Monthly Archives: May, 2016

በቦሌ ወረገኑ በሕገወጥ ግንባታ ምክንያት ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ጉዳት ደረሰ

ታምሩ ጽጌ

‹‹መንግሥት ያለምንም ርህራሔ በክረምት ጐዳና ላይ በተነን›› ቤት የፈረሰባቸው ነዋሪዎች

‹‹መንግሥት ዜጎቹን በማክበር ሕገወጥ ተግባራትን ይከላከላል›› የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

Addis ababa city

በአዲስ አበባ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ቦሌ ቡልቡላ ወረገኑ በመባል በሚታወቀውና በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች እንደሚገኙበት በተገለጸው ሥፍራ፣ ከሕገወጥ ግንባታ ጋር በተገናኘ ረቡዕ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ነዋሪዎችና የፀጥታ ኃይሎች ተጋጭተው ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ተጠቆመ፡፡

በአካባቢው ከ2000 ዓ.ም. ጀምሮ ያለምሪት ቤት የሠሩ ቁጥራቸው በርካታ (ከ20 ሺሕ በላይ መሆናቸውን ይገልጻሉ) የሚሆኑ ነዋሪዎች የሚገኙ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 12 አስተዳደር የገነባቸው ቤቶች ሕገወጥ መሆናቸውን በመግለጽ በተደጋጋሚ እንዲያፈርሱ ቢነግራቸውም፣ ‹‹ወዴት እንሂድ? በድህነት አቅማችን የሠራነውን ቤት ግምት ወጥቶለትና ካርታ ተሠርቶለት ሕጋዊ እንሁን፤›› በማለት ሲከራከሩ መክረማቸውን ነዋሪዎቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በአስተዳደሩና በነዋሪዎቹ መካከል መግባባት ሳይፈጠር ቆይቶ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች የታጀበው የወረዳው አፍራሽ ግብረ ኃይል ወደ ነዋሪዎቹ መንደር በመሄዱ፣ ከነዋሪዎቹ ተቃውሞ እንደገጠመው ተገልጿል፡፡
ነዋሪዎች አንድ ላይ በመሆን በድህነት ያቋቋሙት ጎጆ መፍረስ እንደሌለበት በመግለጽ ለመከላከል ባደረጉት እንቅስቃሴ፣ ከፀጥታ አስከባሪዎች ጋር ወደ ከረረ ግጭት በመግባታቸው ሁለቱም ወገኖች መጐዳዳታቸውን የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በወቅቱ በርካታ ጥይት የተተኮሰ በመሆኑ ቁጥራቸው ያልተገለጹ ሰዎች እንደሞቱ የተነገረ ቢሆንም፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ግን አንድም የሞተ ሰው እንደሌለ አስታውቋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አሰግድ ጌታቸው እንደተናገሩት፣ በሕገወጥ መንገድ የተገነቡ 1,040 ቤቶች አሉ፡፡ ሕገወጥ በመሆናቸው እንዲፈርሱ ተደርጓል፡፡ ቤቶቹ ሲፈርሱ በአካባቢው ግርግር ለመፍጠር የሞከሩ የነበሩ ቢሆንም፣ ነገር ግን አንድም ሰው የሞተ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡

የአካባቢው ነዋሪዎችም በወቅቱ አስለቃሽ ጭስ በመርጨት የነበረውን ግርግር ለመበተን ጥረት ሲደረግ ማየታቸውን፣ የጥይት ድምፅ እንደነበርና በርከት ያሉ አምቡላንሶች ሲመላለሱ በማየታቸው፣ የሞተ ሰው ሊኖር እንደሚችል ከመገመት ባለፈ የሞተ ሰው አለማየታቸውን ተናግረዋል፡፡

ነዋሪዎቹ ጨምረው እንዳስረዱት፣ ወረዳው ሰብስቧቸው በአካባቢው ረጅም ዓመታት ለቆዩ አርሶ አደሮች ምትክ ቦታና ካሳ እንደሚሰጥ ገልጾ፣ ሌሎች ነዋሪዎች ግን በቅርቡ የመጡና በሕገወጥ መንገድ የገነቡ በመሆናቸው እንዲያፈርሱ አስጠንቅቆ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ክረምት እየገባ በመሆኑና በድህነት የቀለሷትን ጎጆ አፍርሰው የት እንደሚሄዱ ግራ በመጋባታቸው፣ መንግሥትን ለመለመን በመዘጋጀት ላይ እያሉ ባላሰቡት ቀን መጥቶ ከነንብረታቸው በግሬደር እንዳረሰባቸው ተናግረዋል፡፡
‹‹እኛ ኃይል የለንም፣ ኃይል የእግዚአብሔር ነው፣ ዜጎቹን የመንከባከብና የማስተዳደር ኃላፊነትና ግዴታ ያለበት መንግሥት በጎዳና ላይ ከበተነን እኛ ኢትዮጵያውያን ነን?›› በማለት ጠይቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የተፈጸመባቸውን በደል አይቶ ብይን እንዲሰጣቸውም ጠይቀዋል፡፡

በአካባቢው የሚገኙ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውንና ልጆቻቸውም ትምህርት ማቆማቸውን ጠቁመው፣ ‹‹የትምህርት ዘመኑ እስኪጠናቀቅና መጪው ክረምት እስከሚወጣ ቢታገሱን ምን ችግር ነበረው?›› በማለትም የተፈጠረባቸውን ሐዘን ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ1988 ዓ.ም. እስከ 1997 ዓ.ም. ግንቦት ወር ድረስ፣ በሕገወጥ መንገድ ቤት ለሠሩ ሰነድ አልባ ቦታዎች ካርታ ሠርቶ በመስጠት ሕጋዊ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ከግንቦት ወር 1997 ዓ.ም. ወዲህ የተያዙ ሕገወጥ ግንባታዎች ግን ሕገወጥ ይዞታዎች መሆናቸውን በማስታወቅ፣ ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑንም አስተዳደሩ ይናገራል፡፡

በቦሌ ወረዳ 12 ወረገኑ በሚባለው አካባቢ ስለተሠሩት ቤቶች የአስተዳደሩ መሬት ልማት ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ኃይሌ እንደገለጹት፣ ግንባታዎቹ ከ2004 ዓ.ም. ወዲህ የተገነቡና ሕገወጥ ይዞታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም አስተዳደሩ በሕገወጥ ይዞታዎች ላይ የማያወላውል ዕርምጃ እንደሚወስድ ተናግረው፣ በወረገኑ የተወሰደው ዕርምጃም ከዚህ የተለየ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡
ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ

እውነት እና ፖለቲካዊ ትክክለኛነት

አቤል ዋበላ

Abel Wabella

እውነትን ለማስረዳት የሄግሊያን ትንታኔን መሰረት ማድረግ መርጣለው፡፡ እንደ ሄግሊያን ትንታኔ እውነት በወቅታዊ ሁኔታው የተረጋጋ የሚመስል እና ለውጥን በራሱ አቅጣጫ የሚያስተካክል ነው፡፡ ከታሪክ ፣ከትምህርት እና በአስተውሎት የሚገኙ እውነቶች አሉ፡፡ እነዚህ እውነቶችን መሰረት ያደረገ የቡድንም ሆነ የግለሰብ እንቅስቃሴ በስኬት የመጠናቀቅ ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ በዙርያችን ያሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ለእነዚህ እውነቶች ከመቆም ያግዱናል፡፡ ወይ እነርሱን የሙጢኝ ብለን የቀረን እንደሆን እኛን እሰከመጥፋት የሚያደርሱ ጉዳቶች ያስከትላሉ፡፡ ስለዚህ ህልውናችን ከሁሉም ነገር ስለሚበልጥን እያወቅን ዝም እንላለን፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ እውነቱን ብንናገር ለማኀበረሰቡም የማይጠቅም ነባራዊ ሁኔታዎችን ያላገናዘበ ይሆንና በሆድ ይፍጀው እናልፈዋለን፡፡

ከዚህ ጋር አያይዤ ማንሳት የምፈለገው ሌላው ነጥብ ደግሞ በእንግሊዘኛው Political Correctness የሚባለውን ነው፡፡ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ግርድፍ ትርጉሙ ሌሎችን ሊያስቆጣ ይቻላል በማለት እንቅስቃሴን እና ንግግርን መገደብ ወይም ለሌሎች በሚመች መልኩ ማስተካከል ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት ጥሩ ፖለቲከኛ የሚባለውም እንደ እውነቱ የሚያደርግ ሳይሆን እንደጊዜው የሚናገር እና የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ ይህ ለህዝቦች በሰላም፣ በእኩልነት፣ በነጻነት አብሮ መኖር እና ወንድማማችነት ሲባል የተደረገ ሲሆን ለአድራጊው ክብር የሚያጎናጽፍ እና አስተዋይነቱን የሚያስረዳ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ለዕኩይ ዓላማ፣ ለፍቅረ ነዋይ፣ ለስልጣን ጥማት፣ ለእዩኝ እዩኝ ባይነት(Publicity) አልያም በማስተዋል እጦት እና በሞኛሞኝነት ሲሆን ደግሞ አደጋው የከፋ ይሆናል፡፡ እውነትን ስላልተከተለ የስኬት መጠኑ የተገደበ ይሆናል፡፡ ማኀበረሰቡም ከእውነት እና ከታቀደለት ስኬት ስለሚርቅ ድርብ ኪሳራ ይደርስበታል፡፡

ይህንን ሳስብ ሁልጊዜ ወደ ህሊናዬ የሚመጣው መለስ እና ኢሳያስ የሄዱበት መንገድ ነው፡፡ መለስ እና ኢሳያስ ለዕኩይ ዓላማቸው ሲሉ እውነትን ያጣመሙ እና በተንኮል ብዙዎችን ያሳቱ ናቸው፡፡ ኢሳያስ አፈወርቂ በትውልድ ከመለስ ዜናዊ የበለጠ የትግራይ ተወላጅ ሆኖ ሳለ ኤርትራን ከኢትዮጵያ ለመገንጠል ነፍጥ አነሳ፡፡ (የመገንጠል ጥያቄ እንዲነሳ ያደረጉ ሌሎች ታሪካዊ እውነታዎች መኖራቸውን እየካድኩኝ አለመሆኑ ይሰመርበት) የኤርትራ ህዝብ በደም፣ በ ስነ ልቦና ቅርጽ፣ በኢኮኖሚ እና በባህል ከኢትዮጵያ ተነጥሎ መኖር እንደማይችል ሳይረዳው ቀርቶ አይደለም፡፡ ነገር ግን ይህንን እውነት ከአደባባይ ገሸሽ አድርጎ አትራፊ የመሰለውን ለግለሰባዊ ፍላጎቱ የተመቸውን መንገድ መረጠ፡፡ የኤርትራ እና ሌላው የኢትዮጵያ ክፍል የእርስ በርስ ጥገኝነት በትዕቢቱ ብቻ ሊለውጠው እንደማይችል ሲረዳ ይህንን የሚያስቀጥልበት ሸር ጎነጎነ፡፡ ለዚህም ወያኔን እንደ አሻንጉሊት በኢትዮጵያ በማንገስ እንደፈለገው እየጠመዘዘ ኤርትራን በቀጥታ ኢትዮጵያን ደግሞ በእጅ አዙር መግዛት ፈለገ፡፡ ይህ ለተወሰኑ አመታት የተሳካለት መሰለ፡፡ በመጀመሪያዎቹ የወያኔ አገዛዝ ዓመታት የኢትዮጵያ የደህንነት እና ፖሊስ የመሳሰሉ ወሳኝ የፖለቲካ ሀይል ማዕከሎች በኤርትራውያን የበላይነት ነበር የሚመሩት፡፡ በኢትዮጵያ የሚበቅሉ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ኤርትራ ከአንጋፋ አቅራቢ ሀገሮች አንዷ የሆነችበት አመታትም ነበሩ፡፡ ይህ ከእውነት ርቆ ያዋቀረው ደባ በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት ፈረሰበት፡፡ ለዚህም ይመስላል ከጦርነቱ ወዲህ ኢትዮጵያን የኤርትራ ዋነኛ ጠላት አድርጎ ብዙኃኑን ኤርትራዊ ለስደት ዳርጎ ካርታው ጠፍቶበት የተቀመጠው፡፡ ህዝቡም ይህንን ‘አጋሜ አምባገነን’ የሚያስወግድበት መላ ጠፍቶት እየባከነ ይገኛል፡፡

በአንጻሩ መለስ ዜናዊ መጀመሪያ አከባቢ ምንም እንኳን ከኢሳያስ አፈወርቂ የበለጠ የኤርትራ ደም ቢኖረውም በትግራይ ብሔርተኝነት እና “ትግራይ-ትግሪኝ” በምትባል ሐሳባዊ ማንነት ሲዋልል እንደነበር መገመት ይቻላል፡፡ ነገር ግን እንደ ኢሳያስ አፈወርቂ ትግራይንም ሆነ ኤርትራን ከኢትዮጵያ የተነጠሉ ሀገሮች ማድረግ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚበልጥ በመረዳቱ ከኢሳያስ በመንፈሱ አንድ የሆነ ነገር ግን በቅርጹ የተለየ ሴራን ሸረበ፡፡ ትግራይ ብቻዋን በመሆኗ ከሌላው የኢትዮጵያ ክፍል የምታጣውን ነገር ለማካካስ ከትግራይ ዘውግ ውጪ ያሉ ደካማዎችን በመሰብሰብ እነርሱን የሌላው ህዝብ የይስሙላ እንደራሴ በማድረግ በመላው ኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ አዛዥ ሆነ፡፡ እውነትን ትቶ በተንኮል መንገድ ስለሄደ ሁሉንም የሚያስማማው ስኬት ላይ ባይደርስም እርሱ እና ቤተሰቡ፣ በርከት ያሉ ከአንድ ዘውግ የተገኙ እና ሌሎች ጥቂት ሰዎች የሀገሪቱን ሀብት እንዲበዘብዙ መንገድ ከፈተ፡፡ እርሱን ሞት ቢወስደውም ይህ የብዝበዛ መንገድ በቅርቡ የሚዘጋ አይመስልም፡፡

ይህ የተንኮል መንገድ እና የደረሰብን ሀገራዊ ኪሳራ ብዙ ሊያስተምረን ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ከአንዳንድ ሁኔታዎች ለመረዳት እንደሞከርኩት የገባን አልመሰለኝም፡፡ በውሽት እና በሸር መንግስት የሚባል ነገር ተቋቋመ ያንን ተከትለን ፈሰስን፡፡ የወንበዴ ስብስብ ፓርቲ ነኝ ሲል እንዳልሆነ እያወቅን ለፖለቲካዊ ትክክለኝነት ስንል ተቀበልነው፡፡ ይባስ ብሎ ይህ የወንበዴ ቡድን ራሱ ጠፍጥፎ ካዘጋጃቸው ሦስት ቡድኖች ጋር ሆኖ ሀገራዊ ፓርቲ ነኝ ሲል አንዴ መስመሩ ስለገባን ይህንንም ከመቀበል በቀር አማራጭ አልነበረንም፡፡ ከፕሮፌሰር አስራት ጀምሮ ብዙዎች ለዚህ ወንበዴ ቡድን እውቅና ሰጥተው ወንበዴው ባዘጋጀው ቀመር መሰረት መጫወትን መረጡ፡፡ እንደ ፕሮፌሰር መስፍን ያሉ ጥቂቶች ገና ስርዓቱ ሲጀመር አንስቶ ይህ ስርዓት ቅንነት እና መዋቅራዊ ርዕቱነት ይጎለዋል ቢሉም የሰማቸው አልነበረም፡፡ ለዚህ ለወንበዴ ቡድን የሚሰጥ ዕውቅና ጫፍ ላይ የደረሰው በ97 ምርጫ ነው፡፡ገና ከጫካ ያልወጣውን ቡድን ሀገር በሙሉ ተሰብስቦ የዴሞክራሲ አዋላጅ አደረገው፡፡ ያን ጊዜ በባህሪው ያልነበረውን ነገር መሸከም ስላልቻለ እውነተኛ ማንነቱ ገሀድ ወጣ፡፡ ከጠብመንጃ አፈሙዝ በቀር ሌላ ቋንቋ እንደሌለው ከህጻናት እስከ አረጋውያን በመግደል አረጋገጠ፡፡ ከዚያ ወዲህ ባሉት አመታት ማስመሰሉን ቀንሶ እንዳሻው እያሰረ፣ እያሰቃየ አንዳንዴም እየገደለ ዛሬ ላይ ደርሷል፡፡ ድፍን ሀያ አምስት የተንኮል አመታት፡፡

ከላይ በመግቢያዬ እንዳነሳኹት ለህዝብ ጥቅም በጎ ዓላማ ሲባል እያወቅን እውነትን ብንጎዳትም ከሰው የሚበልጥ ነገር በምድር ስለሌለ ይኹን ብለን ማለፉ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ነገር ግን እንዲህ እውነትን እየጎዳን፣ ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን እየመረጥን ሀያ አምስት አመታትን አሳልፈን ህዝቡን ለብሔራዊ ጭቆና፣ ችጋር እና ስደት ከዳረግነው ሀገሪቱን ለመጠን አልባ ምዝበራ ከተውናት የሄድንበትን መንገድ ቆም ብለን ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ሁሉም የዱር እንሰሳ ስላባበልነው ብቻ ለማዳ ይሆናል ማለት ዘበት ነው፡፡ አንዳንድ የዱር እንስሳት ፈጽሞ ሰው አይለምዱም፡፡ ወያኔም እንደነዚያ አራዊት መሆኑን ባለፉት ሀያ አምስት አመታት አስመስክሯል፡፡ እስኪ እውነት ይዘን ደግሞ እንሞክረው፡፡ በንድፈ ሐሳብ ደረጃም እውነት ወደ ስኬት ለማድረስ የተሻለ ዕድል አለው፡፡

ለግለሰባዊ ፍላጎቱ የቆመ ሰው ምንም አይነት አሳማኝ ነጥቦች ብንደረድርለት ፖለቲካዊ ትክክለኝነቱን የሙጢኝ ማለቱ አይቀሬ ነው፡፡ ምክንያቱ የእንጀራ ገመዱ በዚያ የታሰረ ሰለሆነ ነው፡፡ አሁን እኔ ለመሞገት እየሞከርኩኝ ያለኹት በማስተዋል እጥረት ወይም በሞኛሞኝነት እንደው በዚህ መንገድ ብንሞክር ብለው ለሚያስቡ የዋሃን ነው፡፡ ይህንን ሙከራ የሚወልደው ህዝባዊ እምቢተኝነት እና ሰላማዊ ትግልን በትክክል አለመረዳት ይመስለኛል፡፡ አንድ ሰላማዊ ተጋይ ገዢው በፈቀደለት ቦይ ብቻ የሚፈስ ከሆነ ትግሉን ይጀምረዋል እንጂ አይጨርሰውም፡፡ ሰላማዊ ትግል ግን የህዝብን እውነት መሰረት አድርጎ በተፈቀደለትም ባልተፈቀደለትም የሚጓዝ ነው፡፡ ህዝባዊ እምቢተኝነት ቀመር ያለው ሳይሆን እንደየሀገሮች ሁኔታ ባልተለመደ(unorthodox) መልኩ የሚደራጅ ነው፡፡ይህ ያልተለመደ መልክ ምዕራባዊ ቀመር አያስፈልገውም፡፡ ይህ ህዝባዊ እምቢተኝነት የሚጀምረው ጨቋኙ ስርዓት ከህዝቡ የሚፈልገውን እውቅና በመንፈግ ነው፡፡ የህዝብን እውነት የያዘ በቂ ሰው እውቅና እሰኪነፍገው ድረስ ስርዓቱ በሁለት እግሩ እንደቆመ ይቀጥላል፡፡

በሀገራችን ያለውን ጨቋኝ ስርዓት ዕድሜውን የሚያራዝመው ሲጨንቀው ሀይል (Force) ከመጠቀሙ በቀር ብዙኃኑን ኢትዮጵያዊ እና ዓለምአቀፉን ማኀበረሰብ በማታለል (fraud) ነው፡፡ ይህንን ማታለል ደግሞ መስበር የሚቻለው ዕውቅና በመንፈግ ነው፡፡ ኢህአዴግ የሚባል የአራት ፓርቲዎች ስብስብ አይደለም ሕወኃት የሚባል የፖለቲካ ማኀበር ሀገሪቱን እየመራት እንዳልሆነ ለፖለቲካዊ ትክክለኝነት ብለን ካልሆነ በቀር ሁላችንም እናውቃለን፡፡ ይህ ቡድን ስሙ “ወያኔ” ነው፡፡ እውቅና መንፈግ የሚጀመረው ይህንን ጭምብል በማውለቅ ነው፡፡ ማን ትዕዛዝ እያስተላለፈ የሰብዓዊ መብት ረጋጣ እንደሚፈጸም እነርሱ እጅ ገብቶ የነበረ ሰው ሁሉ ይረዳዋል፡፡ ወያኔ የሚለውን የትግርኛ ቃል እየጠቀሱ ትርጉሙ እንዲህ ነው እንዲያ ነው የሚል ሁሉ የዚህን ቡድን የተረት ጅብድ አጽዳቂዎች ናቸው፡፡ ወያኔ የሚለው ቃል የትግርኛ ትርጉሙን ተሻግሮ በሕገ ወጥ መንገድ የፖለቲካ ሀይልን ለሀያ አምስት አመታት ይዞ የዜጎችን ሰብዓዊ መብት ሲገፍ የቆየ ቡድን መጠሪያ ሆኗል፡፡ ስለ ነጻነት የምር ግድ የሚለው ሁሉ ከዚህ ቡድን እና መጠሪያው ‘ወያኔ’ መሻገር ይገባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ኢዮብ ባልቻ እንዳስተዋለው ‘የዘመኑ ወጣት በጭፍን የ “ያ ትውልድ”ን ታሪክ በጭፍን ከማድነቅ ወጥቶ በጥንቃቄ ወደ መመልከት እንደገባው’ የትግራይ ወጣትም ለህዝቦች በሰላም፣ በእኩልነት፣ በነጻነት አብሮ መኖር እና ወንድማማችነት ሲል ከባዶ ተረት ወደ እውነታ መምጣት ይገባዋል፡፡ የዚህ ቡድን ሰዎች ላለፉት ሀያ አምስት አመታት በሀገሪቱ ላይ የፈጸሟቸውን ተግባሮች ተመልክቶ ትምህርታቸውን ጥለው ጫካ ገብተው ያንን የትግራይ ገበሬ ብዙ የህይወት መስዋዕትነት ያስከፈሉት ለምንድን ነው ብሎ መጠየቅ ይገባዋል፡፡

በመጨረሻም የወያኔ አገዛዝ እውነትን ሳይከተል ነገር ግን ሌሎቻችን በሰጠነው የፖለቲካ ትክክለኛነት ይሁንታ ሀያ አምስት አመታትን ተጉዟል፡፡ ወደ መፍትሔው ስንመጣ ወደኋላ መመለስ አለብን ማለት አይደለም፡፡ ምንም እንኳን ስርዓቱ ቅንነት ቢጎለውም በእነዚህ ዓመታት በጎም ሆነ መጥፎ ነገሮች ተከስተዋል፡፡ እነዚህ በጎ ነገሮች እና ከመጥፎዎቹ ውስጥ ደግሞ ወደኋላ ለመመለስ የሚከብዱ ነባራዊ ሁኔታዎችን ለመለየት ሰፊ ጥናት እና የሰከነ ውይይትን አድርገን ነገን ማሰብ መጀመር ይኖርብናል፡፡ ነገር ግን ይህ ለወያኔ እውቅና መስጠትን አይጨምርም፡፡ ምክንያቱም ወያኔን ያለስሙ ኢህአዴግ ወይም ሕወሓት ብለን ስንጠራው ጭቆናው ለሚቀጥሉት ሀያ አምስት እና ሐምሳ አመታት እንዲቀጥል እየወሰንን ነው፡፡

የሚዲያና የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች በኢሕአዴግ ላይ የሰላ ትችት አቀረቡ

የማነ ናግሽ

‹‹ሙስና የሥርዓቱ ባህል እየሆነ መጥቷል›› በማለት ኢሕአዴግ ላይ የሰላ ትችት ያቀረቡት የሚዲያና የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ባለፉት 25 ዓመታት ሙሉ የሚወራው ስለሙስና መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ባለፈው ዓርብ ግንቦት 12 ቀን 2008 ዓ.ም. 25ኛውን ዓመት የግንቦት 20 የብር ኢዮቤልዮ በዓል አስመልክቶ ከጋዜጠኞችና ከኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ጋር በብሔራዊ ቴአትር በተደረገው ውይይት፣ ተሳታፊዎቹ ኢሕአዴግንና እሱን የሚመራው መንግሥትን ገምግመዋል፡፡ ድርጅቱ ሥልጣን ከያዘ ጊዜ ጀምሮ ስለሙስና፣ ስለኪራይ ሰብሳቢነትና በሥልጣን ስለመባለግ ቢወራም ተመጣጣኝ ዕርምጃ ሲወሰድ አልታየም በማለት ክፉኛ ተችተዋል፡፡

ለውይይቱ መነሻ የሚሆን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ ፍሬሕይወት አያሌው የግምገማ ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን፣ ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት ይደበቃል፡፡ ሕዝቡ ግልጽ ሆኖለት ከተታገለው ግን እታች ተወርዶ ማቃጠል ይቻላል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ይህች አገር ፈርሳ ነው እየተሠራች ያለችው፡፡ እስካሁን ያስመዘገብናቸው ድሎችም ሊፈርሱ ይችላሉ፤›› በማለት ነበር የኪራይ ሰብሳቢነት አደጋን አስመልክተው በሰጡት ሐሳብ ጽሑፋቸውን የደመደሙት፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ፈተናው ትልቅ ነው ይላል፡፡ አይደለም ድልን ልናስመዘግብ ያረጋገጥነውም ሊበላብን ይችላል፣ ወደኋላ ሊወረውረንም ይችላል፤›› በማለት፡፡

ውይይቱን የመሩት የብሮድካስቲንግ ባለሥልጣን ኃላፊ አቶ ዘርአይ አስገዶም መድረኩን ለተሳታፊዎች ክፍት ሲያደርጉ አንዳንድ አድናቆቶች የቀረቡ ቢሆንም፣ በአብዛኛው የትችት ሐሳቦች ተንፀባርቀዋል፡፡

አቶ እንድርያስ ተረፈ አስተያየት ከሰጡት መካከል የመጀመርያው ናቸው፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ወደ አዲስ አበባ ሲገባ ‘ሌባ አይወድም’ ይባል ነበር፡፡ ዛሬ ግን ራሱ ኢሕአዴግ ሌብነት መገለጫው እየሆነ መጥቷል፡፡ 25 ዓመት ሙሉ የምናወራው ስለሙስና ነው፡፡ ሌብነት የሥርዓቱ ባህል እስከመሆን ደርሷል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹መኖር ከአቅም በላይ በሆነበት ዘመን ዛሬም የምናወራው ስለሙስና ነው፡፡ ከ25 ዓመት በኋላ ዛሬ ምን ተለወጠ? ምን አገኘንና በምን እንለካው?›› በማለት አክለዋል፡፡

‹‹ቤት አገኛለሁ ብዬ ኮንዶሚኒየም የተመዘገብኩት 97 ላይ ነበር፡፡ ዛሬ ግን ቤቶቹ ጠፉ እየተባሉ ነው፡፡ አንድ ሕንፃ ሲጠፋ ማን ተጠየቀ? ሕንፃዎቹ እስኪጠፉ መንግሥት የት ነበር?›› ብለዋል፡፡

የኪነጥበብ ባለሙያው አቶ ኃይላይ ታደሰ በበኩላቸው የቀረበው ሪፖርት ወደ ጥንካሬው ያመዘነ መሆኑን ገልጸው ነበር ትችታቸውን ያቀረቡት፡፡ ‹‹እንደ ባለሙያዎች እምብዛም ተጠቃሚ አይደለንም፡፡ አንቀጽ 29 ላይ የተቀመጡ መብቶችን እንዳንጠቀም የሚያግዱ አፋኝ ደንቦች እየተረቀቁ ይገኛሉ፡፡ ይኼ ከሴንሰርሺፕ (ሳንሱር) ተለይቶ የሚታይ አይደለም፤›› ብለዋል፡፡

አቶ ኃይላይ ትችታቸውን በመቀጠል፣ ‹‹ኢሕአዴግ ከአፄ ኃይለ ሥላሴና ከደርግ ጋር ራሱን እያወዳደረ ዕድገት አስመዘገብኩ ሲለኝ ያንስብኛል፣ ይወርድብኛል፤›› በማለት ድርጅቱ እንደ መንግሥት በራሱ ከያዘው ዕቅድ አንፃር፣ ከሰፊው ሕዝብ ተጠቃሚነት አንፃር መመዘን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡

‹‹ስብሰባና በዓል ታበዛላችሁ፡፡ ይኼ ሁሉ የተከፈለው መስዋዕትነት በተግባር ቢለካ አንድ ሰው ሌባ ከሆነ ሌብነቱን በሕዝብ ፊት አጋልጡት፡፡ አለበለዚያ ቁርጠኝነቱ ያላችሁ አይመስለንም፡፡ ከአንድ ቦታ አንስታችሁ ሌላ ቦታ ትሾሙታላችሁ፡፡ ለእኔ ቀልድ ነው የሚመስለኝ፡፡ ተግባብቶ ለውጥ የሚያመጣ ተግባር እያካሄዳችሁ አይመስለኝም፤›› በማለት ቀጥለዋል፡፡

‹‹አንድ ለልማት ተነሽ የሆነ አካባቢ ስታፈርሱትና ስታነሱት በጣም ነው የምትጣደፉት፡፡ አጥራችሁ ስታስቀምጡ ግን ረዥም ጊዜ ነው፡፡ አራት ከንቲባዎች ሲቀያየሩ ታጥሮ የተቀመጠ ቦታ የለም ወይ?›› በማለት የፍትሕ ማጣትና ሌሎች ማሳያዎችንም አቅርበዋል፡፡
ሕዝቡ የዕድገቱ ተጠቃሚ አለመሆኑንና ከአቅሙ በላይ በኑሮ እየተሰቃየ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ ‹‹ዕድገቱ ጤነኛ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ጥቂት ከጉምሩክና ከሌሎች ባለሥልጣናት ጋር የሚመሳጠሩ ዜጎች ያገኙትና የተሠሩ ነገሮች እንደ ዕድገት ከተለኩ እኔ ትክክል አይመስለኝም፡፡ የሕዝቡ ቁጥር መጨመርና ዘመኑ የደረሰበት ቴክኖሎጂ መለኪያው ያ ከሆነ አይገባኝም፤›› በማለት መንግሥት ባልተሠሩ ነገሮች ላይ ትኩረት አድርጎ እንዲንቀሳቀስ አሳስበዋል፡፡ ‹‹ችግሮቹ ያመዝናሉ፤›› በማለት፡፡

‹‹ሥርዓቱ ውስጥ በተደራጀ በቡድን አንዱ ሌላውን የሚጠልፍበት ሁኔታ የለም? ከሕዝብ የተደበቀ ነው? አይመስለኝም፡፡ ራሳችሁን ፈትሹ፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን የፈጠራችሁት እናንተ ናችሁ፡፡ ከሕዝብ የተደበቀ ነገር የለም፡፡ የክፍለ ከተማ ሹማምንቶች ቪ-8 አይደለም የሚያሽከረክሩት? ቪ-8 የሚነዳባት አገር ናት እንዴ ይህች አገር? ታክስ አልከፈልክም ተብሎ ግን ዘብጥያ ይወርዳል፤›› በማለት አስተያየታቸውን የቀጠሉት አቶ ኃይላይ፣ ‹‹ትግሉን ረስታችሁታል፡፡ ከተከፈለው መስዋዕትነት አንፃር ያማል፡፡ ስለዚህ የዚች 25 ዓመታት ስኬት እንደ ትምክህት እንድትወስዷት አልፈቅድም፡፡ መውደቂያችሁ እሱ ነው የሚመስለኝ፡፡ በ1993 ዓ.ም. ታደስን ትላላችሁ፡፡ እሱ ህዳሴ አልነበረም፡፡ መታደስ ያለባችሁ ዛሬ ነው፤›› በማለት ሐሳባቸውን ቀጠሉ፡፡

የመድረክ መሪዎችም ተሳታፊዎችም በፅሞና እያዳመጡ ነው፡፡ አቶ ኃይላይ ግን ትችታቸውን ቀጥለዋል፡፡ ‹‹ለምሳሌ ያ ሁሉ መስዋዕትነት የተከፈለበት አካባቢ ምን ይመስላል? ዛሬ ከማንም የተደበቀ አይደለም፤›› በማለት አንዳንድ የትግራይ ክልል አካባቢዎችን በመጥቀስ በትግል ጊዜ የተጠቀሙበት መንገድ ባለበትና አህያም ተጭና የማትሄድበት ጊዜ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሌላው አስተያየት ሰጪ የዓባይ ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ጋዜጠኛ ሲሆን፣ ውይይቱ እንደተለመደው የፕሮግራም ማሟያ እንዳይሆን ሥጋቱን ገልጾ አስተያየቱን ጀመረ፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት የተሠሩ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ገልጾ፣ ‹‹የተሠሩ ትልልቅ ነገሮችን የሚሸፍኑ የማይረቡ ትንንሽ ስህተቶች ትሠራላችሁ፤›› ሲል በሕዝቡና በመንግሥት በኩል አሉ ያላቸውን ችግሮች ተናግረዋል፡፡ ‹‹በአሁኑ ጊዜ ወረዳዎችና ቀበሌዎች እኮ ትልልቅ መንግሥታት ናቸው፤›› በማለት የተዘረጋው ሥርዓት ለሌብነትና ለስርቆት የተመቸ መሆኑን ተናግሯል፡፡
በጋዜጠኛው ሌባ ለማስያዝ የሚደረግ ጥረት እንደማይሳካና ፍርድ ቤት ተሂዶም ፍትሕ እንደማይገኝ ገልጾ፣ ‹‹እንዲያው ሳስበው ዛሬ ፍትሕ ያለው በኢቢሲ የሚተላለፈው ‹‹ችሎት›› ፕሮግራም ላይ ብቻ ነው፤›› በማለት ተሰብሳቢዎችን ፈገግ አሰኝቷል፡፡ ‹‹ትልቅ ስህተት የምለው፣ የኢሕአዴግ ትልቅ ስህተት የምለው የቀበሌና የወረዳ አስተዳደሮች የፓርቲው አባል በመሆናቸው ነው፡፡ ከአንድ ቦታ በሌብነት የተባረረ ሌላ ቦታ ተቀይሮ ተሹሞ እናገኘዋለን፡፡ ደንበኛ የአሠራረቅ ልምድ ይዞ ሄዷል፡፡ እዚህ ቀበሌ ሌባ የነበረ ሰው እዚያ ሲሄድ ወንበዴ ይሆናል፡፡ ማንም የማይመልሰው ወንበዴ፡፡ ከዚህ በኋላ ያፈጠጡ ሌቦች እንዲሆኑ እያደረጋችኋቸው ነው፡፡ የፓርቲ አባል ስለሆኑ፡፡ በእኔ እምነት ይኼ ሁሉ የፓርቲ አባል አያስፈልጋችሁም፡፡ የፓርቲ ቁጥር አይደለም ሥራ የሚሠራው፡፡ አስተሳሰቡ ያልተለወጠ ሰው ለውጥ አያመጣም፤›› በማለት አንድ ምሳሌ አነሳ፡፡

‹‹በሌላ እንዳይያዝብኝ ስለፓርቲ አይደለም እያወራሁ ያለሁት፤›› በማለት ቀጥሎ ያቀረበው ምሳሌ በ1997 ዓ.ም. ምርጫ ቀንደኛ የቅንጅት ደጋፊ የነበረ ሰው፣ የኢሕአዴግ ደጋፊ ናቸው ብሎ ያሰባቸው ብዙ ሰዎችን ጉዳት እንዳደረሰባቸው ተናግሯል፡፡ ‹‹አሁን ብትሄዱ ወረዳውን አልነግራችሁም ራሳችሁ ድረሱበት፤›› ካለ በኋላ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ውስጥ የአንድ ወረዳ የፀጥታ ኃላፊ እንደሆነ በመግለጽ፣ ‹‹ያን ጊዜ ያላዳረሳቸውን አሁን ለማዳረስ እንዲመቸው ይሁን እኔ አልገባኝም፡፡ ይኼ ሰው በሌላ ማልያ እንዲጫወት ተፈቅዶለታል፡፡ በትክክል ሥራቸውን ሲሠሩ የነበሩ ሰዎች ደግሞ ችግር ደርሶባቸው ሌላ ችግር ላይ የወደቁ አሉ፤›› በማለት እንዲህ ዓይነት ችግሮች እንዲስተካከሉ አሳስቧል፡፡

እንደ ጋዜጠኛ በ2004 ዓ.ም. ተንዳሆ መሄዱን አስታውሶ ቦታው ላይ የነበረው ሥራ የሚያስደስት እንደነበር ይናገራል፡፡ ‹‹25 ሺሕ ቶን ስኳር ማምረት ይችል ነበር፡፡ በአፍሪካ ሁለተኛ መሆን ይችል ነበር፡፡ ያኔ መጠናቀቅ ነበረበት፡፡ ዛሬም ድረስ ግን አልተጠናቀቀም፡፡ ስኳር ፋብሪካው ሲወድቅ በሒደት ነው፡፡ በአንድ ጊዜ ግንድስ አላለም፡፡ በአንድ ጊዜ ግንድስ ቢል ይሰማ ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ነው ዛሬ የተገነደሰው፡፡ የት ነበራችሁ? 88 ሕንፃዎች ጠፉ ሲባል የት ነበራችሁ? የተረከበውና ያስረከበውን የት ገቡ? ምን ዓይነት ሰዎች ናቸው ፈርመው ያስረከቡት? ስለዚህ ችግሮቹ በአንድ ጊዜ የመጡ አይደሉም፡፡ ፀረ ሙስና ጠንካራ ነው ስትሉን ሳቄ ነው የሚመጣው፡፡ የሚከሰው የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ነው፡፡ ፀረ ሙስና ይዞ የሚለቃቸው ሰዎች አሉ እሱም ተከፋይ ነው፤›› በማለት ጋዜጠኛው ምሳሌዎችን በመደርደር ወቀሳውን ደርድሯል፡፡

ወ/ሮ ፍሬሕይወት በሰጡት ምላሽ ያቀረቡት ሪፖርት ሚዛኑ የጠበቀ መሆኑን ተናግረው፣ የቀረቡትን ቅሬታዎች ማጣራት ያስፈልግ ይሆናል በማለት አልፈዋቸዋል፡፡

የኪራይ ሰብሳቢነት ምሽግ የተባሉ ዘርፎች ተለይተው በዚያ መሠረት ዕርምጃ እየተወሰደ እንደሆነ፣ እያንዳንዱ ተቋም በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ የሚገመገምበት ቋሚ አሠራር መዘርጋቱን ተናግረዋል፡፡ ከቀበሌ ጀምሮ ላይ ያሉት ዥንጉርጉር አሠራሮች መስተካከል እንዳለባቸው አስረድተዋል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን በተመለከተ ግን፣ ‹‹መንግሥት ሊፈጥረው አይችልም፡፡ ሕዝብን አገለግላለሁ የሚል መንግሥት ሙስናን ሊፈጥር አይችልም፤›› በማለት ተመጣጣኝ ዕርምጃ አይወሰድም የሚለውን አልተቀበሉትም፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች ግን መንግሥትን ጨምሮ የማይረባ ሥራ እንደሚሠራ ተቀብለዋል፡፡

‹‹ዋናውን ጉዳይ ግን መንግሥት ሕዝባዊ ነው፣ ያነሳችኋቸው ችግሮች የሉም ማለት አይቻልም፣ ጨለማ ግን አይታየኝም፤›› ብለዋል፡፡
አቶ ዘርአይ በሰጡት የማጠቃለያ ሐሳብ፣ ‹‹ሥርዓቱ 100 ሺሕ፣ 200 መቶ ሺሕ መስዋዕትነት ተከፍሎበት የመጣ ነው፡፡ ሥርዓቱ በቃኝ ይኼን ሠርቼያለሁ ብሎ ከቆመ የሞተ ነው ማለት ነው፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡

‹‹ኢሕአዴግ የራሱን ሌቦችም እየቆረጠ የሚጥል ነው፡፡ ታጋይ የነበሩ በኃላፊነት ላይ ሆነው ሲባልጉ ቆርጦ የሚጥል ቆራጥ ነው፡፡ ኢሕአዴግ እንደ ኢሕአዴግ ሌባ አይደለም፡፡ አሁንም ቦታው ላይ ነው ያለው፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡

በቅርቡ በጋምቤላ በተፈጸመው ጥቃትና በኤርትራ በተፈጸሙ ተደጋጋሚ ጥቃቶች ላይ ዕርምጃ ለምን አይወሰድም ተብሎ ጥያቄ ቀርቧል፡፡ አቶ ዘርዓይ፣ ‹‹የኤርትራ መንግሥት በ1993 ዓ.ም. አይደለም የገደልነው፡፡ አሁን ነው የገደልነው ጦርነት ባለመግጠም፤›› በማለት ሐሳባቸውን ደምድመዋል፡፡ ከዚህ ውጪ የመንግሥት ሚዲያን በተመለከተ በርከት ያሉ ትችቶች ቀርበዋል፡፡ ሚዲያው ራሱ ነፃና ሳይሆን የሕዝብ ሳይሆን፣ ሚዲያ ሳይያዝ ሙስናን እንዴት መታገል ይቻላል የሚሉ ጥያቄዎችም ቀርበዋል፡፡

ባለፈው ዓመት ሕወሓት 40ኛ ዓመቱን ሲያከብር አርቲስቶችና ጋዜጠኞች ወደ ድርጅቱ ታሪካዊ ቦታዎች እንዲሄዱ ባደረገበት ወቅት፣ ለድርጅቱ ሹማምንት ተመሳሳይ ጥያቄዎች ቀርበው እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

እንደኔ ቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰውራችኹ!

አቤል ዋበላ

Abel-Wabella

“እያዩ ፈንገስ” ወይም “ፌስታሌን” የተሰኘውን ትያትር ብዙዎቻችኹ አይታችኹታል ብዬ ገምታለው አልያም ስለ ማኀበራዊ እና ፖለቲካ ቀመስ ትችቶቹ በወሬ በወሬ ሰምታችኃል፡፡ እኔ ዝናውን የሰማኹት እስር ቤት ሳለኹኝ ነበር፡፡ ወያኔ እግዜር የስራዋን ይስጣትና እኔ ከወህኒ እስክወጣ ድረስ መድረክ ላይ አቆየችው፡፡ በትያትር ቤት ታድሜ እንደተዋራለት ሆኖ አገኘኹት፡፡ ይህን ጥበብ ለመድረክ እንዲበቃ ያደረጉትን እና በመድረክ እንዳይታይ ለማስተጓጎል ያልሞከሩትን አመስግኛለው፡፡

የትያትሩ አንድ ገቢር ግን እስካኹን ድረስ ውስጤ ቀርቷል፡፡ የተነሳኹበትን ሐሳብ ለማስረዳት ይረዳኛልና ይህንን ክፍል እንድተርከው ይፈቀድልኝ፡፡ እያዩ ፈንገስ ውድ ንብረቶቼ የሚላቸው ዕቃዎቹን የያዘ አንድ ፌስታል እንደጠፋበት ይናገር እና ለፍለጋ ይሰማራል፡፡ በሚኖርበት ሰፈር አቅራቢያ በሚገኙ ገንዳዎች፣ ቆሻሻ መጣያ ስፍራዎች ፈልጎ ያጣዋል፡፡ የክፍለ ከተማው ቆሻሻ መጣያ ስፍራ ሄዶ ቢፈልግም እንዳላገኘው ለተመልካቹ በሞኖሎግ ያስረዳል፡፡ በመጨረሻም የአዲስ አባባ ቆሻሻ በሙሉ “ቆሼ” እንደሚጣል እንደሰማ ተናግሮ ለፍለጋ ወደ መድረክ በስተጀርባ (ወደ ቆሼ) ይሄዳል፡፡ ከዚያ ሲመለስ የተናገረው ነገር ነው የኔን ቀልብ የማረከው፡፡ እያዩ አንዲት ፌስታሉን ፍለጋ ቆሼ ቢሄድ እራሱን ተራራ ከሚያክለው ቆሻሻ ጋር አወዳድሮ ወደተመልካቹ ተንበርክኮ “ዛሬ በቆሻሻ ፊት አነስኩላችኹ፤ እንደ እኔ በቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰወራችኹ” ሲል ሲቃ በተመላበት ድምጽ ተናገረ፡፡

ይህንን እንደተናገረ እኔ ከዚያ ትያትር ቤት ወጣኹኝ፡፡ በሐሳብ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ማዕከላዊ፣ አዲስ አበባ የቀጠሮ እስረኛ ማረፊያ ቤት ቂሊንጦ እና ልደታ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አስራ ዘጠነኛ ወንጀል ችሎት ሄጃለው፡፡ ለአንድ አመት ከስድስት ወር በቆሻሻ ፊት ያነስኩባከቸውን ጊዜያት አስታውስኩኝ፡፡ እየታመመኩኝ ውስጤ የሚሰማኝን ነገር አውጥቼ እንዳልናገረው የመግለጽ አቅም እያነሰኝ እያለ እያዩ ፈንገስ ደረሰልኝ፡፡

በቆሻሻ ፊት ማነስ እንዲህ ነው በሀገርህ እንደሁለተኛ ዜጋ ስለምትታይ የመብት ጥያቄዎችን አታነሳም ስለዚህ ከስርዓቱ አገልጋዮች ጋር ያለህ ግንኙነት የተገደበ ነው፡፡ ነገር ግን ሰው ነንና መሰረታዊ፣ ሰብዓዊ ፍላጎቶች ይኖሩናል፡፡ እነዚህን ለማግኘት ከማንም ጋር ይሁን መነጋገር፣ እርዳታን መጠየቅ እንገደዳለን፡፡ ለምሳሌ ሳይቤሪያ እያለን ከእስረኞቹ መሀል አንድ ሰው ይታመማል፡፡ አንዳንዴ ህመሙ እንደአተት(የሆድ ህመም) የሚደርግ ይሆንና እንቸገራለን፡፡ በር ደብድበን ይህ ሰው ሽንት ቤት ደርሶ እንዲመጣ ካላደረግን ማታ መጥተው ለአስር ደቂቃ ሽንት ቤት እንድንሄድ እስኪፈቅዱልን ድረስ የማይሆን ነገር እያየን እና እያሸተትን መቆየታችን ነው፡፡ በር ስንደበድብ ሰላማዊ ዋርድያ ካጋጠመን ታማሚውን “ቶሎ ደርሰህ ተመለስ” ይለውና ለእኛ ደግሞ ትንሽ ንጹህ አየር እንዲገባ በሩን ከፈት አድርጎት ይቆማል፡፡ ሁልጊዜ ግን ሰላማዊ ሰው ላያጋጥም ይችላል፡፡ “እዛው ቁጭ ይበል” ብሎ የሚል ይኖራል፡፡ ውጤቱ የከፋ ስለሚሆን ‘አረ ባክህ እረዳን . . . እና ሌሎች ኢትዮጵያዊ የልመና ዘዴዎችን’ ተጠቅመን ልቡን ለማለስለስ እንሞክራለን፡፡ ብዙ ጊዜ አይሳካም፡፡ ከዚህ በታች ከቆሻሻ በታች ማነስ ከየት ይመጣል፡፡ ባለ ማዕረግ ከሆነ ደግሞ ኮማንደር ወይም ሳጅን ማለትም ይጠበቅብናል፡፡

ቅሊንጦም እንዲሁ በቆሻሻ ፊት ሳንስ ከርሜ ነው የወጣኹት፡፡ ታመህ ቤተሰብ መድሃኒት እንዲያስገባልህ ለመጠየቅ ወይም ለሌላ በጣም አስፈላጊ ሰብዓዊ ጉዳይ አጋጥሞህ ሱፐር ኢንቴንዳንት፣ ኦፌሰር ምናምን ብለህ ያልተከበረውን አክብረህ መጥራት ይጠበቅብሃል፡፡ ሌላው ይቅርና “ካቴናው እጄን አጥብቆ ይዞታል ትንሽ አላላልኝ” ማለት በራሱ ለስድብ እና ማንጓጠጥ ሊዳርግ ይችላል፡፡ አንዳንድ በቆሻሻ ፊት ማነስን እና ንትርኩን የጠሉ ወዳጆቼ ካቴናው እጃቸውን እየሰረሰረው ችለው ይቀመጣሉ፡፡

ፍርድ ቤት ደግሞ ሌላው መተናነሻ ቦታ ነው፡፡ እንደኔ እንደኔ ጠበቃ ባላቆም፣ ባልከራከር እና የተውኔቱ አካል ባልሆን እመርጥ ነበር፡፡ ነገር ግን በጓደኛ እና ቤተሰብ ግፊት የማልሆነውን ሆኜ ነው የከረምኩት፡፡ የዐቃቤ ህግ በሬ ወለደ ክስ እና ሙያዊ ብቃት ማነስ አእምሮ ሊገምተው ከሚችለው በላይ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ያለህ ብቸኛ ምክኒያታዊ ድርጊት ከት ከት ብሎ መሳቅ ነው፡፡ ነገር ግን ችሎት በመድፈር እስከስድስት ወር እስራት ስለሚፈረድብህ ከቆሻሻ አንሰህ ሰብዓዊነትህን ለቀህ ምንም እንዳልተገረመ ሰው ለመሆን ትሞክራለህ፡፡ ለማይረባ ጉዳይ አንድ ወር ወይም ሁለት ወር ሲቀጥርህ የተከበረ ዳኛ እና ፍርድ ቤት እንደሌሉ እያወቅክ “የተከበረው ፍርድ ቤት፣ ክቡር ዳኛ ይህ ነገር ትንሽ አልዘገየም? በማረሚያ ቤት ሆነን እየተንገላታን ስለሆነ ቀኑን አጠር ቢያደርጉት” ልትል እጅህን ብታነሳ አይተው እንዳላየ ያልፉሃል፡፡ እንድትናገር ዕድሉን እንዲሰጡህ ድምጽህን ስታሰማ ስነ ስርዓት የጎደላቸው ሰዎች “ስነ ስርዓት፣ ስነ ስርዓት” ብለው ይገስጹሃል፡፡

እያዩ ተራራ በሚያክል ቆሻሻ ፊት ማነሱን ሲናገር እነዚህን እና ሌሎች በርካታ ህሊናን የመፈታተኑ ቅጽበታቶችን ነው ያስታወስኩት፡፡ ነገም ቆሼ መውረድ አልቀረልኝም፡፡ ነገ ከጓደኞቼ BefeQadu Z. Hailu, Natnail Feleke, Atnaf Brhane እና Soleyana Shimeles Gebremichael (በሌለችበት) ጋር ጠቅላይ ፍርድ ቤት እቀርባለው፡፡ ያው እያዩ ከክፍለ ከተማ ወደ ከተማ ሲሄድ የቆሻሻ ተራራው ግዝፈት እንዳስደነገጠው እኔም እንዲሁ ክው ብያለው፡፡ ክርክር ተሰምቶ ስላለቀ የመጨረሻውን ብይን ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ወይ ቂሊንጦ አለያም ፒያሳ እንገናኝ፡፡ ምንም እንኳን አረጋዊ ሁኜ ለምርቃት ባልበቃም መልካም ምኞቴን ትቼላችኹ ልሂድ፡- እንደኔ በቆሻሻ ፊት ከማነስ ይሰውራችኹ!

የዋና ኦዲተር ሪፖርት የመንግሥት ተቋማት የፋይናንስ ጥሰትና አፈጻጸም ከዓመት ዓመት እየባሰበት ነው አለ

ዮናስ ዓብይ

•ከሁለት ቢሊዮን ብር በላይ ያልተወራረደ ሒሳብ ተገኝቷል
• ጊዜው ያለፈባቸው አደገኛ ኬሚካሎች ለዜጎች እየተሸጡ ነው
• ሊብሬ ያላቸው ተሽከርካሪዎች በአካል የት እንደገቡ አይታወቅም
• የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና ዩኒቨርሲቲዎች ተወቀሱ

Gemechu Dubiso (General auditor)

የፌዴራል ዋና ኦዲተር ጽሕፈት ቤት የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች የ2007 የበጀት ዓመት ሒሳብ ኦዲት ማክሰኞ ግንቦት 9 ቀን 2008 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቀረበው ሪፖርት፣ አብዛኞቹ በጀት ተቀባይ የመንግሥት ተቋማት አስደንጋጭ የተባለ የሕግ ጥሰት የተገኘባቸው መሆኑን አስታወቀ፡፡ በዚህ ሪፖርት መነሻም ፓርላማው በአስፈጻሚ አካላት ላይ ቁጣውን ገልጿል፡፡

ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ ዱቢሶ በምክር ቤቱ ተገኝተው ባቀረቡት ሪፖርት፣ ብዛት ያላቸው የመንግሥት ተቋማት በተደጋጋሚ በየዓመቱ የሚሰጣቸውን አስተያየት ተግባራዊ በማድረግ ከማሻሻል ይልቅ፣ ወደባሰ ጥፋት እየገቡ መሆናቸውንና ለዚህም ዋና ምክንያቱ ተጠያቂ ያለመደረጋቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ዋና ኦዲተር ጽሕፈት ቤት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በስተቀር በሁሉም መሥሪያ ቤቶች የኦዲት ሥራ ማከናወኑን አስታውቋል፡፡ ዋና ዋና የተባሉና ልዩ ትኩረት የሚሹ የኦዲት ግኝቶችን ዋና ኦዲተር ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡

ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ አጠቃላይ ሪፖርታቸው በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የፋይናንስና ሕጋዊነት ኦዲት፣ በክዋኔ ኦዲትና በመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ድጋፍ (PBS) ላይ ባተኮሩ ሦስት ክፍሎች የቀረበ ነበር፡፡

ምንም እንኳ ተጠያቂ መደረግ አለባቸው የተባሉ የተለያዩ ተቋማት በዝርዝር ሪፖርቱ የተካተቱ ቢሆንም፣ በኦዲት ግኝቱ ስማቸው የተነሳው የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና አሥር ያህል ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው፡፡
በሕግ በተደነገገው መሠረት የሰነድ ሒሳብ በወቅቱ መወራረዱን ለማጣራት በተደረገው የኦዲት ሥራ፣ በ94 መሥሪያ ቤቶችና በ11 ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች 2.079 ቢሊዮን ብር በደንቡ መሠረት በወቅቱ መወራረድ አለመቻሉን ሪፖርቱ ያሳያል፡፡

ከዚህ ውዝፍ ሒሳብ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የያዙት የመንግሥት ግዢና ንብረት ማስወገድ አገልግሎት፣ የትምህርት ሚኒስቴር፣ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የአገር መከላከያ ሚኒስቴር፣ ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፣ ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

በተሰብሳቢ ሒሳብ ላይ የታዩ ዋና ዋና የአሠራር ችግሮች ያሉትን አቶ ገመቹ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን፣ በአራት መሥሪያ ቤቶች የተሰብሳቢ ሒሳብ ተቀፅላ ሌጀር ያልተዘጋጀላቸው ሒሳብ ከ174 ሚሊዮን ብር በላይ ተገኝቷል ብለዋል፡፡

በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሥር ባሉ ሦስት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶችና በሌሎች ሁለት መሥሪያ ቤቶች ከ15.9 ሚሊዮን ብር በላይ በወጪ ተመዝግቦ ሪፖርት መደረግ ሲገባው፣ ያላግባብ በተሰብሳቢ ሒሳብ ተይዞ መገኘቱን አስረድተዋል፡፡

የመንግሥት ገቢ በወጡት ሕጎች መሠረት በአግባቡ መሰብሰቡን ለማጣራት በተደረገ ኦዲት፣ በ34 መሥሪያ ቤቶችና በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሥር ባሉ አሥራ አምስት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች በድምሩ 118.7 ሚሊዮን ብር፣ እንዲሁም በአንድ መሥሪያ ቤት ተማሪዎች በገቡት ውል መሠረት ግዴታቸውን ባለመወጣታቸው ያልተሰበሰበ 211,930 ዶላር ግብር፣ ቀረጥና ታክስ አለመሰብሰቡንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡
በገቢ ሰብሳቢ መሥሪያ ቤቶችና ድርጅቶች ከፍተኛ የሚባሉ ገንዘቦች አለመሰብሰባቸውን የዋና ኦዲተር ሪፖርት በዝርዝር አስፍሯል፡፡ ለአብነትም በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከ689 ሚሊዮን ብር በላይ በበጀት ዓመቱ አለመሰብሰቡን አሳይቷል፡፡

የገቢ ሒሳብ ሪፖርት ውስጥ ያልተካተተ ገቢን አስመልክቶ የኦዲት ግኝቱ እንደሚያስረዳው፣ ገቢ እንዲሰበሰቡ በተፈቀደላቸው ተቋማት በትክክል ተመዝግቦ በገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር መቅረቡን ለማረጋገጥ በተደረገ የኦዲት ሥራ በስድስት መሥሪያ ቤቶች ከ76.7 ሚሊዮን ብር በላይ፣ በሌሎች አምስት መሥሪያ ቤቶች በገንዘብ መጠን ያልተገለጸ የውስጥ ገቢ ባቀረቡት ዓመታዊ የገቢ ሒሳብ ሪፖርት ሳይካተት መገኘቱን አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ ገልጸዋል፡፡

የገቢ ሒሳብ በሪፖርት ከማያካትቱት መሥሪያ ቤቶች አብዛኞቹ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሲሆኑ፣ ይህ አሠራር በገቢ ሒሳብ ላይ የሚደረገውን ቁጥጥር በማላላት ለምዝበራ በር የሚከፍት ከመሆኑም በላይ፣ መሥሪያ ቤቶቹ በራሳቸው የሚያዘጋጁዋቸው የሒሳብ መግለጫዎች የመንግሥት አጠቃላይ ገቢና ወጪ ሒሳብ ትክክለኛ ገጽታ እንዳያሳዩ ያደርጋል ብለዋል፡፡

በወጪ ሒሳብ አያያዝ፣ በግንባታ ኮንትራት ውል፣ በግዢና ንብረት አወጋገድና አስተዳደር ከፍተኛ የሕግ ጥሰትና አግባብነት የጎደለው አሠራር በአብዛኞቹ መሥሪያ ቤት ቢታዩም፣ ከፍተኛ ችግር የታየባቸውም ሆነ በተከታታይ ዓመታት መሻሻል ያላሳዩት አብዛኞቹ ዩኒቨርሲቲዎች መሆናቸውን ዋና ኦዲተሩ ገልጸዋል፡፡
የወጪ ሒሳብን በተመለከተ በ24 መሥሪያ ቤቶች የተሟላ መረጃ ሳይቀርብ ከ221.8 ሚሊዮን ብር በላይ በወጪ ተመዝግቦ መገኘቱን የኦዲት ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡ የተሟላ የወጪ ማስረጃ ሳይቀርብ በወጪ ከመዘገቡት መሥሪያ ቤቶች ትምህርት ሚኒስቴር 95,526,864.83 ብር፣ ሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ 26,417,436.86 ብር፣ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 10,000,000 ብር፣ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ 8,601,445.18 ብር፣ ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ 5,100,434.00 ብር፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ 4,646,850.00 ብር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

እንዲሁም ኦዲት በተደረጉ 56 መሥሪያ ቤቶችና አራት ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች ከደንብና ከመመርያ ውጪ ያላግባብ 61,397,293.70 ብር ተከፍሎ መገኘቱን የዋናው ኦዲተሩ ሪፖርት ያመለክታል፡፡
ማንኛውም ግንባታ ሲከናወን ሥራው በትክክል ስለመሠራቱ ብቃቱ ተረጋጋጦ የማማከር አገልግሎት እንዲሰጥ በሚመለከተው መንግሥታዊ አካል ፈቃድ በተሰጠው አማካሪ ድርጅት ሲረጋገጥ ብቻ፣ ክፍያዎች ሊፈጽሙ እንደሚገባ የሕግ አግባቡን ዋና ኦዲተሩ አስረድተዋል፡፡ ሆኖም በአራት መሥሪያ ቤቶች የፕሮጀክቶችን ሥራ እንዲከታተሉ የተቋቋሙ፣ ነገር ግን የማማከር ፈቃድ በሌላቸው የግንባታ ጽሕፈት ቤቶች በኮንትራክተሮች የተሠራው ሥራ ትክክለኛነት እየተረጋገጠ በሐሮማያ ዩኒቨርሲቲ 717,312,735.03 ብር፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ 74,495,345.59 ብር፣ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ 35,419,596.22 ብር እና በአክሱም ዩኒቨርሲቲ 7,428,032.90 ብር በድምሩ 834,655,709.74 ብር ገንዘብ ወጪ ሆኖ ተገኝቷል ሲሉም ገልጸዋል፡፡

የእነዚህን ዩኒቨርሲቲዎች ጉዳይ በተመለከተ ተጠያቂ የማድረግ ዕርምጃ ከመውሰድ በተጨማሪ የመፍትሔ ሐሳብ ያሉትንም አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲዎች ከዓመት ዓመት የሚፈጸሙት ስህተት እየተባባሰ በመሆኑ በትምህርት ላይ ብቻ እንዲያተኩሩ፣ ግዢ፣ ግንባታንና መሰል ሥራዎችን በተመለከተ ሌላ ተቋም ማቋቋም እንደሚገባ፣ ወይም በትምህርት ሚኒስቴር ሥር ለዚህ ዓላማ አንድ ዘርፍ እንዲቋቋም በማለት ለምክር ቤቱ አሳስበዋል፡፡ ነገር ግን ትምህርት ሚኒስቴር በራሱ ብዙ የኦዲት ችግር ከተገኘባቸው መሥሪያ ቤቶች አንዱ በመሆኑ፣ ይህንን ሥራ በአግባቡ ስለመፈጸሙ በአንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ጥያቄ ተነስቶበታል፡፡

በሌላ በኩል የምክር ቤቱን አባላት ያስደነገጠው ሌላው ጉዳይ በግብርና ምርት ማሳደጊያዎች አቅራቢ ድርጅት፣ የአገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎች ለአርሶ አደሮች የሚሸጡ መሆናቸው በዋና ኦዲተሩ ሪፖርት ሲቀርብ ነው፡፡ የተለያዩ የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ያለፈባቸው ኬሚካሎች በዝርዝር የተጠቀሱ ሲሆን፣ በኦዲት ሥራው ወቅት ኬሚካሎቹ ከሁለት ወራት እስከ ሁለት ዓመታት የመጠቀሚያ ጊዜያቸው ቢያልፍም በቀጥታ ለአርሶ አደሮች ሲሸጡ መታየታቸው በሪፖርቱ ተካቷል፡፡

በተጨማሪም በመድኃኒት ፈንድና አቅርቦት ኤጀንሲ የተገዙ ግምታቸው 570 ሚሊዮን ብር የሚሆኑ መድኃኒቶች፣ በዋናው መሥሪያ ቤትና በቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች በመጋዘን ተቀምጠው የመጠቀሚያ ጊዜያቸው አልፎ መገኘቱንም አቶ ገመቹ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል፡፡

ሕፃናትን በጉዲፈቻ መልክ ወደ ውጭ መላክን በተመለከተ የዋና ኦዲተር ሪፖርት ግኝቱንም አመላክቷል፡፡ በተለይ የሴቶችና ሕፃናት ሚኒስቴር የሚመለከታቸው ኃላፊዎች ከ2004 እስከ 2007 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት ውስጥ በናሙና ተመርጠው በታዩት የጉዲፈቻ አስፈጻሚ ድርጅቶች፣ ወደ አሜሪካና አውሮፓ ሕፃናትን በላኩባቸው አገሮች ጉብኝት ማድረጋቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ ነገር ግን ኃላፊዎቹ በሄዱባቸው አገሮች ያገኙዋቸው በጉዲፈቻ የተሰጡ ሕፃናት ደኅንነታቸው መጠበቁንና የጉዲፈቻ ተጠቃሚ መሆናቸውን የጉብኝት ዝርዝር ሪፖርት ቢያቀርቡም፣ እንዲሁም ባቀረቡት ሪፖርት መሠረት አስፈላጊውን ዕርምጃ መውሰድና ግብረ መልስ ሊሰጡ የሚገባ ቢሆንም ይህ የማይፈጸም መሆኑን በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡

የገቢና ወጪ ዕቃዎችን በተመለከተ ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ ወይም እንዳይወጡ በኢትዮጵያ ተስማሚነት ምዘና ድርጅት የላብራቶሪ ውጤት፣ ወይም ዓለም አቀፍ የሦስተኛ ወገን ሠርተፊኬት አምጥተው ትክክለኛነቱ ተረጋግጦ ደረጃቸውን የሚያሟሉ መሆናቸው ተረጋግጦ፣ ንግድ ሚኒስቴር ከሕግ አግባብ ውጪ በተቃራኒው ደብዳቤ በመጻፍ እንዲለቀቁ ማድረጉን የኦዲተሩ ሪፖርት አጋልጧል፡፡ እንዲሁም በሦስተኛ ወገን ሳይረጋገጡና የላቦራቶሪ ውጤት ሳይገለጽ ምርቶች ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ እያደረገ መሆኑንም ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡

በንብረት አስተዳደርም በርካታ የኦዲት ግኝቶች ለምክር ቤቱ የቀረቡ ሲሆን፣ የፓርላማ አባላቱን በቁጭት ፈገግ ያሰኘው የኢትዮጵያ ብዝኃ ሕይወት ኢንስቲትዩት በስሙ ከተመዘገቡ ተሽከርካሪዎች ውስጥ አሥሩ ሊብሬ ቢኖራቸውም፣ ተሽከርካሪዎቹ የት እንደደረሱ ምንም የማይታወቅ መሆኑን አቶ ገመቹ ሲገልጹ ነው፡፡
ከዋና ኦዲተሩ ሪፖርት በኋላም የት እንዳሉ የማይታወቁትን አሥሩን የኢንስቲትዩቱ ተሽከርካሪዎች አስመልክተው አስተያየት የሰጡት የምክር ቤቱ አባል አቶ ዱቤ ጂሎ፣ ‹‹ባለፉት ቀናት ከ88 በላይ የኮንዶሚኒየም ሕንፃዎች ጠፉ ተባልን፡፡ ዛሬ ደግሞ አሥር ተሽከርካሪዎች ከአንድ ተቋም ከጠፉ ነገ የተገነባ መንገድ ጠፋ የማንባልበት ምክንያት ላይኖር ነው?›› በማለት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

በዕለቱ አስተያየትና ጥያቄዎችን ሲያቀርቡ የነበሩ አብዛኛዎቹ የምክር ቤት አባላት ዋና ኦዲተሩን አቶ ገመቹን ላቀረቡት ሪፖርት ውዳሴና አድናቆት ሲያቀርቡላቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሥራ አስፈጻሚውን አካል ሲተቹ ውለዋል፡፡

ወ/ሮ ሙሉ ገብረ እግዚአብሔር የተባሉ የምክር ቤት አባል በሪፖርቱ ማዘናቸውን ገልጸው እያንዳንዱ መሥሪያ ቤት በሕግ ሊጠየቅ ይገባዋል ካሉ በኋላ፣ ‹‹ከዚህ በኋላ አንላቀቅም፡፡ ከማንኛውም አካል ጋር እንጠያየቃለን፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡ እኚሁ አባል፣ ‹‹ለብዙ ዓመታት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከተዘፈቀበት መውጣት አለመቻሉን ስመለከት ለእኔ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን፣ እስከ መክሰስ የሚያደርስ ዕርምጃ መወሰድ አለበት፤›› ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲዎችንም በተለመከተ ሕግ፣ አካውንቲንግ ወይም ማንኛውንም የትምህርት ዓይነት የሚያስተምር ተቋም እንዴት የራሱን ስህተት ሊያርም አይችልም በማለት ጠይቀዋል፡፡

አቶ መሐሪ ዘለቀ የተባሉ ሌላ የምክር ቤት አባል በበኩላቸው፣ ‹‹ጊዜ ያለፈባቸውን ኬሚካሎች የሚሸጥ ተቋምን በአስተያየት ብቻ ማለፍ የለብንም፡፡ በሕግ ጭምር የግድ መጠየቅ አለበት፡፡ በሰው ሕይወት የራሱን ትርፍ ለማጋበስ የሚሞክር ተቋም ዝም ሊባል አይገባውም፤›› ብለዋል፡፡

በተደጋጋሚ ዓመታት ተመሳሳይ የኦዲት ግኝት ቀርቦባቸው መሻሻል በማያሳዩ ላይ በምክር ቤቱ በኩልም ሆነ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት ዕርምጃ መወሰድ እንዳለበት፣ በርከት ያሉ የምክር ቤቱ አባላት ተመሳሳይ አቋማቸውን ሲሰነዝሩ ተስተውለዋል፡፡ ዋና ኦዲተሩ አቶ ገመቹ የመንግሥት ተቋማቱ በተደጋጋሚ የሕግ ጥሰት የሚፈጽሙት ተጠያቂ ባለመሆናቸው ምክንያት መሆኑን አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

በምክር ቤቱ አሠራር መሠረት ለመጀመርያ ጊዜ ዋናው ኦዲተሩ ሪፖርታቸውን ሲያቀርቡ፣ የኦዲት ተደራጊ መሥሪያ ቤቶች ኃላፊዎች በምክር ቤቱ ተገኝተው ሪፖርቱን እንዲከታተሉ በአፈ ጉባዔው ጥሪ ተገኝተዋል፡፡ ነገር ግን ከሰዓት በኋላ በነበረው የጥያቄና መልስ ክፍለ ጊዜ አብዛኛዎቹ የተቋማቱ ኃላፊዎች ባለመገኘታቸው በአንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት ትችት ተሰንዝሮባቸዋል፡፡

ምንጭ፡-ሪፖርተር ጋዜጣ