Monthly Archives: May, 2016

‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› ማለት ሊቀር ነውን?

Daniel Kibret

ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

ቅዱስ ሲኖዶስ የፓትርያርኩን እንደራሴ ሹመት በተመለከተ ለመወያት የያዘው አጀንዳ የመንግሥት ተወካይ ባለበት እንዲታይ መወሰኑን ዛሬ ጠዋት ሰማን፡፡ ከብጹዐን ጳጳሳት በቀር ካህናትና ቆሞሳት እንኳን የማይገቡበት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አማኝ ይሁን ኢአማኒ፣ ሙስሊም ይሁን ክርስቲያን የማይታወቅ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝበት መጋበዙ የደረስንበትን የውርደት ደረጃ የሚያሳየን ነው፡፡

በአንድ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ወሳኝ አካል መሆኑን ስናስበው፤ በሌላ በኩል የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የሚደረገው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ነው፤ ውሳኔውም በሐዋርያት ሥራ እንደተገለጠው ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› የሚባልበት ነው(የሐዋ. 15፣29) የሚለውን ስናየው ‹የመንግሥት ተወካይ ይኑርልን› የሚለውን ውሳኔ ኢሃይማኖታዊ ነው ያሰኘዋል፡፡ ለአንድ የሲኖዶስ ጉባኤ የመንፈስ ቅዱስ መገኘት አልበቃው ብሎ ነው የመንግሥትን ተወካይ የሚጋብዘው? ‹ሱባኤ ይዘን፣ ጸሎት አድርገን፤ አንድ ገዳም ወርደን፣ ከእግዚአብሔር ጋር መክረን› አይደለም ይሉን አባቶቻችን፡፡ ‹የመንግሥትን ተወካይ ጋብዘን› ነው ያሉን፡፡ እንዲያውም ቀኖናው የሊቀ ጳጳሳቱ(ፓትርያርኩ) ጉዳይ ሲታይ ‹በመቀመጫቸው መካከል አንድ ወንበር አስቀምጠው፣ ቅዱስ ወንጌሉን በዚያ ላይ አኑረው፣ ሊቀ ጳጳሳቱ በፊታቸው ተቀምጦ፣ አንድነት ተነሥተው በሩን ዘግተው ይጸልዩ፤ የተሰበሰቡበትንም ጉዳይ በሥውር(በኅቡእ) ይመርምሩ› ነው የሚለው(ፍ.ነ. ዐ.168)፡፡ እንዴት ተደርጎ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የሚታየው? አግዚአብሔር ያየናል የሚለው ጠፍቶ ታዛቢ ቢያስፈልግ እንኳን የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ለታዛቢነት አይበቁም? ቅዱስ ጳውሎስ ‹በወንድሞች መካከል ሽማግሌ ሊሆን የሚችል አንድ አስተዋይ ሰው በእናንተ ዘንድ አይገኝምን?› (1ኛቆሮ. 6፣5) ያለው ለዚህ ጊዜ አይሆነንም?

በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ላይ የመንግሥት ተወካይ እንዲገኝ መጋበዙ በአንድ በኩል የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዕልና የሚነካ በሌላ በኩልም ሕገ መንግሥቱን የሚጥስ፤ በመጨረሻም ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚያፈርስ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያለ ማንም ጣልቃ ገብነትና ታዛቢነት የራስዋን ጉዳዮች በራስዋ ሕግጋት፣ ቀኖናና ሥርዓት መሠረት የመወሰን መብት አላት፡፡ አባቶቻችን ከንጉሥ ሐርቤ ዘመን ጀምረው ከግብጽ ሲኖዶስ ጋር ሲሟገቱ የኖሩት ይህን ሉዐላዊነት ለቤተ ክርስቲያናቸው ለማስገኘት ነው፡፡ ጳጳሳትን ለማግኘት የግብጽ ሡልጣኖች መለማመጥ፣ የግብጽንም ፓትርያርኮች መለመን ሰልችቷቸው፡፡ ከግብጽ ቀድማ ክርስትናና የተቀበለች ሀገር፣ የራስዋን ጉዳይ ለመወሰን አለመቻሏ አስደናቂ ስለሆነባቸው፡፡ ከቤተ ክርስቲያንዋ ታላቅነትና ከሀገሪቱ ክብር ጋር ስላልተመጣጠነላቸው፡፡

ዛሬ ያ ሁሉ ተረስቶ መንግሥትን በገዛ ፈቃዳቸው ‹አንተ በመካከላችን ካልተገኘህ አንሰበሰብም› የሚሉ አባቶች መጡ፡፡ ቀደምት አበው ‹አንተ ከኛ ጋር ሁን› የሚሉት ፈጣሪያቸው ነበር፡፡ ዘመን ተቀየረ፡፡ በቀደመው ጊዜ ‹መንግሥት ለምን በጉዳያችን ውስጥ ይገባል?› ነበር ክርክሩ፡፡ ‹አሁን መንግሥት ከሌለ ይህንን አጀንዳ አናይም› የሚባልበት ዘመን ላይ ደረስን፡፡ የፓትርያርክ እንደራሴ ጉዳይ የሃይማኖት ጉዳይ ነው፡፡ እንደራሴውም የሚፈጽመው ሃይማኖታዊ ጉዳዮችን ነው፡፡ የሥልጣን ክልሉም በቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን ክልል ነው፡፡ ታድያ ለምንድን ነው መንግሥት ያስፈለገው? ይህንን ጥያቄ ፓትርያርኩ ጠይቀውት ይሆናል፡፡ እንደመከራከሪያ ቢያቀርቡት አይገርምም፤ ቢያሳዝንም፡፡ የምልዐተ ጉባኤው መቀበል ግን ሕመም ነው፡፡

መንግሥትስ ቢሆን ምን ብሎ ነው ተወካይ የሚልከው? ምናልባት ‹ጠሩኝ፣ ሄድኩ› ካላለ በቀር፡፡ ሕገ መንግሥታችን መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ እንደማይገባ በግልጽ እየደነገገ እንዴት አድርጎ ነው በቀኖናዊ ስብሰባ ላይ የሚገኘው? ውሳኔውንስ ከየትኞቹ የቀኖና መጻሕፍት ጋር ሊያገናዝብ ነው? በጉባኤው የሚኖረውስ ሚና ምን ሊሆን ነው? ምን ዓይነት ወኪልስ ነው የሚወክለው? በየትኛው ሥልጣንና ሕግ ነው የሚገኘው? የዚህ ዓይነቱ አሠራርስ መጨረሻው ምን ይሆናል? በጉባኤው ላይ የሚተላለፈው ውሳኔ የማን ውሳኔ ነው? ‹የእኛና መንፈስ ቅዱስ› ወይስ ‹የእኛና የመንግሥት›? መንግሥትም ጉዳዩን ሊያስብበት ይገባል፤ ‹ሲጠሩት አቤት› ሳይሆን ‹ሲጠሩት ለምን?› መሆን አለበት፡፡

የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ኤጲስ ቆጶስ በዚህ ዓለም መኳንንት ርዳታ አንዳይቆም ያዝዛል፡፡ በእምነቱና በእግዚአብሔር ቃል ብቻ እንዲጸና፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ 176፤ረስጠብ 21) በዲድስቅልያም ላይ ‹ከቤተ ክርስቲያን ሹሞች በቀር ሕዝባዊ አይፍረድ› ይላል (ዐንቀጽ 71)፡፡ ታድያ በምን ሕግ ነው የመንግሥት ተወካይ ባለበት የቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤውን የሚያደርገው?

ዛሬ እንደዋዛ የሚከፈተው በር ነገ እንዝጋህ ቢሉት አስቸጋሪ ነው፡፡ አንድ አባት የመንግሥት ተወካይ ይገኝልኝ ባለ ቁጥር የሚፈቀድ ከሆነ፤ ነገ ደግሞ ወንድሜ ባለበት፤ እናቴ ባለችበት፤ ሐኪሜ ባለበት፣ ፖሊስ በተገኘበት ይሄ አጀንዳ ይታይ የሚል ነገር መስማታችን አይቀሬ ነው፡፡ ጋባዡም፤ ተጋባዡም ቆመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ መቼም እንደዘንድሮ የእንጦንስና ጳውሊ ራእይ በተግባር የታየበት ዘመን የለም፡፡

ሀገር አቀፉ የ12ኛ ክፍል ዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ተደረገ

(አዲስ ሚዲያ) ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሐሙስ ግንቦት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊሰጥ የነበረው ሀገር አቀፍ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግቢያ የሆነው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ተቋረጠ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር መገለጫውን በድረ-ገፁ እንዳስታወቀው ከሆነ፤ ብሔራዊ ፈተናው እንዲቋረጥ የተደረገበት ምክንያት ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ኮድ 14 የእንግሊዘኛ ፈተና በመውጣቱ ነው፡፡ ሚኒስተሩን አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በመስሪያ ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ሌሎች ፈተናዎች ላለመውጣታቸው ምንም ዓይነት ማረጋገጫ ባለመኖሩ ሁሉም ፈተናዎች እንዲቋረጡ መደረጉን በመጠቆም፤ ተማሪዎችን እና ወላጆቻቸውን ይቅርታ ጠይቀዋል፡፡

ENEA cancelled press released, 2016

ይሁን እንጂ እንዲቋረጥ የተደረገው የዚህ ዓመት የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ሌላ ፈተና በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚዘጋጅ ከመግለፅ ውጭ፤ መቼ ሊሰጥ እንደተወሰነ የተገለፀ ነገር የለም፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የፈተናውን መቋረጥ አስመልክቶ ዛሬ አራት ኪሎ በሚገኘው ዋና ጽህፈት ቤቱ ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤ ፈተናው ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ለምን እና እንዴት ወጥቶ ሊሰራጭ እንደቻለ እና ለተፈጠረው ችግር ማን ኃላፊነት መውሰድ እንዳለበት ከመግለፅ ተቆጥቧል፡፡

ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ እንግሊዘኛ ኮድ 14 ከመፈተኛው ቀን አስቀድሞ ወጥቷል ቢሉም፤ በተመሳሳይ ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. የሂሳብ ትምህርት የተፈጥሮ ሳይንስ እና ማኀበራዊ ሳይንስ የሂሳብ ትምህርት ፈተናም በተመሳሳይ መልኩ ከነ መልሶቻቸው በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨታቸው ታውቋል፡፡ የአዲስ ሚዲያ ምንጮች ከሆነ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. ሊጀመር የነበረው ሁሉም የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተናዎች ግንቦት 11 ቀን 2008 ዓ.ም.በተለይ በኦሮሚያ ክልል ለወራት ትምህርታቸው የተስተጓጎለባቸው ተማሪዎችን ታሳቢ ሳያደርግ የፈተናውን መሰጠት በሚቃወሙና ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች ከመፈተኛው ቀናት አስቀድሞ ፈተናውን አዘጋጅቶ ከሚያሰራጨው ትምህርት ሚኒስቴር፤ ሀገር አቀፍ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች ኤጀንሲ ቢሮ እንደወጣ ጠቁመዋል፡፡

NEAEA,Ethiopia

በተመሳሳይም ባለፈው ሳምንት የተሰጠው የ10ኛ ክፍል ፈተናም እንደ 12ኛ ክፍሉ ባይሆንም አስቀድሞ መውጣቱና በተወሰነ መልኩ መሰራጨቱ ቢገለፅም፤ እንደ 12ኛ ክፍል ፈተና በማኀበራዊ ሚዲያ ባለመሰራጨቱ እና በገለልተኛ አካል ይፋ ባይገለፅም፤ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ግን የ10ኛ ክፍል ፈተናም ወጥቶ መሰራጨቱን አስተባብለዋል፡፡ ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ከዛሬው መግለጫና የወጣው ፈተናው በማኀበራዊ ሚዲያ ከመሰራጨቱ በፊት ትናንት እሁድ ግንቦት 21 ቀን በኢቢሲ ዜና እወጃ “ፈተናው ተሰርቆ ወጥቷል የሚባለው መረጃ ሐሰት ነው፤ ስለዚህ ተማሪዎች ለዛሬው ፈተና ተረጋግተው እንዲዘጋጁ” የሚል ማሳሰቢያ መስጠታቸው አይዘነጋም፡፡

ለፈተናው ቀድሞ መውጣትና በማኀበራዊ ሚዲያ መሰራጨት ዋነኛ ምክንያት፤ ከህዳር 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ለ5 ተከታታይ ወራት የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ልዩ ዞን አዲሱ የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ተቃውሞ በተለይ መንግሥት በኦሮሚያ ክልል የወሰደውን የኃይል እርምጃ ተከትሎ በተፈጠረ አለመረጋጋት ፈተናው እንዲራዘም የቀረበው የተማሪዎቹና የወላጆቻቸው ጥያቄ ውድቅ በመደረጉ የተወሰደ የአፀፋ እርምጃ እንደሆነ ፈተናውን ካሰራጩት አካላት ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክ የዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ከተማሪዎች መፈተኛ ቀን አስቀድሞ ወጥቶ የተሰራጨበትም ሆነ ፈተናው በሀገር አቀፍ ደረጃ ሙሉ ለሙሉ እንዲቋረጥ ሲደረግ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡

“ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ መብትና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡት ድርጊት ልከሰስ አይገባም” አቶ ዮናታን ተስፋዬ

ታምሩ ጽጌ

በፌስቡክ አድራሻቸው አመፁና ብጥብጥ ቀስቃሽ ጽሑፎችን በማሠራጨት፣ የኦነግን ዓላማ ለማስፈጸም ተንቀሳቅሰዋል ተብለው በሽብር ተግባር ወንጀል ተጠርጥረው የተከሰሱት የቀድሞ የሰማያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ የቀረበባቸውን ክስ ተቃወሙ፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ፣ ‹‹ሕገ መንግሥቱ በሰጠኝ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትና በክሱ የተጠቀሰው ብጥብጥና አመፅ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባረጋገጡበት ሁኔታ ልከሰስ አይገባም፤›› ሲሉም ተቃውሞአቸውን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

Yonatan Tesfaye

በኦሮሚያ ክልል ተከስቶ የነበረው ብጥብጥና አመፅ ‹‹የመልካም አስተዳደር ዕጦት ችግር ነው፡፡ የሌላ ሦስተኛ አካል ተሳትፎ የለበትም፤›› በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ማረጋገጣቸውን ያስረዱት ተከሳሹ አቶ ዮናታን፣ የተለያዩ የፌደራልና የክልል ሥራ ኃላፊዎችና ባለሥልጣናትም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር በማጠናከር፣ ዕርምጃ የወሰዱበትና በርካታ ሹማምንትም ከኃላፊነት መነሳታቸውን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ የሚያውቀውና ከማንም ያልተደበቀ በመሆኑ፣ ግልጽ የሆነ የሕግ ግምት (Judicial Notice) የሚወስድበት ጉዳይ መሆኑን አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ዞኖች፣ ወረዳዎችና ቀበሌዎች የተደረገው አመፅና ብጥብጥ የመልካም አስተዳደር ዕጦት መሆኑ ተረጋግጦ ሳለ፣ በቀረበባቸው ክስ ላይ በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) እንደተጀመረና እሳቸው በፌስቡክ ገጻቸው ባሠራጩት መጣጥፍ ለማስቀጠል የተደረገ እንደሆነ መገለጹ፣ ከአዋጁ መንፈስ ውጪ መሆኑን በመጠቆም ክሱ ውድቅ ተደርጐ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

አቶ ዮናታን በክስ መቃሚያቸው ላይ እንዳብራሩት፣ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (4)ን መተላለፋቸው ተገልጿል፡፡ በአንቀጹ እንደተገለጸው ተላልፈዋል የተባለው ድርጊት ማቀድ፣ መዘጋጀት፣ ማሴር፣ ማነሳሳትና መሞከር የሚል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ በክሱ ያሰፈረው አቶ ዮናታን ኦነግ ያስጀመረውን አመፅና ብጥብጥ ለማስቀጠል በፌስቡክ ገጻቸው ላይ የተለያዩ ቀስቃሽ ጽሑፎችን ማሠራጨታቸውን የሚገልጽ በመሆኑ፣ በአዋጁ አንቀጽ ሥር ከተመለከቱት ውስጥ በአንዱም የማይሸፈን መሆኑን በመግለጽ አብራርተዋል፡፡ በመሆኑም የዓቃቤ ሕግ ክስ በወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 112 የተደነገገውን ማለትም ‹‹… ወንጀለኛው የፈጸመው ተግባር፣ ወንጀል ከሚያደርገው የሕግ አነጋገር ጋር በጣም የተቀራረበ መሆን አለበት፤›› ከሚለው ድንጋጌ ጋር የሚጋጭ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

አቶ ዮናታን ፈጽመውታል ለተባለው ክስ በማስረጃነት የቀረበው የሰነድ ማስረጃ በፌስቡክ ገጻቸው ተሠራጨ የተባለው መጣጥፍ መሆኑን ገልጸው፣ ፌስቡክ ደግሞ ዘመናዊ የመልዕክት መለዋወጫ ዘዴ መሆኑን፣ ይኼም በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ድንጋጌ ከመሆኑ አንፃር፣ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በየትኛውም ሕግ ገደብና ክልከላ ያልተደረገባቸውና በቀረበባቸው ክስ በተጠቀሰው አንቀጽ ሥር የማይሸፈንና የሽብርተኝነት ተግባር አለመሆኑንም አቶ ዮናታን አክለዋል፡፡ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ ሕገ መንግሥታዊና ሰብዓዊ መብታቸውን ለማስከበር የተቀመጡ መርሆዎችንና ድንጋጌዎችን የማያሟላ ክስ መሆኑን ገልጸው፣ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸው ክስ ሐሳቡና ይዘቱ አርትኦትና የቃላት ማስተካከል የጎደለው ከመሆኑም በተጨማሪ ለመረዳት የሚያስቸግር፣ በረጃጅም ዓረፍተ ነገሮችና አባባሎች አሳሳች ሆኖ የቀረበ በመሆኑ በወንጀል መዝገብ ሥነ ሥርዓት ቁጥር 111 ድንጋጌን ማለትም፣ ‹‹… የክስ ማመልከቻ ቀን፣ ዓመተ ምሕረት የተጻፈበትና የተፈረመበት…›› የሚለውን የማያሟላ መሆኑን አቶ ዮናታን ጠቁመው፣ ክሱ ተሰርዞ በነፃ እንዲሰናበቱ ጠይቀዋል፡፡

ዓቃቤ ሕግ ክሱን የሚያሻሽል ከሆነም በሕጉ አግባብ ሥነ ሥርዓቱን ተከትሎ በሚያቀርበው ክስ ላይ የሚጠቅሰው የሕግ አንቀጽ፣ ከክሱ ጋር የሚቀራረብና የተከሳሹን የመከራከር መብት የማያጣብብ አድርጐ እንዲያዘጋጅ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው፣ ጉዳዩን ለሚከታተለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ግንቦት 15 ቀን 2008 ዓ.ም. አመልክተዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም የዓቃቤ ሕግን ምላሽ ለመጠባበቅ ለግንቦት 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
ምንጭ፡- ሪፖርተር ጋዜጣ

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የሽብርተኝነት ክስ ተመሰረተበት

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

Getachew Shiferaw

የፌደራል አቃቤ ህግ ግንቦት 10 ቀን 2008 ዓ.ም በተጻፈ የክስ ማመልከቻ የሽብር ክስ የመሰረተበት የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ላይ የቀረበው ክስ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ 7(1) ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት መተላለፍ የሚል ነው፡፡
ተከሳሹ ከ24/05/2006 ዓ.ም እስከ 13/04/2008 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ግንቦት ሰባት ከተባለ የሽብር ድርጅት አመራሮች ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ በተለይም ፌስቡክ እና ስልክ ግንኙነት በመፍጠር ለሽብር ቡድኑ ተልዕኮ የተለያዩ መረጃዎች በማስተላለፍና በሽብር ድርጅት ውስጥ መሳተፍ ወንጀል ፈጽሟል ሲል አቃቤ ህግ በክሱ ላይ ጠቅሷል፡፡

በአቃቤ ህግ ክስ ላይ እንደተመለከተው ተከሳሽ ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው በህግ ተመዝግቦ በሀገር ውስጥ ህጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ የሚያደርገው ሰማያዊ ፓርቲ አባላት ጋር ያደረገው የመልዕክት ልውውጥ ክስ ሆኖ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው ከተለያዩ ውጭ ሀገር ከሚገኙ ሚዲያዎች ባለሙያዎች በተለይም ኢሳት ጋር ያደረጋቸው ቃለ-መጠይቆችና የመረጃ ልውውጦችም በሽብር ክስነት ቀርበውበታል፡፡ ተከሳሹ በሽብርተኝነት ክስ ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ቤተሰቦቻቸውን እንዴት ማገዝ ይቻላል በሚል ከዳያስፖራ አባላት ጋር በማህበራዊ ድረ ገጽ የተለዋወጣቸው መልዕክቶችም በክሱ ላይ ተካተው ቀርበዋል፡፡
በአጠቃላይ ጌታቸው ‹‹…በተለያዩ አካባቢዎች ከሚገኙ የሽብር ቡድኑ አባላት ጋር እየተገናኘ መረጃ በመሰብሰብ በውጭ ሀገር ለሚገኙ የሽብር ቡድኑ አመራሮች መረጃ በማስተላለፍ….›› በሽብር ድርጅት ውስጥ በማናቸውም መልኩ መሳተፍ ወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሺፈራው ለአምስት ወራት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ቆይቶ ባለፈው ሳምንት ክስ ተመስርቶበት ቂሊንጦ በእስር ላይ ይገኛል፡፡ ግንቦት 26 ቀን 2008 ዓ.ም የቀረበበት ክስ በፍርድ ቤት ሊነበብለት ቀጠሮ ተሰጥቶታል፡፡

ጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው የዕንቁ መፅሔት አምደኛ፣ የነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ፣ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ መስራች አባልና የጊዜያዊ አስተባባሪው አመራር እንዲሁም አዲስ ሚዲያ ተባባሪ እና በራሱ የማኀበራዊ ገፅ ብሎገር እንደነበር አይዘነጋም፡፡
ምንጭ፡- EHRP.

የብሄራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ሃላፊ አቶ ኢሳይያስ ወልደ ጊዮርጊስ ከስልጣናቸው ተባረሩ

ባሌቤታቸውም ከስራቸው የተነሱ ሲሆን፡ ሁለቱም በጸጥታ ሃይሎች ክትትል ውስጥ ይገኛሉ። በአቶ ኢሳይያስ ምትክ በደርግ ዘመን የደርግ ደህንነት የነበሩት ሃደራ አበራ ተክተዋቸዋል።

Esayas Woldegiorgis ,Inteliggence
ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ቅርብ የነበሩት አቶ ኢሳይያስ ወልደጊዮርጊስ መባረራቸውን ተከትሎ በሌሎች ሃላፊዎችም ሆነ ሰራተኞች ላይ ስለተወሰደ ርምጃ የታወቀ ነገር የለም።

ወ/ሮ አዜብ መስፍን ግን የአቶ ኢሳይያስን ስንብት ተከትሎ ባለፈው ቅዳሜ አሜሪካ ገብተዋል፡ ዋሺንግተን ዳላስ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ካሜራ ዕይታ ውስጥ የገቡት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ከአንድ ልጃቸው ጋር ሰለመጡብት ምክንያት በውል የታወቀ ነገር የለም።
ምንጭ፡- ኢሳት

%d bloggers like this: