በቅርቡ ከእስር ከተፈቱት መካከል ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና አቶ አንዱዓለም አራጌን ጨምሮ 11 ሰዎች በድጋሚ ታሰሩ
(ዳጉ ሚዲያ) እሁድ መጋቢት 16 ቀን 2010 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ወጣቶች በቅርቡ ከእስር ለተፈቱት ጋዜጠኞች፥ የመብት ተሟጋቾች እና ፖለቲከኞችን “እናመሰግናለን” በሚል በጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት በተዘጋጀ መርሃ ግብር ላይ ተገኝተው ከነበሩት መካከል 11 ያህሉ በፖሊስ ታግተው መቆየታቸው ታውቋል። ፖሊስም ታጋቾቹን ከጋዜጠና ተመስገን ደሳለኝ ቤተሰብ መኖሪያ ቤት በበርካታ የፖሊስ ኃይል በማጀብ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ስር በሚገኘው ጀሞ ፖሊስ ጣቢያ የወሰዷችው ሲሆን፤ ከምሽቱ 4፡30 ሰዓት ላይ ጎተራ ወደ ሚገኘው ፖሊስ መምሪያ ወስደው እንዳሰሯቸው ለማወቅ ተችሏል።
አቶ አንዱዓለም አራጌ ኤና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ
እንደምንጮች መረጃ ከሆነ፤ ለእገታው ምክንያት የሆነው በመርሃ ግብሩ ላይ የገዥው ስርዓት መለያ የሌለበት የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ተሰቅሎ በማየታቸው በተቆጡ የአገዛዙ ፖሊሶች በፈጠሩት አለመግባባት መሆኑ ተጠቁሟል። በተለይም በስፍራው የነበረው መርሃ ግብር ከተጠናቀቀ በኋላ በስፍራው ደርሰው የነበሩ ሁለት ፖሊሶች ሰንደቅ ዓላማውን ከተሰቀለበት በግድ ነጥቀው በመውሰድ ድርጊቱን ስብሰባ አድርጎ በመቁጠር ለምን አላስፈቀዳችሁም በሚል ለድርጊቱ ኃላፊነቱን የሚወስድ አካል ማናገር እንፈልጋለን በማለት ፖሊሶቹ ታዳሚውን ለማስፈራራት ሞክረዋል። ይህንንም ተከትሎ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝም የነበረው መርሃ ግብር የተለመደ የማኀበራዊ ወዳጅነት እንጂ ስብሰባ አይደለም፥ ለማኀበራዊ ወዳጅነት ፈቃድ እያስፈልግም ሲል ምላሽ በመስጠቱ በተለይ ሲያናግረው የነበረውን ፖሊስ እንዳስቆጣ ለማወቅ ተችላል።
በጋዜጠኛው ምላሽ ደስተኛ ያልነበረው ፖሊስ ጉዳዩን በማክረር ኃላፊነቱን የሚወስዱ 3 ሰዎችን ማናገር እንፈልጋለን ወደሚል እልህ ውስጥ መግባቱን ተከትሎ አቶ አንዱዓለም አራጌ ጉዳዩን ለማረጋጋት በሚል ፖሊሱን ለማግባባት ቢሞክርም፤ ፖሊሱ ፈቃደኛ ሳይሆን ቀርቷል። በመጨረሻም አቶ አንዱዓለም አራጌ ለፖሊሱ ” ችግር አለ ብላችሁ ምታምኑት ነገር ካለ እና ማናገር ከፈለጋችሁ ሁላችንንም ወስዳችሁ ማናገር ትችላላችሁ፤ ከዛ ውጭ በተናጥል ኃላፊነት የሚወስድም ሆነ የሚያናግር የለም” የሚል ምላሽ ይሰጣል።
በተሰጣቸው ምላሽ ደስተኛ እና ፈቃደኛ ያልሆነው ፖሊስ በመርሃ ግብሩ ላይ ከተሳተፉት መካከል በወቅቱ በስፍራው የነበሩትን እንዳይንቀሳቀሱ በማስገደድ፤ በያዘው የፖሊስ መገናኛ ሬዲዮ ወደበላይ አለቆቹ በመደወል በአካባቢው ከፍተኛ ችግር እንዳለ እና ለዚህም በርካታ የፖሊስ ኃይል እንዲታዘዝለት ጥሪ ያስተላልፋል። ከተወሰኑ ደቂቃዎች በኋላም በተሽከርካሪ መኪና ተጭነው የመጡ በርካታ ፖሊሶች የጦር መሳሪያዎቻቸውን በመደገን አካባቢውን በመቆጣጠር በስፍራው በቅርቡ ከእስር ከተፈቱት እና በወቅቱ የ “እናመሰግናለን” ሽልማት መርሃ ግብር ከተጠናቀቀ በኋላ በስፍራው የነበሩትና ከእስር ተለቀው የነበሩ 11 የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች አቶ አንዱዓለም አራጌ፥ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፥ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ፥ ጋዜጠኛ እና ጦማሪ በፈቃዱ ኃይሉ፥ ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁን፥ ጦማሪ ዘለዓለም ወርቅአገኘሁ፥ የመብት ተሟጋች ወጣቶች አቶ ስንታየሁ ቸኮል፥ አቶ አዲሱ ጌታነህ፥ ወ/ት ወይንሸት ሞላ፥ አቶ ይድነቃቸው አዲስ እና አቶ ተፈራ ተስፋዬ በድጋሚ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለዋል።
ፖሊስ አግቶ ያሰራቸውን 11 ሰዎች ለምን እንደሆነ እስካሁን በይፋ የሰጠው ማብራሪያም ሆነ ምክንያት የለም። ይሁን እንጂ የታገቱት ጋዜጠኞችና የመብት ተሟጋቾች ታፍነው ተወስደውበት ከነበረው ጀሞ ፖሊስ ጣቢያ ማምሻውን ጎተራ ፊትለፊት ወደሚገኘው የንፋስ ስልክ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ እንደታሰሩ ለማወቅ ተችሏል። ጋዜጠኞቹ እና የመብት ተሟጋቾቹ በታሰሩብት ዕለት ቀደም ሲል በቅርቡ በሀገሪቱ ላለፉት 3 ዓመታት ጀምሮ ያልተቋረጠውን የፀረ ጭቆና አገዛ ህዝባዊ ተቃውሞን ተከትሎ በቅርቡ ከእስር ከተፈቱት በርካታ የፖለቲካና የህሊና እስረኞች ጋር የሰማያዊ ፓርቲ ባዘጋአጀው ተመሳሳይ መርሃ ግብር ላይ ተሳትፈው ካጠናቀቁ በኋላ ተጨማሪ በሌሎች በጎ ፈቃድ ወጣቶች ባዘጋጁት መርሃ ግብርን አጠናቀው ርስ በርስ በመጨዋወት ላይ እያሉ መታሰራቸውን ለማወቅ ተችሏል።
በአሁን ወቅት ሀገሪቱ ለ6 ወራት በሚቆይ የአስቸኳይ አወጅ ስር ሆና በወታደራዊ ዕዝ ቁጥጥር ስር መውደቋ ይታወቃል።
የጣይቱ ልጆች ፤የኢትዮጵያ ደም መላሾች
አድማሱ ገበየሁ (ዶ/ር፣ ኢንጂነር)
(ጥቅምት 25 ቀን 2009 ዓ.ም)
ጣይቱ አሰኔ በወሎ ክፍለ-ሀገር በቦረና አውራጃ በጫቀታ ወረዳ ልዩ ስሙ ጅሩ ጉጣ ከተባለው ቀበሌ ተወለደች። ገና ልጅ እንዳለች ባሻ ዘለቀ ላቀውን አገባች። ዘለቀ የተወለደው በወሎ ክፍለ-ሀገር፡ ቦረና አውራጃ፡ ጫቀታ ም/ወረዳ፡ ልዩ ስሙ ገዛዛ አቦ ከተባለው ቀበሌ ነው። ጣይቱና ዘለቀ ሁለቱም የጫቀታ ተወላጆች ሲሆኑ መኖሪያቸው ጅሩ ጉጣ (ከጣይቱ ትውልድ ቦታ) ነበር።
የጣይቱ አሰኔ አባት አሰኔ ወዳጅ (አባ ጨፍልቅ) ይባላሉ። አባ ጨፍልቅ የንጉሥ ሚካኤል ባለሟልና የአንድ ክፍለ ጦር አዛዥ ነበሩ። አባ ጨፍልቅ አድዋ ጦርነት ላይ ሲዋጉ ጥይት አልቆባቸው አንድ ጠላት በአለንጋ መተው ገድለዋል ይባላል። ይህንን በተመለከተ፡
“ሰው ሁሉ የሚገል በጎራዴ ነው፤
ሰው ሁሉ የሚገል በመሣሪያ ነው፤
የእኛ አሰኔ ወዳጅ በአለንጋው ነው።”
የሚል ተገጥሞላቸዋል። አባጨፍልቅ “የኢትዮጵያ ዳር ድንበር ባሕር ጠረፍ ነው።” ይሉ እንደነበር ይነገራል። አባ ጨፍልቅ በዘወትር ፀሎታቸው “ድንበር አልፎ የገባውን ጠላት (ጣልያና ፈረንሳይን) ሳናባርር ሞትን እንዳትልክብኝ፣ ያዝልኝ።” ይሉ ነበር ይባላል።
ጣይቱ በ1904 ዓ.ም በላይ ዘለቀን ወለደች። ከሁለት ዓመት በኋላም በ1906 ዓ.ም እጅጉ ዘለቀን ወለደች። እጅጉ እንደተወለደ የጣይቱ ባለቤት ባሻ ዘለቀ ከቤተሰብ ተለይቶ ወደ ዳር አገር ዘመተ። ብዙም ሳይቆይ ጣይቱ መሸሻ አደምን አገባች። መሸሻ አደም የተወለደው በወሎ ክፍለ-ሀገር፡ ቦረና አውራጃ፡ በሜታ ም/ወረዳ፡ ልዩ ስሙ ወርቄ አቦ በተባለው ቀበሌ ነው። ጣይቱ ሦስተኛ ልጅ አያሌው መሸሻን በ1908 ዓ.ም ከመሸሻ ወለደች።
ጣይቱ ሁለት ባሎች አከታትላ ብታገባም አብራ ለመኖር ግን አልታደለችም። የበፊተኛው ማለትም ዘለቀ ላቀው ከልጅ ኢያሱ ሠራዊት ጋር ተቀላቀለ። በጥቅምት ወር 1909 ዓ.ም ደግሞ የአያሌው አባት መሸሻ አደም የንጉሥ ሚካኤልን የዘመቻ ጥሪ ተቀብሎ ሰገሌ (ሸዋ ደብረ ብርሃን አጠገብ) በተደረገው ጦርነት ለመሳተፍ ዘመተ። ግን አልተመለሰም በዚያው ቀረ።
ስለ ጣይቱ ልጆች (በላይ፡ እጅጉና አያሌው) ታሪክ መነሻ ለማግኜት ይረዳ ዘንድ ስለ ባሻ ዘለቀ ማወቅ ይጠቅማል። ባሻ ዘለቀን ለመዝመት ያነሳሳው ልጅ ኢያሱ የኢትዮጵያን ወሰን መልሶ እስከ ባሕር ጠረፍ ለማድረስ ብርቱ ምኞት እንደነበረው ከአማቱ (ከጣይቱ አባት ከሀሰኔ ወዳጅ) ይሰማ ስለነበር ነው። ልጅ ኢያሱ ከመንገሡ በፊት ጣልያንና ፈረንሳይን ከአገራችን በማባረር ጠረፋችንን ለማስከበር አስቧል የሚል ወሬ በስፋት ይሰማ ነበር። ይንንም ለማሳካት ልጅ ኢያሱ ከጀርመንና ከቱርክ ጋር ተፈጣጥሟል ተብሎም ተወርቶ ነበር። ባሻ ዘለቀ ላቀው ከልጅ እያሱ ሠራዊት ጋር ተቀላቀለ። ከልጅ ኢያሱ ጋር ሆኖ በአፋር፡ በጅቡቲ መስመር (ሶማሌ)፡ እና በሐረር አካባቢ ሲንቀሳቀስ ቆዬ።
መስከረም 17 ቀን 1909 ዓ.ም የመስቀል ዕለት ባሻ ዘለቀ ከልጅ ኢያሱ ጋር ሐረር ነበር። አኩለ ቀን ሲሆን “የሸዋ ሰው አዲስ አበባ ላይ ስብሰባ አድርጎ አዲስ መንግሥት አቋቁሟል፤ ወይዘሮ ዘውዲቱን ንግሥት፤ ደጃማች ተፈሪን ደግሞ አልጋ ወራሽ አድርጎ ሾሟል” ተብሎ ተነገረ። ብዙም ሳይቆይ የኢያሱ አባት ንጉሥ ሚካኤል የልጃቸውን ሥልጣን ለማስመለስ ወደ ሸዋ ዘምተዋል የሚል መልእክት ደረሰ። የልጅ ኢያሱም ሠራዊት ከንጉሥ ሚካኤል ሠራዊት ጋር ለመቀላቀል ገሠገሠ። ይሁን እንጂ ንጉሥ ሚካኤል በለስ እንዳልቀናቸውና እንደተማረኩ ተረጋገጠ።
ለባሻ ዘለቀ ሌላ ተጨማሪ መርዶ ደረሰው። “መስከረም 22 ቀን 1909 ዓ.ም. በቤተ መንግሥት ሹም ሽር ሆኖ የሰላሌው ገዢ ደጃዝማች ካሣ ኃይሉ በግዛታቸው በሰላሌና በላስታ ላይ እንሳሮና መራቤቴ፣ ደራ፣ ሚዳ፣ ቦረና ተጨምሮላቸው ራስ ተባሉ።” የሚል መረጃ ደረሰው። ባሻ ዘለቀ ወደ ቦረና ቢመለስ አደጋ ላይ እንደሚወድቅ ገመተ። ያለው አማራጭ እስከመጨረሻው ከልጅ ኢያሱ አለመለየት ነው ብሎ ወሰነ።
ባሻ ዘለቀ ከልጅ ኢያሱ ጋር በወሎና በትግራይ አካባበቢ ለአምስት ዓመታት ያህል ሲንቀሳቀስ ቆዬ። ልጅ ኢያሱ ተይዞ ኮረማሽ ታሰረ፤ ብዙም ሳይቆይ በኅዳር 29 ቀን 1914 ዓ.ም ወደ ፍቼ ተዛውሮ በሰላሌ ገዢ በራስ ኃይሉ ጠባቂነት እንዲታሰር ተደረገ። ከልጅ ኢያሱ መታሰር በኋላ ባሻ ዘለቀ ወደ ቦረና ሄዶ የዘመድ አዝማድ ከለላ ማግኘትን መረጠ። በጫቀታ ወረዳ ልዩ ስሙ ጣቀት መደሎ ከተባለው ቀበሌ ተቀምጦ እንዳለ አንድ ሰው በእጁ ጠፋበት (ሞተበት)። ከዚያም ሸፈቶ በጎጃም ክፍለ ሀገር በቢቸና አውራጃ በእነማይ ወረዳ ልዩ ስሙ ለምጨን ከተባለው ቀበሌ እንደተቀመጠ ከደብረማርቆስ በታዘዘ ጦር ተገደለ።
በላይ ዘለቀና እጅጉ ዘለቀ አባታቸው ሲሞት ገና የ10 እና የ12 ዓመት ልጆች ነበሩ። እድሜያቸው ከፍ ሲልና አካላቸው ሲጠነክር አባታቸውን በጥቆማ መርቶ ያስገደለውን ግራዝማች ደርሰህ የተባለውን ሰው ገድለው ጫካ ገቡ። የእናታቸው ልጅ ታናሽ ወንዳማቸው አያሌውም በሽፍትነቱ ተቀላቀላቸው።
ሦስቱ ወንድማማቾች በሽፍትነት በአባይ ወንዝ ዳርቻ ባለው በርሃ በመንቀሳቀስ ከየዘመዱ ስንቅ እያሰባሰቡ ጥቂት ዓመታት እንዳሳለፉ የጣልያን ጦር ደብረማርቆስ መግባቱ ተሰማ። እነበላይም የእናትና የአባታቸውን ወገን ሰብስበው ምን ማድረግ እንዳለባቸው ተመካከሩ። ጣልያን በ1928 ዓመት አገራችንን ሲወር የጣይቱ ልጆች በላይ ዘለቀ 24፡ እጅጉ ዘለቀ 22፡ እና አያሌው መሸሻ 20 ዓመታቸው ነበር። የአክስታቸው ልጅ ሺፈራው ገርባውም 17 ዓመቱ ነበር።
በላይም ዘለቀም እንዲህ ሲል ጠየቀ። “ፋሽስት ጣልያን እየገፋ መጣ። ንጉሡም ከማይጨው ሸሽተው አዲሰ አበባ ከገቡ በኋላ፤ የሚወልዷቸውንና የሚወዷቸውን ይዘው፤ የሚችሉትን ያህል የኢትዮጵያን ገንዘብ ዘርፈው፤ ያልቻሉትን ለዘራፊ አጋልጠው፤ ከነቤተሰቦቻቸው ከድተው ባሕር ማዶ ሄዱ ይባላል። ስለዚህ እኛስ ይህንን የመጣ እንግዳችንን እንዴት ነው የምናስተናግደው አስኪ መላ አምጡ።” ብሎ ጠየቀ። በመጨረሻም ከብዙ ምክክር በኋላ የተሰበሰበው ቤተሰብና ዘመድ ዝማድ በሙሉ ጠላትን ለመፋለም ወሰነ።
እነ በላይ በመቀጠልም በየአካባቢው ላሉት ሽፍቶች መልእክት ላኩ። “ሽፍትነትም ወግ የሚኖረው አገር አማን ሲሆን ነው። ሁላችንንም የሚያጠፋ የከፋ የውጭ ጠላት መጥቶብናል። ሁላችንም አንድ ልብ ሆነን ልንመክተው ይገባል። የሚያድኑን ደመኞቻችን ከጠላት የከፉ አይሆኑም። የእኛው ወገኖች ናቸው። ሽማግሌ እየላክን አገር አማን ሲሆን የጉማ ሥርዓት ፈጽመን (ማንኛውም የሚጣልብን ካሳ ክሰን) ለመታረቅ መቁረጥ አለብን። ደመኞቻችንም እኛም (ሽፍቶቹ) አንድ ላይ ካልሆንን ከምድር በጠመንጃና በመድፍ ከሰማይ በሮቢላ የመጣብንን ጠላት መመከት አንችልም። እንግዳችን በተደጋጋሚ አገራችንን የደፈረው ጠላታችን ጣልያን ነው። ሕፃን፡ ሴት፡ ሽማግሌ የማይለይ አረመኔ ነው። ሃሳባችንን የወደዳችሁ ሁሉ የሚቀጥለው እሁድ … እኛ ዘንድ መጥታችሁ እንመካከር” የሚል ደብዳቤ ከእነ አንባቢው ላኩ። (ሚስጢሩን ጠላት እንዳይደርስበት በማሰብ የመሰብሰቢያ ቦታው ስም የሚነገረው በቃል ብቻ ነበ፡፡)
በስብሳው ቀን በተባለው ቦታ የአካባቢው ሽፍታ ሁሉ ልቅም ብሎ መጣ። በላይም ዘለቀም እንዲህ ሲል ተናገረ። “እኛ የጣይቱ ልጆች፡ ቤተሰብና ዘመድ አዝማድ በሙሉ የአባይን ወንዝ ይዘን፡ የአለቱን ድንጋይ ተንተርሰን፡ አሸዋውን ለብሰን፡ ዋሻውንና ተራራውን ምሽግ አድርገን፡ የመጣውን ጠላት ለመመለስ ወስነናል። ከዚህ ፍንክች አንልም። እናት ሀገራችን ስትደፈር ከማየት ሞታችንን እንመርጣለን። የፈራህ ልቀቀን። ለአገር ለወገንህ ለመሰዋት የምትፈልግ ሁሉ እኛን ተከተለን።” ብሎ በጣይቱ ልጆች፡ ቤተሰብና ዘመድ አዝማድ ስም ቁርጥ ያለ ጥያቄ አቀረበ። ከዚያም ተሰበሰበው ሽፍታ ሁሉ ገባላቸው። ሽፍታው ሁሉ ላይከዳ መሣሪያውን እንዳጎረሰ አጋድሞ ዮሔ ቢሰት ዮሔ አይሳተኝ በማለት እየማለ ቃል ገባላቸው። በወቅቱ እስከ 200 የሚደርስ የሽፍቶች ሠራዊት አሰባሰቡ። በላይ ዘለቀንም የጎበዝ አለቃ አድርገው መረጡት። በኋላም ሌሎች ሽፍቶች ካያለበት እየወጡ ገቡላቸው።
ከበላይ ጋር ሆነው ጣልያንን ለመፋም ቆርጠው የተነሱት ጀግኖች ለጣልያን ካደሩት ባንዶች ጋር ተደጋጋሚ ፍልሚያ አደረጉ። ተደጋጋሚ በለስም ቀናቸው። ባደረጓቸው ጦርነትም ከገደሏቸውና ከማረኳቸው ባንዶች ላይ ብዙ መሣሪያ ገፈፉ። በርካታ ምርኮኞችንም ወደ አርበኛነት ለወጧቸው። ቀስ በቀስም የቦረና፡ የደራ፡ የደብረ ጉራቻ፡ የእንሳሮ፡ ሕዝብ አነ በላይን ተቀላቀለ። አብዛኛው የምሥራቅ ጎጃም ሕዝብም በትግሉ ተቀላቀለ፤ አርበኞችንም አቅፎ ደግፎ ያዘ።
በላይ ዘለቀ በውጊያ ለተማረኩት ባንዳዎች የሚያደርጋቸው ንግግሮች የብዙ ባንዳዎችን አሰላለፍ ለወጠ። ንግግሩም፡- “እናንተ ከጣልያን ታዛችሁ አገራችሁን በመክዳት በተደረገው ጦርነት ከሞት ተርፋችሁ የተማረካችሁ፣ ኢትዮጵያዊ የሆናችሁ ወገኖቻችን ሁሉ፣ አሁን በእኛ በኩል ምረናችኋል። እናት ሀገርህና ወገንህን የምትል ተከተለን፣ ወይም አርሰህ ብላ። ነገር ግን ሁለተኛ ለጠላት ገብተህ ብትገኝ ነገ እኛገኝሃለን።” የሚል ነበር። በዚህ አቀራረብም በየካቲት ወር 1929 ብቻ ደረቤን፡ ቅንቧትን፡ ባሰን፡ ሊበንን፡ ድድሜትን፡ ደጀንን፡ አምበልን፡ በጠቅላላው አስከ ጨሞጋ ያለውን አሣምነው እንዲከተላቸው አድርገዋል። በ1933 ዓ.ም ጦርነቱ ሊያበቃ ሲቃረብ የነበላይ ጦር በ102 ጦር አዛዦች የሚመራ 111, 000 ሠራዊት ነበረው። በሠራዊቱም ውስጥ የማዕረግ ስም የተሰጣቸው አርበኞች 986 ደርሰው ነበር።
በ1930 ዓ.ም የጣልያን ሠራዊት የበላይን ሚስት ሸክሚቱ አለማየሁንና እህቷን ዘውዲቱ አለማየሁን ገድለው ልጁን የሻሽወርቅ በላይን ማርከው ወሰዷት። ለበላይ ዘለቀም ልጁን ማግኘት ከፈለገ ማድረግ ያለበትን የሚያሳውቅ መልእት በጣልያን መንግሥት ስም ላኩለት።
በላይም ለጣልያን መንግሥት መልእክት የሰጠው መልስ እንደሚከተለው ነበር።“ይድረስ ለጣልያን መንግሥት ሰላም ላንተ ይሁን። የላክልኝን እንግዶች እነ ቀኛዝማች እጅጉ ለማን በአክብሮት ተቀብዬ በማስተናገድ ሥፍራ ሥፍራ ሰጥቻቸዋለሁ። ላንተ ግን ትርጁማን (አስተርጓሚ) ብለህ የላከውን እሌላ ቦታ ስትልክ እንዳይቸግርህ መልሼ ልኬልሃለሁ። ልጅህን እመልስልሃለሁ ለምትለው፣ ለአንድ ልጅ ብዬ እናት ሀገሬን ኢትዮያን ከድቼ ከአንተ ጋር አልታረቅም። ከዛሬ ጀምሮ በእኔ በኩል ያለውን ምኞትህን አንሳ። እኔን ፈልገህ ማጥፋት እንጂ አንዲት ልጅ ወስዶ ማስጨነቅና ማጉላለላት ደስ የሚልህ ከሆነ እንደፈለግህ አድርጋት። ሲሆን ለሷም የፈጠራት አምላክ እግዚአብሔር ፍቃዱ ከሆነ ከአንተው እጅ ላመጣት እችል ይሆናል። ጎጃምን በእንደራሴነት ልስጥህ የምትለው አንተ የሰው አገር ሰው ከምትሰጠኝ እኔው ሀገሬን አስተዳድረው የለምዎይ። የቦለቲካ ወሬህን ከምትነዛ የኢትዮጵያ አርበኛ እየቆማመጠ ለአሞራ ከሚሰጥህ፣ በዱር በገደሉ ወድቀህ ከምትቀር በመጣህበት መንገድ አገርህ ግባ!” ይላል።
የሻሽርቅ በላይም በ1930 ዓ.ም ፋሺስት ኢጣልያ ማርኮ እስከ ሮማ ተወስዳ በደረሰባት እንግልትና ሥቃይ ምክኒያት እግሯ ሽባ ሆነ። ከዚያም ወደ ቢቸና ተመልሳ በጣልያን ካምፕ በከባድ ጥበቃ ስር ሆነች። በግንቦት ወር 1932 ዓ.ም በታሰረች በሁለት ዓመቷ በአባቷ ብርታት ከቢቸና እስር ቤት አመለጠች።
በመስከረም ወር 1933 ዓ.ም ደጃዝማች ከበደ ተሰማ ከንጉሡ የተላከው ደብዳቤ አመጡ። መልእክቱም፡- “ይድረስ ለልጅ በላይ ዘለቀ፤ ሰላም ለአንተ ይሁን ሥራህንና ጥንክርናህን ሰምቻለሁ። በጣም የሚያስደስትና የሚያኮራ ሥራ በመሥራትህ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል። እኔም በመንገድ ላይ ነኝ። መጣሁ አይዞህ ጠንክር። የእግዚአብሔር ፍቃዱ ከሆና በዋናው ቤተመንግሥቴ ለመግባት የበቃሁ እንደሆነ ውለታህን በእጥፍ አድርጌ እመልሳለሁ። እስከዚያው ሰው ላክና መሣሪያ ከዚህ ከከሰላ አስወስድ። በተረፈ ጠንክር አይዞህ!” የሚል ነበር።
ጣልያን ተሸንፎ በ1933 ዓ.ም ከአገራችንን ሲወጣ የጣይቱ ልጆች በላይ ዘለቀ 29፡ እጅጉ ዘለቀ 27፡ እና አያሌው መሸሻ 25 ዓመታቸው ነበር። የአክስታቸው ልጅ ሺፈራው ገርባው ደግሞ 22 ዓመቱ ነበር።
በላይ ዘለቀ በደማርቆስ ከተማ ከንጉሡ ጋር በተገናኘ ጊዜ የሚከተለውን ተናግሮ ነበር። “በአምስቱ ዓመት የጠላት ወረራ ዘመን ውስጥ ከጣልያን ፋሽሽት ጋር በሰልፉ ያይዋቸውን ወንድሞቼን ይዤ በምዋጋበት ጊዜ እንደሥራ ችሎታቸውና እንደየአገልግሎታቸው የማዕረግ ስም ሰጥቻለሁ። ስለሆነም ሕዝቡን ለማስተባበርና ጦሩን ለማጠናከር፣ የጠላትንም ቅስም ለመስበርና ለማጥቃት ችያለሁ፤” ሲል ተናገረ።
ንጉሡም የበላይን ንግግር ካዳመጡ በኋላ፤ “አንተ የማዕረግ ስም የሰጠኸውን እኔ ከመጨመር በስተቀር አልቀንስም፤ መርቄልሃለሁ። ለእኔ የትናንትናው ሰልፍህና ሁኔታህ ብቻ ይበቃኛል። ደስታዬ ወሰን የለውም። በዋናው ቤተመንግሥቴ እንደገባሁ ያንተን ውለታ እመልሳለሁ፤” ሲሉ ተናገሩ። ቀጥለውም “አዲስ አበባ አብረኽኝ እንሂድ፤ አድርሰኝ፤” ሲሉ ንጉሡ ተናገሩ።
በላይም “እኔ አሁን አብሬዎት አልሄድም። ያለኝም እረፍት አሁን ነው። በጦር ሜዳም፡ በየበረሃው አጥንታቸው ረግፎና ተከስክሶ፣ ደማቸው ፈሶ፣ ሥጋቸው ለአሞራ ሲሳይ በመሆን ለአገራችን ሲሉ የተሰውትን የወንድሞቼን አጽም ከየረገፈበት ሰብስቤ በሥርዓት አስቀብራለሁ። ስለዚህ ከእርስዎ ዘንድ ወደፊት በጥቅምት ወር እመጣለሁ።” ብሎ ተናገረ። ንጉሡም “ጥሩ ሃሳብ ነው። መልካም ነው። እኔም ሃሳብህን እደግፋለሁ፤” ብለው ተናገሩ።
ጥቅምት ወር 1934 ዓ.ም በላይ፡ እጅጉና አያሌው አዲስ አበባ መጡ። ከዚያም የኢያሱን ልጅ ዮሐንስ ኢያሱን ለማንገሥ አድማችኋል በማለት በክቡር ዘበኛ ወታደሮች ተይዘው ታሰሩ። ጉዳዩ ሲጣራ እነበላይ በሤራው እንደሌሉበት ተረጋገጠ። ከጥቅምት እስከ ሰኔ ወር መጨረሻ ድረስ ዘጠኝ ወር ሙሉ ከአዲስ አበባ እንዳይወጡ በግዞት ቆዩ። በመጨረሻም ንጉሡ ቀደም ብለው ደብረማርቆስ ከበላይ ዘለቀ ጋር ሲገናኙ ለሠራዊቱ አዛዦች በበላይ ዘለቀ የተሰጣቸውን ማዕረግ መርቄያለሁ ያሉትን ለወጡት (ካዱ)። በአርበኛ መሪዎች የተሰጠው ማዕረግ ሁሉ ተቀነሰ። አስከነአካቴውም አንዳንዶቹ የተሰጣቸው ማዕረግ ሙሉ በሙሉ ተሰረዘ። ለበላይ ዘለቀም የደጃዝማችነት ማዕረግ ተሰጠው። ንጉሡ ደብረማርቆስ ሲደርሱ የገቡትን ቃል፡ አዲስ አበባ ሲገቡ መቀየራቸው (መካዳቸው) የጣይቱን ልጆች በጣም አስከፋ፤ አስቆጣ።
የጣይቱ ልጆችም አዲስ አበባ የመጡበት ጉዳይ ባለመሳከቱ እያዘኑ አኩርፈው ወደ ቢቸና ተመለሱ። በኋላም ንጉሡ በላይን አዲስ አበባ እንዲመጣ ቢልኩበት አሁን አይመቸኝም አልመጣም ብሎ ቀረ። እነበላይ የመጣው ቢመጣ ወደ ንጉሡ ላለመሄድ ወስኑ። የቅርብ ዘመድና ወዳጅ ያካተተ ሠራዊት አሰባስበው በተጠንቀቅ ሲጠባበቁ ቆዩ። (እዚህ ላይ መታወቅ ያለበት በጠላት ጊዜ የነበረው ያ ሁሉ ሠራዊት ከሁለት ዓመት በፊት የነበረው የአርበኞን በ1933 ዓ.ም መበተኑን ነው።
እንደታሰበውም በመጋቢት ወር 1935 ዓ.ም ከንጉሡ የታዘዘ በርካታ ሠራዊት ያለው ጦር እነበላይን ሶማ ደጋ ከተባለው ትልቅ ተራራና አምባ ላይ እንደመሸጉ ከበባቸው። ከንጉሡ ለሠራዊቱ የተሰጠው ትዕዛዝ፡ እነበላይን ከተቻለ ይዘው እንዲያመጡ ካልተቻለ ደግሞ ባሉበት እንዲደመሰሱ ነበር። የነበላይ ሠራዊት አሥር እጥፍ ቁጥር ካለው ከንጉሡ ሠራዊት ጋር ለ15 ቀናት ሌት ከቀን ተዋጋ። እነበላይ ጊዜው በረዘመ መጠን የውሃ ጥም ቢበረታባቸውም የያዙት ቦታ አመቺ በመሆኑ በርትተው ሲከላከሉ ሰነበቱ።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከንጉሡ ለበላይ የተላከ ደብዳቤ መጣ። ደብዳቤውም፡ “ይድረስ ለደጃዝማች በላይ ዘለቀ ሰላም ለአንተ ይሁን። በሰደድናቸው ዳኞች በሊጋባ በቀለ፡ በፊታውራሪ ይልማ በሺ፡ እና በአቶ ዳዊት አማካኝነት እንድትመጣ። እኛ በክፉ አናይህም። በክፉ ብናይህ ውድ ልጃንን ልዑል መኮንን ይሁንብን።” የሚል የመሃላ ደብዳቤው ላይ “ሞኣ አንበሳ ዘዕምነ ነገደ ይሁዳ እኛ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ስዩመ እግዚአብሔር” የሚል ማህተም ያለበትን ደብዳቤ ላኩ።
ይሁን እንጂ መተማመን ስለጠፋ ጦርነቱ እንደገና ተቀሰቀሰ። በሁለቱም ወገን ብዙ ሰዎች ሞቱ። እጅጉ ዘለቀ በከባድ ሁኔታ ግራና ቀኝ ታፋውን ተመታ። የጋሜዎች አዛዥ የነበረውም ልጅ ሺፈራው ገርባው ሞተ። በመጨረሻም በላይ የወንድሙን የእጅጉን ሕይዎት ለማትረፍ ሲል እጁን ለመስጠት ወሰነ።
በግንቦት ወር 1935 ዓ.ም አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ 12 ሚኒስትሮች ለሦስት ወር ያህል በዋናው ቤተመንግሥት ሲመረመሩ ቆይተው ውሣኔ ተሰጠ። ውሳኔውም፡- አንደኛ፡ በላይ ዘለቀና እጅጉ ዘለቀ ቢቸና ተወስደው እንዲሰቀሉ። ሁለተኛ፡ አያሌው መሸሻና ሌሎች 15 የጦር አዛዦች በእድሜ ይፍታህ እንዲታሰሩ ተወሰነባቸው። ንጉሡም በሚኒስትሮች የተሰጠውን ውሳኔ አፀደቁት፡፡
በፍርዱ መሠረት በላይና እጅጉ ለመሰቀል ወደ ጎጃም ጠቅላይ ግዛት ሲጓዙ እንዳለ አባይ ሲደርሱ የጎጃምና የቦረና ሕዝብ አንጎራጉሯል ማለትን ስለሰሙ እረብሻ እንዳይፈጠር በማለት የአባይ ውሃ ሞልቶ አላሻግረን ብሎ ከለከለን አሰኙ። ከአባይ መልሰው አምጥተው በወሊሶ ከተማ በደጃዝማች በቀለ ወያ እጅ እንዲታሰሩ ላኳቸው። ቀጥሎም በቤተመንግሥት ግቢ ውስጥ እንዲታሠሩ ተደረገ። በታኅሳስ ወር 1937 ዓ.ም ከእስር ቤት ሰብረው ወደ ጎጃም ሲሄዱ ተያዙ። ከዚያም በላይ ዘለቀ በ33 ዓመቱ፣ እጅጉ ዘለቀ ደግሞ በ31 ዓመቱ ጥር 12 ቀን 1937 ዓ.ም አድስ አበባ ውስጥ ተሰቀሉ።
ስለእነ በላይ መሰቀል በርካታ ግጥሞች ተገጠሙ በዘፈንም ተሰምተዋል፤ ከነዚህም አንዱ እንዲህ የሚል ነበር።
“ተሰቀለ ቢሉኝ ሽጉጡ ነው ብዬ፣
ተሰቀለ ቢሉኝ ጠመንጃ ነው ብዬ፣
ተሰቀለ ቢሉኝ ዝናሩ ነው ብዬ፣
ለካስ በላይ ኖሯል ትልቁ ሰውዬ!”
ሌላው ደግሞ፡-
“አሁን ምን ያደርጋል እኔ ባበጃጅ፣
መማርህ ነበረ ላገር የሚበጅ፤”
እንዲሁም፡
ሰው ማለት፣
ሰው የሚሆን ነው፣
ሰው የሌለ ዕለት።
ወራሪ ጠላትን ለአምስት ዓመታት ያለመታከት ሌት ከቀን ወጥረው መግቢያ መውጫ ያሳጡት ጀግኖች የጣይቱ ልጆች በራሳችን መሪዎች እንደዋዛ በአደባባይ ተሰቀሉ። በዚህም ከጣይቱ ልጆች ጋር ሆነው ጣልያኖችንና ባንዳዎችን አሸንፈው አገራችንን ለድል ያበቁት አርበኞች ሁሉ በሁኔታው በጣም ተሸማቀቁ። አርበኝነትም በይፋ በአደባባይ የሚያስፎክር ጀብዱ መሆኑ ቀረ። እነበላይ ከተሰቀሉ በኋላ በርካታ አርበኞች በተሰጣቸው ማዕረግ እንዳይጠሩ ለቤተሰብና ለዘመድ አዝማድ አሳወቁ። በመሆኑም በቦረና ውስጥ በጣልያን ወረራ ጊዜ በተሰጠ የአርበኝነት ማዕረግ የሚጠራ አልነበረም። ከነበላይ ወዲያ ብሎ ሁሉም እርም ብሎ እርግፍ አድርጎ ተወው።
የጣይቱ ልጆች የትውልድ ሐረግ
በላይ ዘለቀ (የአርበኞች ጠቅላይ አዛዥ) ጥር ወር 1937 ዓ.ም በተወለደ በ33 ዓመቱ ተሰቀለ። እጅጉ ዘለቀ (የአርበኞች ምክትል ጠቅላይ አዛዥና የበረንታ ጦር አዛዥ) ጥር ወር 1937 ዓ.ም በተወለደ በ31 ዓመቱ ተሰቀለ። ሺፈራው ገርባው (የጋሜዎች አዛዥ) መጋቢት ወር 1935 በንጉሡ በታዘዘው ጦር ተገደለ። አያሌው መሸሻ (የመትረየስ ተኳሾች አዛዥ) ከ 1934 ዓ.ም ጀምሮ ለሰላሳ ዓመታት ቦንጋ በእስርና በግዞት ቆይቶ በ1964 ዓ.ም ተለቆ፣ በ1983 ዓ.ም አረፈ።
ጣይቱ አሰኔ … አባቷን አሰኔ ወዳጅን፤ ወንድሟን ለገሠ አሰኔን፣ ባሎቿን ዘለቀ ላቀውንና መሸሻ አደምን፣ ልጆቿን በላይ ዘለቀን ፡ እጅጉ ዘለቀን በሞት ተነጠቀች። ከሞት የተረፈው ሦሰተኛውና የመጨረሻው ልጇም አያሌው መሸሻ በእድሜ ልክ አሥራት ተፈርዶበት ወህኒ ቤት ገባ (1964 ዓ.ም ሲፈታም በሕይዎት አልነበረችም።) ጣይ እስከ ሕይወቷ መጨረሻ ድረስ ሁለት ስሜቶች ሲፈራረቁባት ነበር። በአንድ በኩል በቤተሰቦቿ በደረሰው እልቂት ምክኒያት ቀኑ ሲጨልምባትና ሃዘኑም ሲበረታባት ለጉድ የፈጠረኝ ምነው እኔን ቢያስቀድመኝ ትላለች። በሌላ ቡል ደግሞ የቤተሰቦቿ የአርበኝነት ገድል ልቧን በኩራት ይሞላዋል። ጣይቱ ባለፈችበት ሁሉ ከሕዝብ የሚሰጣት ከበሬታ በልጅቿ አኩሪ ታሪክ ምክኒያት በመሆኑ ፈጣሪን ታመሰግነናለች። ሞት ላይቀር! እንደደኔ ማን የታደለ እናት አለ ትላለች ጣይቱ፤ ወዲያው ደግሞ እንደ ሰው ልጅ ሳይዘሉ፡ ሳይጨፍሩ …. ትልና ለቅሶዋን ታቀልጠዋለች።
ጣይቱ ነፍስ ያወቁ ዘመዶቿን ብታጣም የልጅ ልጆቿን ማሳግን ሥራዬ ብላ ተያያዛው ነበር። የልጅ ልጆቿም የአባቶቻቸውን ታሪክ እንዲያውቁ የተቻላትን ያህል ሞክራለች። ስለ ጦርነቱና ስለ ልጆቿ ገድል በራሷ ብዙም ልትነግራቸው አትችልም ነበር። ይሁን እንጂ በተለያዩ ጊዜያት አብረው ዘምተው የነበሩ ዘመድ አዝማድ ወደ ሠፈሯ ሲመጡ ስለ ልጆቿ የአርበኝነት ገድል ለልጅ ልጆቿ እንዲያወጉላት ታደርግ ነበር። በተጨማሪም እሷ በራሷ ለልጅ ልጆቿ ያስተማረቻቸው ቁም ነገር ነበረ። ይኸውም የልጇን የትውልድ ሐረግ ለልጅ ልጆቿ ማሳወቅ ነበር። በመሆኑም የሚከተለውን የጣይቱን ልጆች የትውልድ ሐረግ መረጃ ያገኘሁት ጣይቱ ካሳደገቻቸው ከየሻሽ-ወርቅ በላይ ዘለቀና ከመንግሥቴ አያሌው መሸሻ ነው። እኔም በራሴ በኩል ከአባቴና ከእናቴ ማረጋገጫ የሚሆነኝ መረጃ አግኝቻለሁ።
በጣይቱ አሰኔ በኩል ያለው የትውልድ ሐረግ (ከበዳሳ አንስቶ እስከ ጣይቱ ልጆች) እነደሚከተለው ነው።
(1) በዳሳ፡ (2) ዋጁ፡ (3) ሜታ፡ (4) ገረሱ፡ (5) አቡ፡ (6) ጃርሶ፡ (7) ቢቂሊ፡ (8) ባቦ፡ (9) ድምቶ፡ (10) ወዳጅ (ወዳይ)፡ (11) አሰኔ (እንሰኔ)፡ (12) ጣይቱ፡ (13) በላይ፡ እጅጉና አያሌው፡፡
በዘለቀ ላቀው በኩል ያለው የትውልድ ሐረግ (ከዋዩ አንስቶ እስከ በላይና እጅጉ) እነደሚከተለው ነው።
(1) ዋዩ፡ (2) ጫንጮ፡ (3) ቂልጡ፡ (4) ገልገል፡ (5) ሃጌ፡ (6) ላቀው፡ (7) ዘለቀ፡ (8) በላይና እጅጉ፡
መሸሻ አደም በኩል ያለው የትውልድ ሐረግ (ከበዳሳ አንስቶ እስከ አያሌው) እነደሚከተለው ነው።
(1) በዳሳ፡ (2) ዋጁ፡ (3) ሜታ፡ (4) ገረሱ፡ (5) አቡ፡ (6) ጃርሶ፡ (7) ቢቂሊ፡ (8) ባቦ፡ (9) ዲዶ፡ (10) ጎበና፡ (11) ቦሩ፡ (12) ይመር፡ (13) አደም፡ (14) መሸሻ፡ (15) አያሌ፡፡
የሺፈራው ገርባውም የትውልድ ሐረግ (በእናቱ በአያህሉሽ ዘለቀ በኩል) እንደሚከተለው ነው።
(1) ዋዩ፡ (2) ጫንጮ፡ (3) ቂልጡ፡ (4) ገልገል፡ (5) ሃጌ፡ (6) ላቀው፡ (7) አያህሉሽ ዘለቀ (የዘለቀ ላቀው እህት፡) (8) ሺፈራው፡ (የሽፈራው የትውልድ ቦታ ወሎ ክፍለ-ሀገር፡ ቦረና አውራጃ፡ ወግዲ ወረዳ፡ መነ-ዲጋ ቀበሌ ነው።)
የራሴ የትውልድ ሐረግና የተወለድኩበት አካበባቢ
አስቲ ከአያቴ ከየሺ ሰምቤ (የአባቴ እናት) ስለራሴ የትውልድ ሀረግ የሰማሁትን ልንገራችሁ። አያቴ ከመቶ ዓመት በላይ ኖራለች። በርካታ ዘመዶቻችን እየመጡ የትውልድ ሐረጋቸውን እንድትነግራቸው ይጠይቋት ነበር። ዋነኛ መነሻቸው የቅርብ ዘመዳሞች እንዳይጋቡ ለመከላከል ነው። አያቴም ጥርት አድርጋ ትቆጥርላቸው ነበር። በዚህም ረክተው ይመለሱ እንደነበር ትዝ ይለኛል። ዘመዶቼ ከገጠር አዲስ አበባ ሲመጡም ለልጆቼ የሚነግሩት የትውልድ ሐረጋችንን ነበር። እንግዲህ ወደራሴው ልመልሳች፡፡
እኔ ራሴ (አድማሱ ገበየሁ) ከጣይቱ አሰኔ ጋር በ10ኛው ወዳጅ በሚባለው እገናኛለሁ፤ ከአንደኛው ማለትም ከበዳሳ ጀምሮ 14ኛ ትውልድ ላይ ነኝ፡፡እንዲሁም ከአያሌው መሸሻ ጋር በ13ኛው አደም በሚባለው እገናኛለሁ፤ ከአንደኛው ማለትም ከበዳሳ ጀምሮ 17ኛ ትውልድ ላይ ነኝ፡፡ በሌሎችም በተቀሩት በሁለቱ አያቶቼ በኩል ትውልድ ሐረጌ (1) በዳሳ፡ (2) ዋጁ፡ (3) ሜታ፡ ከሚባሉት ጋር ይገናኛል።
ይህ የትውልድ ሀረግ የሚያሳየው እኔ (አድማሱ ገበየሁ) በማንኛውም አቅጣጫ (በአራቱም አያቶቹ በኩል) ኦሮሞ መሆኔን ነው።
ዘመዶቼ የሚኖሩበትና እኔም በልጅነቴ ያደግሁበትና የተማርሁበት አካባቢ የሚገኘው በደቡብ ምዕራብ ወሎ ነው።
(1) የተወለድኩት ቦረና ወረዳ ውስጥ ዲቢ የሚባል አካባቢ ነው። መንደራችን መነ ገጃ (ፊንጫ) እየተባለ የሚጠራ ሲሆን፡ በርካታ ዘመዶቻችን የሚኖሩባቸው ጎረቤቶቻችን ደግሞ መነ-ከተሜ፡ መነ-ደርሶ፡ መነ-ቱፋ፡ መነ-ደግሉ ይባላሉ።እስከ 8ኛ ክፍል የተማርኩት መካነሰላም ከተማ የሚገኘው ቦረና ትምህርት ቤት ነው።
(2) ቦረና ወረዳ ውስጥ በርካታ የገጠር አካባቢዎች አውቃለሁ፤ ተዘዋውሬም ጎብኝቻለሁ። እነሱም፡- ሜታ (ጅሩ መነቡኮ፡ ወቦ፡ መነዶዩ፡ ወርቄ አቦ፡ ተዋ፡ ወርቄ አቡ፡ በታ፡ መነደጋ፡ አይቻል ቦነያ፡ መስካቤ፡) ወግሎ፡ (ዶክስ፡ መስካቤ፡ ቢሊ፡ ሴፋጢራ፡ አቡ አደሬ፡ ዲቢ ጪሪ፡ ዶንቆሮጫካ፡) ደምቢ፡ (ሰምቦ፡ ሶዬ፡ ደራሜ፡ ወርቄ መስቀሌ፡) አያና፡ ይባላሉ።
(3) በወግዲ ወረዳ (ሌንጮ፡ ለሚ፡ ጫቀታ፡ ጎረንጅ፡) አልፎ አልፎም ቢሆን ዘመዶች አሉኝ። በመሐል ሳይንት (ከደንቆሮ ጫካ እስከ ድንሳ፡) እና በለገሂዳ ወረዳ (አስከ ወለቃ ወንዝ፡) ጥቂት ዘመዶች አሉኝ።
በምሥራቅ ጎጃም ዞን ውስጥ በእነብሴ ሳር ምድር፡እናርጅ እናውጋ፡ እና ሸበል በረንታ ወረዳዎች (በአባይ ወንዝ ዳርቻዎች አከካባቢ) አልፎ አልፎም ቢሆን ዘመዶች አሉኝ።
ከላይ በጠቀስኳቸው አካባቢዎች የሚኖሩት ዘመዶቼ ሁሉ የትውልድ ሀረጋቸው የሚቋጠረው ሜታ በሚባለው ግንድ ነው። እስከ አያቶቼ ትውልድ ድረስ ያሉት መስማትና መናገር የሚችሉት ኦሮምኛ ቋንቋን ነበር። የአባቴ ትውልድ ትንሽ ትንሽ ኦሮምኛ መስማትና መናገር ይችል ነበር። ከእኔ ትውልድ ጀምሮ ኦሮምኛ መስማትና መናገር የሚችል ማግኜት በጣም አስቸጋሪ ነው። የእኔ ትውልድ (ሁላችንም ማለት ይቻላል) መስማትና መናገር የምንችለው አማርኛ ብቻ ነው።
ለአሁኑ ይህን ያህል ካልሁ፣ ወደፊት ስለኢትዮጵያ ፖለቲካ ያለኝን አስተያየትና አቋም ይዤ እቀርባለሁ።