የ‹‹ደሃው›› አቶ መለስ 3 ቢሊዮን ዶላር የት ነው?
ቴዎድሮስ ባልቻ
አቶ መለስ ዜናዊ የእረፍታቸው ዜና ከተነገረ በኋላ በህይወት ሳሉ የሌላቸውን ባህርይ ሳይቀር በመግለፅ ደጋፊዎቻቸው ጣዖት ማምለክ እስኪመስል ድረስ እንዲመለኩ ይፈልጋሉ፡፡ እውነታው ግን አቶ መለስ የኢህአዴግ ደጋፊዎች የሚያወሩላቸውን ያህል ግለሰብ ስላለመሆናቸው የማይረሱ በርካታ ስራዎቻቸው ይናገራሉ፡፡ ይህ ማለት ግን አንዳችም ጥሩ ስራ የላቸውም ማለት ሳይሆን በንፅፅር ሲቀርብ ግን ጥሩ መሪ ነበሩ ማለት በገለልተኛ አካላት ሰፊ ጥናት መደረግ ያስፈልገዋል፡፡
አመራሮቹማ ከቤተ መንግስት እስከ ገጠር ቀበሌ የእሳቸውን ሞት ተከትሎ ምስላቸውን የያዙ ፖስተሮች መለጠፋቸው ሰውየውን ‹‹ቅዱስ›› ለማስመሰል ከመሞከር ባለፈ ለፖለቲካ ትርፍ እየተጠቀሙባቸው መሆኑን ያሳብቃል፡፡ ይህንን ለማርከስም ሆነ ህዝቡ ስለ እሳቸው ትክክለኛ ማንነት እንዲያውቅ አማራጭ የሀገር ውስጥ ነፃ ሚዲያ ያለመኖር በመጋረጃ ውስጥ ያሉት መለስ ተዘንግተዋል፡፡ ለዚህም በሀገሪቱ ስለሳቸው ትክክለኛ ማንነት የተወሰኑ ተግባራቸው የአደባባይ ምስጢር ቢሆንም እሳቸው ከሚያደንቋቸው የውጭ ሚዲያ መዳሰሱ የተሻለ ሳይሆን አይቀርም፡፡
በቅርቡ የዓለም መሪዎችንና ባለሃብቶችን ሃብትና የግል ታሪክ በማስነበብ የሚታወቀው ድህረ ገፅ ስለእሳቸው በአጭሩ ያስቀመጠውን እንመልከት፡፡ የመረጃው መረብ ሰውዬውን ከልደት ዘመን እስከሞታቸው ከመግለፁ በተጨማሪ አንድ አስደንጋጭ (ለኢህኢዴግዎች) መረጃም አክሎበታል፡፡ ይህም ያላቸውን የሃብት መጠን ከዓለም ጠቅላይ ሚኒስትሮች መካከከል ከጣሊያኑ ጠቅላይ ሚኒስትርና የታወቁ ባለሃብት ከሆኑት ሲልቪዮ በርሎስኮኒ በመቀጠል በ3 ቢሊዮን ደላር (56 ቢሊዮን ብር ገደማ) 2ኛ ደረጃን እንደያዙ www. therichest.org በግልፅ ተቀምጧል፡፡ ለዚህም http://www.therichest.org/celebnetworth/politician/minister/meles-zenawi-net-worth/ መጎብኘት ይቻላል፡፡
በተለይ ነገሩን አስደንጋጭና አሳፋሪ የሚያደርገው በህይወት ያሉት ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን በባህርዳሩ የኢህአዴግ ጉባዔ ሳይጠየቁ የአቶ መለስን ድህነት ሲናገሩ ነበርና፡፡ ያኔ ባለቤታቸው ከመንግስት መደበኛ 6 ሺህ ብር ደመወዛቸው ላይ ተቆራርጦ 4 ሺህ ብር ያህል እንደሚደርሳቸውና በዚህም ይተዳደሩ እንደነበር መግለጣቸው አይዘነጋም፡፡ በርግጥ ያኔ ባለቤታቸው የተናገሩትን ህዝቡ ተቀብሏቸዋል ለማለት ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም 21 ዓመታትን ሙሉ ያለመላከ ሞት ከቤተመንግስት አልወጣም ብለው የመሸጉትን የህዝብና የሀገርና የወገን ፍቅር ኖሯቸው እንዳልነበረ እንቅስቃሴያቸው ያሳብቅ ነበርና፡፡
‹‹ደሃው ›› አቶ መለስ
ዛሬ እንደጣዖት ፎቶአቸውን በየቦታው ተለጥፎ የምናገኛቸው አቶ መለስ ዝናዊ ምናልባት በመሪ አስተሳሰብ ካልሆነ በቀር በገንዘብ በኩል ደሃ ነበሩ ለማለት ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያን ያለባህርበር ከማስቀረት አልፈው በታሪክ የኢትዮጵያ እንደሆነ የሚታወቀውን አሰብ ወደብንና አካባቢውን ትውልዱ ያንን እንዳያስብ በማድረግ ሽንጣቸውን ገትረው ሲከራከሩ ተስተውለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ስንቶች የሞቱለትን የሀገሪቱን ሰንደቅዓላማ ‹‹ጨርቅ ነው›› ብለው አራክሰዋል፡፡ የአክሱም ሐውልት ለወላይታ ምኑ ነው ሲሉም ከመናገር ያለፈ የአስተሳሰብ ድህነት የለም፡፡
እሳቸውም በአንድ ወቅት በቴሌቪዥን መስኮት ቀርበው እንደድሮ (ጫካ ሳሉ) እንደማይርባቸውና የቆሸሸ እንደማይለብሱ ከማስታወስ ውጭ በገንዘብ በኩል ያኔ ደሃ እንደነበሩ ተናግረዋል፡፡ እውነታው ግን ያ ስለመሆኑ ህዝቡ መርምሮ እንዲያውቅ ዕድል አልሰጡትም፡፡ ዛሬ ግን ተከታዮቻቸው ከእራሳቸው አልፈው መላው ህዝብ ንፁህና ቅዱስ አድርጐ እንዲመለከታቸው በየመድረኩ የሚነገረው አሰልቺ ወሬ ገመናቸውን ሊደብቅ እንደማይችል የተረዱት አይመስልም፡፡
በተለይ በገንዘብ ደረጃ ምንም ያልነበራቸውና ይሄንንም ራሳቸው የተናገሩ ቢሆንም ስለ እሳቸው ዝርዝር የህይወት ታሪክ በግልፅ በማስቀመጥ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ መሆናቸውን ግን በህይወታቸውም ሆነ በሞታቸው አላስተባበሉም፡፡ ስለዚህ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ከሆነ በባዶ እጃቸው ጫካ ገብተው የወጡት አቶ መለስ ነግደው ሳያተርፉ ቢሊየነር ባለጠጋ የሆኑት ከህዝብ ሃብት ዘርፈው ካልሆነ ከየትም ሊያመጡ እንደማይችሉ እሙን ነው፡፡ ስለሆነም ሰውዬው ይወራ እንደነበረው ዓይነት እንዳልሆኑ ውሎ ሲያድር እየጠራ ነው፡፡
የግል ማኀደራቸው በአጭሩ
አቶ መለስ (ለገሰ) ዜናዊ በወርሃ ግንቦት 1947 ዓ.ም. በአድዋ ተወለዱ፡፡ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስም በአድዋ ንግስት ሳባ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲከታተሉ የሁለተኛ ደረጃን አዲስ አበባ በሚገኘው ጀነራል ዊንጌት ተከታትለው በመጨረስ የከፍተኛ ትምህርታቸውን በቀድሞ ቀዳማዊ ኃ/ስላሴ በአሁኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ገብተዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲው ከአንድ ዓመት ቆይታ በኋላ በሁለተኛው ዓመት አቋርጠው ወደጫካ ከመግባታቸው ውጭ በኢትዮጵያ ምንም ዓይነት የከፍተኛ ትምህርት ማጠናቀቃቸውን የሚገልፅ የምስክር ወረቀት የላቸውም፡፡
ነገር ግን የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በምን ዘርፍ፣ ከየትና መቼ እንዳገኙ የሚያሳይ ማስረጃ እስካሁን ባይገለፅም ከእንግሊዙ ኦፕን ዩኒቨርስቲ በህዝብ አስተዳደር ማስተርስ ዲግሪ ማግኘታቸው ተገልጧል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኔዘርላንድስ ሮተርዳም ከሚገኘው ኤራስመስ ዩኒቨርስቲ በኢኮኖሚክስ የማስተርስ ዲግሪ ባለቤት ከመሆን ውጭ በትምህርት ሌላ ደረጃ እንደሌላቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
አቶ መለስ ከወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር ጋብቻ በመመስረት ሰናይ፣ ሰመሃል እና ማርዳ የሚባሉ የሶስት ልጆች አባት እንደሆኑም በመካነ ድሩ የመረጃ መረብ ላይ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ በመጨረሻም ለ21 ዓመታት በስልጣን ላይ ከቆዩ በኋላ በተወለዱ 57 ዓመታቸው ነሐሴ 14 ቀን 2ዐዐ4 ዓ.ም (እንደ መንግስት ገለፃ) መሞታቸውን፤ የ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ እንደነበሩ ደግሞ http://www.therichest.org›› የተሰኘው ድህረ- ገጽ በግልፅ አስፍሯል፡፡
ሌላው ደቀመዝሙሩ ከመምህሩ እንደሚማር ሁሉ የታችኞቹ ሙሰኞች መሰረት የላይኞቹ ባለስልጣናት ልምድና ተሞክሮ መሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ‹‹ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን ውጭ ታሳድራለች›› እንዲሉ የታችኞቹ ሙሰኞች (ከቀበሌ እስከየ መስሪያ ቤቶች ባለስልጣን) ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስን እና መሰሎቻቸውን ፈለግ ተከትለው ባይተማመኑ እነ አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በቤታቸው የዶላርና የብር ክምችት ባልተገኘ ነበር፡፡
ስለዚህ በኢትዮጵያ ያለውን የሙስና ተግባር በእጅጉ ለመቀነስ ከተፈለገ ወኔውና ድፍረቱ ካላቸው አቶ ኃ/ማርያም ደሳለኝና የፌደራሉ የስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ምርመራ በ3 ቢሊዮን ዶላር ባለጠጋ እንደሆኑ ከተነገረላቸው ከቀድሞው የቤተመንግስት የስልጣን ባህታዊ ከሆኑት ሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ እና ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን እስከ ሚኒስትሮችና የጦር ጀነራሎች መዝለቁ የግድ ይላል፡፡
ከላይ የተጠቀሰው አቶ መለስ አላቸው ከተባለው 3 ቢሊዮን ዶላር ውጭ የሃብት ምንጫቸው ያልታወቁ ጊዜ አመጣሽ ከበርቴዎችን መዳሰሱ ያላቸውን ቁርጠኝነት ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡ በዚህም አለ የተባለው ሃበት እውነትነት መርምሮ ለህዝብ የማሳወቅም ግዴታ አለበት፡፡ ለዚህም ይረዳ ዘንድ በሀገሪቱ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ እና የፕሬስ ነፃነት በወረቀት በህገመንግስቱ ከማስፈር ውጭ በተግባር የሚረጋገጥ ከሆነ በርካታ የሙስና ተግባራትንና ብልሹ አሰራሮችን በማጋለጥ የኮሚሽኑንና የሌሎች የፍትህ ተቋማትን ስራ ያቀላል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ከመካላከያ ሚኒስቴር፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት (ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች)፣ የከተማ መስተዳድሮች ውስጥን ጨምሮ በተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ያሉ የብልሹ አሰራሮች ምን ያህል ለሙስና እንደተጋለጡም የፌዴራሉ ኦዲተር መስሪያ ቤት የመረጃ ዘገባዎችን /ሪፖርቶቹን / እንደግብዓት መጠቀም አስፈላጊ ቢሆንም እስካሁን በተግባር የታየ እርምጃ ግን የለም አለበለዚያ እንደ ዳዊት ‹‹ሙስና›› እያሉ መደጋገሙና ትናንሾቹ ላይ ብቻ ጃስ ማለት የህዝብን የትኩረት አቅጣጫ ከማስቀየር ባለፈ ለሀገርና ለህዝብ ሃብት ተቆርቋሪነትን አያሳይም፡፡
እሳቸውስ ሞቱ 3 ቢሊዮን ዶላሩስ?
በተለይ ወደ ፖለቲካው የሀገር አስተዳደርነት ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት የሳይንሱን ትምህርት በርቀት ሳይሆን በመደበኛ ተከታትለው የህግ ምሁሩና ድምፃዊ የነበሩት የኤሲ ሚላኑ እግርኳስ ክለብ ባለቤት ከሆኑት ከ76 ዓመቱ የጣሊያኑ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ሲልቪዮ በርሎስኮኒ የ6 ቢሊዮን ዶላር ባለቤት ቀጥለው ከጫካ በትጥቅ ትግል ወደ ስልጣን የወጡት አቶ መለስ በ3 ቢሊዮን ዶላር ሁለተኛነትን ይዘዋል፡፡ በመቀጠልም የሊባኖሱ የሐርቫርድና የቤሩት ዪኒቨርስቲ ምሩቅና ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው በፊት የተለያዩ ኩባንያዎች ባለቤት የሆኑት የ57 ዓመቱ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ነጂብ አዝሚ ሚካቲ በ 3 ቢሊዮን ዶላር 3ኛነትን ይዘው ይከተላሉ፡፡
አቶ መለስ ግን ከጫካ ወደ ፖለቲካ ስልጣን ከመውጣት ውጭ የተጠቀሰው ሃብታቸው ከየት መጣ? የሚል ጥያቄን ያጭራል፡፡ ምክንያቱም ህዝብ ከሚያውቀው እውነታ ውጭ እሳቸውም ምንም እንደሌላቸው ከመሞታቸው በፊት ተናግረዋልና፡፡ በጣም የሚገርመው የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ዊሊያም ዶናልድ ካሜሩን እንኳ ያላቸው ሃብት ሲታይ 6 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ብቻ እንደሆነ እና የዚህም ሃብታቸው ምንጭ ፖለቲካ እንደሆነ ድህረ-ገፁ ሲጠቁም የአቶ መለስ ዜናዊ 3 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ምንጭም ፖለቲካ እንደሆነ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ በዚህም ሟቹ አቶ መለስ ይህን ያህል ሃብት በፖለቲካ ስራ ባለቤት ከሆኑ የሌሎቹ ባለስልጣናት ቢጣራ ስንት ይሆን የሚል ጥያቄን ከማስነሳቱ በተጨማሪ ሀገሪቷ ምን ቀራት ያሰኛል፡፡
በርግጥ የአቶ መለስንና ባለቤታቸውን ከፍተኛ ባለጠግነትን (ቢሊየነርነትን) በተመለከተ ምስጢራዊ መረጃዎችን በመልቀቅ የሚታወቀው ‹‹wikleaks›› የተሰኘው ድህረ- ገፅ ‹‹Ethiopian Super rich persons›› ሲል የተለያዩ የቅርብ ወዳጆቻቸውን የቃለመጠይቅ ምስክርነት ማስረጃ ሳይቀር አስደግፎ ማስነበቡ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ‹‹therichest›› ድህረ – ገፅ ያላቸውን የገንዘብ መጠን 3 ቢሊዮን ዶላር ብሎ ባይገልፅም ከፍተኛ የሀገሪቱ ባለጠጋ መሆናቸውን አልሸሸገም ነበር፡፡
በአሁኑ ሰዓት አቶ መለስ ሞተዋል፤ አላቸው የባለው 3 ቢሊዮን ዶላርስ የት ገባ? ምን እየሰራስ ነው? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ቢሆንም እዚህ ላይ ቀን ከሌት ስለመለስ ሙገሳና አድናቆት አውርተው የማይጠግቡት የአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያ ደሳለኝ ከባድ የቤት ስራና ፈተና ነው፡፡ ከእሳቸው በተጨማሪ የፌደራሉ የሥነ – ምግባርና ፀረ – ሙስና ኮሚሽን ቁርጠኝነትንና ተዓማኒነት ለማረጋገጥ የአቶ መለስ አላቸው የተባለው 3 ቢሊዮን ዶላር የት እንዳለና ምን እየሰራ እንደሆነ ከነምንጩ ከመረጃ መረቦቹም ሆነ በራሳቸው ዘዴ አጣርተው የመግለፅ ትልቅ ፈተና ይጠበቅባቸዋል፡፡
የገንዘቡ መገኘት ከተረጋገጠ በኋላም ገንዘቡ ከድሃው የኢትዮጵያ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቆ የተዘረፈ ስለመሆኑ ማንም ሊጠራጠር አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከራስ በላይ ምስክር የለምና ሁለቱም የህወሐት ኢህአዴግ እና የሀገሪቱ የስልጣን ቁንጮዎች በገንዘብ አቅም ድሃ ስለመሆናቸው ተናግረዋልና፡፡ ስለዚህ እነኛ ታማኝ የመረጃ ምንጮች የገፁት በተለይ ‹‹therichest›› ያሰፈረው 57 ቢሊዮን ብር (3 ቢሊዮን ዳላር ) ወደ ተዘረፈው ህዝብ ተመልሶ ጥቅም ላይ ሊውል ይገባል፡፡
‹‹ ዓሳ የሚገማው ከጭንቅላቱ ነው››
አበው ሲተርቱ ‹‹ዓሳ የሚገማው ከጭንቅላቱ ነው ›› ይላሉ፡፡ ዓሳ ከምግቦች ሁሉ የተሸለና ሁሉንም ጠቃሚ ንጥረ ነገሮችን አሟልቶ የያዘ ተወዳጅ ምግብ ቢሆንም ለምግብነት ከመሰናዳቱ በፊት ከመኖሪያው ውሃ ውስጥ እንደወጣ የማይወደድ ሽታ አለው፡፡ የዚህ ‹‹መጥፎ ሽታ›› መነሻው ደግሞ ጭንቅላቱ እንጂ ሌላው አካሉ እንዳልሆነ ይነገራል፡፡ በዚህም ዓሳ ከውሃ ውስጥ ከወጣ በኋላ ያለው መጥፎ ጠረን ጭንቅላቱ ስለሆነ ተቆርጦ መጣል እንዳለበትና ያኔም ሌላው አካሉ ከመጥፎ ሽታ እንደሚፀዳ አመላካች ንግግር ነው፡፡
በኢትዮጵያ ስላለው ቅጥ ያጣ የሙስና ተግባርም ሆነ ብልሹ አሰራር መነሻው ገዥው ኢህአዴግና ቁንጮዎቹ እንደሆኑ የሰሞኑ መረጃ በራሱ በቂ ማሳያ ነው፡፡ ለዚህም ከሚኒስትር አቶ መላኩ ፈንታና ረዳታቸው የሙስና ተግባር መጠርጠር በተጨማሪ በወ/ሮ አዜብ መስፍን ‹‹ድሃ›› ስለመሆናቸው የተመሰከረላቸው ግን በዓለም 2ኛው ባለጠጋ ጠቅላይ ሚኒስትር(በ3 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር) እንደሆኑ የተነገረላቸው ሟቹ አቶ መለስ ዜናዊ አለ የተባለው ሃብት ምንነት ካልተጣራና ካልተመለሰ የመንደር ሌቦችን ብቻ ማሳደድ ሙስናን ሊገታ አይችልም፡፡
ምንጭ፡- ኢቦኒ መፅሔት(ሰኔ በ2005ዓ.ም.)
የሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ንብረት እያወዛገበ ነው
1ሚ. ብር አበድሬአቸዋለሁ የሚል ድርጅት ክስ ሊመሰርት ነው የአዋሣው ቤታቸው ተሸጦ ስም መዛወሩ እያነጋገረ ነው
እጅግ የተከበሩ የአለም ሎሬት አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ ንብረት እያወዛገበ ነው፡፡ አርቲስቱ በሕይወት ሳሉ አንድ ሚሊዮን ብር አበድሬአቸዋለሁ የሚል ድርጅት ለክስ ወደ ፍርድ ቤት ማምራቱን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ ሎሬት አፈወርቅ በህይወት ሳሉ የስዕል ሥራዎቻቸውን፣ ቪላ አልፋንና ሙሉ ንብረታቸውን ለመንግስት ማውረሳቸውን ተከትሎ፣ መንግስት ንብረቱን ለመረከብ እንቅስቃሴ ጀምሮ እንደነበር ይታወቃል፡፡ የእኚሁን ታላቅ አርቲስት ንብረት ለማጣራትና ለመመዝገብም ከፍርድ ቤት፣ ከታዋቂ ሰዎችና ከሙያ ባልደረቦች የተውጣጣ ኮሚቴ ተቋቁሞ ምዝገባና ቆጠራ ቢጀመርም ፍፃሜ ሣያገኝ ተቋርጧል፡፡ ሎሬት አፈወርቅ ተክሌ በህይወት ሣሉ የአክሲዮን ባለ መብት ለመሆን አንድ ሚሊዮን ብር ወስደዋል በሚል የአርቲስቱን ስዕሎች ይሸጥ በነበረ አንድ የማስታወቂያ ድርጅት ክስ ሊመሰረት መሆኑን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ጉዳዩ በፍርድ ቤት እልባት እንዲያገኝ ለኮልፌ ምድብ ችሎት ተመርቶ እየታየ መሆኑን የጠቆሙት ምንጮች፤ ለጊዜው የንብረት ምዝገባና ቆጠራው መቋረጡን ገልፀዋል፡፡ በአዋሣ ከተማ የሚገኘውና በሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ስም የተመዘገበው ቤት በቀድሞ ባለቤታቸው አማካኝነት መሸጡን የጠቆሙት ምንጮች፤ የቤቱ ስም የተዛወረበት አሠራር ሕጋዊነት አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል፡፡ በሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ስም በለንደንና በስኮትላንድ ባንኮች ያለ ገንዘብ እንዲመለስ ጥረት እየተደረገ ሲሆን በተለያዩ አገራት ያሉ ስዕሎችና ንብረቶችን ለማስመለስም እየተሞከረ ነው ተብሏል፡፡ የአርቲስቱ ንብረት ካለባቸው አገራት መካከልም ንብረቱንና ገንዘባቸውን ለመመለስ ፈቃደኛ የሆኑና በመመለስ ሂደት ላይ የሚገኙ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡
የሎሬት አፈወርቅ ተክሌ ቪላ አልፋ፤ በኮሚቴዎቹ ሲከፈት በሺዎች የሚቆጠር ፓውንድ በካዝናቸው ውስጥ መገኘቱንና ይህም በንብረት ዝርዝር ላይ ተመዝግቦ መያዙን ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በፍርድ ቤት ጉዳይ የተቋረጠው የሎሬት አፈወርቅ ንብረት ቆጠራና ርክክብ መዘግየት በንብረቱ ላይ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል የጠቆሙት ምንጮች፤ እጅግ ውድ ዋጋ ያላቸው
ስዕሎቻቸውና የአርቲስቱ የመኖሪያ ቤትና የስዕል ስቱዲዮ የሆነው ቪላ አልፋም የመበላሸት አደጋ አንዣቦበታል ብለዋል፡፡ የሎሬት አፈወርቅ ተክሌ የቀብር ሥፍራ ምንም አይነት የማስታወሻ ሐውልት ሣይሰራበት መቅረቱን የጠቀሱት ምንጮች፤ ከጥቂት ጊዜ በኋላ የቀብራቸው ሥፍራ ሊጠፋ ይችላል የሚል ሥጋት መፈጠሩን ገልፀዋል፡፡
Written by መታሰቢያ ካሣዬ- http://www.addisadmassnews.com/
በአዲስ አበባ ከ 8 ዓመታት በኋላ ታላቅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ
ሰማያዊ ፓርቲ ግንቦት 25 ቀን 2005ዓ.ም. በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ከ1997ዓ.ም. ምርጫ 8 ዓመት በኋላ ታላቅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ፡፡ ፓርቲው በዋነናነት አንግቦ የተነሳው 4 ጥያቄዎችን ሲሆን እነኚህም ሙያዊ ግዴታቸውን በመወጣታቸው ብቻ የታሰሩ ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች እንዲፈቱ፣ የኃይማኖት ነፃነት ይከበር በሚል ጥያቄ በማንሳታቸው ብቻ የታሰሩ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች እንዲፈቱ፣ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ከሚኖሩበት ቦታ እንዲፈናቀሉ የተደረጉ ዜጎች ካሳ ተከፍሏቸው በነበሩበት ቀዬ እንዲኖሩና የድርጊቱ ፈፃሚዎች ለህግ እንዲቀርቡ ፣ ኢህአዴግ በሚከተለው የተሳሳተ ፖሊሲ ምክንያት ሙስና እና ስራ አጥነት እንዲሁም ብልሹ አሰራሮች በአስቸኳይ እንዲታረሙ የሚሉ ጥያቄዎች ናቸው፡፡
ሰላማዊ ሰልፉም ከፓርቲው ጽህፈት ቤት ግንፍሌ መነሻ በማድረግ አራት ኪሎ የድል ሐውልት፣ ፒያሳ ከዚያም ቸርችል ጎዳና በማድረግ ወደ መዳረሻው ዋናው ፖስታ ቤት ፊትለፊት በሚገኘው ኢትዮ-ኩባ የወዳጅነት አደባባይ በሺህዎች የሚቀጠሩ ሰዎች በተገኙበት ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል፡፡ በሰልፉም ላይ በርካታ መፈክሮች የቀረቡ ሲሆን ከነኚህም መካከል ያለ ነፃ ፕሬስ ዴሞክራሲ የለም፣ ኢቴቪ ሌባ፣ ኢህአዴግ ሌባ፣አንለያይም፣ አንድ ነን(ሙስሊምና ክርስቲያን)፣ አሸባሪ አይደለንም፣ የታሰሩ ይፈቱ፣ ህገመንግስቱን የሚፃረሩ አፋኝ አዋጆች በአስቸኳይ ይሰረዙ፣…የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡ በሰልፉ ላይም በርካታ ሙስሊሞችን ጨምሮ የሰማያዊ፣ የአንድነት፣ የመኢአድና የመደኢዴፓ እንዲሁም የመድረክ ወጣቶች በብዛት መገኘታቸውን ለማየት ተችሏል፡፡ በመጨረሻም በሰልፉ መዳረሻ በነበረው ኢትዮ-ኩባ አደባባይ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም፣ አቶ አለሙ ጎቤቦ(የጋዜጠኛ ርዕዮት አባት) እና የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሰልፈኞቹ በሰላማዊና በኢትዮጵያዊ ጨዋነት በማካሄዳቸው አመስግነው በተለይ ኢንጅነር ይልቃል በንግስት አራቱንም ጥያቄ በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ ካልመለሰ በድጋሚ ለተቃውሞ ሰልፍ እንደሚወጡ በመግለፅ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፉ በተሳካ ሁኔታ ከቀኑ በ 8፡00 ሰዓት ተጠናቋል፡፡
በሰልፉ ወቅትምየታሰሩ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፣ጋዜጠኞች እስክንድር ነጋ፣ውብሸት ታዬ እና ርዕዮት አለሙ፤ ከፖለቲከኞች አቶ አንዱዓለም አራጌ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን፣ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ኦልባና ሌሊሳ በተጨማሪ ከቢኒሻንጉል ጉሙዝ የተፈናቀሉ የአማርኛ ተናገሪ ኢትዮጵያዊያን ፎቶ በትልቁ ተዘጋጅቶ ይታይ ነበር፡፡
“ሙሰኞቹ” የተያዙት በሟቹ አቶ መለስ ጥቆማ ከሆነ፤ ነገስ?
አየነው በጊዜው
(ከአዲስ አበባ)
የኢትጵያ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሚኒስትርነት ማዕረግ የትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን አቶ መላኩ ፈንታንና ምክትላቸው አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስን፣ የኢንተር ኮንትኔታል ሆቴል ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ እና የኬኬ ኩባንያ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደን ጨምሮ 12 ሰዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል፡፡ እነኚህ ሰዎች ደግሞ ሊያዙ የቻሉት ከዛሬ 3 ዓመት በፊት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ መለስ ዜናዊ ጥቆማና ትዕዛዝ መሰረት መሆኑን ኮሚሽነሩ እግረ መንገዳቸውን ጠቁመዋል፡፡
እነኚህ ተጠርጣሪዎችም ወዲያው ለፍርድ እንዲቀርቡ መደረጉ የሚታወስ ነው፡፡ ኮሚሽኑም እንደትልቅ ጀብዱ በከፍተኛ የደስታ ስሜት ግንቦት 6 ቀን 2005ዓ.ም. ለፓርላማ ሪፖርት ሲያቀርብ የተያዙትን ተጠርጣሪዎች እንደ ትልቅ ስኬታማ ናሙና ስራ ሲጠቅስ ነበር፡፡ በርግጥ የሃገር ሃብት የሚመዘብሩ መያዛቸው ባይከፋም እስከዛሬ ትላልቅ ባለስልጣናት ላይ ለምን ዝምታን መርጦ ዛሬ እንደ ድል ይቆጥረዋል? የሚል ጥያቄን ማጫሩ አይቀሬ ነው፡፡
እንደኮሚሽኑ ገለፃ ከሆነ በአሁን ወቅት በቁጥጥር ስር ያሉት የመንግስት ሹመኞችና ነጋዴዎች ከመታሰራቸው በፊት ለሶስት ዓመታት ክትተል እየተደረገባቸው እንደነበርና ተግባራዊ ክትትሉም ከዛሬ አንድ ዓመት በፊት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር አሳሳቢነት ዛሬ ላይ መድረሳቸውን ኮሚሽነሩ በይፋ ተናግረዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ዛሬ አቶ መላኩን ጨምሮ የመንግስት ሹመኞችን ብልሹ አሰራር በማጋለጣቸው ጭለማ ቤት ውስጥ እንደታሰሩ ጋዜጠኞችና ተቃዋሚ ፖለቲከኞች አቶ መላኩና ምክትላቸው ከልማታዊ ባለሃብቶቹ ጋር የዚህ ሰለባ ሆነዋል፡፡
እነኚህ ተጠርጣሪ ሙሰኞች ትናንት ሲወደሱና ሲመሰገኑ ከርመው ዛሬ ለረጅም ጊዜ ክትትል ይደረግባቸው እንደነበር መግለፁ ከበስተጀርባ ሌላ ነገር እንዳለ የሚያሳይ ይመስላል፡፡ ምክንያቱም እንደ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ከሆነ እስከዛሬ ንብረትነቱ በውል የማን እንደሆነ የማይታወቀውን በቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ የሚንቀሳቀሰው ኤፈርት ኦዲት ተደርጎ ባለማወቁ ሙስና ከተባለ የድርጅቱ ባለቤቶችና አንቀሳቃሾች መቅደም ነበረባቸው ሲሉ ግምታቸውን ይሰጣሉ፡፡
በተለይ የሃብታቸው ምንጭ ምን እንደሆነ ያልታወቁት አብዛኞቹ አዳዲሶቹ የአዲስ አበባ ህንፃዎች ከባለስልጣና ጋር በመሞዳሞድ በሙስና የተሰሩ ሊሆኑ ስለሚችሉ እስካሁን በፌደራሉ ስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምንም የተደረገ አመላካች እርምጃ ባለመታየቱ አሁን በባለሃብቶቹና በባለስልጣናቱ ላይ የተወሰደው እርምጃ ከሙስና ይልቅ የፖለቲካ ጉዳይ ሊሆን እንደሚችል አመላካች እንደሆነ በስፋት ይነገራል፡፡ ለዚህም ድምዳሜ መሰረቱ የሙስናው ክትትል ከቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ከሟቹ አቶ መለስ ዜናዊና በስፋት በዚሁ ተግባር ከሚታሙት ባለቤታቸው ወ/ሮ አዜብ መስፍን መጀመር እንደነበረበት በመጠቆም፡፡
በተለይ ሌላው አስገራሚው ነገር ኮሚሽኑ አሁን በቁጥጥር ስር ያዋላቸውን ተጠርጣሪዎች ከዓመታት በፊት በሟቹ አቶ መለስ ጥቆማ መሆኑ እስከ ዛሬስ ለምን ቆየ; አሁንም ቢሆን ኮሚሽኑ ዛሬ መድፈሩን ያሳየን በራሱ ተነሳሽነትና ጥረት ሳይሆን በፖለቲካ ስልጣን የበላዩ በመጠቆሙ በመሆኑ ነው፡፡ ይህም የሚያመለክተው ኮሚሽኑ በነፃነት ስራውን የመስራት አቅምም ሆነ ፍላጎት እንደሌለው አመላካች ከመሆኑም በተጨማሪ ለዛሬው ድል መሳካት ትልቅ ሚና የተጫወተው እሱ ሳይሆን ሟቹ ግለሰብ መሆናቸውን በተደጋጋሚ መግለፁ ነው፡፡
ኮሚሽኑ ከተቋቋመ ምንም እንኳ 10 ዓመት ቢሆነውም ሀገሪቱ በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ 11.2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር(ከ207 ቢሊዮን ብር በላይ) የተዘረፈች መሆኗንና በተለይ ኮሚሽኑ ከተቋቋመበት ዓመት አንስቶ ደግሞ ወደ 8.2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር(ወደ 152 ሚሊዮን ብር ገደማ) መዘረፉን መረጃዎች ቢጠቁሙም ኮሚሽኑ የመንደር ሌቦችን ብቻ እያሰሰ የፖሊስን ስራ ይሰራ እንደነበር የሚያወሱ በርካቶች ናቸው፡፡ በዚህም ሀገሪቱ ማዳን የነበረባትን ዝርፊያና የአባሕ ግድን የሚያህሉ ከሁለት በላይ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ሊገነባ የሚችል የሀገሪቱ ሃብት ሲዘረፍ በተለያ የመረጃ አውታሮች ቢነገርም ኮሚሽኑ እስካሁን ያለው ነገር ባለመኖሩ እራሱ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከሙስና ፀድቶ ነው ወይ የሚሉ በርካቶች ናቸው፡፡
ከላይ የተጠቀሱትን እንኳ ብንተው በሀገር ውስጥ ምን ያህል ህገወጥ ስራ በመንግስት መስሪያ ቤቶች እንደሚፈፀምና ለሙስና የተጋለጡ በርካታ ተቋማትን ኦዲት በማድረግ ይፋ የሚያደርገው የፌደራሉ ኦዲተር መስሪያ ቤት ሪፖርት በራሱ በቂ ማስረጃ ነበር፡፡ ነገር ግን ፀረ-ሙስና ኮሚሽኑ በቅርቡ እንደገለፀው በጠቅላይ ሚኒስትሩ አሳሳቢነትና ጥቆማ ካልሆነ በይፋ ለሙስና የተጋለጡ ጸቋማት ላይ የሚያደርገው ክትትልና ምርመራ እንደማይሰራም በተዘዋዋሪ መንገድ መግለፁ ከነ አቶ መላኩ ፈንታ እስር ጀርባ የፖለቲካ ጉዳይ እንዳለበት ቢያመላክት ስህተት ነው ማለት አይቻልም፡፡ ይህ ሲባል ግን ተጠርጣሪዎቹ ንፁኃን ናቸው፣ ሙስና አይፈፅሙም ማለት ሳይሆን ኮኮሚሽኑ እስካሁን የሚጠበቅበትን ምን ያህል ሰራ ብንል እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡
ጉዳዩ የሙስና ከሆነ አንድም የኢትዮጵያ ባለስልጣን ከሊቅ እስከ ደቂቅ ከሙስና ተግባር ሊነፁ እንደማይችሉ፤ ይህም የስርዓቱ መለያ ባህርይ በመሆኑ የፖለቲካ ልዩነት ሲያንፀባርቁ ብቻ ካርታ ለመምዘዝና የፖለቲካ ባርያ ለማድረግ በማሰብ ሙስና እንዲፈፅሙ እንደሚመቻች አንዳንድ የቀድሞ ታጋዮች ዛሬም ድረስ ይናገራሉ፡፡ ለአብነትም በ1993 ዓ.ም. በህወሓት መካከል የነበረውን ክፍፍል መሰረት በማድረግ ከነ ወንድሞቻቸው እንዲታሰሩ የሙስና ካርታ የተመዘዘባቸው የቀድሞ የህወሓት ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩትን አቶ ስየ አብርሃን እስር የሚያስታውሱ አልታጡም፡፡
በርግጥ የሙስና ተግባር ለሀገርና ለህዝብ ጠንቅ መሆኑ ቢታወቅ ኖሮ ህዝቡ ዛሬ የስቃይ ኑሮ ገፈት ቀማሽ ባልሆነ ነበር፡፡ ምክንያቱም ገዥው ኢህአዴግ አባላቱን ሲመለምል ቀድሞውንም ቢሆን ርዕዮተ ዓለሙን ሸጦና አሳምኖ ሳይሆን በፍቅረ ንዋይ የነደዱትን በማማለል እንደሆነ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ለዚህም ነው ዛሬ በሀገራችን የተማሩ አብዛኞቹ ወጣቶች በሙያቸው ሰርተው ተዓምር ለመፍጠር ከመሞከር ይልቅ የኢህአዴግ አባል በመሆን ትልቅ ስልጣን ላይ መውጣትን የሚሹት፡፡ የዚህም ምስጢር ያሉት የመንግስት ተቋማት በስርዓቱ ቸልተኝነት ለሙስና በመጋለጣቸው ነው፡፡
በአጠቃላይ ዛሬ የፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሙሰኞች ሲል የያዛውን ሰዎች በአቶመለስ ጥቆማ መሆኑን ከነገረን ነገ አቶ ኃይለማርያም ካልጠቆሙ ስራውን ሊያቆም ነው ማለት ነው ወይስ እንደለመደው ትናንሽ ዓሳዎችን ጃስ በማለት ጊዜውን ሊያባክን ነው; ይህን ወደፊት አብረን የምናየው ነው የሚሆነው፡፡ ምክንያቱም ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በፊት ለፊታቸው ምንም ያህል ሙስና በባልስልጣኖቹ ቢፈፀም እርምጃ እንዲወሰድባቸው የመጠቆምና የማዘዝ ድፍረቱ ይኖራቸዋል የሚል እምነት የለኝም፤ አቶ ኃ/ማርያም በራሳቸው አዲስ የአመራር ዕቅድ ከመከተል ይልቅ የሟቹን ጠቅላይ ሚኒስትር ሌጋሲ ለማስጠበቅ እየተጉ ነውና፡፡
ምንጭ፡- ኢቦኒ መፅሔት(ግንቦት 2005ዓ.ም.)
የመከነው የአፍሪካ ራዕይ
ልክ የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ. በ1963 ዓ.ም የአፍሪካ ጥቁሮች ከባርነት ቅኝ ግዛት ለመውጣት የተወሰኑ መሪዎቿ ሽር ጉድ እያሉ ነበር፡፡ ሽርጉዱም የአፍሪካ ምድር በአውሮፓውያን ጨካኝ አገዛዝ መዳፍ ውስጥ የወደቁትን ሀገሮች ነፃ ለማውጣት በጥቂት ጥቁር መሪዎች ምክክር ሊካሄድ ነው፡፡
ይሄን የሰሙት ገዥዎች በተለይም እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ፖርቹጋልና፣ ጣሊያን ይበልጥ በጥቁሮች ላይ በደል መፈፀምን ተያያዙት፡፡ ይህን የተመለከቱት የአፍሪካ የአብራክ ልጆች በቁጭት በመንገብገብ ወገኖቻቸውን ከጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ መዘየድ ጀመሩ፡፡ ያኔ ግን የተለያዩ ሀገሮች በተለይም ጋና፣ ናይጄሪያና ደቡብ አፍሪካውያነ በየሀገሮቻቸው የተናጥል ትግል ያደርጉ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ትግሉ ፈቀቅ አላለም፡፡ ምክንያቱም ብቻቸውን ነበሩና፡፡
በወቅቱ ፈረንሳይ የሰሜን አፍሪካ ሀገሮችን በተለይም ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮን እንዲሁም በምዕራብ እንደ ማሊና ኮትዲቫርን በምስራቅ ጅቡቲን ይዛ ነበር፡፡ እንግሊዝ በበኩሏ በምስራቅ አፍሪካ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ሯንዳ፣ ክፊል ሱማሊያ በምዕራብ ናይጄሪያ፣ ጋና በደቡብ የቀድሞ ሮዴዥያ (ዙምባቤና ዛምቢያ)፣ደቡብ አፍሪካ የመሳሰሉ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ይዛ ነበር፡፡ ፖርቹጋል ደግሞ በደቡብ ምዕራብ አንጐላን ስትቆጣጠር ጣሊያንም እንዳቅሟ ሊቢያንና ምስራቅ ሶማሊያን ተቆጣጥራ ነበር፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ለናሙና እንጂ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት የወደቁ ሌሎችም በርካታ የአፍሪካ ሀገሮች ነበሩ፡፡
ነፃ ሀገር
በተፈጥሮ የበለፀገችዋ እማማ አፍሪካ ምንም እንኳ በልጆቿ ስቃይ ማቅ ብትለብስም በወቅቱ እንደሀገር ሉዓላዊነት ያላቸው ሁለት ሀገሮች ነበሯት፡፡ እነኚህም በስተምስራቅ ታሪካዊቷ ኢትዮጵያ እና በምዕራብ የአልማዝ ምድር የሆነችው ላይቤሪያ ናቸው፡፡ በርግጥ ላይቤሪያ እንደሀገር ብትታይም ከነ ሰንደቅዓላማዋ ከአሜሪካ ቁጥጥር ስር ውጭ ነበረች ማለት አልነበረም፡፡ ምክንያቱም እንደ ሀገር ከመመስረቷ በፊት የማንም ያልነበረች በኋላ ግን አሜሪካ በባርነት ከአፍሪካ ተወስደው በሀገሯ እየተባዙ የመጡትን የጥቁሮች ቁጥር ስጋት ላይ እንዳይጥላት በማሰብ ወደዛሬዋ ላይቤሪያ አብዛኞቹን ጭና በማራገፍ የዛሬዎቹ ላይበሪያውያን መኖሪያ አድርጋለች፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1888 እና በ1928 ዓ.ም በጣሊያን የቅኝ ግዛት ሙከራ ቢደረግም በጥቁር አናብስት ትግል ሳይሳካ በመቅረቱ ከአፍሪካ ብቸኛዋ ነፃ ሀገር ሆና ቆይታለች፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በዳግማዊ አጼ ምኒሊክ መሪነት የጥቁር አናብስት በጣሊያን ላይ በተቀዳጁት ድል ለሌሎችም ፋና ወጊ በመሆን የነፃነት ትግል እንዲቀጣጠል ፈር ቀዷል፡፡
የነፃነት ናፍቆት ህብር
አፍሪካውያን የነፃነት ናፍቆት ቢያንገበግባቸውም ትግሉ በተናጥል ስለሆነ በተፈለገው ፍጥነት ውጤታማ ሊሆን አልቻለም፡፡ ለዚህም የናይጄሪያውን ኢቦ ኢቢቦ፣ የጋናው አሻንቲ እና የደቡብ አፍሪካውን የነ ባሱቶ ዙሉ ትግልን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለሆነም ትግሉ እንዲሰምር በገዥዎች ሀገር ይኖሩ የነበሩ የጥቁሮች የአብራክ ክፋይ እነ ኩዋሜ ኑኩሩማ፣ ጆሞ ኬንያታ የመሳሰሉት በጋራ መታገሉ የተሻለ እንደሆነ በማሰብ በነፃይቱ የጥቁር አናብስት ምድር ንጉስ ከሆኑት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኃ/ስላሴ ጋር መከሩ፡፡
ምክክራቸውንም በማጧጧፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገሮች ገፉበት፡፡ በዚህም ጥቁሮች ሲነቃቁ ቅኝ ገዥ አውሮፓውያን ግን ድንጋጤ ወሯቸው ነበር፡፡ በተቃራኒው ጥቁሮች ደግሞ ከፍተኛ የአሸናፊነት ወኔን ተላብሰው ለልጆቻቸው ከጭቆና ነፃ የሆነ ምድር ለማውረሰና ለራሳቸውም ነፃነት ተግተው ተፋለሙ፡፡
ይሄን የተረዱት የትግሉ ውጤት ናፋቂዎች እነ አፄ ኃ/ስላሴና ኩዋሜ ኑኩርማን ጨምሮ ሌሎች የወቅቱ የአፍሪካ የቁርጥ ቀን ልጆች አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ይላቀቁ ዘንድ አፍሪካውያን በአንድ ስም ተጠርተው የሚጠለሉበትን ተቋም መመስረት እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ የዚህም ተቋም ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከቅኝ ግዛት ነፃ ማውጣት ነበር፡፡
የአፍሪካ አንድነት ድርጅት
አፍሪካውያንን የነፃነት ድል ለማቀዳጀት ሲባል የዛሬ 5ዐ ዓመት እ.አ.አ ግንቦት 1963 ዓ.ም በነፃይቱ ታሪካዊት ሀገር አዲስ አበባ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ተመሰረተ፡፡ ድርጅቱ ሲመሰረትም ሊቀመንበር ሆነው የተመረጡት ኢትዮጵያው ንጉስ አጼ ኃ/ስላሴ ነበሩ፡፡
በወቅቱ ተቋሙ ምንም እንኳ ቢመሰረትም ወዲያው የራሱን ቢሮና ለምክክር የሚሆን አዳራሽ መገንባት የማይቻል ቢሆንም ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃ/ስላሴ መንግስታቸውና መላው የሀገራቸው ህዝብ አፍሪካውያን ወገኖቹ ነፃ እንዲወጡ እንደሚሻ ተናገሩ፡፡ በዚህም ሳያበቁ በመንግስታቸውና በህዝባቸው ስም ዛሬ የህብረቱ አሮጌው ህንፃ ለፖሊስ ጽህፈት ቤት ተብሎ የተሰራውን ከነሙሉ ግቢው በነፃ ለድርጅቱ አስረከቡ፡፡ ድርጅቱም በነፃይቱ ምድር ያለማንም ከልካይ በነፃነት በመምከር የአፍሪካውያንን መፃኢ ተስፋ ብሩህ ለማድረግ ተግቶ ይሰራ ጀመር፡፡
በድርጅቱ ያላሰለሰ ጥረትም ጋና ቀድማ ከእንግሊዞች ቅኝ ግዛት ነፃ ስትወጣ ሌሎችም ተከታትለው ነፃ ወጥተዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ግን ከአሰቃቂው የአፓርታይድ ዘረኝነት አገዛዝ ነፃ የወጣችው ዘግይታ ነበር፡፡
ያኔ በአዲስ አበባ የተመሰረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋነኛ ዓላማ አፍሪካውያንን ከባርነት ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት በተጨማሪ የአህጉሪቱ ሃብት በአውሮፓውያን ተወስደው ዜጐቿ እንዳይራቆቱ ነበር፡፡ የአፍሪካ አንጡራ ሃብት በቅኝ ገዥዎች ከልጆቿ ጉሮሮ ተነጥቆ እንዳይወሰድና ልጆቿ በእናት ምድራቸው በነፃነት እንዲቦርቁ ታስቦ በቀድሞው አባቶች መልካም ፈቃድ የተቋቋመው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት /አ.አ.ድ/ ዛሬ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ይህም የሆነበት ምከንያት ድርጅቱ የተቋቋመለትን አፍሪካውያንን ከባርነትና ጭቆና ነፃ ማውጣት የሚለውን አሳክቶ ጨርሷል በሚል ነው፡፡
የጨነገፈው ፅንስ
የቀድሞ የአፍሪካ መሪዎች ያነገቡት ወገኖቻቸውን ነፃ የማውጣት መልካም ራዕይ በአሁኖቹ የአስተሳሰብ አድማስ እሳቤ ተሳክቷል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የዛሬ 12 ዓመት ግንቦት 2ዐዐ1 (እ.አ.አ) ደቡብ አፍሪካ በተወሰነው ውሳኔ መሰረት ወደ አፍሪካ ህብረት ተቀይሯል፡፡ እውነት ለመናገር ዛሬም ድረስ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፤ ነፃ የነበሩትም በአብራኮቻቸው ክፋይ ቅኝ ግዛት ውስጥ ገብተዋልና፡፡
በተለይ በዛሬዎቹ መሪዎች ድርጅቱ ዓላማውን አሳክቷል፤ ግቡን መቷል በሚል የአህጉሪቱን ልማት መሰረት በማድረግ የአፍሪካ ህብረት ተቋቁሞ መቀመጫውንም እዚሁ አዲስ አበባ አድርጓል፡፡
ያኔ ቅኝ ገዥዎች ባላገሮቹን በግፍ ይጨቁኑ ነበር፣ ህዝቡ በስርዓቱ ላይ ያለውን ተቃውሞ ሲያቀርብ በጥይት እሩምታ በመረሸን የቀሩትን ወደ አሰቃቂ እስር ቤት ይከቱ ነበር፡፡ ይህ ግን ነፃዋን ኢትዮጵያን አይመለከትም ነበር፡፡ ምክንያቱም ንጉሷም መሪዋም ባዕድ ሳይሆኑ ያው ያብራኳ ክፋይ አፄ ኃ/ስላሴና ኢትዮጵያውያን ናቸውና በመካከል የቅኝ ገዥነት እሳቤ የለም፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያውያን በንጉሱ ስርዓት ቅሬታ ሲሰማቸው በነፃነት ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ለዚህም እ.አ.አ በ197ዐ ዎቹ መጀመሪያ ላይ የነበረውን የነዳጅ ጭማሪ ዋጋ በመቃወም የነበረውን ማስታወሱ በቂ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል፡፡ ከዛም በፊት ወጣቶች መሬት ላራሹ ተቃውሞን በነፃነት አሰምተዋል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ግን የማይቻል ነው፤ ቅኝ ገዥዎች ናቸውና፡፡
ዛሬ ግን ምናልባት አንፃራዊ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት አስተዳደር ያላቸው ጋና እና ደቡብ አፍሪካ ካልሆነ በስተቀር አፍሪካውያን በራሳቸው ጥቁር ገዥዎች የጭቆና ቀንበር ስር ወድቀዋል፡፡ ለዚህም በግብፅ፣ በሊቢያ፣ በኮትዲቫር፣ በቱኒዚያ፣ በሞሮኮና በአልጄሪያ ያሉትን ጨቋኝ አስተዳደሮች በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ የወጡት ከቅኝ ገዥዎች በባሰ በአሽከሮቻቸው ታጣቂዎች በአደባባይ የጥይት እራት ሆነዋል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያም የተመለከትን እንደሆነ አፍሪካውያን ነፃ ወጥተዋል በሚል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ወደ ህብረት ከተቀየረ በኋላ በቅኝ ያልተገዙት ኢትዮጵያውያን የመንግስት ገዥዎች በርካታ እኩይ ተግባራትን ለመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ቢፈልጉም ለመጨረሻ ጊዜ በሚል ይመስላል እ.አ.አ በ2ዐዐ5 (በ1997 ዓ.ም) በምርጫ ወቅት ነበር የተደረገው፡፡ ከዚያም የምርጨውን ውጤት ተከትሎ በተፈጠረ ተቃውሞ አሁን በስልጣን ላይ ባለው ገዥው ቡድን መሪ በነበሩት በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ጨቅላ ህፃናትን ጨምሮ ከ86ዐ በላይ ዜጐች የጥይት ናዳ አርፎባቸው እስከወዲያኛው አሸልበዋል፡፡
በኬንያና በሱዳንም ሆነ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገሮች በተመሳሳይ መልኩ ገዥዎችን ለመደገፍ ካልሆነ ለተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ለሞት ይዳርጋል፡፡ ይህንን ደግሞ ቅኝ ገዥዎች ያደርጉት የነበረው አስከፊ ድርጊት በጥቁር ቆዳ ካባ በለበሱ አምባገነን መሪዎች መደገፍ አፍሪካውያንም ሆኑ አፍሪካ ነፃ ወጥተዋል ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የድጋፍ የድጋፍማ ቅኝ ገዥዎችም አሳምረው በመፍቀድ መፈክር እና ሌላ ወጭ በመሸፈን ይከናወን ነበር፤ ተቃውሞ ባይቻለም፡፡
ሌላው ያኔ በቅኝ ገዥዎች ወቅት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ተዝቆና ተሸጦ ወደ አውሮፓ ካዝና ይገባ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ በእራሳቸው በአፍሪካውያን መሪዎች ከአህጉሪቱ ህዝብ ጉሮሮ ተነጥቀው አንጡራ ሃብቷን ዝቀውና ሸጠው ወደ አውሮፓና እስያ ሀገሮች ካዝና ያስገባሉ፤ አፍሪካውያን ግን ዛሬም ይራባሉ፣ይታሰራሉ፣ ይገረፋሉ፣ ይጨቆናሉ፣ይሰደዳሉ፣ይገደላሉ፣ይዘረፋሉ፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የተቋቋመለትን ዜጐቿን ነፃ የማውጣት ራዕይ ግቡን ሳይመታና ሳያሳካ የነፃነት ፅንሱ በዚህ መልክ ጨንግፏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእስያዎቹ ቻይና፣ ህንድና የአረብ ሀገራትን ጨምሮ አሜሪካና አውሮፓ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ እጃቸውን አላወጡም፣ ዛሬም በዘመናዊው እጅ አዙር ቅኝ ጋዛት ቀፍድደው ይዘዋልና፡፡ ስለዚህ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዓላማ ተጨናግፋል እንጂ ተሳክቷል ማለት አይቻልም፡፡
በትረ ከረባት ነዳያን
የቀድሞ ለነፃነት ቀናዒ የሆኑ የአባቶቻችንን ዓላማ ተሳክቷል በሚል ክህደት የዛሬዎቹ በትረ ከረባት ነዳያን የአፍሪካ ህብረትን አቋቁመዋል፡፡ የህብረቱም ዓላማ በአፍሪካ ልማትን ማምጣትና ማፋጠን እንዲሁም ማስተሳሰር የሚል ነው፡፡ በዚህም ስም በስልጣን ላይ ያሉት የአህጉሪቱ መሪዎች የራሳቸውን ሆድና ስልጣን ታሳቢ በማድረግ በአህጉሪቱ ህዝብ ስም ከረባት አስረው ለምነው የሚያመጡትን ገንዘብ በሌላ መንገድ በስማቸው ወደ ለጋሽ ሀገሮች ካዝና ይቋጥራሉ፡፡
ለዚህም የሊቢያ፣ የግብፅ፣ የቱኒዚያና የኢትዮጵያ መሪዎችን ጨምሮ አብዛኞቹ የዚህ ባለሟል ናቸው፡፡ አብዛኞቹ መሪዎችም እጃቸው ከዜጐቻቸው የግፍ ደምና የህዝቡ አንጡራ ሃብት ዝርፍያ የፀዳ አይደለም፡፡ በዚህም ምክንያት ዛሬም ድረስ ዜጐቻቸውን እጅግ ከቅኝ ገዥዎች በባሰ መልኩ በመጨቆን አንዳንዶቹ በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ሌሎቹ ደግሞ በምርጫ ስም ህዝብን በማጭበርበር በትረስልጣናቸውን እያደላደሉ ይገኛሉ፡፡
አሁን በስልጣን ላይ ያሉት የአፍሪካ ማሪዎች የእነሱ የስልጣን ዕድሜ እስከረዘመና ዝርፊያውን እስኳጧጧፉ ድረስ የአህጉሪቱን አንጡራ ሃብት ጥቅም በማዘረፍ ተወዳዳሪ የላቸውም፡፡ በዚህም ለዜጐቻቸው ያላቸው ቀናዒነትና ተቆርቋሪነት ከቀድሞዎቹ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መስራቾች ጋር ሲነፃፀር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ የበትረ ከረባት ነዳይ ሆነው የአህጉሪቱን ሃብት እያዘረፉ የዜጐቻቸውን ነፃ አስተሳሰብና ነፃ ሚዲያን በማፈን ከፍተኛ ጭቆና እያደረጉ ስለመሆኑ የህብረቱ ዋና መቀመጫ የሆነችውን ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛው አፍሪካ ሀገሮችን ማየት በቂ ነው፡፡
በአጠቃላይ አሁን እ.አ.አ. በያዝነው ግንቦት 2ዐ13 የአፍሪካ ህብረት ምስረታ 5ዐኛ ዓመት ክብረ በዓል ለመሪዎቹ ብቻ ካልሆነ በቀር ለአህጉሪቱ ህዝብ ይሄ ነው የሚባል የፈየደው ነገር አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ምክንያቱም እየተሰሩ ያሉት መሰረተ ልማቶችና ሌሎች የህዝብ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ግንባታ ሰብዓዊ ልማትን ወደጐን በመተው እየተደረገ ያለው ቅኝ ገዥዎች በጊዜያቸው ሲያደርጉት ከነበረው እምብዛም የተለየ አይደለምና፡፡ በዚህም አፍሪካ ቀድሞ የነበራት ራዕይ በአሁኖቹ በትረ ከረባት ነዳይ መክኖ ቀርቷል ማለት ይቻላል፡፡ ያኔ ቅኝ ገዥዎች ሰብዓዊ መብትን በመርገጥ በቁሳዊ ልማት ህዝቡን ለመደለል ይሹ እንደነበረው ዛሬም እንዲሁ ነው፡፡



