የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ሁለት የስራ ሀላፊዎችን ከሃላፊነታቸው አነሳ

የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ኦህዴድ/ ማዕከላዊ ኮሚቴ ከየካቲት 25 ጀምሮ ለአምስት ቀናት በአዳማ ከተማ ባካሄደው ጉባኤ ሁለት የስራ ሀላፊዎችን ከሀላፊነታቸው እንዲነሱ በማድረግ እና የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቋል።
የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ የስራ ሃላፊዎቹ ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ የተደረገው በአመራር ችግር መሆኑን አስታውቋል።
በዚህም 1ኛ የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሞቴ የስራ አስፈጻሚ አባል እና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባል እንዲሁም የኦህዴድ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ ዳባ ደበሌ ሲሆኑ፥ በታየባቸው የአመራር ችግር ምክንያት ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ መወሰኑን እና ከኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባልነት ተነስተው ነገር ግን የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ወስኗል።
2ኛ የኦህዴድ እና የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ አባል እና የኦሮሚያ ክልል የእርሻ እና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ሃላፊ አቶ ዘላለም ጀማነ ሲሆኑ፥ እስከ ቀጣዩ የድርጀቱ ጉባኤ ድርስ ከማንኛውም የድርጅት እንቅስቃሴ መታገዳቸውን ድርጅቱ ማስታወቁን ፋና ቢሲ ዘግቧል፡፡
ምንጭ፡ http://www.fanabc.com/index.php/news/item/1428
በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ በከፍተኛ ደረጃ ለተቃዋሚዎች ድጋፍ እየሰጠ መሆኑን ተከትሎ ገዥው ፓርቲ ኦህዴድ/ኢህአዴግ ምርጫውን ከወዲሁ ማስጀመሩ ተገለፀ
ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ገዥው ፓርቲ ምርጫውን ከአሁኑ እንደጀመረው ምንጮች ገለፁ፡፡ በተለያዩ የኦሮሚያ ክፍሎች የገዥው ኢህአዴግ ካድሬዎች መራጮችን በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ እያደራጁ “ኦህዴድ/ኢህአዴግን መርጫለሁ” በሚል እያስፈረሙና ፎርም እያስሞሉ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጋንታ፣ በሴልና በኔትወርክ ተደራጅተው ‹‹ኦህዴድን መርጠናል›› ብለው እንዲፈርሙ የተደረጉ ዜጎች ፎርሙን ከሞሉበት ቀን ጀምሮ የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ መሪዎቻቸው እንደሚሰጡ ታውቋል፡፡ የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ መሪዎችም ኢህአዴግን ከአሁኑ መርጠዋል ተብለው የተደራጁ ዜጎችን ስምና የምርጫ ካርድም ለኦህዴድ/ኢህአዴግ ከፍተኛ ካድሬዎች እንደሚሰጡ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡
የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ግንቦት 16 ቀን በፊት የምርጫ ካርዳቸውን ለጋንታ፣ ለሴልና ለኔትወርክ መሪዎች የሚሰጡትን ዜጎች ቤት ለቤት እየዞሩ እያስፈረሙ እንደሚገኙ ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡ በጋንታ፣ ሴልና ኔትወርክ ተደራጅተው ኦህዴድ/ኢህአዴግን ከአሁኑ እንደመረጡ በፊርማቸው አረጋግጠዋል የተባሉት ዜጎች ግንቦት 16 ቀን 2007 ዓ.ም በሚደረገው ምርጫ እንደማይሳተፉ የታወቀ ሲሆን አብዛኛዎቹ በግዳጅና በማስፈራሪያ እየሞሉ እንደሚገኙ ተገልጾአል፡፡
የጋንታ፣ የሴልና የኔትወርክ እንዲሁም የመራጮች ስምና ፊርማቸው እየሰፈረበት ከግንቦት 16 በፊት እንደመረጡ ተደርጎ ዜጎች እንዲሞሉት የሚደረገውና ከስር የሚታየው ቅጽ ካድሬዎች በአርሲ ዞን በቆጅ ወረዳ ቤት ለቤት ሲያስሞሉ መገኘቱ ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይም በምዕራብ ኢትዮጵያ እዚሁ ኦሮሚያ ክልል ተመሳሳይ ድርጊት እየተፈፀመ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን፤ በተለይ በዶ/ር መረራ ጉዲና የሚመራው ቡድን በአካባቢው የተጠናከረ የምርጫ ቅስቀሳ በማድረጋቸውና ኦፌኮ/መድረክ በአካባቢው ህዝብ ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘቱን ተከትሎ የኦህዴድ/ኢህአዴግ ካድሬዎች ከአካባቢው የፀጥታ ኃይል ጋር በመሆን የተቃዋሚ ደጋፊዎችና የአካባቢው እጮዎች ጭምር ድብደባና እስራት እየፈፀመባቸው መሆኑን ምንጮችን ጠቅሶ ነገረ-ኢትዮጵያ ዘግቧል ፡፡
