አቶ ዮናታን ተስፋዬ ከኦነግ ጋር ተያይዞ የሽብር ክስ ተመሰረተበት
የቀድሞው የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ እና በምርጫ 2007 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ወረዳ 17 የፓርላማ እጩ ተወዳዳሪ የነበረው አቶ ዮናታን ተስፋዬ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ 652/2001 የወጣውን አንቀጽ 4 ስር የተመለከተውን ተላልፏል በሚል ክስ ተመስርቶበታል፡፡
ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ክሱ በዳኞች ቢሮ በንባብ የተሰማበት አቶ ዮናታን ተስፋዬ፤ የአዲስ አበባ ከተማ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ሽፋን በማድረግ ከህዳር 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ተከሳሹ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ በተለይም ፌስቡክ አማካኝነት በኦሮሚያ ክልል የተነሳውን “አመፅና ብጥብጥ” ለማስቀጠል የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን ዓላማ ተቀብሎ ተንቀሳቅሷል ሲል አቃቤ ህግ ክስ መስርቶበታል፡፡ የክስ ፋይሉ ሌላ ተከሳሽ ውጭ ለአቶ ዮናታን ብቻ የቀረበበት የማስረጃ ዝርዝር በማኀበራዊ ሚዲያ የለጠፋቸው ፅሑፎች ናቸው፡፡
በዚህም ተከሳሹ የቡድን (ኦነግ) ዓላማን ለማሳካት አመፅና ብጥብጥ እንዲቀጥልና ሌሎችን ለማነሳሳት አስቦ በሚጠቀምበት ድረ-ገፅ (ፌስቡክ) ቀስቃሽ ፅሑፎችን በመፃፍ የሽብርተኝነት ድርጊት ለመፈፀም ማቀድ፣ ማዘጋጀት፣ ማሴር እና ማነሳሳት ወንጀል ክስ በአቃቤ ህግ እንደቀረበበት ታውቋል፡፡
አቶ ዮናታን ተስፋዬ በተለያዩ ቀናት በግል የፌስቡክ ገጹ ላይ ያስነበባቸው ፅሑፎች ክሱ ላይ ተካተው በማስረጃነት ቀርቦበታል፡፡
ታህሣሥ 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጭቆና መሳሪያነት የሚያገለግሉ ማናቸውንም ቁሳቁሶች ማቃጠልና ማውደም እንዲሁም መንገድ መዝጋትን በተመለከተ፣ ታህሣሥ 11 ቀን 2008 ዓ.ም. ኢህአዴግ ችግር ማዳፈን እንጂ ችግር መፍታት አይችልም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ሲጀመር ምንም ዓይነት መሪ ዕቅድ (ማስተር ፕላን) የለም በሚል የፃፈው፣ ታህሣሥ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. የተቃውሞ ትግሉ ቀጥሏል በሚል የፃፈው፣ ህዳር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. እነሆ 7 መልዕክት ብሎ በፃፈው እና በሌሎችም ፅሑፎች አማካኝነት ቅስቀሳ አድርጓል ሲል አቃቤ ህግ ክስ አቅርቦበታል፡፡
ዮናታን ተስፋዬ በነጠላ መዝገብ ብቻውን ክስ የተመሰረተበት ሲሆን፤ በዕለቱ ክሱ በንባብ በተሰማበት ወቅት ዳኛ አልተሟላም በሚል ምክንያት በዳኞች ቢሮ መታየቱን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የክሱን ሂደት ዬናታን ቤተሰቦችም፣ ወዳጆችና ጋዜጠኞች በችሎት መታደም ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ አቶ ዮናታንም የክስ መቃወሚያውን ይዞ ለፊታችን ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዲቀርብ ቀነ ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡
ምንጭ፡- EHRP.
ነባር የኢሕአዴግ አመራሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ለመከላከያ ምስክርነት ተቆጠሩ
ምሁራንና ፖለቲከኞችም ተካተዋል
በታምሩ ጽጌ
ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲሄዱ ማይካድራ በተባለ ቦታ ላይ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው የተለገጸውና በሽብር ድርጊት ወንጀል የተከሰሱ አራት ተጠርጣሪዎች፣ አቶ በረከት ስምኦን፣ አቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ አቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሃት)፣ አቶ አዲሱ ለገሰ፣ አቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ጄነራል ሳሞራ የኑስንና ሌሎችንም ነባር ታጋዮችንና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ጨምሮ 141 ሰዎች በመከላከያ ምስክርነት ቆጠሩ፡፡
መከላከያ ምስክሮቹን የቆጠሩት ተጠርጣሪዎች የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት የነበሩት አቶ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ወ/ሪት እየሩሳሌም ተስፋውና አቶ ፍቅረማርያም አስማማው ናቸው፡፡ በክሱ ከላይ የተጠቀሱትን ተጠርጣሪዎች ወደ ኤርትራ ድንበር እንዲሻገሩ በመምራት የተጠረጠረው አቶ ደሴ ካህሳይም ተካቷል፡፡
ተከሳሾቹ ከዓመት በፊት የካቲት 18 ቀን 2007 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለው ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክስ የተመሠረተባቸው፣ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ወንጀል ሆኖ የተደነገገውን ለሽብርተኛ ድርጅት ውስጥ መሳተፍን ተላልፈዋል በሚል ነው፡፡
ተከሳሾቹ ከላይ የተጠቀሱትን የሕግ ድንጋጌዎች በመተላለፍ፣ የሰው ሕይወት በማጥፋትና ንብረት በማውደም፣ በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ፖለቲካዊ ሥልጣን ለመያዝ እየተንቀሳቀሰ ካለው የግንቦት ሰባት ድርጅት ጋር አብሮ ለመሥራት መዘጋጀታቸውም ተጠቅሷል፡፡ ከአዲስ አበባ ተነስተው በባህር ዳር፣ በጎንደርና በሁመራ አድርገው ወደ ኤርትራ ለመሻገር ሲንቀሳቀሱ በፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውንም፣ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡
ዓቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ ያቀረበውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች የመረመረው ፍርድ ቤቱ፣ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ታኅሳስ 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ብይን ሰጥቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን (141) በዝርዝር ጽፈው አቅርበዋል፡፡ ከምስክሮቻቸው መካከል ለአቶ በረከት ስምዖን፣ ለአቶ ዓባይ ፀሐዬ፣ ለአቶ አዲሱ ለገሰ፣ ለወ/ሮ ሮማን ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ተፈራ ዋልዋ፣ ለአቶ ስብሀት ነጋ (አቦይ ስብሀት)፣ ለወ/ሮ ፍሬ ሕይወት አያሌው፣ ለዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል፣ ለጄኔራል ሳሞራ የኑስና ለአቶ ቴዎድሮስ ሐጐስ እነሱ መጥሪያ ለማድረስ እንደማይችሉ (ከፍተኛ ባለሥልጣናት በመሆናቸው) በፍርድ ቤቱ በኩል እንዲደርሳቸው እንዲደረግ አመልክተዋል፡፡
ለፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፣ ለዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ለአቶ አስገደ ገብረ ሥላሴ፣ ለአቶ ገብሩ አሥራት፣ ለወ/ሮ አረጋሽ አዳነ፣ ለአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ (ቃሊቲ)፣ ለጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ (ዝዋይ)፣ ለአምስት ጦማሪያን፣ ለጠበቃ ተማም አባቡልጉ፣ ለኢንጂነር ይልቃል ጌትነት (ሰማያዊ ፓርቲ) ጨምሮ በድምሩ 141 የመከላከያ ምስክሮችን በመቁጠር ለፍርድ ቤቱ አሳውቀዋል፡፡ ረቡዕ ሚያዝያ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ተከሳሾቹ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ