብሔር እያፈረሳችሁ ፎቅ ትጠብቃላችሁ፤”ብሎ ሕዝቡ በጣም ተቆጨ፤
“ስንቱስ ንብረት ወደመ? የእነርሱ መዘዝ ነው፤ ወጣቱ አበላሸ የምንለው ነገር የለም፤”
“መከላከያ ይውጣ፤ ወጣቱ ከከተማው ፖሊስ ጋር ይጠብቀዋል፤” በሚል ተስማማን፤
ርእሰ መስተዳድሩም፣ “ሠራዊቱን አስወጣለሁ፤ አጣሪ እልካለሁ፤ አጥፊው ለሕግ ይቀርባል፤ ይፋም አደርጋለሁ፤” ብለዋል፤ ልቅሶ ቤትም ገብተው አብረው እያለቀሱ አጽናንተዋል፤
“ከኹለት ዙር ውይይት በኋላ፣ ወጣቱን በየአቅጣጫው የሚመሩ ካህናት መድበን ወደየቤቱ እንዲገባ አድርገናል፤ በሰላም እየዘመረም ወደየቤቱ ተመልሷል፤”
“እኛም በየሐዘን ቤቱ እየዞርን ስናጽናና ውለናል፤ ርእሰ መስተዳድሩ ከተመለሱ በኋላ ከላኳቸው ልኡካን ጋራ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ተካትተን እየመከርን ነው፤”
†††

ፎቶ፡ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ፤ የሰሜን ወሎ እና ከሚሴ ዞን ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ
በሰሜን ወሎ ዞን ወልዲያ ከተማ፣ በጥምቀት እና በቃና ዘገሊላ በዓል አከባበር ወቅት የተቀሰቀሰው ግጭትና የተፈጸመው ግድያ፣ በጸጥታ ኃይሉ ስሕተት የደረሰ ነው፤ ያሉት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ረዳት፣ ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ፣ ለጠፋው የዜጎች ሕይወት እና ለወደመው ንብረት ወቀሱት፡፡
የቃና ዘገሊላ በዓል፣ እንደ በዓለ ጥምቀት ኹሉ በሥርዐቱ እየተከበረ በሰላም ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ሰዓት የመጣው የጸጥታ ኃይል “ያልተጠራ” እንደነበር የጠቀሱት ብፁዕነታቸው፣ ከመጣ ችግር እንደሚፈጠር ስለታመነ እንዳይመጣ ሊቀ ጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ቀድመው አሳስበው እንደነበር አውስተዋል፡፡
his-grace-abune-qerlos
ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ፤ የሰሜን ወሎ እና ዋግ ኽምራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
ለበዓሉ አከባበር፣ ሀገረ ስብከቱ ከዞኑ ሓላፊዎች ጋራ እየተናበበ በመሥራቱ የተጠየቀ ተጨማሪ ኃይል እንዳልነበርና “እነርሱ አይምጡ፤ እኛው በእኛው ፕሮግራማችንን እንመራለን፤” በማለት ቀድሞ እንዳሳወቀ ብፁዕነታቸው ጠቁመዋል፡፡
ይኹንና በመምጣታቸው ወጣቱን ለተቃውሞ እንዳነሣሡ ተናግረዋል፤ “ወጣቱን አሳበዱት፤ የተሳደበም ይመስለኛል፤ ድንጋይም ሳይወረውር አይቀርም፤ በጥይት ለቀሙት፤” በማለት የርምጃውን ኢፍትሐዊነት አስረድተዋል፡፡ በማግሥቱም ቀጥሎ የነበረው ግጭትና የንብረት ውድመት መንሥኤ የጸጥታ ኃይሉ እንደኾነ የተናገሩት ብፁዕነታቸው፣ “የእነርሱ መዘዝ ነው፤ እኛ ወጣቱ አበላሸ የምንለው ምንም ነገር የለም፤” ሲሉ ድርጊቱን ኮንነዋል፡፡
በሞትና መቁሰል ስለደረሰው ጉዳትም፣ “ብዙ ሰው ነው የተጎዳብን፤ ያላወቅነውም ይኖራል፤” ብለዋል ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ፡፡ ግጭቱ በተከሠተበት ወቅት ከመርሳ ከተማ ወደ ወልዲያ ተመልሰው በዚያው አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ለማስተማር በዝግጅት ላይ እንደነበሩ ገልጸው፣ የጸጥታ ኃይሎቹ ለብተና በተጠቀሙበት አስለቃሽ ጢስ ታቦቱን ያከበሩት ካህናት፣ “በጎናቸው ባሉ ካህናት ተገድፈው ነው እንጅ ወድቀዋል፤” ብለዋል ጥልቅ ቅሬታ በሚደመጥበት አነጋገር፡፡
የጸጥታ ኃይሉን ለምን ማሠማራት እንዳስፈለገ እንደማያውቁ ብፁዕነታቸው ጠቅሰው፣ ኾነ ተብሎ የታቀደ እንደሚመስላቸው ሳይገልጹ አላለፉም – “ለምን እንደመጡ አናውቅም፤ ኾን ብለው ለመምታት ይመስላል፤ ከራሳቸው መካከልም የሚያጠፋ ያለ ይመስለኛል፤” ብለዋል፡፡ አያይዘውም፣ “ወጣቱን ሌላ የፖሊቲካ አካል ቀሰቀሰው ይባል፤ እነርሱን ወታደሮቹን ማን ነው የቀሰቀሳቸው? ሰላም እንዳይኾን!” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ከክልሉ ርእሰ መስተዳድር ጋራ በኹለት ዙሮች በተካሔደው ውይይት፣ ወጣቱ በአጠፌታ ተሠማርቶበት ከነበረው የንብረት ማቃጠልና ማውደም አረጋግተው ወደ አዳራሽ እንዲገባ በማድረግ ከሌሎች የሃይማኖት አባቶች እና የአገር ሽማግሌዎች ጋራ የተሳካ ሥራ እንደሠሩ ብፁዕነታቸው ይገልጻሉ፡፡ ቀደም ሲል ከእግር ኳስ ጨዋታ ጋራ ተያይዞ ተከሥቶ በነበረው የከተማዋ ግጭት በተለይ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን የማረጋጋት አባታዊ ሚና እንደነበራቸው በማውሳት፣ “ቤተ ክርስቲያኗን ወጣቱ ሰምቶልናል፤” ሲሉ አመስግነዋል፡፡
ባለፈው ሰኞ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር በተገኙበት በተደረገው ውይይት፣ የመንግሥት ጥፋት በግልጽና በዝርዝር መቅረቡን፤ ለከተማው ሰላምና ጸጥታ በሚረዱ አጠቃላይ መፍትሔዎች ላይም ስምምነት እንደተደረሰ አስታውቀዋል፡፡ ሠራዊቱን ከከተማው እንደሚያስወጡ ርእሰ መስተዳድሩ የገለጹ ሲኾን፣ ለሰላሙና ጸጥታው ወጣቱ ከፖሊስ ተባብሮ እንደሚሠራም አረጋግጧል፡፡ ርእሰ መስተዳድሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ “ስለተፈጸመው ነገር የሚያጣራ አካል እልካለሁ፤ አጥፊው ለሕግ ይቀርባል፤ ለእናንተም ይፋ አደርጋለሁ፤” ማለታቸው ታውቋል፡፡
ከውይይቱ በኋላ አቶ ገዱ፣ ሐዘንተኞችን በየቤታቸው ተገኝተው በማጽናናታቸው ያመሰገኑት ብፁዕነታቸው፣ በቤተ ክርስቲያንም በኩል ካህናትን መድቦ ወጣቱ በሰላም ወደየቤቱ እንዲገባ ከማድረግ ባሻገር፣ እስከ ትላንት ድረስ ሐዘንተኞችን ሲያጽናኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡ በአኹኑ ወቅትም በክልሉ መንግሥት ተሠይሞ ከተላከው ልኡካን ቡድን ጋራ፣ እርሳቸውን ጨምሮ የከተማው የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች የተካተቱበት ምክክር እየተካሔደ እንዳለ አስታውቀዋል፡፡
እየተከሠተ ያለው የግፍና የጥፋት ድርጊት፣ ሕዝብን ከሕዝብ እያለያየ መኾኑ በእጅጉ እንደሚያሳዝናቸው ብፁዕነታቸው ተናግረዋል፡፡ “ተዉ ማለት ያለበት፣ ይህን ማስተካከልና መሥመር ማስያዝ ያለበት መንፈሳዊ አባት ነው፤” ሲሉ ቤተ ክርስቲያን ጥፋትን የመከላከል፣ አጥፊውን የማውገዝና የመገሠጽ፣ የተበደለው እንዲካስና እንዲጽናና የማድረግ በአጠቃላይ የአገርን ሰላምና የሕዝብን አንድነት የማስጠበቅ ከባድ መንፈሳዊና ታሪካዊ ሓላፊነት እንዳለባት አመልክተዋል፡፡
አባቶችና መንበረ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ክብር በመዳፈርና ሥርዐቷን በመጣስ ጭምር ስለተፈጸመው የወልዲያው ግፍ፣ አቋማቸውን እንዲያሳውቁና ኖላዊነታቸውን እንዲያረጋግጡ በብዙኃን መገናኛዎችና በመግለጫዎች የሚሰነዘሩት ጥያቄዎችና ወቀሳዎች እንደቀጠሉ ናቸው፡፡
መኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች፣ ከትላንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የጥምቀት እና የቃና ዘገሊላ በዓልን ለማክበር በወጡ የወልዲያ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የተፈጸመውን ግድያ የተመለከተችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ድርጊቱን አለማውገዟ ያስተዛዝበናል፤ ብለዋል፡፡
ለተነሣው ግጭትና ለተወሰደው የግድያ ርምጃ የቀረበው ምክንያት፣ “መንግሥትን የሚቃወም ዜማ አሰማችሁ፤” የሚል እንደኾነ በመግለጫቸው የጠቀሱት ፓርቲዎቹ፣ “ይህ ደግሞ መብት መጣስ ነው፤” ብለዋል፡፡
አክለውም፣ “የጸጥታ ኃይሎች ቅዱስ ታቦትን ባከበሩ ቀሳውስት ላይ አስለቃሽ ጭስ መተኮሳቸው ሃይማኖቱን መዳፈር በመኾኑ መንግሥት ድርጊቱን በማውገዝ የእምነቱን ተከታዮች በዐደባባይ ይቅርታ ይጠይቅ፤ ለሟች ቤተ ሰዎች የደም ካሳ እንዲከፍል፤ ግድያው እንዲፈጸም ትእዛዝ የሰጡም ኾነ ጉዳዩን በቸልተኝነት የተመለከቱ የዞኑ ባለሥልጣናት በሕግ እንዲጠየቁ፤ ግድያውን የፈጸሙ የመንግሥት ታጣቂዎች ለሕግ እንዲቀርቡ እንጠይቃለን፤” ሲሉ አቋማቸውን አስታውቀዋል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤን በመወከል በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ርእሰ መንበርነት አመራር የሚሰጠው ቋሚ ሲኖዶስ፣ ከልደት ጀምሮ በነበሩት ዐበይት ክብረ በዓላት ሳቢያ የተመደቡት ተለዋጭ አባላቱ ብፁዓን አባቶች በየአህጉረ ስብከታቸው በመኾናቸው አለመሰብሰቡ ተጠቁሟል፡፡ ሰሞኑን እስከ ግንቦቱ የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ድረስ በተለዋጭነት በተመደቡት አራት ብፁዓን አባቶች አባላቱ በሚቀጥለው ሳምንታዊ መደበኛ ስብሰባው፣ ጉዳዩን ይመለከተው እንደኾነም ለማረጋገጥ አልተቻለም፡፡
ምንጭ፦ ሐራ ዘተዋሕዶ
President’s office requests list of convicted, charged political party leaders
By Tamiru Tsige

Photo: The governor EPRDF Chairmen’s
The Office of the President requested the Federal Prisons Administration and the Federal Attorney General respectively to provide it with a list of political party members and leaders who are eligible for pardon as well as political party leaders and members currently on trial, The Reporter learnt.
According to sources close to the matter, the President’s Office is due to receive the lists within two days.
It is to be remembered that, in a joint briefing they gave to the Ethiopian Broadcasting Corporation (EBC) and Ethiopian News Agency (ENA) yesterday, the leadership of the four member parties of the EPRDF announced that opposition party members and leaders will be released and that charges against those undergoing trial will be withdrawn.
The infamous detention and investigation center also known as “Maekelawi” was also said to be closed and converted to a modern museum.
Source: Reporter
ፍርድ ቤቱ ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጣ
በጌታቸው ሺፈራው
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእስር ላይ የምትገኘው ጫልቱ ታከለን በገንዘብ ቀጥቷል። በእነ ደቻሳ ሞሲሳ የክስ መዝገብ 4 ተከሳሽ ጫልቱ ታከለ “እናንተ ኢህአዴግ ናችሁ፣ ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አልጠብቅም” ብላ ተናግራለች በሚል በችሎት መድፈር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።

ፎቶ፡- ጫልቱ ታከለ
ህዳር 28 ቀን 2010 ዓም እነ ደቻሳ ሞሲሳ ተከላከሉ የሚል ብይን በተሰጠባቸው ወቅት 3ኛ ተከሳሽ የሆነችው ጫልቱ በሰነድ ማስረጃነት የቀረበባት የደህንነት ሪፖርት ወደ ኤርትራ ስለመሄድ የጠቀሰው ነገር ሳይኖር ብይን ላይ ወደ ኤርትራ ልትሄድ እንደነበር ተጠቅሶ ተከላከይ መባሏ እንዳሳዘናት ገልፃለች።
ጫልቱ ታከለ በወቅቱ “ከኢህአዴግ ፍርድ ቤት ምንም አንጠብቅም። ወደፊትም ፍትህ እንደማናገኝ ነው የምናስበው።” ብላ በመናገሯ በችሎት መድፈር ጥፋተኛ ተብላ በአዳር ዛሬ ህዳር 29 ቀን 2010ዓ.ም. የ500 ብር የገንዘብ ቅጣት ተጥሎባታል።
ጫልቱ ታከለ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ክስ ተፈርዶባት ፍርዷን ጨርሳ እንደወጣች ተገልጿል።
የፖለቲካ እስረኞች በኢትዮጵያ እየተፈፀመባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትን አስመልክቶ የድረሱልን ጥሪ አቀረቡ
በመቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ ላይ ያሉ 38ቱ ተከሳሾች አቤቱታ
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን(ኢሰመኮ) ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!

ፎቶ፡- ማስረሻ ሰጤ
~ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የተሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።
~አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።
እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተከሰን በነበርንበት ክስ የዋስትና መብተችንን ተከልክለን እንደማንኛውም እስረኛ ክሳችንን በቀጠሮ እየተከታተልን ሳለን ነሃሴ 28/ 2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ውስጥ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ ምክንያት “ሊያመልጡ ሞክረዋል!” በሚል ሰበብ፣ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ የመብት ጥያቄ የሚጠይቁ ወንድሞቻችን (ጓደኞቻችንን) እኛ ፊት በጥይት ገድለው እሳት ውስጥ ጨምረው አቃጥለዋቸዋል።
እንዲህ ያለ አረመኔያዊ ድርጊት ከፈፀሙ በኋላ ገና ለገና ይህንን እውነት ያጋልጡብናል ብለው በመስጋት እኛን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት በመውሰድ ለ3ወራት ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ በማፈን፣ ለምርመራ በሚል ሰበብ በዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ በሚመራው ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሰማዕታት ሙዝዬም ውስጥ ሀውልት የተሰራለት የ”ቶርች” ገረፋ ተፈፅሞብናል።
በካቴና ታስረን፣ ተሰቅለን ተገርፈናል። ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። በኤሌክትሪክ ሾክ ተደርገናል። በሚስማር ውስጥ እግራችንና ጀርባችን ተበሳስቷል። ጭንቅላታችንን በሰደፍ ፈንክተውናል። የተወሰንን ታራሚዎች ተለይተን ብልታችን ላይ ሁለት ሊትር ሀይላንድ ውሃ ተንጠልጥሎብናል። ሌሎችም ተዘርዝረው የማያልቁ ብዙ በደሎች ተፈፅመውብናል።
ይህ የደረሰብን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ታህሳስ 14/2009 ዓ•ም ለፍርድ ቤት በማሳየትና በማስረዳት ፎቶ መነሳት አለብን ብንልም ፍርድ ቤቱ ጥያቄያችን ሊቀበለን አልቻለም። ወደ ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ስንመለስ ደግሞ “ፍርድ ቤት ሄዳችሁ ብትለፈልፉ ምንም አታመጡም!” በማለት እስከ መጋቢት 12/2009 ዓ•ም ድረሰ ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ውስጥ ከተው የቤተሰብ ግንኙነት ከልክለውን በፀሀይ ብርሃን እጦት መልካችን ቢጫ እስኪሆንና አይናችን ብርሃን ማየት እስኪያቅተው ድረስ ተቆልፎብን ተሰቃይተናል።
እንደዚህ አይነት ግፍ የተፈፀመብን በወቅቱ የነበሩ በጣት የሚቆጠሩ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችን ከተጠያቂነት ለማዳን በጣም ደካማ አስተሳሰብ ያላቸው የመንግስት ኃላፊዎች እኛን የፖለቲካ መልስ ለማድረግ የወሰኑት ውሳኔ ነው። ህሊናቸውን ሸጠው በእኛ በንፁሃን ላይ እንዲህ አይነት ስቃይ የፈፀሙብን፣ ያስፈፀሙብን እንዲሁም ሀሳት የተቀነባበረ ክሰ የከሰሱን።
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት የኮምሽኑ መርማሪዎች ከ10 ወራት ቆይታ በኋላም ቢሆን በአይናቸው ያዩትን እውነት በዝርዝር በሪፖርት ለፍርድ ቤት አቅርበዋል። ፍርድ ቤቱም ሰብአዊ መብት ኮምሽን ሪፖርት ላይ ብይን ለመስጠት ለህዳር 29/ 2010 ዓ•ም ቀጠሮ ይዟል።
#የኢትዮጵያሰብአዊመብትኮምሽን ስላቀረበው ሪፖርት ያለን አስተያየት:_
1) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን (ኢሰመኮ) የተፈፀመብንን ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ሙሉ ለሙሉ አላካተተም።
2)የኢሰመኮ ኢ _ሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ በማለት ቁርጥ ያለ ሪፖርት ማቅረብ ሲገባው እና የኮምሽን መስርያ ቤቱ ጉዳዩን ተከታትሎ በዜጎች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት ያደረሱ አካላት በሕግ ማስቀጣት ሲገባው ምክረ ሀሳብ በማለት የተለሳለሰ የፍራቻ የሚመስል ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል። መስርያ ቤቱ እውነቱን እያወቀ እንዲህ ያለ ሪፖርት በማቅረቡ ምን ያህል የደህንነት ቢሮ ተፅዕኖ እንዳለበት እና በራስ መተማመን የጎደለው መስርያ ቤት መሆኑን የሚያሳይ ነው።
3) ኢሰመኮ በእኛ ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙ አካላትን እንዲመረምር ወይም እንዲያጣራ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽንና ለህክምና ቡድን አባላት በመፃፉ ቅር ተሰኝተናል። ምክንያቱም ኢ_ሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ነው። ውሻ ነከሰን ብለን ለጅብ እንድንናገር መደረግ የለበትም።
4) ኢሰመኮ በዚህ መልክም (በጥቂቱም) ቢሆን የተፈፀመብንን ግፍ በሪፖርት በማቅረቡ ምስጋና እናቀርባለን። ምክንያቱም ምን ያህል ተገደን ለፖሊስ ቃል እንደሰጠንና ለዶክመንተሪ ፊልማቸው በቪዲዮ እንደተቀረፅን የሚያሳይ ነው። በፍርድ ቤቱም በ27(2) ቃላችን ውድቅ እንዲደረግ የሚጠቅመን የሰነድ ማድረጃ በመሆኑ ነው።
#የህዝብተወካዮች ምክር ቤት እና የፌደራል ማረሚ ያ ቤቶች ላይ ያለን አስተያየት:-
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ነን፣ ለምርመራ ነው የመጣነው ብለው በግልና በጋራ አናግረው መርምረው ምንም አይነት መፍትሄ አልሰጡንም። ምንም አይነት ሪፖርትም አላቅረቡም። በዚህም በጣም ቅር ተሰኝተናል። እንዲህ ነው እንጅ የህዝብ ተወካይ መሆን፤
1) የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር እውነቱን እያወቀ፣ እኛ እንድንከሰስ በማቀነባበር፣ በህግ ጥላ ስር እያለን ወደ ሸዋሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን ያ ሁሉ ኢሰብአዊ ድርጊት እንዲፈፀምብን ማድረጉ፣
~ በማረሚያ ቤቱ ውስጥ ያሉ እስረኞችን በማስፈራራትና በማባበል ወደ ቃሊቲ ማረሚያ ቤት በመውሰድ በእኛ ላይ እንዲመሰክሩብን በማድረጉ፣
~መርማሪዎች ነን ከሚሉ አካላት ጋር በመተባበር እኛን በመደብደብና በማስደብደብ ጨለማ ቤት አስገብቶ፣ ቤተሰብ ግንኙነት ከልክሎ በማሰቃየት በተፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት ቅር ተሰኝተናል።
2) በዚህ ኢትዮጵያዊነት በጎደለው በዘራችንና በሀይማኖታችን ተመርጠን፣ በሀሰት ተከሰን ለአመታት እንዲህ ያለ ስቃይ እንድንሰቃይ መደረጋችን ታሪክ የማይሽረው ጠባሳ በልባችን ላይ ጥላችሁብናል። የሞቱት ጓደኞቻችን! ገዳይ እናንተ! በሀሰት ተከሰን የምንሰቃየው እኛ! ፈጣሪን አትፈሩም? ግፍ አይደለም? ነገ በልጆቻችሁ አይደርስም? ከትግራይ ተወላጆች ውጭ ሌላው ዘር ጠላት ነው? ያሳዝናል!
3) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከትግሬ ውጭ ሌላ አመራር የለም። አንድም የተማረ ወይም የበሰለ አስተዳደር የለም። ተናዳጅ፣ ተቆጭ፣ መሃይሞች ብቻ ናቸው። አብዛኛዎቹ ታጋይ የነበሩና በዘረኝነት ያበዱ ከትግሬ ውጭ ሌላው ዘር ሰው የማይመስላቸው ያልሰለጡ ናቸው። ይህ ደግሞ ለጭካኔና አረሜኔያዊ ተግባር ለመፈፀም አግዟቸዋል። ለዚህ ነው ፍርድ ቤት ሄደን ስንናገር የምንደበደበው። ጨለማ ቤት የምንገባው ማገናዘብ በማይችሉ አመራሮች ስለምንመራ ነው።
ቂሊንጦ ማረፊያ የሆኑት ዋና ሱፐር ኢንተንደንት አሰፋ ኪዳነ ቃጠሎው ሲደርስ ዝዋይ ማረሚያ ቤት ነበርኩ ብለው ተጠርጣሪዎች በቆይታቸው ምንም ጉዳት አልደረሰባቸውም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። ሰብአዊ መብት ኮምሽን መርማሪዎች የደረሰብንን ጉዳት እያወቀ! በምን አይነት ሰዎች እጅ ተይዘን እንዳለን ማሳያ ነው።
#በ19ኛወንጀልችሎት ዳኞች ላይ ያለን ቅሬታ
ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ዐቃቤ ሕግ ምስክሮችን እንዲያሰማ ቀጠሮ የተያዘ ቢሆንም ሌሎች መዝገቦችን በተደራቢ በመስራት በጠዋቱ ፕሮግራም ላይ ዳኞች ከ4 ሰዓት በፊት ባለመግባት ጉዳያችን ተጓትቶብናል።
ይህ ሳያንስ ቀሪ የዐቃቤ ህግ ምስክሮችን ለመስማት በሚል ነሃዴ 12/2009 ዓም፣ ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3 /2010 ዓም ድረስ የግማሽ አመት ቀጠሮ ተቀጥሮብናል። በዚህም ቅር ተሰኝተናል። “የዘገየ ፍትህ እንደተከለከለ ይቆጠራል” የሚለውን መርህ የጣሰ ተግባር ነው።
2) በፍርድ ቤቱ ውስጥ ለሟች ቤተሰቦች፣ ለእኛ ቤተሰቦችና የእኛን ጉዳይ መከታታል እና መታዘብ ለሚፈልጉ የትኛውም ወገኖች በችሎት ውስጥ በቂ የመቀመጫ ወንበር አለመኖር፣ የችሎት መጥበብ፣ በምስክር አሰጣጥ ወቅት ዳኞች ገለልተኛ አለመሆን ቅር አሰኝቶናል።
#ለኢትዮጵያሕዝብና #ለዓለምአቀፍ ማህበረሰብ የምናቀርበው የድረሱልን ጥሪ!
1) ይህ ክስ ባለቤት አለው። ክሱ ለባለቤቶቹ ይሰጥ! ክሱ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎችና ፖሊሶች ነው።
2) ኢትዮጵያ ውስጥ እውነት መንግስትና ሕግ ካለ በእኛ ላይ የቀረበው ክስ ሊቋረጥ ይገባዋል። የምናውቀው ብዙ ሚስጥር አለን። ከፍተኛ የመንግስት አካላት መጥተው ሊነጋግሩን ይገባል።
3) የብሔራዊ ደህንነት ስብሰባ ላይ በቴሌቪዝን ያየነው ዋና ኢንስፔክተር አለማየሁ ኃይሉ የተባለው የማዕከላዊ መርማሪ ፖሊስ የሚመራው ቡድን ለፈፀመብንና ላስፈፀመብን ኢሰብአዊ ድርጊት በህግ ይጠየቅልን።
4) ኢሰመኮ ያቀረበውን ሪፖርት አያይዘን ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጀኔባ ለመክሰስ የተገደድን ስለሆነ ስለ ሰዎች መብትና ነፃነት የሚያስብ፣ የሚቆረቆር ግለሰብም ሆነ ተቋም ፣ የማንኛውም ሀገር ዜጋ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላትን በህግ እንድንፋረዳቸው እንድትረዱን፣ ለዓለም ህዝብ እንድታደርሱልን ጥሪ እናቀርባለን!
5) ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ የሚያሰማቸውን የሀሰት ምስክሮችና የሀሰት ሁኔታ እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።
6) በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ቃጠሎ ምክንያት ከእኛ ከ38ቱ ተከሳሾች ውጭ 121 ተጠርጣሪዎች በዚሁ ወንጀል ከ20 እስከ 25 ተከፋፍለው በሌላ መዝገብ መከሰሳቸው ይተወቃል። ከእነሱ ውስጥ አርማዬ ዋቄ በማረሚያ ቤት ፖሊሶች ተደብድቦ የተገደለ በመሆኑ ጉዳዩ በሕግ ተይዞ እየተመረመረ ይገኛል። ሌሎቻችን ሰውነታችን በድብደባ በልዞ፣ ዝለን፣ ከነገ ዛሬ ገደሉን እያለን ስጋት ላይ ስለሆንን ይህ ግፍ እንዲቆም እንጠይቃለን።
#ለዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮምሽን
#ጀኔባ
እኛ 38ቱ ተከሳሾች ቀድሞ ተጠርጥረን በታሰርንበት ክስ የዋስትና መብታችን ተከልክለን ክሳችን በመከታተል ላይ እያለን ነሃሴ 28/2008 ዓ•ም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በደረሰበት የእሳት ቃጠሎ ሊያመልጡ ሞክረዋል በሚል ምክንያት በእስር ቤት ውስጥ የመብት ጥያቄ ይጠይቁ የነበሩ በርካታ ወንድሞቻችን ተነጥለው በማረሚያ ቤተ ፖሊሶች በጥይት እኛ ፊት ተገድለውብናል። ይህ ሳያንሳቸው ራሳቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን እኛ ለምርመራ በሚል ሰበብ ወደ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደን በዘራችን ብቻ ተመርጠን የአማራ፣ የኦሮሞና የጉራጌ ተወላጆች ብቻ ከፍተኛ የሆነ ኢሰብአዊ ድርጊት ተፈፅሞብናል።
ጥፍራችን በፒንሳ ተነቅሏል። ኢትዮጵያ ውስጥ አይደገምም ተብሎ ሀውልት የየሰራለት የቶርች ገረፋ ተፈፅሞብናል። ንብረታችንን ዘርፈውናል። ህክምና ተከልክለናል። ለነርቭ፣ ስነ ልቦና እና ለተለያዩ በሽታዎችና ቀውስ ተዳርገናል። ይህንን የደረሰብንን በደል ለፍርድ ቤት በመናገራችን ለ3 ወራት ጨለማ ቤት ከተውን ቤተሰቦቻችን እንዳናገኝ ተከልክለን ሕገ መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል።
አማራና ጉራጌ ግንቦት ሰባት፣ ኦሮሞን ኦነግ፣ ሙስሊሞችን አልሻባብ በማለት መብታችን ተረግጧል። ይህን ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጥቅምት 20/2010 መርምሬ አረጋግጫለሁ ባለው ሪፖርት ላይ በመጠኑም ቢሆን ተፈፀመብንን ኢ ሰብአዊ ድርጊት አቅርቧል። በእኛ በተከሳሾች ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን ምርመራ እንዲያካሂድ ግልባጭ የተላከለት ቢሆንም እስካሁን ድረስ ቀርቦ ያናገረን አካል የለም። ይህም በመሆኑ የሰዎችን መብት ለማስጠበቅ ኃላፊነት ላለበት ዓለም አቀፈ የሰብአዊ መብት ኮምሽን ለማመልከት ተገደናል።
1)አሁንም የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ከፍተኛ የሆነ ድብደባ፣ ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰብን ስለሆነ፣ አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ ነው። በዚሁ በቃጠሎ ምክንያት በሌላ መዝገብ ከተከሰሱ ወንድሞቻችን ውስጥ አርማዬ ዋቄ የተባለ ተከሳሽ በማረሚያ ቤት ፖሊስ ተደብድቦ ተገድሎ ቤተሰቦቹ በክስ ላይ ይገኛሉ
2) ከነሃሴ 1 እስከ 12/2009 ዓ•ም ድረስ ዐቃቤ ሕግ በሀሰት ያሰለጠናቸውን ምሰረክሮች ያሰማ ሲሆን ቀሪ ምስክሮችን ለማሰማት በሚል ከታህሳስ 23 እስከ ጥር 3/2010ዓ•ም በተከታታይ ቀናት ተቀጥረናል። እስካሁንም ፍርድ ቤት ቀርበው የመሰከሩ ምስክሮች በተፅዕኖ ስር ሆነው ዐቃቤ ሕግ ባሰለጠናቸው መሰረት የመሰከሩ ናቸው። ቀሪ ምስክሮችም እንደ ቀድሞ ምስክሮች የታሰሩና በተፅዕኖ ስር ሆነው የሚመሰክሩ ናቸው። አንዳንድ በዋስት እና በነፃ የተፈቱ ምስክሮችን በዐቃቤ ሕግና ፖሊስ “እኛ በምንላችሁ መሰረት ነው የምትመሰክሩት” እየተባሉ ፣”ይህን ካደረጋችሁ ከቀድሞ ክሳችሁ ነፃ ትባላላችሁ” እያሉ በመደለል እንዲሁም፣ የተለያየ ማስፈራሪያና ዛቻ እየደረሰባቸው እንደሆነ አረጋግጠናል። ይህንን በተፅዕኖና ምስክሮችን በማስገደድ የሚደረግ አመሰካከር እንድትታዘቡልን ጥሪ እናቀርባለን።
3) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ባቀረበው ሪፖርት መሰረት በእኛ በተከሳሾች ላይ ኢሰብአዊ ድርጊት የፈፀሙብን አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ግፊት እንድታደርጉልን እንጠይቃለን። ነገር ግን ኢሰብአዊ ድርጊት ከፈፀሙብን አንዱ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን በመሆኑ በሌላ ገለልተኛ ወገን ምርመራው እንዲካሄድ እንጠይቃለን።
4) ኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ ኤምባሲዎች ይህንን በሀገራችን እየተፈፀመብን ያለውን ኢሰብአዊ ድርጊት እንድትቃወሙልንና አሁንም ህይወታችን አደጋ ላይ በመሆኑ የድረሱልን ጥሪ እናቀርባለን።
5) የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ምርመራ አረጋግጫለሁ ብሎ ባቀረበው ሪፖርት ላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የፈፀሙ አካላት በሕግ እንዲጠየቁ ማድረግ ሲገባው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮምሽን የወንጀል ምርመራ ክፍልና የህክምና ባለሙያዎች አስፈላጊ ምርመራ በማድረግ ውጤቱን ለሚመለከተው አካል አስተላልፈው የተደረሰበትን ድምዳሜ ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን እንዲያቀርቡ ምክረ ሀሰብ ቀርቧል በማለት ያቀረበው ሪፖርት ላይ በጣም ቅር ተሰኝተናል።
ምክንያቱም በሕግ ሊጠየቁ የሚገባቸው አካላት በሕግ ሊጠየቁ ይገበል ማለት ሲገባው፣ ጉዳዩን ተከታትሎ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ሲገባው በጣም ተለሳልሶ የፍራቻ የሚመስል መደምደሚያ ሪፖርት በማቅረቡ ቅር ተሰኝተናል።
#ግልባጭ:_
#ለአፍሪካ ህብረት
#ለአሜሪካ፣ ለብሪታኒያ፣ ስውይድን፣ ካናዳ፣ ኖርዎይ ኤምባሲዎች
#ለማህበራዊ ሚዲያ፣ ለራዲዮ ጣቢያዎች፣ ኢቢሲና ሌሎች ሚዲያዎች ይድረስልን
#ወደእንግሊዝኛና አረብኝ ተተርጉሙ ለዓለም ህዝብ ይድረስልን