Tag Archives: UDJ Party Ethiopia

“የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና ምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!” በምርጫ ቦርድ የፈረሰው አንድነት

በቅርቡ በ”ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ፈርሶ ዋና ጽህፈት ቤቱ በፖሊስና በደህንነት ቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ፤ የፓርቲው ጽህፈትም “ምርጫ ቦርድ” መርጫቸዋለሁ ላላቸው አካላት ከተላለፈ በኋላ አባላቱና አመራሩ ትግላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል፡፡ ፓርቲው የአንድነት ዓላማዎችና እሴቶች በገዥው ፓርቲ እና ምርቻ ቦርድ ህገ-ወጥ ሴራ እንደማይጠፋ ጥር 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-

udj

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)

ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የተሠጠ መግለጫ
********************************************************************************

የአንድነት ፓርቲ አላማዎችና እሴቶች በገዢው ፓርቲ እና በምርጫ ቦርድ ህገወጥ ሴራ አይጠፋም!!
***********************************************************************************
ገዢው ፓርቲ ለጻፋቸው ህጎችም ሆነ ይህን እንዲተገብሩ ኃላፊነት የወሰዱትን ሰዎች ክብር በሚያዋርድ መንገድ፤ በየደረጃው ያሉ ምርጫ ቦርድ ኃላፊዎችም ለመዋረድ ፈቃደኛ ሆነው በአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) አባላት አንድ ድምፅ ለማግኘት ለተቸገረ፤ ነገር ግን ለገዢው ፓርቲ ለመላላክ ቁርጠኛ ለሆነ ግለሰብ ዕውቅና ሰጥቻለሁ ማለቱ የሚታወስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ አንድነት ፓርቲ የተቋቋመበት መሰረት የምርጫ ቦርድ ዕውቅና ሳይሆን በእያንዳንዱ አባላት ዘንድ የሚቀጣጠለው የነፃነት ስሜት እና ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ የአንድነት ፓርቲን መንፈስ፣ አላማዎቸና እሴቶች በዚህ ዓይነት እኩይ ደባ ከአባላትና ደጋፊ አዕምሮ ማውጣት አይቻለም፡፡

የምርጫ ቦርድ ተብዬው ተቋም በገዢው ፓርቲ ደህንነት የተደራጁ የፓርቲ ጠቅላላ ጉባዔ አባላት ያልሆኑ ሰዎች ያካሄዱትን ህገወጥ ስብሰባ ጉባዔ ነው በማለት እውቅና ሰጥቻለሁ ሲል፤ የተሰበሰቡት ሰዎች የአንድነት አባላት መሆናቸውን እና የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ መሆናቸውን አረጋግጣችኃል ወይ? ለሚል ቀላል የጋዜጠኛ ጥያቄ መልስ መስጠት አልቻሉም፡፡ ዕቅዱም አንድነትን እንደተቋም ማፍረስ ስለነበር ይህን ሊያስፈፅም ለሚችል ተላላኪ መስጠታቸውን በይፋ ከተናገሩ በኋላ በማግስቱም የፓርቲውን ፅ/ቤት በጠብመንጃ አፈሙዝ አስወርረው ለህገወጥ ቡድን በህገወጥ መንገድ አስረክበዋል፡፡

የአንድነት ፓርቲ በዚህ ዓይነት ህገወጥ ድርጊት የሚፈርስ አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በየትም ቦታ የምትገኙ ሁሉ ይህን ህገወጥ እርምጃ በፅኑ እየተቃወማችሁ ለነፃነትና ለኢትዮጵያዊነት የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመከፍል ዝግጁ መሆን ይኖርባቸኋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ስልት የሚያምን በመሆኑ ይህን ትግል በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አበክሮ ይስራል፡፡ እያንዳንዱ አባልም አሁን በተፈጠረው ሁኔታ ሳይደናገጥ ለሰላማዊ ትግል ያለውን ፅናት እንደሚያስቀጥል እምነታችን ነው። በአንድነት ስራ አስፈፃሚ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ ተቀበረዋል የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሰናል።

በመሆኑም ስርዓቱ ለመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ የሚመች የአስተሳሰብ ለውጥ እሰካላመጣ ድረስ ምርጫን በየአምሰት ዓመት የሚደረግ ክብረ በዓል አድርጎ ለማድመቅ እና የህዝብ ሀብት ለማባከን በሚደረግ ሂደት ተሳተፊ ለመሆን አዲስ ፓርቲ መመስረትም ሆኖ አሁን ካሉት ፓርቲዎች ጋር ተቀላቅሎ መታገል የሚያመጣው ለውጥ የለም፡፡ ምክንያቱም እነርሱም ልከ በአንድነት ላይ እንደተደረገው በሀይል እንዲፈርሱ የማይደረጉበት ምንም ዓይነት ዋስትና አለ ብለን ስለማናምን ነው። ከዚህ በኋላ በመድብለ ፓርቲ ሰርዓት ስልጣን ይያዛል ብሎ ማመን ህዝቡን ማታለል ነው የሚል ፅኑ እምነት አለን፡፡ ነገር ግን አሁንም የፓርቲ ፖለቲካ አላበቃም ብለው የሚያምኑ የአንድነት አባላት ካሉ በራሳቸው ነፃ ውሳኔ ወደ ፈለጉት ፓርቲ ተቀላቅለው የመታግል መብታቸው የተጠበቀ ነው።

የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን ካለበት አምባገነናዊ ስርዓት ተላቆ ወደ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲሸጋገር ለማድረግ ህዝቡ የትግሉ ባለቤት ሆኖ የስርዓት ለውጥ እንዲመጣ እኛም የበኩላችንን ሀገራዊ ግዴታችንን ለመወጣት ቁርጠኞች ነን፡፡

ድል የህዝብ ነው!!!

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)

ጥር 26 ቀን 2007

አንድነቶች፤ በምርጫ ጨዋታዉ ግጥሚያው ሳይጀመር አሸንፈናቸዋል፤ በሰላማዊ ትግሉም የመጨሻውን ሽንፈት ይጎነጫሉ!!

ተክሌ በቀለ

 ተክሌ በቀለ  (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)

ተክሌ በቀለ (የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)

ምርጫ 2007 ለለዉጥ ብለን ተነሳን፡፡በሙሉ ልብና ዝግጅት ለህዝቡ አማረጭ ለመሆን ለምርጫ የሚየስፈልገዉን ግብኣት ይዘን ተሰለፍን፡፡አጥቂዎችን ከተከላካዮች ለይተን ደጀኖችን ከኃላ አሰልፈን በትምህርት ዝግጅትና በአባላት ጥራት እንዲሁም በሃሳብ የበላይነት ከኢህአዴግ የሚበልለጡ እጩዎችን አዘጋጀን፡፡ከሃቀኛ ፓርቲዎች ጋር ላለመወዳደር በሰጥቶ መቀበል መርህ ለመዳረደርና ለህዝቡ ብቁ ተመራጭ ይዞ ለመቅረብ ተደራዳሪ ኮሚቲም አቋቋምን፡፡

ህወሓት ሃሳብ የለዉም፡፡ቢኖረዉም ያረጀ ነዉ፡፡ለዚህ ትዉልድ አይመጥንም፡፡የሚጮኸዉን ያህል ቀርቶ ከኣባለቱ ሩብ ያህል እንኳን አድማጭ የለዉም፡፡እኛ ብዙ ተምረናል፡፡ከወደቁትና ዛሬም በጽናት ከሚታገሉቱ ቡድኖችና ግለሰቦች ትምህርት ቀስመናል፡፡ ከአሮጌዉ ህወሓትም ይሁን ከወጣቱ ሰማያዊ ፓርቲ የምንቀስመዉን ቀስመናል፤ለመማር ዝግ አይደለንም፡፡ለዉህደትና ለትብብርም እንዲሁ፡፡እደሉም ስላልነበራቸዉ እነሱ የብሄረሰብን ጥያቄ ከነስታሊን መጽሃፍት የቃረሙት ሲሆን እኛ በተግባር አብርን ኖረን የምናዉቀዉ፤በብሄረሰብ መሰረት ከተደራጁ ሃይሎች ጋር ግንባር ፈጥረን ችግረቸዉን ተረድተን የህዝብን ጥያቄ በተግባር ለመመለስ የቆረጥን በህዝብና በሃገር ሉኣለዊነት የማንደራደር የዘመኑ አስተሳሰብ ዉጤት ነን፡፡በመሳሪያና በገንዘብ ሳይሆን በሃሳብ የበላይነት ኮርተን፤ ዳኛዉን ሳይሆን ህዝቡን ተማምነን ለምርጫ ጨዋታዉ ዝግጁ ሆነን ነበር፡፡

ሽንፈቱ ከወዲሁ የገባዉ ህወሓት መጋረጃ ዉስጥ ሆኖ ጨዋታዉን ከወዲሁ አበላሸዉ፤አንድነት ፓርቲን ቢያሸዉ ቢደፈጥጠዉ ጎማ ሆነበት፡፡አልፈርጥለት ሲል የመጨረሻዉን አደረገ፡፡በጠራራ ጸሃይ ከህግ በላይ በጉልበት ዋናዉን ቢሮ ወረረዉ፡፡ምን እንደወሰዱ ምንስ እንዳስገቡብን አናቅም፡፡እርጉዝ ሴት በዱላ መትተዉ የወርቅ ሃብል የወሰዱ፤ጽህፈት ቤት ገብተዉ ምን እንደሚያደርጉ መገመት ይቻላል፡፡ያለ ህግዊና በእማኝ ፊት ርክክብ ሳይደረግ እንደልማዳቸዉ የህዝብ ሃብት ነጥቀዋል፡፡በሂደቱም ግለሰቦችና የህወሓትን ተግባር ለመፈጸም የተቋቋሙ ተቋማት ጥቁር ታሪካቸዉን ሲያኖሩ በእስር እየማቀቁ ያሉቱ የለዉጥ ሃይሎችና በዚህ ሂደት የለዉጥ ሃይሉን ከሚመራዉ ጋር የቆሙ የእንድነት አባላትና ደጋፊዎች ታሪካቸዉን በወርቅ ቀለም ጽፈዉ አኑረዋል፡፡እንዲሆም ድርጊቱን በማዉገዝ ከጎናችን የቆማችሁ ሁሉ በነጻነት ትግሉ የክብር ቦታ አላችሁ፡፡
አንድነቶች በምርጫ ጨዋታዉ ግጥሚያዉ ሳይጀመር አሸንፈናቸዋል፤በሰላማዊ ትግሉም የመጨሻዉን ሽንፈት ይጎነጫሉ፡፡ ዛሬም የነፃ አዉጪን ስም የተሸከመዉ ህወሓት የሚያስበዉ እንደራሱ ነዉ፡፡የፓርቲ ስም፤አርማና ማህተም በዚህ ትዉልድ ቦታ እንደሌላቸዉ አልተረዳዉም፡፡የትውልዱ ጥያቄ በእኩልነት ላይ መሰረትዋን ያኖረች ጠንካራ ሃገር እንጂ እወክለዋለሁ የሚለዉን ህዝብ እንኳን በበለጠ የሚያፍን የፓርቲ ስም አይነት አይደለም፡፡

የአንድነት ፓርቲ ፕሮግራምና የኛ ራዕይና በኛና በህዝብ ልብ እንዲሁም በሌሎች ፓርቲዎች ዉስጥ እንደሚገኝ አልገባቸዉምና ፓርቲን ሲነጥቁ ሰላማዊ ትግሉን የገደሉ፤እኛንም የበተኑ መስሎአችዋል፡፡የለዉጥና የአንድነት ሃይል ይበልጥ ይጠናከራል እንጂ አይበተንም፡፡እርግጥ ነዉ የመድበለ ፓርቲ ስርኣትን አደጋ ላይ ጥለዉታል፡፡ህዝባዊ ሰላማዊ ትግሉ ላይ ግን ጉልበትና ተጨማሪ እድል ጨምረዉለታል፡፡ የአንድነትና የለዉጥ ሃይሎች ዛሬም ይበልጥ ቁርኝነታችንን በማጠንከር ለሰላማዊ ትግሉ መጎልበት ያለንን አቅም ልናበረክት ይገባል፡፡ሁላችንም እድሉን እንጠቀምበት፤የጠበቡ ቤቶችንም ለሁሉም እንዲሆኑ ባፋጣኝ እናስፋቸዉ !
ይህ ተውልድ የቃል እዳ አለበት፤እነአንዷለምም እነ አሞራዉም የሚሉቱና እያሉ ያሉቱ ይህን ነዉ፤ ፍትህና ነጻነት በኢትዮጵያችን በትግላችን ይሰፍናሉ!!

የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋለ

የአዲስ አበባ ፖሊስ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽ/ቤትን ሲቆጣጠር የሚያሳይ

የአዲስ አበባ ፖሊስ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጽ/ቤትን ሲቆጣጠር የሚያሳይ

አዲስ አበባ ቀበና የሚገኘው የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ዋና ጽህፈት ቤት በፖሊስ እና ደህንነቶች ቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት በቁጥጥር ስራ የዋለው ምርቻ ቦርድ ለእኔ ይታዘዘኛል በሚል የፓርቲውን ስምና ህልውና ለነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማስረከቡን ተከትሎ ነው፡፡ ፖሊስ አርብ ጥር 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ጽህፈት ቤቱን ከመቆጣጠሩ በፊት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ስብሰባ ተቀምጠው እንደነበርና በዕለቱ ከሰዓት በኋላ የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት በምርጫ ቦርድ ውሳኔ ጉዳይ ለመምከር ወደ ጽህፈት ቤቱ ሲያመሩ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተረጋግጣል፡፡ በዕለቱ ጠዋት ስራ አስፈፃሚው በጉዳዩ ዙሪያ ከመከረና ከተወያየ በኋላ ለምሳ ወጥተው ለምክር ቤቱ ስብሰባ ሲመለሱ ወደ ቢሮው መግባት የተከለከሉ ሲሆን፤ ቢሮው በፖለስ ቁጥጥር ስር በመዋሉ ቀጠሮ የተያዘለት የፓርቲው ምክር ቤት ስብሰባም ሳይካሄድ መቅረቱ ታውቋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚዎች ለምሳ ሲወጡ ትተዋቸው የሄዷቸውን ተሸከርካሪም ሆነ ማንኛውንም ወረቀት ይዘው እንዳይወጡ ከታገዱ በኋላ ፖሊሶቹ በስልክ በተሰጣቸው ትዕዛዝ ስራ አስፈፃሚዎቹ መኪናቸው ብቻ ተፈትሾ እንዲወጣ መደረጉን የፓርቲው ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን ሲቆጣጠር ከስራ አስፈፃሚው ውጭ በቢሮ ያሉ የፅህፈት ቤት ሰራተኞችና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች ላልተወሰነ ጊዜ ከቢሮ እንዳይወጡ፣ከግቢ ውጭ የነበሩትም እንዳይገቡ መደረጉን የአይን እማኞች ለአዲስ ሚዲያ ገልፀዋል፡፡ ፖሊስ ቢሮውን በኃይል ሲቆጣጠር ምንም ዓይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አለመያዙ ታውቋል፡፡ የአንድነት ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት በምርጫ ቦርድ እነ ትዕግስቱ አወሉ ከተመረጡ በኋላ አሁንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ይገኛል፡፡

በተመሳሳይ ዜና አዲስ አበባ ቸርችል ጎዳና አካባቢ የሚገኘው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ዋና ጽህፈት ቤትም በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋሉ ተጠቁሟል፡፡ ፖሊስ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ የፓርቲዎቹን ዋና ጽህፈት ቤት ለምን እንደተቆጣጠረ እስካሁን የተገለፀ ነገር የለም፡፡ የአዲስ ሚዲያ ፖሊስ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሆነ፤ፖሊሶችም የፓርቲዎቹን ቢሮዎች ተቆጣጠሩ የሚል ትዕዛዝ ከመሰጠቱ በስተቀር ለምን እንደተቆጣጠሩ ራሳቸውም ምክንያቱን እንደማያውቁ ተጠቁሟል፡፡ ምርጫ ቦርድ መጪውን ምርጫ 2007 ዓ.ም. ሂደትን ተክትሎ በዋዜማው ሁለት አንድነት እና መኢአድ ፓርቲዎችን በማፍረስ ሌላ አዲስ ታሪክ አስመዝግቧል፡፡ ቀደም ሲል “የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ” ከህወሓት/ኢህአዴግ የተሰጠውን ትዕዛዝ ከማስፈፀም ውጭ ነፃና ገለልተኛ አይደለም፣ቦርዱን የሚመሩት ስራ አስፈፃሚዎችም ተቋሙን ለመምራት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት ስለሌላቸው ለተቋሙ አይመጥኑም፣..በሚል በተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተደጋጋሚ ትችት ይቀርብበት እንደነበር አይዘነጋም፡፡

አሁን ያለው የቦርዱ እንቅስቃሴ በቀጣይ ቀናትም ከምርጫው ዋዜማ እስከ ድህረ ምርጫ አዳዲስ ውሳኔዎችን እና እንቅስቃሴዎችን ሊያሳይ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡

ሰበር ዜና፤ ምርጫ ቦርድ አንድነትና መኢአድን ፓርቲን ለእነ ትግስቱ አወሉና ለእነ አበባው መሐሪ ሰጠ

  • ‹‹እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው›› -ፕሮፌሰር መርጋ በቃና

nebe

ምርጫ ቦርድ አንድነትን ለእነ ትግስቱ አወሉ፣ እንዲሁም መኢአድን ለእነ አበባው መሃሪ መስጠቱን ዛሬ ጥር 21 ቀን 2007 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አሳወቀ፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹የእነ በላይ በፍቃዱ ቡድን›› በጠቅላላ ጉባኤ እንዳልተመረጠ፣ አምስት አባላት ያሉት አስመራጭ ኮሚቴ አባላት እንዳልመረጠ፣ የተመረጡበትም 51 ሲደመር አንድ መርህ አለመሆኑን፣ ጠቅላላ ጉባኤ ሲያደርግ ሪፖርት አለማድረጉንና ለአባላቱና ለፓርቲው ክብር የሌለው በመሆኑ ፓርቲውን ማስቀጠል እንደማይችል ገልጾአል፡፡

udj

በሌላ በኩል የትግስቱ አወሉ ቡድን መርህ ይከበር እያለ እየታገለ በመሆኑ፣ የኢ/ር ግዛቸው ካቤኔ አባላት ተገፍተው የወጡ በመሆናቸው፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርገው ለቦርዱ ሪፖርት እንዳደረጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን›› ፈቃደኛ ባለመሆኑ እንጂ እነሱ ችግራቸውን በውይይት ለመፍታት ፈቃደኛ በመሆናቸው እንዲሁም ለአባላቶቻቸውና ለፓርቲው ክብር ስላላቸው እውቅናውን ለእነሱ ሰጥቻለው ብሏል፡፡ ምርጫ ቦርድ በመግለጫው ‹‹ምርጫ የሚገባ ፓርቲ በማስፈለጉ፣ ‹‹የእነ በላይ ቡድን ፓርቲውን የሚያስቀጥለው ባለመሆኑና ፓርቲውን እንደ ፓርቲ እንዲቆይ ስለሚፈለግ ዛሬ ጥር 21 ቦርዱ ባደረው አስቸኳይ ስብሰባ እነ ትግስቱ አወሉ ወደ ምርጫ እንዲገቡ ወስኗል›› ብሏል፡፡

የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና ‹‹የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ያካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ ስለመሆኑ በምን ታረጋግጡልናላችሁ?›› በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ‹‹ሁለቱም ችግር አለባቸው፡፡ እኛ ያየነው በአንጻራዊነት ነው፡፡ የእነ ትግስቱ አወሉ ቡድን ችግር ቢኖርበትም ከዛኛው የተሻለ ነው፡፡ እውቅናውን የሰጠነው ለቦርዱ ለሚታዘዘው ነው፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

aeup

በተመሳሳይ እነ ማሙሸት አማረ በጠቅላላ ጉባኤ ባለመመረጣቸው፣ ለተከታታይ 3 ወራት ወርሃዊ መዋጮ ያላወጣ አባል ከአባልነት የሚሰረዝ በመሆኑና ከፓርቲ አባልነትም ስለተባረሩ እንዲሁም ህገ ወጥ ማህተም በማሳተማቸው እውቅና እንዳልሰጣቸው ገልጾአል፡፡ በሌላ በኩል 2005 ዓ.ም ላይ አበባው መሃሪ የተመረጡበት ጠቅላላ ጉባኤ የተሟላ እንዳልነበር ቢታመንም በተደረገ ምርመራ የተሟላ መሆኑ በመታወቁ፣ በትክክለኛው ማህተም ስለሚጠቀም፣ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጉ በተባለበት ወቅት ጠቅላላ ጉባኤ በማድረጉና ሪፖርቱንም ስላቀረበ ወደ ምርጫው እንዲገባ ወስኛለሁ ማለቱን ነገረ ኢትዮጵያ ዘግቧል፡፡

ይሁን እንጂ ፓርቲዎቹ ምርጫ 2007 ዓ.ም. ለመሳተፍ መወሰናቸውን ተከትሎ ህወሓት/ኢህአዴግ  በምርጫ ቦርድ አማካኝነት ሊያፈርሳቸው የተለያየ ህገወጥ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፣ ቦርዱ ገለልተኛ እና ነፃ አለመሆኑን በድርጊቱ እየገለፀ ነው ሲሉ በተደጋጋሚ ተቃውሞና ቅሬታ እያቀረቡ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

አንድነት ፓርቲ በድብደባ ትግሉን እንደማያቆም በመግለፅ በድጋሚ የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጠራ

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የምርጫ ቦርድ በፓርቲው ላይ የሚያሳየውን ጣልቀ ገብነትና ፓርቲውን ለማፍረስ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ በመቃወም የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ ጠርቶ ነበር፡፡ በዕለቱም በደብረ ማርቆስ፣ በጋሞ ጎፋ ከንባ እና በሰሜን ሸዋ ሸዋሮቢት የተሳካ የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጉን ድርጅቱ አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ በዕለቱ በአዲስ አበባ የሰልፉ ጅማሮ ላይ ከ26 በላይ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች እና በቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ የነበሩ የ70 ዓመት አዛውንትን ጨምሮ በፖሊስ ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈፀመባቸው የዓይን እማኞች፣ የህክምና እና የምስል ማስረጃ ማረጋገጥ ተችሏል፡፡

በዕለቱ በፖሊስ ከተፈፀሙ ድብደባዎች የአካል ጉዳት የደረሰባቸውና ነፍሰጡር ሴት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ ፓርቲው የዕለቱን ሰላማዊ ሰልፍ በፖሊስ ድብደባ እንቋረጥ ቢደረገም ፤ ለጥር 24 ቀን 2007 ዓ.ም. መነሻውን ቀበና ከሚገኘው የፓርቲው ጽህፈት ቤት አንስቶ በፒያሳ በዳረሻውን ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ጀርባ በሚገኘው የኢትዮ-ኩባ አደባባይ በድጋሚ ሰልፍ ጠርቷል፡፡ በተመሳሳይ ዕለትም ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በክልል ከተሞች  በደሴ፣ በባህርዳር ፣በደብረ ታቦርና በሌሎች የክልል ከተሞች የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፍ የጠርቷል፡፡

በተለይ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በፓርቲው አባላት፣ደጋፊዎችና ቤተክርስቲያን ለፀሎት የተቀመጡ አዘውንት ምዕመናን በፖሊስ የተፈፀመባቸውን ድብደባ በማውገዝ፣ ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና የተቃውሞ ሰላማዊ ሰልፎችንም በአዲስ አበባና በተለያዩ የክልል ከተሞች እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡ ይህንንም ሰላማዊ ትግሉ በጭፍጨፋና በውንድብና ለማቆም መሞከር ሀላፊነት የጎደለው ተግባር ነው! ሲል አዲስ አበባ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ ሙሉ መግለጫውን ከታች ይመልከቱ፡-

udj1

አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)

UNITY FOR DEMOCRACY AND JUSTICE PARTY (UDJ)
=============================
ሰላማዊ ትግሉ በጭፍጨፋና በውንድብና ለማቆም መሞከር ሀላፊነት የጎደለው ተግባር ነው!

ከአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት)
የተሰጠ መግለጫ
================================

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ /አንድነት/ ህጉ በሚፈቅደው መሰረት የጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ሰልፍ መጥራቱ ይታወቃል። ነገር ግን ስርዓቱ ህገ ወጥ ሰልፍ ነው በማለት በአንድነት አመራሮችና አባለት ላይ ያደረሰው አሰቃቂ ድብደባ ወደር የማይገኝለት ነው። እርጉዞች፣ ህፃናት፣ አዛውንቶችና ሽማግሌዎች ሳይቀሩ ደማቸው ፈሷል፤ አጥንታቸው ተሰብሯል። ሰላማዊ ሰልፉ ስርዓቱ እንደሚለው ህገ ወጥ አልነበረም፤ ስልፍ እንደምናደርግ ደብዳቤ ስንልክላቸው አንቀበለም ብለው ሲያንገራግሩ ደብዳቤውን እዚያ አስቀምጠንላቸዋል፤ ይህ ብቻ አይደለም በሬኮማንድ በድጋሚ ተልኮላቸው ተቀብለዋል። ህጉ አስተዳደሩ በአስራ ሁለት ሰዓት ውስጥ መልስ መስጠት አለበት ቢልም ከሰባ ሁለት ሰዓት በኋላ በሚዲያ “ሰልፉ ህገወጥ ነው” የሚል መግለጫ ከማውጣት ውጪ በደብዳቤ የመለሱት ነገር አልነበረም። በመሰረቱ በስብሰባና በሰልፍ አዋጁ መሰረት አንድ ፓርቲ ሰልፍ እንደሚያደርግ ለአስተዳዳሩ ማሳወቅ ነው ያለበት። አስተዳደሩ ሰላማዊ ሰልፉ በሰላም እንዲጠናቀቅ የፀጥታ ኃይል በመመደብ ሀላፊነቱን በአግባቡ መወጣት እንጂ ሰልፍ መፍቀድም ሆነ መከልከል አይችልም።

አምባገነኑ የህወሀት/ኢህአዴግ መንግስት የዘንድሮውን ሀገራዊ ምርጫ ሂደቱንም ጭምር በማበላሸት ጠንክራ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ከምርጫው ውጪ እንዲሆኑ ለማድረግ ላይ ታች እያለ ነው። በተለይ አንድነት ፓርቲ ላይ በምርጫ ቦርድ፣ በኢቲቪ እና በሬዲዮ ፋና የሶስትዮሽ ግንባር በመክፈት በህዝቡ ዘንድ ብዥታ እንዲፈጠር፣ ምርጫው ያለጠንካራ ተዋዳደሪ እንዲካሄድ በማድረግ የምርጫውን ዋጋ ቢስነት ከማረጋገጡም በተጨማሪ ፓርቲውን ለማፍረስ ቀን ከሌሊት እየሰራ እንደሆነ ጥርጥር የለውም። ስርዓቱና ምርጫ ቦርድ የጥቅም ምንደኞች በማዘጋጀት ተለጣፊ አንድነትን በመጠፍጠፍ ፓርቲውን ከእውነተኛ አባላቱና ደጋፊዎቹ ለመቀማት እጅግ አሳፋሪ የሆነ የሽፍትነት ስራ በመስራት ላይ ይገኛል።

አሁንም ቢሆን አንድነት ይህን የህወሀት/ኢህአዴግ ሴራና ውንብድና በመቃወም ለሚቀጥለው እሁድ ጥር 24/2007 በአዲስ አበባና በሌሎች የተለያዩ የክልል ከተሞች ላይ ሰልፍ ያድርጋል። በአዲስ አበባ ላይ የሚካሄደው ሰልፍ በተለምዶ ኢትዮ ኩባ አደባባይ (ድላችን ሀወልት) ሲሆን በትናንትናው ጥር 18/2007 ለአስተዳደሩ በደብዳቤ አስገብተናል። ይህ በአዲስ አበባ የሚካሄደው ሰልፍ አስተዳደሩ አሳማኝ ምክንያት አቅርቦ ተለዋጭ የጊዜ ወይም የቦታ አማራጭ እስካላቀረበ ድረስ በምንም ሁኔታ የሚታጠፍ አይደለም። አንድነት ስብሰባና ሰልፍ የማድርግ ህገመንግስታዊ መብት እስኪረጋገጥ ድረስ በህዝባዊ ንቅናቄና በሰላማዊ መንገድ ትግሉን ይቀጥላል።

ድል የሕዝብ ነው!!
ጥር 19 ቀን 2007 ዓ.ም
አዲስ አበባ

ስልክ ቁ. ዐዐ11-1- 22-62-88

ፖ.ሣ.ቁ 4222