Tag Archives: Ethiopian Justice

77 ቢሊዮን ብር የሚያንቀሳቅሰው ስኳር ኮርፖሬሽን የገጠመው ፈተና

‹‹ለስኳር ኮርፖሬሽን መውደቅ ሜቴክ ትልቅ ድርሻ አለው› ‹‹የስኳር ኮርፖሬሽን የቀድሞ አመራሮች መጠየቅ አለባቸው››

MP, Sugar projects failures

የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች

በዮሐንስ አንበርብር

በ2003 ዓ.ም. በተካሄደው የመጀመርያ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ትልቅ ትኩረት ከተሰጣቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል የስኳር ልማት አንደኛው ነው፡፡ አገሪቱ ለስኳር ልማት ያላትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም አሥር ግዙፍና አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎችን በመገንባት በዓመት 4.07 ሚሊዮን በላይ ስኳር በማምረትና ለውጭ ገበያ በማቅረብ፣ በ2007 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ 1.2 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት በዕቅድ ተይዞ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ይህ ዕቅድ በጣም የተለጠጠ መሆኑ በስተመጨረሻ ሲታወቅ፣ ሰባት ፋብሪካዎችን በመጀመርያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ማጠናቀቅ ተብሎ እንዲከለስ ተደርጓል፡፡

እነዚህ አዳዲስና ግዙፍ ፕሮጀክቶች በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገነቡት ኩራዝ አንድ፣ ኩራዝ ሁለት፣ ኩራዝ ሦስት፣ በለስ አንድ፣ በለስ ሁለት፣ ከሰም፣ ወልቃይት፣ አርጆ፣ ደዴሳና ተንዳሆ ናቸው፡፡

መንግሥት ፕሮጀክቶቹን አጠናቆ ስኳር ለውጭ ገበያ በማቅረብ በሚገኝ የውጭ ምንዛሪ ዕዳ መክፈል እንደሚችል በማሳመን ለስኳር ፋብሪካዎቹ መገንቢያ ከተለያዩ አበዳሪዎች ሁለት ቢሊዮን ዶላር ተበድሯል፡፡ ከአገር ውስጥ ባንኮችም ከፍተኛ ብድር አግኝቷል፡፡ በአጠቃላይ የስኳር ልማቱን የሚመራው የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን 77 ቢሊዮን ብር በላይ እያንቀሳቀሰ የሚገኝ ቢሆንም፣ አንድም ፋብሪካ እስካሁን ተጠናቆ ወደ ሥራ አልገባም፡፡ በሌሎች አገሮች አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ ግፋ ቢል አንድ ዓመት የሚፈጅ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ስኳር ልማት ኮርፖሬሽን ግን አንድ ዓመት ከስድስት ወራት (18 ወራት) አንድ ስኳር ፋብሪካን ለማጠናቀቅ አቅዶ የውል ስምምነቶችን ቢያደርግም፣ አንድ ፋብሪካ ሥራ ሳይጀምር ስድስተኛ ዓመት ላይ ተደርሷል፡፡

የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የሥራ ኃላፊዎች በ2008 የበጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለማቅረብ ባለፈው ሰኞ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ተገኝተዋል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ከተሾሙ የወራት ዕድሜን ያስቆጠሩት አቶ እንዳወቅ አብቴና ሌሎች ምክትል ሥራ አስፈጻሚዎች ያቀረቡት ሪፖርት ‹‹ተስፋ በመቁረጥና እያመመን ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከሰባት ዓመት በፊት ግንባታው የተጀመረው ተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ በኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ስኳር ማምረት ቢጀምርም ጥራቱ የተጓደለ የእንፋሎት አቅርቦት፣ የፋብሪካውን ፊልተር በቆሻሻ በመዝጋቱና በተርባይን ላይ ጉዳት በማድረሱ እንዲቆም መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ጥገና ከተደረገ በኋላ በአገሪቱ በተከሰተው ድርቅ ለፋብሪካውና ለመስኖ የሚሆን የውኃ አቅርቦት ችግር ወደ ምርት እንዳይገባ እንዳደረገው ጠቁመዋል፡፡
የተንዳሆ ቁጥር ሁለት ፋብሪካ ግንባታም ገና 27 በመቶ ላይ ይገኛል፡፡ ኩራዝ አንድ የተባለው ፋብሪካ ኮንትራት ውል የተገባው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ የውል ማሻሻያ ሰኔ 2004 ዓ.ም. ላይ እንደተደረገ አቶ እንዳወቅ አስረድተዋል፡፡

በዚህ መሠረት ግንባታውን የሚያከናውነው አገር በቀሉ የኢትዮጵያ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ፕሮጀክቱን በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. አጠናቆ ማስረከብ ይጠበቅበት ነበር፡፡
ፕሮጀክቱ በመጋቢት ወር 2008 ዓ.ም. ላይ የደረሰበት ደረጃ 83 በመቶ ሲሆን፣ ሜቴክ ግን 97 በመቶ ክፍያ እንደተፈጸመለት አቶ እንዳወቅ ተናግረዋል፡፡ ኩራዝ ሁለት የተባለውን ፋብሪካ ለማስገንበት ውል የተፈረመው እ.ኤ.አ. በሐምሌ ወር 2014 ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 58 በመቶ መድረሱን ይጠቅሳሉ፡፡ በውሉ መሠረት በመጪው ሐምሌ ወር ፕሮጀክቱ መጠናቀቅ የነበረበት ቢሆንም መዘግየቱን አስታውቀዋል፡፡ የፕሮጀክቱ ኮንትራክተር የፕሮጀክቱ ማጠናቀቂያ ጊዜ እንዲራዘምለት ጠይቆ እስከ መጪው ኅዳር ወር እንዲያጠናቅቅ መመርያ እንደተሰጠው አብራርተዋል፡፡

ኩራዝ ሦስት ግንባታው የተጀመረው እ.ኤ.አ. በፌብሯሪ 2015 ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ አፈጻጸም 25 በመቶ ደርሷል፡፡ ይህም ቢሆን መሆን ከነበረበት ወደ ኋላ የቀረ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ኩራዝ አምስት ስኳር ፋብሪካን ለማስጀመር ከቻይና ኩባንያ ጋር ውል የተፈጸመ ሲሆን፣ ወደ ሥራ ለመግባት ኩባንያው ዝግጅት ላይ መሆኑን አቶ እንዳወቅ ይገልጻሉ፡፡ በለስ አንድ ስኳር ፕሮጀክት ወደ ሥራ የገባው በየካቲት 2003 ዓ.ም. ነው፡፡ በሰኔ ወር 2004 ዓ.ም. የውል ማሻሻያ መደረጉንና በመጋቢት ወር 2005 ዓ.ም. ኮንትራክተሩ ሜቴክ አጠናቆ ማስረከብ የነበረበት ቢሆንም፣ የፕሮጀክቱ አፈጻጸም በአሁኑ ወቅት ገና 60 በመቶ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ኮንትራክተሩ ግን 94 በመቶ የሚሆነውን ክፍያ መቀበሉን ገልጸዋል፡፡

በለስ ሦስት ፋብሪካን ለመገንባት ውል የተፈጸመው በ2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ መጠናቀቅ የሚገባው በ2005 መጋቢት ላይ እንደነበረ ያስረዳሉ፡፡ ይሁን እንጂ ፕሮጀክቱ ገና 23 በመቶ ሲሆን፣ ኮንትራክተሩ ሜቴክ ግን 94 በመቶ ክፍያ እንደተከፈለው ያስረዳሉ፡፡

የከሰም ስኳር ፋብሪካ አፈጻጸም 96 በመቶ መድረሱን ነገር ግን ገና ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ እንዳልገባ አክለዋል፡፡ ወልቃይት ስኳር ፋብሪካም ግንባታው እንዳልተጀመረና በቅርቡ ግንባታው እንደሚጀመር ገልጸዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን ገንብቶና ምርት ኤክስፖርት በማድረግ ዕዳውን የመክፈል ኃላፊነት የተሰጠው ቢሆንም፣ ኤክስፖርት ማድረግ ይቅርና የአገሪቱን የስኳር ፍላጎት ማሟላት አለመቻሉን ገልጸዋል፡፡
ግንባታዎቹን ለማከናወን 77 ቢሊዮን ብር የውጭና የአገር ውስጥ ብድር የተበደረ በመሆኑ፣ አንድም ፋብሪካ ወደ ምርት ባልገባበት በአሁኑ ወቅት 13 ቢሊዮን ብር ዕዳ ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ የመክፈል ኃላፊነት ከፊቱ ተጋርጧል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ተስፋዬ ይገዙና የኮሚቴው አባላት የኮርፖሬሽኑ ችግር ምን እንደሆነ፣ ሥራው ባልተሠራበት ሁኔታ ከ90 በመቶ በላይ ገንዘብ ለምን እንደተከፈለ ማብራሪያ ጠይቀዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ የኢንቨስትመንትና ልማት ዘርፍ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ አብርሃም ደምሴ በሰጡት አስተያየት፣ የአሥሩም አዳዲስ ፋብሪካዎች ኮንትራት የተሰጠው ለአገር በቀሉ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) መሆኑን አስታውሰው፣ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎቹን መገንባት እንዳልቻለ ገልጸዋል፡፡ ይህ ቢሆንም የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን አመራሮች ከሜቴክ ጋር የነበራቸው ግንኙነት በቢዝነስ ኮንትራት ሕግ የማይመራ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

‹‹አሥሩም ፋብሪካዎች በዚህ ኮንትራክተር እንዲሠሩ ነበር የተወሰነው፡፡ በኋላ ላይ የመፈጸም አቅሙ እየታየ ፕሮጀክቶቹ እየተነጠቁ አሁን እጁ ላይ ሦስት ፋብሪካዎች ናቸው የቀሩት፤›› ብለዋል፡፡
ከዚህ ኮንትራክተር (ሜቴክ) ተነጥቀው ፋይናንስ ተገኝቶላቸው ወደ ሥራ ከገቡት መካከል ከሰም ሥራ ለመጀመር ዝግጅት ላይ ሲሆን፣ ሌሎቹ ደግሞ እስከ ኅዳር ወር 2008 ዓ.ም. ይደርሳሉ ብለዋል፡፡ በሜቴክ እጅ የሚገኙት ግን መቼ እንደሚጠናቀቁ እንኳን ለማወቅ አስቸጋሪ እንደሆነባቸውና ከድርጅቱ ጋር ልቅ የሆነው ግንኙነት በውል ያልታሰረ በመሆኑ ዕርምጃ እንኳን ለመውሰድ እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡
ሜቴክ በእጁ የሚገኙትን ሦስት ፋብሪካዎች በተለይም ኩራዝ አንድ ፋብሪካን በመጋቢት ወር 2007 ዓ.ም. ለማጠናቀቅ ገንዘብ እንደሚያስፈልገው ገልጾ፣ በልዩ ሁኔታ ስኳር ኮርፖሬሽን የአገር ውስጥ ብድር እንዲያገኝ ተደርጎ ሊከፈለው መቻሉን አቶ አብርሃም አስረድተዋል፡፡

‹‹ይሁን እንጂ ይህ ፋብሪካ እስካሁን አልተጠናቀቀም፡፡ እኛ ግን ዕዳ የመክፈል አደጋ ከፊታችን ተጋርጧል፤›› ብለዋል፡፡ ፋብሪካዎቹ ባለመድረሳቸው ምክንያት አጠቃላይ የስኳር ኮርፖሬሽን ወጪ እየናረ መሆኑን የሚገልጹት የሥራ ኃላፊው፣ የሸንኮራ አገዳው ቢደርስም አገዳውን ከማስወገድ ሌላ አማራጭ አለመገኘቱን ገልጸዋል፡፡

‹‹ኩራዝ ላይ 870 ሔክታር አገዳ ለማስወገድ ተቃርበናል፡፡ 300 ሺሕ ሔክታር የሸንኮራ አገዳ በለስ ላይ አስወግደናል፡፡ ይህንን ለማስወገድ በሔክታር 50 ሺሕ ብር እያወጣን ነው፤›› በማለት በምሬት ተናግረዋል፡፡
‹‹በዚህ ኮንትራክተር ላይ እንደ ማንኛውም ኩባንያ ቅጣት መጣል እንደማንችል ሁላችሁም ታውቃላችሁ፡፡ የሚያስጠይቅ ነገር ካለ ባለቤቱ ተለይቶ መጠየቅ ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡
ሌላው የኮርፖሬሽኑ አመራርም የሜቴክ ችግር በመገንባት ላይ ባሉት ፋብሪካዎች ላይ ብቻ አለመሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ በማምረት ላይ ለሚገኙ ፋብሪካዎች መለዋወጫ የሚያቀርበው ሜቴክ መሆኑን በመጥቀስ፣ መለዋወጫ ባለማቅረቡ ምክንያት ፋብሪካዎች ለበርካታ ቀናት ምርት እንደማያመርቱ ገልጸዋል፡፡
‹‹የማይችሉትን ሁሉ እንችላለን እያሉ አገርን ዋጋ እያስከፈሉ ነው፡፡ ምክንያቱም ነባሮቹ ፋብሪካዎች ያለ ችግር ቢሠሩ ቢያንስ በውጭ ምንዛሪ ስኳር አናስገባም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ መለዋወጫ ከሜቴክ የመግዛት ግዴታ ለአገሪቱ አዋጭ አለመሆኑን፣ ምክንያቱ ደግሞ ሜቴክ ራሱ ከውጭ ከሚገባው በላይ እየሸጠ መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡ ‹‹ለምሳሌ ሮለር ከውጭ ስንገዛ ከ200 ሺሕ ብር አይበልጥም፡፡ ሜቴክ ግን 600 ሺሕ ብር ነው የሚሸጥልን፤›› ብለዋል፡፡

‹‹እንቢ ብለን እንኳን እንዳንታገል አመራሮች ያሸማቅቁናል፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው ከሌሎች አካላት ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለብቻ በሌላ መድረክ እንደሚያይ አስታውቆ አሁንም የኪራይ ሰብሳቢነት ችግር በኮርፖሬሽኑ ውስጥ መኖሩን በመጥቀስ ፋብሪካዎች ኦዲት እንዲደረጉ አዟል፡፡
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጋዜጣ

ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ 5 ዓመት ከ4 ወር ቅጣት እስር ተበየነበት

( አዲስ ሚዲያ) የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ ላይ 5 ዓመት ከ4 ወር የእስር ቅጣት ተበየነበት፡፡ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የደ ብርሃን ድረ-ገፅ ተባባሪ ብሎገር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ድህረ-ምረቃ ተማሪ የነበረ ሲሆን፤ በውጭ ሀገር የኢንተርኔት ደህንነት ስልጠና ለመውሰድ ማመልከቱ “ለሽብር ተግባር ተሰናድተዋል” በሚል በተመሰረተበት ክስ ፍርድ ቤቱ ጥፋተኛ ሲል መበየኑ ታውቋል፡፡

Zelalem Workagegnehu

በዘለዓለም ወርቅአገኘሁ የክስ መዝገብ ዘለዓለምን ጨምሮ 10 ተከሳሾች ከሰኔ 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸው በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት እየታየ የነበረ ቢሆንም፤ የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ሃታሙ አያሌው እና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበረው የሺዋስ አሰፋ፣ የዓረና ትግራይ/መድረክ አመራር አባል አቶ አብርሃ ደስታ እንሁም መምህር አብርሃም ሰለሞን በተመሰረተባቸው ክስ በነፃ መሰናበታቸው ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ አቶ አብርሃ ደስታ ይህ ዜና እስከተዘገበበት ድሰር አሁንም በእስር ላይ ይገኛል፡፡

አቶ ዮናታን ተስፋዬ ከኦነግ ጋር ተያይዞ የሽብር ክስ ተመሰረተበት

የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና በምርጫ 2007 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ወረዳ 17 የፓርላማ እጩ ተወዳዳሪ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 የወጣውን አንቀጽ 4 ስር የተመለከተውን ተላልፏል በሚል ክስ ተመስርቶበታል፡፡

yonatan tesfaye

ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ክሱ በዳኞች ቢሮ በንባብ የተሰማበት አቶ ዮናታን ተስፋዬ፤ የአዲስ አበባ ከተማ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ሽፋን በማድረግ ከህዳር 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ተከሳሹ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ በተለይም ፌስቡክ አማካኝነት በኦሮሚያ ክልል የተነሳውን “አመፅና ብጥብጥ” ለማስቀጠል የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን ዓላማ ተቀብሎ ተንቀሳቅሷል ሲል አቃቤ ህግ ክስ መስርቶበታል፡፡ የክስ ፋይሉ ሌላ ተከሳሽ ውጭ ለአቶ ዮናታን ብቻ የቀረበበት የማስረጃ ዝርዝር በማኀበራዊ ሚዲያ የለጠፋቸው ፅሑፎች ናቸው፡፡

በዚህም ተከሳሹ የቡድን (ኦነግ) ዓላማን ለማሳካት አመፅና ብጥብጥ እንዲቀጥልና ሌሎችን ለማነሳሳት አስቦ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ (ፌስቡክ) ቀስቃሽ ፅሑፎችን በመፃፍ የሽብርተኝነት ድርጊት ለመፈፀም ማቀድ፣ ማዘጋጀት፣ ማሴር እና ማነሳሳት ወንጀል ክስ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት ታውቋል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ በተለያዩ ቀናት በግል የፌስቡክ ገጹ ላይ ያስነበባቸው ፅሑፎች ክሱ ላይ ተካተው በማስረጃነት ቀርቦበታል፡፡

ታህሣሥ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጭቆና መሳሪያነት የሚያገለግሉ ማናቸውንም ቁሳቁሶች ማቃጠልና ማውደም እንዲሁም መንገድ መዝጋትን በተመለከተ፣ ታህሣሥ 11 ቀን 2008 ዓ.ም. ኢህአዴግ ችግር ማዳፈን እንጂ ችግር መፍታት አይችልም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲጀመር ምንም ዓይነት መሪ ዕቅድ (ማስተር ፕላን) የለም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የተቃውሞ ትግሉ ቀጥሏል በሚል የፃፈው፣ ህዳር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. እነሆ 7 መልዕክት ብሎ በፃፈው እና በሌሎችም ፅሑፎች አማካኝነት ቅስቀሳ አድርጓል ሲል አቃቤ ህግ ክስ አቅርቦበታል፡፡
ዮናታን ተስፋዬ በነጠላ መዝገብ ብቻውን ክስ የተመሰረተበት ሲሆን፤ በዕለቱ ክሱ በንባብ በተሰማበት ወቅት ዳኛ አልተሟላም በሚል ምክንያት በዳኞች ቢሮ መታየቱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የክሱን ሂደት ዬናታን ቤተሰቦችም፣ ወዳጆችና ጋዜጠኞች በችሎት መታደም ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ አቶ ዮናታንም የክስ መቃወሚያውን ይዞ ለፊታችን ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዲቀርብ ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

ነባር የኢሕአዴግ አመራሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለመከላከያ ምስክርነት ተቆጠሩ

ምሁራንና ፖለቲከኞችም ተካተዋል

በታምሩ ጽጌ

TPLF_EPRDF Juntas

ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ማይካድራ በተባለ ቦታ ላይ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው የተለገጸውና በሽብር ድርጊት ወንጀል የተከሰሱ አራት ተጠርጣሪዎች፣ አቶ በረከት ስምኦን፣ አቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ አቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሃት)፣ አቶ አዲሱ ለገሰ፣ አቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ጄነራል ሳሞራ የኑስንና ሌሎችንም ነባር ታጋዮችንና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ጨምሮ 141 ሰዎች በመከላከያ ምስክርነት ቆጠሩ፡፡

መከላከያ ምስክሮቹን የቆጠሩት ተጠርጣሪዎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ወ/ሪት እየሩሳሌም ተስፋውና አቶ ፍቅረማርያም አስማማው ናቸው፡፡ በክሱ ከላይ የተጠቀሱትን ተጠርጣሪዎች ወደ ኤርትራ ድንበር እንዲሻገሩ በመምራት የተጠረጠረው አቶ ደሴ ካህሳይም ተካቷል፡፡
ተከሳሾቹ ከዓመት በፊት የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለው ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክስ የተመሠረተባቸው፣ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ወንጀል ሆኖ የተደነገገውን ለሽብርተኛ ድርጅት ውስጥ መሳተፍን ተላልፈዋል በሚል ነው፡፡

ተከሳሾቹ ከላይ የተጠቀሱትን የሕግ ድንጋጌዎች በመተላለፍ፣ የሰው ሕይወት በማጥፋትና ንብረት በማውደም፣ በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ፖለቲካዊ ሥልጣን ለመያዝ እየተንቀሳቀሰ ካለው የግንቦት ሰባት ድርጅት ጋር አብሮ ለመሥራት መዘጋጀታቸውም ተጠቅሷል፡፡ ከአዲስ አበባ ተነስተው በባህር ዳር፣ በጎንደርና በሁመራ አድርገው ወደ ኤርትራ ለመሻገር ሲንቀሳቀሱ በፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውንም፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ ያቀረበውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤቱ፣ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ታኅሳስ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ብይን ሰጥቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን (141) በዝርዝር ጽፈው አቅርበዋል፡፡ ከምስክሮቻቸው መካከል ለአቶ በረከት ስምዖን፣ ለአቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ ለአቶ አዲሱ ለገሰ፣ ለወ/ሮ ሮማን ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ለአቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሀት)፣ ለወ/ሮ ፍሬ ሕይወት አያሌው፣ ለዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል፣ ለጄኔራል ሳሞራ የኑስና ለአቶ ቴዎድሮስ ሐጐስ እነሱ መጥሪያ ለማድረስ እንደማይችሉ (ከፍተኛ ባለሥልጣናት በመሆናቸው) በፍርድ ቤቱ በኩል እንዲደርሳቸው እንዲደረግ አመልክተዋል፡፡

ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፣ ለዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ለአቶ አስገደ ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ገብሩ አሥራት፣ ለወ/ሮ አረጋሽ አዳነ፣ ለአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ (ዝዋይ)፣ ለአምስት ጦማሪያን፣ ለጠበቃ ተማም አባቡልጉ፣ ለኢንጂነር ይልቃል ጌትነት (ሰማያዊ ፓርቲ) ጨምሮ በድምሩ 141 የመከላከያ ምስክሮችን በመቁጠር ለፍርድ ቤቱ አሳውቀዋል፡፡ ረቡዕ ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ተከሳሾቹ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

እነ ኦኬሎ አኳይ እስከ 9 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ተቀጡ

የፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት እነ ኦኬሎ አኳይ እስከ ዘጠኝ ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ቀጣ፡፡ ተከሳሾችም ሆኑ የፌደራል አቃቤህግ የቅጣት አስተያየታቸውን ሚያዚያ 17 ቀን 2008ዓ.ም ለፍርድቤቱ ያመለከቱ ሲሆን ፍረድቤቱ የግራ ቀኙን አይቶ ዛሬ ሚያዚያ 19 ቀን 2008 የእስራት ፍርድ ስጥቷል፡፡

Okello Akuay

አቃቤህግ ተከሳሾች የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ስራ ላይ ውሎ በነበረበት ግዜም ጭምር ወንጀል መፈፀማቸውን ቀጥለውበት የነበረ መሆኑን ገልፆ ፍርድቤቱ ቅጣት ሲያስተላልፍ በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ እንዲያደርግ ጠይቆ የነበረ ቢሆንም ፍርድቤቱ የወንጀል ድርጊቱ የተፈፀመው በአመዛኙ የተሸሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ከመውጣቱ በፊት በመሆኑ እና በድርጊቱም የተጎዳ ሰውም ሆነ ንብረት ስለሌለ የአቃቤውን ጥያቄ አልተቀበለም፡፡

ተከሳሾች ሲያደርጉት የነበረው እንቅስቃሴ በሰው ህይወት፣ንብረት እና አጠቃላይ በሀገር ደህንነት ላይ ሊያስከትል ከሚችለው ችግር አንፃር በመመዘን የተከሳሾቹን የወንጀል አፈፃፀም በከባድ በማለት ፍርድቤቱ መድቦ እንዲቀጡ አቃቤህግ የጠየቀውን ውድቅ ያደረገው ፍርድቤቱ ተከሳሾች የወንጀል ተግባሩን የፈፀሙት ቡድን መስርተው በስምምነት በመሆኑ እንደማክበጃ የወ/ህ/ቁ 84/1/መ/ እንዲያዝለት አቃቤህግ ያመለከተውን ተቀብሎታል፡፡

ተከሳሾች በበኩላቸው ከዚህ በፊት በምንም አይነት ወንጀል ተከሰው የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዳልተላለፈባቸው፣ሁሉም ተከሳሾች የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሰለመሆናቸው ታሳቢ ተደርጎ ቅጣት እንዲቀልላቸው ያመለከቱተን ፍርድቤቱ የተቀበለ ሲሆን አንደኛ ተከሳሽ በጋምቤላ ክልል ከ1978 እስከ 1992 ለ13 ዓመታት በጤና ቢሮ የተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች እስከ ክልሉ ፕሬዝዳንትነት የክልሉን ህዝብና የፌደራሉን መንግስት ያገለገሉ መሆኑን ጠቅሰው እንደ ቅጣት ማቅለያ እንዲያዝላቸው ያመለከቱትን ግን ፍርድቤቱ አልተቀበለውም፡፡

በዚህም አንደኛ ተከሳሽ ኦኬሎ አኳይ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን እና የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል በቡድን ሆኖ የአመራር ሚናን በኃላፊነት በመምራታቸው በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡

ሁለተኛ ተከሳሽ ዴቪድ ኡጁሉ የጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል እና የውጪ ጉዳይ ኃላፊ በመሆን የጋምቤላ ክልልን ከፌደሬሽኑ ለመገንጠል ቡድኑን በአመራር በማገልገላቸው በተመሳሳይ በዘጠኝ አመት ፅኑ እስራት ቀጥቷል፡፡

ከሶስተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ተከሳሾች (ኡቻን ኦፔይ፣ ኡማን ኝክየው፣ ኡጁሉ ቻም፣ አታካ ኡዋር እና ኡባንግ ኡመድ ) በጋምቤላ ህዘቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋህነን) አባል በመሆን የተለያዩ ተሳትፎዎችን በማድረጋቸው ሁሉም ተከሳሾች በሰባት አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድቤቱ ወሰኗል፡፡
በሰኔ ወር 2006ዓ.ም በፌደራል አቃቤህግ ክስ የተመሰረተባቸው እነ ኦኬሎ አኳይ ለሁለት አመት ከማንኛውም ህዝባዊ መብቶቻቸው እንዲታገዱ ፍርድቤቱ አዟል፡፡
ምንጭ፡-http://ehrp.org