ባለ መሰንቆውና ባለ ወለሎው
በእውቀቱ ሥዩም
“ ሮድ ደሴት” በተባለ አገር ውስጥ እንደ እንደምኖር የነገርኩት ጓደኛየ“ እና ባሣ አጥማጅነት ነው የምትተዳደረው?”ብሎኛል፡፡ ሮድ ደሴት አበሻ እጥረት ክፉኛ ከሚያጠቃቸው ክልሎች አንዱ ነው ፡፡ አሁን ምድሩም ሰማዩም ሰውም ነጭ ነው፡፡
ያገር ሰው በጣም ይናፍቀኛል፡፡ የሆነ ያበሻ ዓይነ ውሃ ያለው አልፎ ሒያጅ መንገድ ላይ ካየሁ ከሚበር አውቶብስ ላይ እንደ ጅምስ ቦንድ ተወርውሬ ወርጀ ስልኩን በቃሌ እቀበለዋለሁ፡፡ ከሁለት ሱዳናውያን ጋር የተዋወቅሁት በዚህ አጋጣሚ ነው፡፡
ያበሻ ናፍቆቴንአናቴ ላይ ሲወጣ ወደአበሻ- ጠገብ ክልሎች እቀላውጣለሁ ፡፡ ባቡሬን ጭኘ መጭ ወደ ውሻንግቶን ዲሲ! ዲሲ የውሃና የመብራት እጥረት የሌለበት አዲስአበባ ማለት ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት ሚኒሶታ ወረድሁ፡፡ ከተማይቱ በበረዶ ተዝረክርካ የሰነፍ ቡሃቃ መስላለች፡፡ የተፈጥሮን ጨካኝነት፤ የቶማስ አልቫ ኤዲሰንን ያለም ቤዛነት ለማረጋገጥ የሚፈልግ ሚኒሶታ ይሂድ፡፡ ወይ አዲስ አበባ! አዱ ገነት፡፡ እብድ የያዘሽ ውበት፡፡ ሰው እንዴት ጥሎሽ ይመጣል? ሰው እንዴት ከገነት ያመልጣ?
ከመኪና ማቆምያው ተሥቼ አዳራሹ ድረስ እስክገባ ድረስ የተቀበልኩት መከራ ራሱን የቻለ ሰማእትነት ሆኖ ለትውልድ ይዘከርልኝ ፡፡ ብዙ ብርድ አጋጥሞኛል እንዲህ አራት ጃኬትና ሁለት ሱሪ ገልቦ፤ አስገድዶ የሚሠር ብርድ ደርሶብኝ አያውቅም፡፡ እድል ፈንታየ ብሎ ብሎ ደም እንደ ብይ በሚጠጥርበት፤ ያፍንጫ ጸጉር እንደጃርት ወስፌ በሚቆምበት አገር ይጣለኝ?
ደሞ እቺም ኑሮ ሆና “በርገርህን እየገመጥክ ትደነፋለህ አይደል?” የሚል ብሽቅ መልክት ይልኩልኛል። ባለመልክቱ! እስቲ ያዲሳባን የጧት ጸሐይ፤ በበርገር ለውጠኝ!!
ሳይደግስ አይጣላም በህይወቴ ባካል ላገኛቸው ከምፈልጋቸው ሰዎችአንዱ የሆነውን ጋዜጠኛ ሰሎሞን ደሬሳን አገኘሁት፡፡ ሰሎሞን ፈላስፋ ነው፡፡የመጀመርያው የሥእል ሓያሲም ነው፡፡ በኦሮምኛ ፤አማርኛ እንግሊዝኛና ፈረንሳይኛ የሚራቀቅ ሊቅ ነው፡፡ ወዳጅ ባታደርገው እንኳ ለፍልምያ የምትመርጠው ሰው ነው፡፡ እንድታስብ የሚገፋፋህ ፤አርፈህ እንድትቀመጥ የማያደርግህ ሰው ማግኘት መታደል አይደል? መጣጥፎቹ ተሰብስበው በመጽሐፍ አለመውጣታቸው ያስቆጫል፡፡ ”ልጅነት ” የምትል በዘልማዳዊው የአማርኛ ስነግጥም ላይ የሸፈተች የግጥም መደብል ሲያሳትም እንደ መናፍቅ ተቆጥሯል፡፡ የትውፊት አስጠባቂው አቤ ጉበኛ በሰሎሞንን ግጥምና በዳኛቸው ወርቁ ልቦለድ ላይ ለማላገጥ “ጎብላንድ አጭበርባሪው ጦጣ”የሚል መጽሐፍ እስከማሳተም ሂዷል፡፡ የአቤ ጎብላንድ ዛሬ በታሪክ ቅርጫት ውስጥ ተጥላለች፡፡ የሰሎሞንና የዳኛቸው መጽሐፎች ግን ገቢያ ላይ በጣም ይፈለጋሉ፡፡ ለምሳሌ ስለባህል ግብዝነት በተነሣ ቁጥር ይችን የሰውየውን ግጥም ማን ይረሣታል?
በኢትዮጵያ ባልጎ መታየቱ
ሳይሆን ቂንጥር ማስቆረጡ
ህጻኗን ልጅ እንደ ቆዳ መስፋቱ
መባለጉ
ኣፉን ሞልቶ” ቂንጥር “ ብሎ መጥራቱ
የሆነ ጊዜ ላይ፤ ስብሐት ገብረእግዚኣብሄር ስለወዳጁ ስለሰሎሞን ”ከሸክስፒርና ከዳንቴ ቀጥሎ ትልቁ ባለቅኔ ሰሎሞን ነው” ብሎ ጻፈ፡፡ ላዲስ ነገር ጋዜጣ የሚሆን ቃለመጠይቅ ሳደርግለት“ሰሎሞንን በዓለም ሦስተኛ ገጣሚ አድርገህ ጽፈሐል፤ አግባብ ነው?”አልኩት፡፡
“እንደዛ ብያለሁ?”
“ኣዎ”
ስብሐት ትንሽ አሰበና መለሰ፤ “ እንዲህ ያልኩት በጣም በናፈቀኝ ሠአት መሆን አለበት“
ከሥነጽሁፉ ምሽት በበኋላ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር ”ሬድ ሲ” ሬስቶራንት ራት ጋበዙን፡፡ እንደምንም እየተንፏቀቅሁ ከሰሎሞን አጠገብ ያለውን ቦታ ያዝኩ፡፡ ይችን ብርቅ አጋጣሚ ተጠቅሜ ከልጅነት እስከ ሽበት ያሳለፈውን ገድሉን አናዝዘዋለሁ ብየ አሰብኩ፡፡አልቀናኝም፡፡ ከሰለሞን ጋር ጨዋታ እንደ ጀመርሁ ከኋላየ ባለጌ ወንበር ላይ የተቀመጠ ተስተናጋጅ፤ ባንገት ጥምጥሜ ጎትቶ ካዞረኝ በኋላ” ቢራውን ትተህ ለምን ጠንከር ያለ ነገር አትወስድም?”በሚል ጥያቄ ጠመደኝ፡፡ ቢራውን ትቸ ጠንከር ያለ ነገር የማልወስድበትን ሰባት ምክንያት ስዘረዝር ራቱ ተገባድዶ ከፍ አለ፡፡
ከእራት በኋላ አዝማሪው ወደ መድረክ ወጣና ማሲንቆውን ማስተከዝ ጀመረ ፡፡ በቤቱ ያለው ሰው በማሲንቆ ዜማ ታጅቦ ወደ ግል ወሬው ተጠመደ፡፡ “ኣንድ ኮርኔስ እዚህ ጋ ያዘዘ ማን ነው?” የሚለው ያስተናጋጇ ድምጽ ካዝማሪው እንጉርጉሮ በላይ ጠብድሎ ይሰማኛል፡፡ ሰሎሞን ከወንበሩ ተነሥቶ በዝግታ እየተራመደ ወደ መድረኩ ከወጣ በኋላ አዝማሪውን ሸልሞ አጠገቡ ቁጭ አለ፡፡ ዓይኑን ለበስ አድርጎ እልምም !! በማሲንቆው ተሳፍሮ የት ደርሶ ይሆን? ወለጋ-አዲስአበባ – ደጃች ውቤ ሠፈር- ፤ የከተማ መኮንን ክራር – ምኒልክና ጊዮርጊስ በፈረቃ ከሚጋልቡት የአራዳ ፈረስ፡፡
ልጅነት በተባለቸው መድብሉ ስለአንድ የውቤ በረሃ ጀግና በጻፈው መወድስ ውስጥ እኒህ መስመሮች ተካትተዋል፡፡
”ደኑ ርቆት፤
መንገዱ ጠፍቶት
ጓዱ ረስቶት
በጨለማ ቤቱን ስቶት“
ዛሬ እኒህ መስመሮች በግዞትና በስደት ሰጥመው የቀሩ ድንቅ ኢትዮጵያውያንን ሁኔታ የሚገልጹ አድርጌ ብተረጉማቸው ማን ይፈርድብኛል?
( ወዳጄ ገጣሚ ዮናስ አንገሶም ኪዳኔ የሰሎሞንን መጽሐፎች ስለሰደድክልኝ ምስጋናየ ይድረስህ፡፡)
እነ ጌታቸው ሽፈራው ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው
*”ከቤተሰቦቻችን ጋር እንዳንገናኝ ተደርገናል” ተጠርጣሪዎች
*”6 ቀን ደንበኛየን ለማግኘት ተመላልሼ ተከልክያለሁ” የጋዜጠኛ ጌታቸው ጠበቃ አምሃ መኮንን
በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከታህሳስ 15/2008 ዓ.ም ጀምሮ በማዕካለዊ ወንጀል ምርመራ በእስር ላይ የሚገኙት እነ ጌታቸው ሺፈራው ፍርድ ቤት ቀርበው ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
በእነ ዳንኤል ተስፋየ ስም በተከፈተው የምርመራ መዝገብ ስር የተካተቱት ሦስት ተጠርጣሪዎች አቶ ዳንኤል ተስፋየ፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል እና ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ሲሆኑ፣ ተጠርጣሪዎች ዛሬ ጥር 14/2008 ዓ.ም ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ቀርበው ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ይሰጠኝ ብሎ ጠይቆ የ27 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋ፡፡
ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ የጠየቀበትን ምክንያት ለፍርድ ቤት ያስረዳ ሲሆን ‹‹የቴክኒክ ማስረጃዎችን ከብሄራዊ ደህንነትና መረጃ ኤጀንሲ ጠይቀን ማስመጣትና ተጨማሪ ግብረ አበሮችን መያዝ ይቀረናል›› ብሏል፡፡
ተጠርጣሪዎች ከተያዙበት ቀን ጀምሮ በማንም እንዳይጎበኙ መከልከላቸውን በማስረዳት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ፣ ‹‹ከተያዝኩ ጀምሮ ቤተሰቦቼን አይቼ አላውቅም፡፡ እስር ላይ ሆኜ በቀን ለ10 ወይም 15 ደቂቃዎች ነው የጸሐይ ብርሃን የማገኘው፤ ይሄ እንዲስተካከልልኝ ፍርድ ቤቱን እጠይቃለሁ›› ሲል ያመለከተ ሲሆን፣ አቶ ሸዋታጠቅ ኃ/መስቀል በበኩሉ፣ ‹‹ቤተሰቦቼን ያየኋቸው ዛሬ ችሎት ስመጣ ከርቀት ነው፤ ቤተሰቦቼን እንዳይ ይፈቀድልኝ›› በማለት እያነባ ጠይቋል፡፡
ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ደግሞ በጠበቃው በኩል ያለውን አቤቱታ ለፍርድ ቤቱ አሰምቷል፡፡ ጠበቃው አቶ አምሃ መኮንን ለስድስት ቀናት ማዕከላዊ ደንበኛቸውን ለማነጋገር ቢመላለሱም ከበር ላይ እንዲመለሱ በመደረጋቸው ከደንበኛቸው ጋር ሳይነጋገሩ ፍርድ ቤት መቅረባቸው አግባብ አለመሆኑንና ድርጊቱ ህገ-መንግስቱን የሚጣረስ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
‹‹ደንበኛየን ያገኘሁት አሁን ነው፡፡ ደንበኛየ የምንፈልገውን ነገር ሳናገኝ ከጠበቃህ ጋር አናገናኝህም ተብሏል፡፡ ይህ በህገ-መንግስቱ የተሰጠውን መብት የጣሰ ተግባር ነው፡፡ አሁንም ደንበኛየ፣ ከዚህ በኋላ እኔን ሳያነጋግር ቃሉን ለመስጠት ፈቃደኛ እንዳልሆነ ፍርድ ቤቱ እንዲመዘግብልኝ እፈልጋለሁ›› ሲሉ ጠበቃ አምሃ መኮንን ለፍርድ ቤቱ ገልጸዋል፡፡ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው እስካሁን በቤተሰብም ሆነ በጓደኞቹም እንዳይጠየቅ መከልከሉ የህግ አግባብ የሌለው የመብት ጥሰት ነው ብለዋል ጠበቃ አምሃ፡፡
ጠበቃ አምሃ ፖሊስ ተጨማሪ ጊዜ የጠየቀበት ምክንያት ደንበኛቸው የዋስትና መብቱ ተከብሮለት ሊከናወን እንደሚችል በማስረዳት የዋስትና መብት እንዲከበርለት ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን በሁሉም ላይ ፖሊስ የጠየቀውን የጊዜ ቀጠሮ በመፍቀድ ለየካቲት 11/2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተመሳሳይ በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ከሦስት ወራት በላይ በማዕከላዊ በእስር ላይ የሚገኙት በጋሞ ጎፋ አርባምንጭ የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪዎች እነ ሉሉ መሰለ እና አየለች አበበ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበው ‹የመጨረሻ› ነው የተባለለትን ተጨማሪ የ28 ቀናት ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
ምንጭ፡- ነገረ ኢትዮጵያ
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ እንደቀጠለ ነው፤ በመንግሥት የኃይል እርምጃ የተገደሉ ዜጎች ቁጥርም ከ140 በላይ ደርሷል
በኦሮሚያ ያለው ህዝባዊ ተቃውሞ አሁንም በተለያዩ ከተሞች እንደቀጠለ ነው፡፡ በርካታ ትምህርት ቤቶች ተዝግተዋል፡፡ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የተገደሉት ዜጎች ቁጥር ከ140 በላይ መድረሱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል እርምጃ ከሰላማዊ ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ ከተሳተፉት እና በቤታቸው እንዲሁም በመንገድ ላይ ሲጓዙ የተገደሉትን 140 ዜጎችን ጨምሮ ከ350 በላይ ሰዎች ሲቆስሉ ከ4 ሺህ በላይ ዜጎች በእስር ላይ እንደሚገኙ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በተለይ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በጅምላ እየወሰዱት ባለው እስር በድጋሚ የታሰሩት የኦፌኮ/መድረክ አመራር አቶ በቀለ ገርባ ልጅ የሆነው እና በአዳማ ዩኒቨርስቲ የ5ኛ ዓመት የህግ ተማሪ የሆነው ናዖል በቀለ ገርባን ጨምሮ በርካታ ተማሪዎች ከሚማሩበት የትምህርት ተቋም ተይዘው መታሰራቸውም ተሰምቷል፡፡
ህዝባዊ ተቃውሞው አሁንም በተለያዩ ከተሞች በተለይም በምዕራብ ኢትዮጵያ በወለጋ፣ ምዕራብ ሸዋ፣ በምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል በምስራቅ እና ምዕራብ ሐረርጌ፣ በአርሲ ፣ በምስራቅ ሸዋ በሚገኙ የተለያዩ ከተሞች እንደቀጠለ ነው፡፡ በመንግሥት የሚገደሉ፣ የሚታሰሩና የሚጎዱ ዜጎችም ቁጥር እየጨመረ እንደሆነ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
የኦፌኮ/መድረክ ዋና ፀሐፊ አቶ በቀለ ነጋዓ እስካሁን በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ከደረሰባቸው ተደጋጋሚ ማስፈራሪያና ዛቻ በኋላ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ የተንቀሳቃሽ ስልካቸው ተነጥቆ ፣ ከመኖሪያ ቤታቸው እንዳይወጡ ተደርጎ እስካሁንም በቁም እስር ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ህዝባዊው ተቃውሞ ባለፈው ህዳር 2008 ዓ.ም. አዲሱን የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ትግበራን በመቃወም መጀመሩ ይታወሳል፡፡
መንግሥት በበኩሉ ለተቃውሞ የወጡትን ፀረ-ህዝብ፣ ፀረ-ሰላም፣ አሸባሪዎች ብሎ መወንጀሉን እና ህዝባዊው ተቃውሞውን በቁጥጥር ስር አውየዋለሁ በሚል ተደጋጋሚ መግለጫ ቢሰጥም፤ ተቃውሞው በያዝነው ሳምንት በተለያዩ የሀገሪቱ ኦሮሚያ ክልሎች ተጠናክሮ መቀጠሉ የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ በሐረርጌ አካባቢ ከአዲስ አበባ ድሬዳዋ እና ሐረር የሚወስዱ ዋና መንገዶች በተቃውሞው ተዘግተው እንደነበር ምንጮች አስታውቀዋል፡፡
ህወሓት እና የእነ ሓጎስ ፖለቲካ
ተክሌ በቀለ
(የቀድሞው የአንድነት ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዘዳንት)
በተቃውሞ እንቅስቃሴዉ ዉስጥ አንድ ያልተፈታ መምታታት ይታያል፡፡ ህዝብንና ድርጅትን መለየት አለመቻል፡፡ አንዳንዴ እንደስልትም ሆን ተብሎ ይሰራበታል፡፡ ግን አክሳሪ ስልት እንደሆነ ትምህርት ሊወሰድ አልተቻለም፡፡ ህወሓት በትግራይ ህዝብ ውስጥ የተፈጠረ ድርጅት ሲሆን ህዝቡ ብዙ ታሪክ እየሰራ ለብዙ ዘመናት እንደኖረ የምንስማማ ይመስለኛል፡፡ ለወደፊቱም ይኖራል፡፡ እነ ሓጎስ ድርጅቱ ውስጥ በአባልነትና በደጋፊነት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በህዝቡ መሃል እየተረገጡም ሊኖሩ ይቻላሉ፡፡ በተቃዋሚው ጎራም ይኖራሉ፡፡ ከሃገር እንዲወጡና እንዳይመለሱ የተደረጉም ይኖራሉ፡፡ ተሰፋ ቆርጠው አንገት ደፍተዉ የተቀመጡም ይኖራሉ፡፡ እነሓጎስ ብዙ ናቸው፡፡ እነ ሓጎስን ከህወሓት ጋር ስንቀላቅላቸው ለደህንነታቸው ይሰጋሉ፡፡ እናም ልዩነታቸውን ረስተው አብረው ይቆማሉ፡፡ በዚህኛው ወገን ያለው ደጋፊም አቅም ያጣል፡፡የወገኖቹን ደህንነት ይፈልጋልና ነው፡፡
የህወሓቶቹን እነ ሃጎስ ያገኘን(ለማሸማቀቅም ይሁን ለማስፈራራት) መስሎን ቀላቅለን ስናያቸው በተቃራኒ ያሉትን ሓጎሶች(ለምሳሌ የዓረና አመራሮችና አባላትን) ሁሉ አቅም እያሳጣናቸዉ ነው፡፡ መሰረታቸውን እያናጋነው ነው፡፡ በህዝባቸው ፊት በህወሓት እንዲቀጠቀጡ ዱላ እያቀበልን ነዉ፡፡ ሲሆን እንሰልጥንና የሁሉም ሓጎሶች ምርጫ ህወሓት ከሆነ ሌሎቻችን እኛን ራሳችንን ነጻ እናውጣና ያገሪቱ ህግ በሚፈቅደዉ መሰረት አብረናቸዉ ለመስራት ዝግጁ እንሁን፡፡ እነሱን ከነሓጎስ ጋር ለማጥፋት ከመስራት እዛው ራሳቸዉን እንዲያስተዳድሩ ራስን ማሳመን ዋጋው ይቀላል፡፡ ሁሉን አቀፍ ድርድር (inclusive negotiation) እኮ አንዱ እፊታችን የሚኖር አማራጭ ይመስለኛል፡፡ ራሳችንን ነጻ ለማዉጣት ከህወሓት ጋር ያሉትን ድጋፍ መጠበቅ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ግን እስኪ ሌሎቻችን በወጉ እንስማማ፡፡ መንግሰትን የሚያክል ግዙፍ ተቋም ለመለወጥና አገር ለመምራት የተናጠል አመጽ ብቻውን በቂ አይመስለኝም፡፡ ህዝብን እንወክላለን የሚሉ ቡድኖች ቢስማሙ፤ቅስቀሳና አስተምህሮቶች ሁሉ ባንድነት ቢቆሙ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ አመጽ ለመቀስቀስ መስራት አይጠበቅም፡፡ ለዚህ ኢህኣዴግ ራሱ ተግቶ እየሰራ ነው፡፡ የተቃውሞው ጎራ አንድነቱን ጠብቆ አማራጭነቱን ከሳየ ህዝባዊ አመጽ ከሆነ ቦታ በሆነ ምክንያት ተነስቶ ስርዓት እንደሚለውጥ በዓለም ላይ በቂ ተሞክሮ አለ፡፡ እኛ የተለየን አንሆንም፡፡
ሳጠቃልለው፤ እነ ሓጎስን ከህወሓት አለመለየት ለትግሉ መዳከምና ለመከራችን መራዘም አስተዋጽኦ ማበርከት ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ በተናጠልም ቢሆን እየተከፈለ ያለውን ውድ መስዋዕትነት ማራከስ ነው፡፡ እነ ሓጎስን በሙሉ ከራሱ ጋር መቀላቀልና የተቀላቀሉ ማስመሰል የሚፈልገዉ ህወሓት ብቻ ነው፡፡ ህዝብና ድርጅት የመለየት ጥበብ ይኑረን፡፡ ልቦናችን ካላሰበው ካፋችን አይጣምና ልቦና ይስጠን፡፡ ተገቢ ቃላትን መጠቀም ለትግሉ ወሳኝነት ይኖረዋል፡፡ ህወሓትና ወያኔም አንድ አይደሉም! ለዚህም ነው ገዥው ቡድን ህዝባዊ ጥያቄዎችን ሁሉ ረብሻ እያስመሰለ የሚያቀርበውና ህይወት እየበላ እንዲቀጥል እድል እተሰጠው ያለው፡፡ በእውነት ያማል!!!!
እነ ሀብታሙ አያሌው ለጥር 10 ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል
አቃቤ ህግ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የሽብርተኝነት ክስ መስርቶባቸው በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ተበይኖላቸው አቃቤ ህግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠይቆባቸው ጉዳያቸውን በእስር ላይ ሆነው እየተከታተሉ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች በድጋሜ ለጥር 10 ቀን 2008 ዓ.ም ተቀጥረዋል፡፡
ዛሬ ታህሳስ 29 ቀን 2008 ዓ.ም ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በእነ ሀብታሙ አያሌው ላይ የተጠየቀው ይግባኝ ላይ ብይን ይሰጣል ተብሎ ቢጠበቅም ዳኛ ዳኜ መላኩ ‹‹የምንመረምረው ነገር አለ›› በሚል ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥተዋል፡፡
ይግባኝ የተጠየቀባቸው ተከሳሾች ሀብታሙ አያሌው፣ የሺዋስ አሰፋ፣ አብርሃ ደስታ፣ ዳንኤል ሺበሺ እና አብርሃም ሰለሞን ሲሆን፣ ሁሉም ተከሳሾች ነሀሴ 14 ቀን 2007 ዓ.ም በስር ፍርድ ቤት ነፃ ቢባሉም እስካሁን በእስር ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ